✨አሃ - /Aha Moment/
“What I always want is to have several little ‘aha’ moments where your brain is very happy.” – Scott Kim
ከመቶ ዓመት በፊት በአንዱ ዕለት ነው፣ ሰውየው የሚያማምሩ አበቦች ባሉበት የቤቱ የአትክልት ስፍራ ላይ ተቀምጦ የዕለቱን ጋዜጦች ያገላብጣል። ድንገት… ‘በሞት የተለዩ ሰዎች’ በሚለው አምድ ላይ የአንድን ሰው ዜና እረፍት አየና ክው ብሎ ደነገጠ፣ ጽሑፉን ሲያነብ ጋዜጣው እንደ መርዶ ነጋሪ ሹክክ ብሎ ቤቱ የተገኘ ጥላቢስ እንጂ ተራ ወረቀት አልመስልህ አለው፣ ክውታና ድንዛዜ፣ ደርሶ ጭውውውውው አለበት።
ብንን ብሎ ጋዜጣውን በድጋሚ ተመለከተው፣ አልተሳሳተም፣ በትክክል የሚያነበው የራሱን ዜና እረፍት ነው፣ Dynamite king dies ይላል። ‘የድማሚቱ ንጉስ አረፈ…’ ያ.. ተራራውን ገምሶ.. ቋጥኙን ፈልፍሎ.. አለታቱን ነድሎ መንገድ የሚተልመውን ድማሚት የፈጠረው ሰው አረፈ እያለ ነው… ሰውየው ራሱን ጠየቀ… ‘ይህን ዜና የማነበው በእውኔ ነው በሕልሜ?’ መልስ የለም።
💡ዜናው በዚህ ቢያበቃ ጥሩ አይደል… ስለ ‘ሟቹ’ ሌላም ነገር ይላል፣ And he was the merchant of death…(የሞት ነጋዴ እንደማለት ነው) ሳይሞት ሞተሃል ከመባሉ በላይ እንደ ሙት የሚታሰብበት መንገድ ሰውየውን የበለጠ አስደነገጠው፣ ተንቀጠቀጠ… ሰበበ ሞት ተደርጎ ነዋ የተገለጸው… የጅምላ ፍጅት ምክንያት ተደርጎ ነው የተሳለው… ‘እውነት ሞቼ ቢሆን ሰዎች የሚያስታውሱኝ እንደዚህ እያሉ ነው?’ ሲል ጠየቀ፣ ‘በፍጹም!!! ይህ ቅጽል መፋቅ አለበት!!’
🧨 ይህ ሰው አልፍሬድ ኖቤል ነው። ኖቤል ድማሚትን ‘በመፍጠሩ’ ይታወቃል፣ ግኝቱ ለመንገድ ስራ ያለው አስተዋጽዎ ጎልቶ የሚነገርለት ቢሆንም ኖቤልን ‘ነፍሰ ገዳይ’ ከሚል ስም አላስጣለውም… የፈረንሳይ ጋዜጦች “Le marchand de la mort est mort” (“The merchant of death is dead.”) ብለው ሲዘግቡ ዜናውን በዚያው ወቅት ፈረንሳይ ውስጥ ከሞተው የአልፍሬድ ኖቤል ወንድም ሉድቪግ ጋር አምታተውት ኖሯል፣ ሆኖም አጋጣሚው ኖቤልን ከጥልቅ እንቅልፉ የሚያነቃው ነበር… እናም ይህን ስም ለውጦ ማለፍ እንዳለበት የወሰነው እዚያው ነበር።
💎በፈጠራው ምክንያት ያገኘውን ሳንቲም ሰብስቦ ለበጎ ተግባር እንዲውል ሰጠ፣ በደህናው ዘመን ስለ ድንቅ ጥበቡ የተበረከተች ሳንቲም በችግሩ ጊዜ ስለ ስሙ መታደስ ወጣች፣ ያቺ ሳንቲም በዝታና በርክታ በዓለም ዙሪያ በሳይንስ፣ በስነጽሑፍ፣ በሰላም፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በፊዚክስና በሌሎችም በርካታ ዘርፎች ከፍ ያለ አስተዋጽዎ ለሚያደርጉ ግለሰቦች ሽልማት ሆና የምትቀርብ ሆነች።
ዛሬ ዛሬ የ Nobel Prize Winner መሆን የልዕልና መግለጫ ሆኗል፣ በዙርያችን ‘እከሌ የኖቤል ተሸላሚ ነው’ የሚለው ስያሜ ትልቅ ማዕረግ ሆኗል፣ ብዙ የምናደንቃቸው የዓለማችን ሰዎች የሽልማቱ አሸናፊ ሆነዋል፣ ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ጨምሮ ፣ አዎን… አሁን ኖቤልን ከሞት ጋር አያይዞ ስሙን የሚያነሳ፣ ከውድመት ጋር አቆራኝቶ ስራውን የሚያወሳ አንድ ስንኳ የለም።
ከ’ሞት’ በኋላ በበጎ መታወስ የሚል ቅዥት ሰከንዶችን ተጋርቶኝ አያውቅም፣ ግና ሰው በኑረት ብቻ ሳይሆን በእልፈቱም ለሌሎች መኖር ከቻለ ድንቅነቱ ይገባኛል፣ ያም ሆኖ የበለጠ የሚመስጠው የተረኩ ክፍል ‘በሌሎች ዘንድ የጠለሸን ስም’ ለማደስ የመቁረጡ ጉዳይ ነው።
🔷አስባችሁታል፣ መንግስት ‘ለካ ሕዝብ የሚረዳኝ እንዲህ ነው?’ ብሎ ስሙን ለማደስ ሲተጋ… ፣ ባል በጸጸት ውስጥ ሆኖ ‘ለካ በሚስቴ ዓይን የምመስለው ይህን ነው?’ ብሎ እንከኑን ሲነቅስ… አባት ‘ለካስ ለልጆቼ ጥሩ ወላጅ አልነበርኩም’ ብሎ መንገዱን ለመቀየር ሲወስን… ተቋማት ‘በደንበኞቻችን ዘንድ ያለን ገጽታ ጥሩ አይደለም ለካ’ ብለው ለምርትም ሆነ አገልግሎት መሻሻል ሲሰሩ… ትራፊኮች በአሽከርካሪ ዓይን፣ አሽከርካሪዎች በተሳፋሪ ዓይን…፣ አለቆች በሰራተኛ፣ መምህራን በተማሪ፣ ፍቅረኞች በተፈቃሪያቸው፣ ብቻ ሁሉም በየአንፃራቸው ቦታ ራሳቸውን አስቀምጠው ‘አሃ…’ ቢሉ
🔑አንዳንዴ በሌሎች መስታወት ውስጥ ካላየነው በቀር የማይገለጥ ቁሸት አያጣንም፣ በወዳጅ ምክር ውስጥ ካልሆነ የማይቀና ጉብጠትም እንዲሁ ፣ ‘ለሌሎች’ ሲባል ሁሉ ይፍረስ አይባልም መቼም… ሁሉን ማስደሰት አለመቻል ብቻ ሳይሆን ‘የራስ ጣዕም’ ማጣትም ልክ አይሆንምና
ግን አለ አይደል… ‘በልክ ነኝ’ ካብ ውስጥ ያደፈጠች ክፋት፣ በማናለብኝ ጎሬ ውስጥ የተሸጎጠች ትዕቢት፣ የሌላውን ምቾት የምትነሳ ክርፋት… ምናል.. ‘አሃ…’ እያልን ብናስወግዳት።
ውብ አሁን❤️
✍ ደምስ ሰይፉ
💯 በዚህ ውብ ድልድይ እንሻገር ፣ ሁላችንም ቻናሉን በአብሮነት እንቀላቀል 💯
👇
@BridgeThoughts@BridgeThoughts✍
@EthioHumanitybot