በትረማርያም አበባው Betremariam Abebaw


Channel's geo and language: Ethiopia, Amharic
Category: Religion


አቀድም አእኵቶቶ ለእግዚአብሔር

Related channels  |  Similar channels

Channel's geo and language
Ethiopia, Amharic
Category
Religion
Statistics
Posts filter


▶️፲፩. መክ.7፥10 ላይ "ከዚህ ዘመን ይልቅ ያለፈው ዘመን ለምን ተሻለ? ብለህ አትናገር። የዚህን ነገር በጥበብ አትጠይቅምና" ይላል። ብዙውን ጊዜ ያለፈውን ዘመን ከአሁኑ ጋር እያነጻጸርን ያለፈውን ጥሩ ዘመን እደነበረ የአሁኑ ደግሞ ካለፈው የማይሻል እናደርጋለን። አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የአሁኑን ካለፈው የተሻለ ዘመን እንደሆነ እንናገራለን። ይህ በቤተክርስቲያን ዘንድ እንዴት ይታያል?

✔️መልስ፦ ስለዘመናት የሚያውቅ እግዚአብሔር ነው። ባለፈው ዘመን ይህ ሆኖ በአሁኑ ዘመን ይህ ለምን ተደረገ አትበል ማለት ስለሁሉ አለማወቅ ስለሚገድበን ሁሉን ለእግዚአብሔር ስጥ ማለት ነው። በሁሉ ዘመን እግዚአብሔር ማመስገን እንጂ ከዚህ በዘለለ መመራመር አይጠቅምም ማለት ነው።

▶️፲፪. "በኃጥኣን የሚደረገው ሥራ የሚደርስባቸው ጻድቃን አሉ። ለጻድቃንም የሚደረገው ሥራ የሚደርስላቸው ኃጥኣን አሉ። ይህም ደግሞ ከንቱ ነው አልሁ" ይላል (መክ.8፥14)። የዚህ ንባብ ትርጓሜ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ በኃጥኣን የሚደረገው ሥራ የሚደርስባቸው ጻድቃን አሉ ማለት ለምሳሌ እንደ ነቢዩ ሳሙኤል ነው። መግደል የኃጥኣን ሥራ ቢሆንም ጻድቁ ሳሙኤል ግን አጋግን ገድሎታልና። ለጻድቃን የሚደረገው ሥራ የሚደርስላቸው ኃጥኣን አሉ የሚለው እንደ ሳኦል ነው። አለመግደል የጻድቃን ሥራ ቢሆንም ክፉው ሳኦል አጋግን ሳይገድለው ቀርቷልና ነው።

▶️፲፫. "ንጉሥሽ ሕፃን የሆነ መኳንንቶችሽም ማልደው የሚበሉ አንች አገር ወዮልሽ!" ይልና "ንጉሥሽ የጌታ ልጅ የሆነ መኳንንቶችሽም ለብርታት በጊዜ የሚበሉ የማያፍሩም አንች ሀገር ሆይ የተመሰገንሽ ነሽ" ይላል (መክ.10፥16-17)። የንባቡ ትርጓሜ ምንድን ነው? ሐሳቦቹስ አይጋጩም? አንዱ የተጠነቀቀበት ሌላኛው የተመሰገነበት ልዩነቱ ምን ላይ ሁኖ ነው?

✔️መልስ፦ ንጉሥሽ ሕፃን የሆነ ማለት ንጉሥሽ ሕፃነ አእምሮ የሆነ ሀገር ወዮልሽ ማለት ነው። መኳንንቶችሽም ማልደው የሚበሉ ማለት የተሾሙት ሊፈርዱ ሆነው ሳለ ፍርዱን ትተው ራሳቸውን ብቻ የሚንከባከቡ መኳንንት ወዮላቸው ማለት ነው። ቀጥሎ ንጉሥሽ የጌታ ልጅ የሆነ የሚለው ንጉሡ በመልካም ሥራው የተከበረ ከሆነ ሀገር የተመሰገነች ትሆናለች ማለት ነው። መኳንንቶችሽም ለብርታት በጊዜ የሚበሉ ማለት ፈርደው ከፍርድ በኋላ የሚበሉ ከሆኑ በሥራቸው ሀገር ትመሰገናለች ማለት ነው።

▶️፲፬. መክ.7፥8 ላይ "የነገር ፍጻሜው ከመጀመሪያው ይሻላል" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ ከዚህ የነገር ፍጻሜ የተባለው የቀማችሁትን መልሱ የሚለው ሲሆን መጀመሪያ የተባለው "ቀሙ" የሚለው ነው። የነገር ፍጻሜው ከመጀመሪያው ይሻላል ማለት ቀሙ ከማለት የቀማችሁትን መልሱ ማለት ይሻላል ማለት ነው።

▶️፲፭. "የሰው ድካም ዅሉ ለአፉ ነው። ነፍሱ ግን አትጠግብም" ይላል (መክ.6፥7)። ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሰው የደከመበት ነገር ሁሉ ለአፉ ነው ማለት ለጊዜያዊ ነገር ብቻ ነው። ነፍሱ ግን አትጠግብም ማለት ሰውነቱ ግን በቃኝ አትልም ማለት ነው።

▶️፲፮. "በዐይን ማየት በነፍስ ከመቅበዝበዝ ይሻላል" ይላል (መክ.6፥9)። ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ከዚህ በነፍስ መቅበዝበዝ የተባለው ባዕለ ጸጋ ራሱ መስጠት ሲገባው በግብዝነት ስጡልኝ ብሎ በሌሎች ሰዎች አማካኝነት ምጽዋት መስጠትን ነው። በዐይን ማየት የተባለው ራሱ ሄዶ ለነዳያን መመጽወትን ነው። ስለዚህ በግብዝነት በሌላ ሰው አማካኝነት ምጽዋት ከመስጠት ራስ ሄዶ በዓይን አይቶ መስጠት ይሻላል ማለት ነው።

▶️፲፯. "ከሣቅ ኀዘን ይሻላል። ከፊት ኀዘን የተነሣ ልብ ደስ ይሰኛልና" ይላል (መክ.7፥3)። ከፊት ኀዘን የተነሣ ልብ ደስ የሚሰኘው እንዴት ነው?

✔️መልስ፦ ይህ ለአላዋቂ ሰው የተነገረ ነው። ለአላዋቂ ሰው ከሚስቁለት ይልቅ ፊትን ማኮሳተር ይሻለዋል ለማለት ነው። ይኸውም ፊትን ሲያኮሳትሩበት ወደልቡ ይመለሳልና። በዚህም የልቡና ደስታን ያገኛልና ነው።

▶️፲፰. "ደጋሚ ሳይደግምባት እባብ ብትነድፍ ለደጋሚው ትርፍ የለውም" ይላል (መክ.10፥11)። ለማለት የተፈለገው ሀሳብ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ከዚህ ደጋሚ የተባለ ባለመድኃኒት ሐኪም ነው። ሐኪም እባብ የነደፈውን ሰው ካላዳነው ለሐኪሙ ትርፍ የለውም ማለት ነው። የሐኪም ትርፉ በሽተኞችን ማዳን ነው ለማለት ነው።

▶️፲፱. "የሰማይ ወፍ ቃሉን ይወስደዋልና። ባለክንፎችም ነገሩን ይናገራሉና በልብኽ ዐሳብ እንኳ ቢኾን ንጉሥን አትስደብ። በመኝታ ቤትኽም ባለጠጋን አትስደብ" ይላል (መክ.10፥20)። የሰማይ ወፍ እና ባለክንፎች የተባሉት እነማን ናቸው?

✔️መልስ፦ ከዚህ የሰማይ ወፍ እና ባለክንፍ የተባለ ነገረ ሠሪ ነው። ባለክንፍ የሰማይ ወፍ ፈጣን እንደሆነ ሁሉ ነገርህን ነገረ ሠሪ በፍጥነት ለንጉሡ ተናግሮ ያስቀጣሀልና ንጉሡን አትማው ማለት ነው።

▶️፳. "ከዚህም ዅሉ በላይ ልጄ ሆይ ተግሣጽን ስማ። ብዙ መጻሕፍትን ማድረግ ፍጻሜ የለውም። እጅግም ምርምር ሰውነትን ያደክማል" ይላል (መክ.12፥12)። ብዙ መጻሕፍትን ማድረግ ፍጻሜ የለውም ሲልና እጅግም ምርምር ሰውነትን ያደክማል ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ብዙ መጻሕፍትን ማድረግ ፍጻሜ የለውም ሲል ብዙ ብሎ የጠቀሰው የሟርት፣ የጥንቆላ መጻሕፍትን ነው። ከቅዱሳት መጻሕፍት ውጭ የሆኑ እነዚህን ክፉ መጻሕፍት አታንብብ ማለት ነው። እጅግም ምርምር ሰውነትን ያደክማል ማለት ክፉ መጻሕፍትን ማንበብ በነፍስም በሥጋም ይጎዳል ማለት ነው።

▶️፳፩. መክ.10፥15 ወደ ከተማ መሄድ ጠቢብ ያደርጋልን?

✔️መልስ፦ ወደ ከተማ መሄድ ብሎ ከዚህ የገለጸው ምጽዋትን ነው። ተመጽዋች በከተማ እንደሚበዛ በከተማው ሰዎችን መናገሩ ነው። ስለዚህ መመጽወት ጠቢብ ያደርጋል ማለት ነው።

▶️፳፪. "ቁጣ በሰነፎች ብብት ያርፋልና" ይላል (መክ.፯፥፱)። ቁጣ በሰነፎች ብብት ያርፋልና ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ ብብት ያለው ልብ ለማለት ነው። በሰነፍ ሰዎች ልቡና ቁጣ ይሠለጥናል ማለት ነው።

▶️፳፫. "እኔም ከሞት ይልቅ የመረረች ነገር አገኘሁ። እርሷም ልቧ ወጥመድና መረብ የሆነ በእጆቿም መሳሪያ ያላት ሴት ናት። በእግዚአብሔርም ፊት ደግ የሆነ ከእርሷ ያመልጣል። ኃጢአተኛ ግን ይጠመድባታል" ይላል (መክ.፯፥፳፮)። ልቧ ወጥመድና መረብ የሆነ በእጆቿም መሣሪያ ያላት ሴት ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ ይህች ሴት በእጇ ፈትፍታ እያበላች ሰውን በሽንገላ የምታጠምድ ዓይነት ሴት ናት።

▶️፳፬. መክ.7፥9 በመንፈስ መቆጣት ማለት ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦በመንፈስ መቆጣት አይገባም። በመንፈስ መቆጣት ማለት ቁጣን በቃል ወይም በነገር መግለጽ ማለት ነው።

▶️፳፭. መክ.10፥7 ንጉሥ እንደ አገልጋይ ሎሌም እንደንጉሥ የሆነበት ምክንያቱ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ክፉ ንጉሥ ሲነግሥ ደግ ንጉሥ እንደ አገልጋይ ሲኖር፣ ንግሥና የማይገባው አገልጋይ ደግሞ ተሹሞ ይገኛል ማለት ነው።

▶️፳፮. መክ.7፥28 ላይ ሰሎሞን ነፍሱ የወደደችውን እንዳላገኘ ሲናገር መሓ.3፥4 ላይ ግን ነፍሱ የወደደችውን እንዳገኘ ይናገራል። አይጋጭም ወይ?

✔️መልስ፦ አይጋጭም። የሰው ልጅ ያለው ነገር ከእግዚአብሔር በጸጋ የተሰጠ ነው። ይህ ጸጋም በተለያዩ ምክንያቶች ሊነሣ ይችላል። ስለዚህ ሰሎሞን ነፍሱ የወደደችውን ቢያገኝም ነገር ግን ጥበቡ የጸጋ እንጂ የባሕርይ ስላልሆነ ሁሉን አላገኝም።


© በትረ ማርያም አበባው


💙 የጥያቄዎች መልስ ክፍል 159 💙

▶️፩. መክ.9፥5 ላይ "ሕያዋን እንዲሞቱ ያውቃሉና ሙታን ግን አንዳች አያውቁም መታሰቢያቸውም ተረስቷልና ከዚያ በኋላ ዋጋ የላቸውም" ይላል። መታሰቢያቸውም ተረስቷልና ከዚያ በኋላ ዋጋ የላቸውም ምን ማለት ነው? ለሞተው ሰው የሙታን መታሰቢያ እየተባለ ከሣልስት ጀምሮ እስከ ሰባት ዓመት የሚወጣለት መታሰቢያ የተፈረደባትን ነፍስ ሊያስምራት አይችልም ማለት ነው? በ40/በ80 የመታሰቢያ ቀን ከመቃብር ላይ የሚፈሰው የፍየል ደምስ ለምውት ነፍስ ይጠቅማታል? ስለ አርባ፣ ስለ ሰማንያ እና ተዝካር የቤተክርስቲያንን አስተምህሮ በደንብ ቢያብራሩልኝ? እኔ ባለሁበት በ40 በ80 መቃብር ላይ የሚታረደው ፍየል ነው በግ አይፈቀድም። ይህ ነገርስ እውነት በግ አይፈቀድም? ለምን እንደው ቢያስረዱኝ?

✔️መልስ፦ ሕያዋን ያላቸው ደጋግ ሰዎችን ነው። እንደሚሞቱ አውቀው ንስሓ ገብተው ሞትን ይጠባበቃሉ። ሙታን ያላቸው ኃጥኣን ናቸው። አያውቁም የተባለው እንደሚሞቱ አውቀው ንስሓ አይገቡም ለማለት ነው። መታሰቢያቸው ተረስቷል፣ ከዚህ በኋላ ዋጋ የላቸውም ማለት ከሞቱ በኋላ ንስሓ መግባት ስለሌለ ዋጋ የላቸውም ማለት የመዳን ተስፋ የላቸውም። መታሰቢያቸው ተረስቷል ማለት በሞት ይረሳሉ ማለት ነው። ለሙታን የሚደረግ ፍትሐት ለሞተው ሰው የራሱ የሆነ ጥቅም አለው። የሞተው ደግ ሆኖ ገነት ገብቶ ከሆነም በገነት በክብሩ ላይ ክብር ይጨምርለታል። የሞተው ኃጥእ ሆኖ በሲኦል የሚኖር ከሆነም መከራው ይቀንስለታል። በ40 እና በ80 ቀን ከሞተው ሰው መቃብር ላይ ፍየል ወይሞ በግ ማረድ እንኳ መጽሐፋዊ አይደለም። ፍየልም በግም ቢሆን በሙታን መቃብር ላይ ማረድ አይገባም። ስለሙታን ፍትሐት ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 22 ይገልጻል። በአርባ፣ በሰማንያ፣ በመን*ፈቅ፣ በዓመት፣ በሣልስት፣ በዕለቱ፣ በሰባት፣ በዘጠኝ፣ በአሥራ ሁለት፣ በስልሳ፣ በሠላሳ ለሞተው ፍትሐት እንዲደረግለት ሥርዓት ተሠርቷል።

▶️፪. መክ.7፥16 ላይ "እጅግ ጻድቅ አትኹን። እጅግ ጠቢብም አትኹን እንዳትጠፋ" ሲል ሐሳቡ ምን ለማለት እንደሆነ ግልጽ ቢያደርጉልኝ?

✔️መልስ፦ እጅግ ጻድቅ አትሁን ማለት ከእግዚአብሔር የበለጠ እውነተኛ ነኝ አትበል ማለት ነው። ይኸውም እንደ ሳኦል ነው። እግዚአብሔር አጋግን እንዲገድል ለሳኦል ትእዛዝ ሰጥቶት ነበር። ሳኦል ግን ከምገድለው ብማርከው ይሻላል ብሎ ማረከው። ይህ ከእግዚአብሔር በላይ አሳቢ ነኝ ማለት ነውና ይህን ለመግለጽ እጅግ ጻድቅ አትሁን ተብሏል። እጅግም ጠቢብ አትሁን ማለትም የእግዚአብሔርን ሕግ ለማፍረስ አትተናኮል ማለት ነው። ለክፉ ነገር የሚጠበብ ሰው አለና እንደዚያ አትሁን ለማለት ነው።

▶️፫. መክ.11፥1-2 ላይ "እንጀራኽን በውሃ ፊት ላይ ጣለው። ከብዙ ቀን በዃላ ታገኘዋለኽና" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ በውሃ ውስጥ የተጣለ እንጀራ እንደማይታይ በስውር መጽውት ማለት ነው። ወደ ውሃ የተጣለ እንጀራ እንደማይገኝ ሁሉ ገንዘብህን ከመጸወትክ በኋላ ነዳያን ይመልሱልኛል ብለህ ተስፋ ሳታደርግ መጽውት (ስጥ) ማለት ነው።

▶️፬. መክ.9፥11 ኃይል፣ ባለጠግነት፣ ሞገስ እና የመሳሰለው በዕድል ይገኛልን?

✔️መልስ፦ እነዚህ ሁሉ ለሚገባው የሚሰጡ እንጂ በእድል የሚገኙ አይደሉም። ነገር ግን ሰው ሠርቶ ብቻም አያገኛቸውም። ረድኤተ እግዚአብሔር ካልተጨመረበት ሰው ጥሮ ግሮ ብቻ ሊያገኛቸው አይችልም። ከዚህ እድል ያለው ረድኤተ እግዚአብሔርን ነው።

▶️፭. መክ.7፥1 ላይ "ከመወለድ ቀንም የሞት ቀን ይሻላል። ወደ ግብዣ ቤትም ከመሄድ ወደ ልቅሶ ቤት መሄድ ይሻላል" ይላል። እንዴት ነው የሚሻለው?

✔️መልስ፦ ከመወለድ ቀን የሞት ቀን የሚሻለው ለጻድቃን ነው። ጻድቃን ከተወለዱ በኋላ እስኪሞቱ ድረስ መከራን እየተቀበሉ ይኖራሉ። ከሞቱ በኋላ ግን ያለ መከራ በዕረፍት ይኖራሉና ከመወለድ ቀናቸው የሞት ቀናቸው ይሻላል ተብሏል። ለኃጥኣንም ቢሆን የተወለዱበት ቀን ይሻላል። በመወለዳቸው በኃጢአት ላይ ኃጢአት እየሠሩ ይኖራሉ። ከሞቱ ግን ኃጢአትን አይሠሩም። ካልሠሩ ደግሞ ፍዳ አይጸናባቸውምና ነው። ግብዣ ቤት ከመሄድ ልቅሶ ቤት መሄድ ይሻላል ማለትም ልቅሶ ቤት ሰው እንደሚሞት አስቦ ንስሓ እንዲገባ ያሳስበዋል። ግብዣ ቤት ተድላ ዓለምን አሳስቦ በዓለም እንድንጠፋ ያደርገናልና ነው።

▶️፮. መክ.12፥1ላይ "የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ" ይላል። የጭንቀት ቀን የተባለች ማን ናት?

✔️መልስ፦ የጭንቀት ቀን የተባለች ሞት ናት። የሞት ቀን ሳይመጣብን በሕይወት እያለን መልካም ሥራን እንሥራ ለማለት ነው።

▶️፯. መክ.9፥4 ላይ "ከሞተ አንበሳ በሕይወት ያለ ውሻ ይሻላል" ሲል ምን ለማለት ነው? መና*ፍ_ቃ/ንም ይህን ሐሳብ ወስደው ከጻድቃን አማላጅነት ጋር ያጣርሱታልና ቢያብራሩልን?

✔️መልስ፦ በአንበሳም በውሻም የመሰሉት ኃጥኣን ናቸው። ከሞተ ኃጥእ ያልሞተ ኃጥእ ይሻላል ማለት ነው። ያልሞተ ኃጥእ ንስሓ ገብቶ ለመዳን እድል አለው። የሞተ ኃጥእ ግን ከሞት በኋላ ንስሓ ስለሌለ ተስፋ የለውምና ነው።

▶️፰. መክ.9፥14-15 ላይ "ታናሽ ከተማ ነበረች ጥቂት ሰዎችም ነበሩባት። ታላቅ ንጉሥም መጣባት ከበባትም። ታላቅም ግንብ ሠራባት። ጠቢብ ድኻ ሰው ነበረባት ያችንም በጥበቡ አዳናት" ይላል። ከዚህ ታናሽ ከተማ የተባለች ማን ናት? ጥቂት ሰዎችስ የተባሉ እነማን ናቸው? ታላቁ ንጉሥስ ማን ነው? ድኻ የተባለውስ ማን ነው?

✔️መልስ፦ ታናሽ ከተማ የተባለች ኢየሩሳሌም ናት። ጥቂት ሰዎችም ነበሩባት የተባሉ ከአሥራ ሁለቱ ነገድ የሁለቱ ነገድ ሰው ብቻ ይኖርባት ነበር ማለት ነው። ታላቅ ንጉሥም ከበባት ማለት ሰናክሬም ኢየሩሳሌምን ለማጥፋት ከበባት። ታላቅም ግንብ ሠራባት ማለት በሠራዊት አስከበባት። ጠቢብ ድኻ ሰው ነበረባት የተባለው ሕዝቅያስ ነው። በጥበቡ አዳናት ማለት ነቢዩ ኢሳይያስ ጸልዮለት፣ እርሱ ራሱ ሕዝቅያስም ጸልዮ ኢየሩሳሌምን ከጥፋት አዳናት ማለት ነው።

▶️፱. "ነፍሴ የፈለገችውን አላገኘሁም። ከሺህ ወንዶች አንድ አገኘሁ። ከእነዚያ ሁሉ መካከል ግን አንዲት ሴት አላገኘሁም" ይላል (መክ.7፥28)። የዚህ ንባብ ትርጓሜው ምንድን ነው? ያገኘው ወንድ ምን ዓይነት ነው? ፈልጎ ያጣት ሴትስ?

✔️መልስ፦ ይህንን የተናገረው ሰሎሞን ነው። ከሺህ ወንዶች አንድ አገኘሁ ያለው የአባቶችን ታሪክ ስመለከት በአብርሃም ዘመን ከብዙ ሰዎች አንድ ደግ አብርሃምን ብቻ አገኘሁ ማለቱ ነው። ከብዙ ሰዎች መካከል ግን አንድ ሴት አላገኘሁም አለ። ይህም ሰሎሞን በዘመኑ ደግ ሴት እንዳላገኘ ያመለክታል።

▶️፲. "ለሰባት ደግሞም ለስምንት ዕድል ፈንታን ክፈል። በምድር ላይ የሚኾነውን ክፉ ነገር ምን እንደ ኾነ አታውቅምና" ሲል ምን ለማለት እንደሆነ ቢያብራሩልኝ (መክ.11፥2)።

✔️መልስ፦ ከዚህ እድል ፈንታ ተብሎ የተገለጸው ምጽዋት ነው። ለሰባት ስጥ ማለት ምጽዋት መጀመሪያ ለምእመናን መስጠት እንደሚገባ ያመለክታል። ሰባት ቁጥር በዕብራውያን ፍጹም ነው። ለስምንትም ስጥ ማለቱ ለምእመናን ከሰጠህ በኋላ ምእመናን ላልሆኑትም ምጽዋት መስጠት ይገባልና ይህን ለመግለጽ ነው።




ይህን መጽሐፍ በPDF ቀጥሎ ታገኙታላችሁ።

ሁሉ ይማርበት ብለው በቀሲስ ዶክተር መብራቱ ኪሮስ ፈቃድ ነው soft copyው የተለቀቀው።




PDF በኋላ በዚሁ የቴሌግራም ቻናሌ ይለቀቃል።


▶️፳፯. መክ.4፥9-10 ላይ "ድካማቸው መልካም ዋጋ አለውና አንድ ብቻ ከመሆን ሁለት መሆን ይሻላል። ቢወድቁ አንዱ ሁለተኛውን ያነሣዋልና። አንዱ ብቻውን ሆኖ በወደቀ ጊዜ ግን የሚያነሣው ሁለተኛ የለውምና ወዮለት" ይላል። ይህ ስለ ባል እና ሚስት የተነገረ ነውን? ትርጉሙ ቢብራራ።

✔️መልስ፦ ይህ ስለማንኛውም አንድነት የተነገረ ነው። በብዙ ጉዳዮች ብቻን ከመሆን ሁለት መሆን የተሻለ ነው። አንዱ ቢደክም አንዱ ያበረታዋልና። ይህ ለትዳርም ይተረጎማል። ሴት ወይም ወንድ ብቻቸውን ከሚኖሩ ተጋብተው አንድ ላይ ቢኖሩ ይሻላል። ይህን ለመግለጽ ነው።

▶️፳፰. መክ.፭፥፳ ላይ "እግዚአብሔር በልቡ ደስታ ስለሚያደክመው እርሱ የሕይወቱን ዘመን ሁሉ እጅግ አያስብም" ይላል። እግዚአብሔር አድካሚ ነው እንዴ?

✔️መልስ፦ እግዚአብሔር በኃይሉ ክፉ ሰዎችን፣ አጋንንትን ያደክማል። ስለዚህ ክፉዎችን አጋንንትን የሚያደክም ስለሆነ አድካሚ ተብሎ ሊነገርለት ይችላል። ከዚህ የተጠቀሰው ግን እግዚአብሔር በደስታ ያደክመዋል ማለት በደስታ እስኪደክም (እስኪሸመግል) ያኖረዋል ማለት ነው።


© በትረ ማርያም አበባው


✝️የዩቲዩብ ቻናሌ:- ንሕነ ዘክርስቶስ https://youtube.com/@edenawizechristos?si=6V4y-73OM3LTzhAf ነው።

🌻የፌስቡክ ገጼ Betremariam Abebaw https://www.facebook.com/profile.php?id=100075547015721 ነው።


▶️፲፭. "ሰነፍ እጆቹን ኰርትሞ ይቀመጣል። የገዛ ሥጋውንም ይበላል። በድካምና ነፋስን በመከተል ከኹለት እጅ ሙሉ ይልቅ አንድ እጅ ሙሉ በዕረፍት ይሻላል" ይላል (መክ.4፥5-6)። እጆቹን ኰርትሞ ይቀመጣል ሲል ምን ዓይነት አቀማመጥ ነው? አንድ እጅ ሙሉ እና ኹለት እጅ ሙሉ የተባሉት ምንድን ናቸው?

✔️መልስ፦ ከሁለት እጅ ሙሉ ይልቅ ማለት በሐሰት ከሚገኝ ሁለት እጅ ይልቅ፣ አንድ እጅ ሙሉ በዕረፍት ይሻላል ማለት በእውነት የሚገኝ አንድ እጅ ይሻላል ማለት ነው። እጅን ኮርትሞ መቀመጥ ማለት እጅን አጣጥፎ መቀመጥ ነው። ይኸውም ሳይሠሩ በስንፍና መኖር ነው።

▶️፲፮. "ወደ እግዚአብሔር ቤት በገባኽ ጊዜ እግርኽን ጠብቅ። ለመስማት መቅረብ ከሰነፎች መሥዋዕት ይበልጣልና። እነርሱም ክፉ እንዲያደርጉ አያውቁምና" ይላል (መክ.5፥1)። እግርኽን ጠብቅ ሲል ምን ማለት ነው? ለመስማት መቅረብ ያለው ምን ለመስማት ነው?

✔️መልስ፦ ወደ እግዚአብሔር ቤት በገባህ ጊዜ እግርህን ጠብቅ ማለት መልአክ እንዳይቀሥፍህ ወዲያ ወዲህ አትበል ማለት ነው። እንዲሁም ከቤተ እግዚአብሔር ሄደህ እንደገና ወደ ቤተ ጣዖት እንዳትሄድ እግርህን ጠብቅ ማለት አትሂድ። የጠቢባንን ቃል ለመስማት መቅረብ ጥበብን ያስገኛል። የሰነፍ መሥዋዕት ግን ከኃጢአት ንጹሕ ሆኖ ስለማያቀርበው ጥበብን ጸጋን አያገኝም ማለት ነው።

▶️፲፯. "ሰው በጥበብና በዕውቀት በብርታትም ከደከመ በኋላ ለሌላ ላልደከመበት ሰው ዕድሉን ያወርሳልና። ይህም ደግሞ ከንቱ ትልቅም መከራ ነው" ይላል (መክ.፪፥፳፩)። ዕድሉን ያወርሳል ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ እድሉን ያወርሳል ማለት ጥሮ ግሮ ያገኘውን ሀብት ያወርሳል ማለት ነው። ከዚህ እድል ያለው ሀብቱን ነው። ሰው ጥሮ ግሮ ያገኘውን በሞተ ጊዜ ሌላ ይወርሰዋል። ይህ ደግሞ መከራ ነው ማለት ነው።

▶️፲፰. "ከፀሐይ በታችም የተሠራው ሥራ ሁሉ በእኔ ላይ ክፉ ነውና ሕይወትን ጠላሁ" ይላል (መክ.2፥16)። ሰሎሞን "ሕይወትን" ጠላሁ ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ ሕይወትን ጠላሁ ማለቱ አዋቂውም ሰነፉም በእኩልነት የሚሞቱ ከሆነ መኖርን (ኑሮዬን) ጠላሁ ብሏል። ሰሎሞን ሞት መኖሩን ሲያስብና ሞት እንደማይቀርለት ሲያስብ የመኖር ጥቅሙ ምንድን ብሎ በዚህ ምድር መኖርን ጠላሁ ማለቱ ነው።

▶️፲፱. "ሰው በጥበብና በዕውቀት በብርታትም ከደከመ በኋላ ለሌላ ላልደከመበት ሰው ዕድሉን ያወርሳልና ይህም ደግሞ ከንቱ ትልቅም መከራ ነው" ይላል (መክ.2፥21)። የኔ ሀገር ሰው ልፋቱም ጥረቱም ለልጆቹ የሚያወርሰውን ጥሪት ማግኘት ነው። ይህ እንዴት ከንቱ ይሆናል?

✔️መልስ፦ ሰው ሠርቶ ለልጆቹ ማውረሱ መልካም ነው። ነገር ግን ከሞተ በኋላ ያ የለፋበት ነገር ለእርሱ ምንም የሚጠቅመው ነገር የለም ማለት በሰበሰበው ነገር በሥጋ አይጠቀምበትም ማለት ነው። ይህ ከሆነ ሰው ሁሉ ለዘለዓለማዊው ሕይወት የሚጠቅመውን ሥራ መሥራት ይገባዋል ማለት ነው።

▶️፳. "ሰነፍ እጆቹን ኮርትሞ ይቀመጣል የገዛ ሥጋውንም ይበላል" ይላል (መክ.4፥5)። "የገዛ ሥጋውን ይበላል" ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ የገዛ ሥጋውን ይበላል ማለት የሚበላው አጥቶ ሥጋውን ያከሳል ያመነምናል ማለት ነው። በተጨማሪም ወገኖቹን ያማል ማለት ነው። ሌላውን ሰው ማማት ያለቢላዋ የሰውን ሥጋ መብላት ነውና። ይኸውም የሚበላው አጥቶ ከዘመዶቹ ሲበላ ይኖርና አንድ ቀን ዘመዶቹ የመለሱት እንደሆነ እነርሱ አግኝተው እኔ ባጣ ያባርሩኝን እያለ ያማቸዋል ማለት ነው።

▶️፳፩. "ብርንና ወርቅን የከበረውንም የነገሥታትና የአውራጃዎችን መዝገብ ሰበሰብሁ። አዝማሪዎችንና አረሆዎችን የሰዎች ልጆችንም ተድላ እጅግ የበዙ ሴቶችንም አከማቸሁ" ይላል (መክ.2፥8)። አረሆዎች የተባሉት እነማን ናቸው? ትርጉሙ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ አረሆዎች የሚላቸው ሴት አዝማሪዎችን ነው። የግእዙ መጽሐፍ ቅዱስና የእንግሊዘኛው የበለጠ ግልጽ አድርገውታል። ግእዙ "አስተጋባእኩ ሊተ ብሩረ ወወርቀ ወጥሪተ መንግሥት ወበሐውርተ። ወገበርኩ ሊተ ኀላይያነ ወኀላይያተ" ያለውን እንግሊዘኛው "I gathered me also silver and gold, and the peculiar treasure of kings and of the provinces: I gat me men singers and women singers" ብሎታል (KJV).

▶️፳፪. መክ.3፥18 ላይ "እኔ በልቤ ስለሰው ልጆች እንደ እንስሳ መሆናቸውን ያሳይ ዘንድ እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል አልሁ" ይላል። ሰውን እንደ እንስሳ ሲል እንዴት? ይፈርድባቸዋል ሲልስ ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሰውም እንስሳም ሞታቸው ተመሳሳይ ነው። ሰውም ሲሞት በደመ ነፍሱ አራቱ ባሕርያት ተለያይተው ይፈርሳል ይበሰብሳል። እንስሳትም እንዲሁ ሲሞቱ አካላቸው ይፈርሳል ይበሰብሳልና ነው። ይፈርድባቸዋል ማለት ሰዎች እንደ እንስሳ እንዲሞቱ ያደርጋቸዋል ማለት ነው። "እንደ" የሚለው አነጻጻሪ በጥቂት ነገር ስለተመሳሰሉ የተነገረ እንጂ በሁሉ ነገር የሰው ሞትና የእንስሳት ሞት ይመሳሰላል ማለት አይደለም። ለሰው ከደማዊት ነፍስ በተጨማሪ የማትሞት የማትፈርስ ነባቢት ነፍስም አለችውና።

▶️፳፫. መክ.5፥5 ላይ "ተስለህ የማትፈጽም ከሆነ ባትሳል ይሻላል" ይላል። ከስእለት ጋር ያለው የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ምንድን ነው? ሰው ስእለት ተስሎ የተሳለው ባይፈጸምለት ስእለቱን አያስገባም። ይህ ኃጢአት ይሆንበታል? ከዚህ ጋር ስእለት በምንሰጥበት ጊዜስ ግራህ ስትሰጥ ቀኝህ አትወቅ ከሚለው ቃል አንጻር ሰዎች በዐውደ ምሕረት ላይ ተጨብጭቦላቸው የሚሰጡትን ስጦታ እግዚአብሔር አይቀበልም ማለት ነው? ቢያብራሩልኝ?

✔️መልስ፦ ስእለት የምንፈልገውን መልካም ነገር ያደርግልን ዘንድ ከእግዚአብሔር ጋር የምንዋዋለው ስምምነት ወይም መሓላ ነው። ስምምነቱ እኛም የምንፈልገው ሲደረግልን የሚፈጸም ይሆናል። የጠየቅነው ነገር ካልተረደገ ስእለት መስጠትም አለመስጠትም ይቻላል። የፈቃድ ነው። የተሳልነው ስእለት በአደባባይ ከሆነ በአደባባይ በዐውደ ምሕረት መስጠት በደል አይሆንብንም። ነገር ግን ለከንቱ ውዳሴ ብለን ከሰጠን ዋጋችንን በምድር ስላገኘን ሰማያዊ ዋጋችንን ይቀንስብናል።

▶️፳፬. መክ.1፥7 ብዙ ውሃ ወደ ባሕር ሲጨመር ይመላ የለም ወይ?

✔️መልስ፦ ውሃ ወደ ውቂያኖስ ሲፈስ ከውቅያኖስ ያለውም በተለያዩ ምክንያት ስለሚተን መሙላት አይችልም። ይህ ብቻ አይደለም። የውቅያኖሱ ውሃ ሊጨምር ይችላል እንጂ ውቅያኖስ ሰፊ ስለሆነ አይሞላም ማለት ነው።

▶️፳፭. መክ.2፥14 የሁለቱ (የብልህ እና የአላዋቂ) መጨረሻ እንዴት ነው አንድ የሚሆነው?

✔️መልስ፦ ያው ሁለቱም በመሞት አንድ ስለሆኑ እንጂ ከሞት በኋላ ባለው ሕይወትስ ይለያያሉ። ጻድቁ በገነት፣ ኃጥኡ በሲኦል ይኖራልና። ሥጋቸው በመበስበስ፣ በመፍረስ ግን የሁለቱም አንድ ነው። ከዚህ የተጠቀሰውም ይህ ነው።

▶️፳፮. መክ.2፥17 ላይ እንዴት ሁሉ ክፉ ነው ይላል? እንደ gnostic ቁስ አካል ክፉ ነው እያለ ነው?

✔️መልስ፦ አይደለም። ከዚህ እየተነገረ ያለው ስለ ቁስ (Matter) አይደለም። ጉዳዩ ከፀሐይ በታች ስለሚደረጉ ድርጊቶች እንጂ ስለፍጥረታቱ አይደለም። በሰዎች ክፉ ድርጊት ምክንያት የዓለም ሕይወት (ኑሮ) ክፉ ሆነብኝ ማለት ከበደኝ ማለቱ ነው። ፍጥረታት ሁሉ ሲፈጠሩ እግዚአብሔር መልካም እንደሆኑ አየ ስለተባሉ በተፈጥሯቸው ክፉ አሉ አንልም።


💙 የጥያቄዎች መልስ ክፍል 158 💙

▶️፩. "ትውልድ ይኼዳል። ትውልድም ይመጣል። ምድር ግን ለዘለዓለም ነው" ይላል (መክ.1፥4)። ምድር ያለው ምንን ነው?

✔️መልስ፦ ምድር ያላት ይህችን የምንኖርባትን መሬት ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ዘለዓለማዊነት በሁለት ይተረጎማል። አንደኛው ብዙ ዘመንን ዘለዓለም ይለዋል። ሌላኛው ፍጻሜ የሌለውን ነገር ዘለዓለም ይለዋል። ከዚህ ምድር ግን ለዘለዓለም ነው ሲል ሰው ሰባ ሰማንያ ዓመት ብቻ ኖሮ ሲሞት ምድር ግን ብዙ ዘመን ትኖራለች ማለት ነው።

▶️፪. "ለማልቀስ ጊዜ አለው። ለመሣቅም ጊዜ አለው። ዋይ ለማለት ጊዜ አለው። ለመዝፈንም ጊዜ አለው" ይላል (መክ.3፥4)። ለመዝፈንም ሲል ለመዘመር ማለት ነው?

✔️መልስ፦ መጻሕፍት መዝሙርን ዘፈን እያሉ የሚገልጹበት መንገድ አለ። ከዚህ ለልቅሶ ጊዜ አለው ማለቱ ሰው ተቸግሮ፣ መከራ ደርሶበት የሚያለቅስበት ጊዜ አለ ማለት ነው። ለመዝፈንም ጊዜ አለው ማለት ሰው ደስ ብሎት የሚያመሰግንበት ጊዜም አለ ማለት ነው እንጂ ዘፈን ጽድቅ የሚሆንበት ጊዜ አለ ለማለት አይደለም።

▶️፫. "ለመውደድ ጊዜ አለው። ለመጥላትም ጊዜ አለው። ለጦርነት ጊዜ አለው። ለሰላምም ጊዜ አለው" ይላል (መክ.3፥8)። ለመጥላትም ጊዜ አለው የተባለው ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ለመጥላት ጊዜ አለው ማለት እግዚአብሔር እስራኤላውያንን በበደላቸው ምክንያት የሚጠላበት ጊዜ አለ ማለት ነው። ይህም እግዚአብሔር በባሕርይው ጥላቻ ኖሮበት የሚጠላቸው ሆኖ አይደለም። እርሱ በባሕርይው ፍቅር ነውና። በበደላቸው ምክንያት ይፈርድባቸዋል ለማለት ነው።

▶️፬. መክ.2፥14 ላይ "የጠቢብ ዓይኖች በራሱ ላይ ናቸው" ሲል ምን ማለት ነው? ቢብራራ።

✔️መልስ፦ የጠቢብ ዓይኖቹ በራሱ ላይ ናቸው ማለት የራሱን በደል እየመረመረ፣ ንስሓ እየገባ ይኖራል ማለት ነው። እንዲሁም በራስ ያለ ዓይን ወደ ሰማይ እንደሚመለከት ጠቢብ ሰውም ሰማያዊ ነገርን ይመለከታል ማለት ነው።

▶️፭. መክ.5፥18 ላይ "ከፀሐይ በታችም በሚደክምበት ድካም ሁሉ ደስ ይለው ዘንድ ነው። ይህ ዕድል ፈንታው ነውና" ይላል። ካልተሳሳትኩ ከዚህ በፊት እንደተማማርነው ዕድል ፈንታ የሚባል ነገር በሃይማኖት እንደሌለ አይተናል። ወይስ ዕድል እና ዕድል ፈንታ ይለያያሉን? ይህ ክፍለ ንባብ እንዴት ይተረጎማል?

✔️መልስ፦ እድልና እድል ፈንታ ልዩነት የላቸውም። ከዚህ ቀድም እድል ፈንታ የለም ያልነው ሥነ ምግባርን መሠረት ባደረገ ጉዳይ ነው። የሰው ልጅ በሚሠራው ሥራ መሠረትነት ገነትን ይወርሳል ወይም ወደ ሲኦል ይገባል እንጂ በእድል አይገባም ማለታችን ነበር። ድኅነት በእድል ሳይሆን ነጻ ፈቃዳችንን ተጠቅመን በምንሠራው ሥራ እና በእግዚአብሔር ቸርነት የሚደረግ መሆኑን ለመግለጽ ነው። ከዚህ ከመጽሐፈ መክብብ እድል ፋንታ ብሎ የገለጸው ነጻ ፈቃዳችንን ተጠቅመን በሠራነው ሥራ ምክንያት የሚደርስብን ወይም የሚደርሰን ውጤቱ ነው። ለምሳሌ ለኃጥኣን እድል ፋንታቸው ገሀነመ እሳት ናት ስንል በምድር በሠሩት ክፉ ሥራቸው ምክንያት ገሀነም ይገባሉ ማለታችን ነውና።

▶️፮. "ከፀሐይ በታች በሚደከምበት ድካም ሁሉ የሰው ትርፉ ምንድን ነው?" ይላል (መክ.1፥3)። ይህን ጥያቄ መልሼ ልጠይቅ። አንድ ክርስቲያን ከፀሐይ በታች ትርፉ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ከፀሐይ በታች በዚህ ምድር ሳለን የመኖራችን ትልቁ ትርፍ መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ የሚያበቃ ሥራን መሥራት ነው። በዚህች ምድር መኖርን ለዘለዓለማዊው ሕይወት ዝግጅት ለማድረግ ካልተጠቀምንበት ትርፉ ኪሳራ ነው።

▶️፯. "ደግሞም ከፀሐይ በታች በጻድቅ ስፍራ ኃጥእ በኃጥእም ስፍራ ጻድቅ እንዳለ አየሁ" ይላል (መክ.3፥16)። የዚህ ንባብ ትርጓሜ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ በዚህች ምድር በጻድቅ ስፍራ ማለት ጻድቃን በሚኖሩበትና በኖሩበት ቦታ ኃጥኣንም ይኖራሉ ማለት ነው። ኃጥኣን በሚኖሩበት ቦታም ጻድቃን ይኖራሉ ማለት ነው። ይህ የሚሆነው ግን ከፀሐይ በታች በዚህ ምድር ነው እንጂ በመንግሥተ ሰማያት ጻድቃን ብቻ ሲኖሩ፣ በገሀነም ኃጥኣን ብቻ ይኖራሉ።

▶️፰. መክ.1፥3 ላይ "እግዚአብሔር ይደክሙበት ዘንድ ክፉ ድካምን ለሰው ልጆች ሰጥቷልና" ይላል። ከዚህ ላይ 'ክፉ ድካም' የተባለ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ክፉ ድካም የተባለው በዚህ ምድር የምንደክመው ድካም ነው። የእግዚአብሔርን ሕጉን በማፍረሳችን፣ ክፉ ሥራን በመሥራታችን የመጣብን ስለሆነ ክፉ ድካም ብሎታል።

▶️፱. "ሕልም በሥራ ብዛት ይታያል" ይላል (መክ.5፥3)። ሕልም በሥራ ብዛት ይታያል ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሰው ቀን ሲሠራ የዋለውን ማታ በሕልሙ የሚናገርበት ጊዜ መኖሩን የሚያመለክት ነው።

▶️፲. "ከሰማይም በታች የተደረገውን ዅሉ በጥበብ እፈልግና እመረምር ዘንድ ልቤን አተጋኹ። እግዚአብሔር ይደክሙባት ዘንድ ይህችን ለሰው ልጆች የሰጠ ክፉ ጥረት ናት" ይላል (መክ.1፥13)። ክፉ ጥረት የተባለችው ምንድን ናት?

✔️መልስ፦ ክፉ ጥረት ማለት ክፉ ድካም ማለት ነው። ጥረት የሚለው ጣረ ከሚለው አማርኛ የተገኘ ነው። ይኸውም በበደላችን ምክንያት የምንደክመው ድካም ነው። ምሥጢሩ ጥረህ ግረህ ብላ ከሚለው ጋር አንድ ነው።

▶️፲፩. "ጥበብንና እብደትን ሞኝነትንም ዐውቅ ዘንድ ልቤን ሰጠኹ። ይህም ደግሞ ነፋስን እንደ መከተል እንደ ኾነ አስተዋልኹ። በጥበብ መብዛት ትካዜ ይበዛልና። ዕውቀትንም የሚጨምር ኀዘንን ይጨምራልና" ይላል (መክ.1፥17-18)። ነፋስን እንደ መከተል ነው ሲል ጥበብን ይጨምራል? በጥበብ መብዛት ትካዜ ይበዛልና ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ነፋስን መከተል ከንቱ ድካም ነው። ነፋስን በመከተል የሚገኝ ጥቅምም ስለሌለ ትርፉ ድካም ብቻ ነው። በጥበብ መብዛት ትካዜ ይበዛል ማለት ጠቢብ ሲያጠፋ የአዋቂ በዳይ ተብሎ ይፈረድበታል ማለት ነው። ጥበብን ያበዛ ሰው በጥበቡ ካልሠራበት ይጠየቅበታልና ነው። ወዘሰ የአምር ገቢሮታ ለሠናይት ወኢየገብራ ኃጢአተ ትከውኖ እንዲል።

▶️፲፪. "ለሰው ከሚበላና ከሚጠጣ በድካሙም ደስ ከሚለው በቀር የሚሻለው ነገር የለም። ይህም ደግሞ ከእግዚአብሔር እጅ እንደ ተሰጠ አየኹ" ይላል (መክ.2፥24)። ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሰው ሲበላ፣ ሲጠጣ እና ደክሞ በሚያገኘው ገንዘብ ደስ ይለዋል ማለት ነው። ምግብ መጠጥ ከእግዚአብሔር ይገኛል። ሰው የፈለገ ቢደክም ረድኤተ እግዚአብሔር ካልተጨመረበት ምንም አያገኝምና ነው።

▶️፲፫. "ነገርን ዅሉ በጊዜው ውብ አድርጎ ሠራው። እግዚአብሔርም ከጥንት ዠምሮ እስከ ፍጻሜ ድረስ የሠራውን ሥራ ሰው መርምሮ እንዳያገኝ ዘለዓለምነትን በልቡ ሰጠው" ይላል (መክ.3፥11)። ዘለዓለምነትን በልቡ ሰጠው ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሰው የእግዚአብሔርን ሥራ እንዳያውቅ እግዚአብሔር ለሰው ዘለዓለምነትን በልቡ ሰጠው ማለት ሰው እግዚአብሔርን በባሕርይው ለዘለዓለም አያውቀውም ማለት ነው።

▶️፲፬. "አኹን ያለው በፊት ነበረ። የሚኾነውም በፊት ኾኖ ነበር። እግዚአብሔርም ያለፈውን መልሶ ይሻዋል" ይላል (መክ.3፥15)። እግዚአብሔርም ያለፈውን መልሶ ይሻዋል ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ለሰው ምጽዋትን የሚሰጥን ሰው እግዚአብሔር ክብር በመሥጠት ይሻዋል ማለት ያከብረዋል ማለት ነው።


💖 መጽሐፈ መክብብ ክፍል 2 💖

💖ምዕራፍ ፮፡-
-እግዚአብሔር ለሰው ሀብትንና ጥሪትን ክብርንም እንደሰጠው

💖ምዕራፍ ፯፡-
-ከመልካም ሽቱ መልካም ስም ከመወለድ ቀንም የሞት ቀን እንደሚሻል

💖ምዕራፍ ፰፡-
-ለኃጥእ ድኅነት እንደሌለው

💖ምዕራፍ ፱፡-
-ከሕያዋን ጋር አንድነት ያለው ማንም ሰው ተስፋ እንዳለው
-ከኃይል ይልቅ ጥበብ እንደምትበልጥ

💖ምዕራፍ ፲፡-
-የሞቱ ዝንቦች የተቀመመውን የዘይት ሽቱ እንደሚያገሙት
-ትዕግሥት ኃጢአትን እንደሚያስተሠርይ
-ለባልንጀራው ጉድጓድን የሚምስ ራሱ እንደሚወድቅበት
-የጠቢብ ሰው የአፉ ቃል ሞገስ እንደሆነች

💖ምዕራፍ ፲፩፡-
-ከልብ ቁጣን ማራቅ ከሰውነትም ክፉ ነገርን ማስወገድ እንደሚገባ

💖ምዕራፍ ፲፪፡-
-የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝና ወራት ፈጣሪን ማሰብ እንደሚገባ

💖የዕለቱ ጥያቄ💖
፩. ከሚከተሉት ውስጥ ትክክል የሆነው የቱ ነው?
ሀ. ትዕግሥት ታላቁን ኃጢአት ያስተሠርያል
ለ. የጠቢብ ሰው የአፉ ቃል ሞገስ ናት
ሐ. ሀ እና ለ
መ. መልስ የለም

https://youtu.be/SSXitc4cElw?si=uLSjYCxKhGQOdGyd






💝 መጽሐፈ መክብብ ክፍል 1 💝

💝ምዕራፍ ፩፡-
-ሰሎሞን ከንቱ ከንቱ የከንቱ ከንቱ ሁሉ ከንቱ ነው እንዳለ
-ከፀሐይ በታች ከተደረገው ሁሉ አዲስ ነገር እንደሌለ መነገሩ

💝ምዕራፍ ፪፡-
-የጠቢብ ዓይኖች በራሱ ላይ እንደሆኑ
-አላዋቂ በከንቱ መናገርን እንደሚያበዛ

💝ምዕራፍ ፫፡-
-ለሁሉ ዘመን እንዳለው መነገሩ
-እግዚአብሔር የሠራው ሥራ ሁሉ በጊዜው መልካም እንደሆነ
-ለሰው ልጆች ሞት እንዳለባቸው መነገሩ

💝ምዕራፍ ፬፡-
_ድካማቸው መልካም ዋጋ አለውና አንድ ብቻ ከመሆን ሁለት መሆን እንደሚሻል

💝ምዕራፍ ፭፡-
-የጠቢባንን ትምህርት ለመስማት መቅረብ እንደሚገባ
-የተሳሉትን ስእለት መስጠት እንደሚገባ

💝የዕለቱ ጥያቄ💝
፩. ከሚከተሉት ውስጥ ትክክል የሆነው የቱ ነው?
ሀ. አላዋቂ ሰው በከንቱ መናገርን ያበዛል
ለ. የጠቢብ ዓይኖች በራሱ ላይ ናቸው
ሐ. እግዚአብሔር የሠራው ሥራ ሁሉ በጊዜው መልካም ነው
መ. ሁሉም

https://youtu.be/XzQU9esB-pc?si=cXC7dUYrhObhdxdM


💙 የጥያቄዎች መልስ ክፍል 157 💙

▶️፩. "ስለ ፍሬው ፋንታ የመላእክትን ምግብ ለሕዝብህ መገብኻቸው" ይላል (ጥበ.16፥20)። "የመላእክት ምግብ" ሲል ምን ማለት ነው? የመላእክት ምግባቸውስ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ይህ በሁለት ይተረጎማል። አንደኛው ተመልአከ አለቃ ሆነ ከሚለው ግሥ መላእክት ሲወጣ አለቆች ተብሎ ይተረጎማል። አለቆቹ እነሙሴ የተመገቡትን ምግብ እስራኤላውያን ሕዝቡ መመገባቸውን ያመለክታል። ሁለተኛው ለአከ ላከ ከሚለው መልእክተኞች ይወጣል። ይህ የእግዚአብሔር መልእክተኞች የሆኑ መላእክትን ያመለክታል። ሕዝቡ የመላእክትን ምግብ በሉ ማለት እንደ መላእክት አመሰገኑ ማለት ነው። የመላእክት ምግብ ያለው ምስጋናን ነው።

▶️፪. ጥበ.፲፯፥፱ ላይ "የሚያውከው ነገር ምንም ባያስፈራቸው የሚበርር ተሓዋሲ እንቅስቃሴ እና የእባቦች ጩኸት አባረራቸው" ይላል። ተሓዋሲ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ጥቃቅን ደማውያን ፍጥረታትን ተሐዋስያን ይላቸዋል። በእንግሊዘኛ Insects ከሚላቸው ጋር የተቀራረበ ትርጉም አለው።

▶️፫. ጥበ.16፥27 ላይ ፀሐይ ተብሎ የተገለጸው ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው? ወይስ ሌላ ነው?

✔️መልስ፦ በምሥጢር ለክርስቶስ ይነገራል። ከሰማይ የወረደላቸውን መና እሳት አያቀልጠውም ነበር። በትንሽ ዋዕየ ፀሐይ ግን ቀልጦ ጠፋ ተብሏል። ፀሐየ ጽድቅ ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ በቤተ መቅደስ ተቀምጦ የነበረው መና ቀልጦ ጠፍቷል። አማናዊው መና ክርስቶስ ተወልዷልና። እስመ ፀሐይኒ የኀሥሥ ይምጻእ ኀቤነ ያለው ይህን የበለጠ ያጎላዋል።

▶️፬. ጥበ.16፥17 ላይ "ዓለም የጻድቃን ረዳት ነው" ይላል። ዓለም የራሱ የሆኑትን እንጂ ከዓለም ያይደሉ ጻድቃንን ይወዳል እንዴ? ሲጀመር ዓለም ጻድቃንን የሚጠላቸው ሆኖ ሳለ እንዴት ይረዳቸዋል ይባላል? (ዮሐ.15፥19)።

✔️መልስ፦ በዚህ ጊዜ ጻድቃን ያላቸው እስራኤላውያንን ነው። ዓለም የተባሉትም ከዚሁ የተጠቀሱት እሳትና ውሃ ናቸው። እነዚህ እስራኤላውያንን ረዱ ማለት ነው። ይኸውም ውሃ ጠላቶቻቸውን እነፈርዖንን በማስጠም፣ እሳት ሌሊት እያበራ መንገድ በመምራት ረድቷቸዋልና ይህን ለመግለጽ ነው።

▶️፭. መና እንዴት ነው የእግዚአብሔር ሰማያዊ መልክዕ አርአያ የሚሆነው? ሲጀመር ከሰው ውጭ በእግዚአብሔር መልክዕ እና አርአያ የተፈጠረ ፍጥረት አለን? (ዘፍ.1፥26)።

✔️መልስ፦ ምሳሌ፣ አርአያ፣ መልክዕ የተባሉት አንጻራዊ አገላለጾች እንጂ ፍጹማዊ አይደሉም። ሰው እግዚአብሔርን ይመስላል ስንል መምሰሉ ሙሉ በሙሉ ሳይሆን በጥቂት ነው። ከሰማይ የወረደው መና የእግዚአብሔር መልክና አርአያ አለው መባሉ እስራኤላውያን ያንን በልተው ከረኀብ እንደዳኑ ወልደ እግዚአብሔርም ሰው ሆኖ ሥጋዬን ብሉ ደሜን ጠጡ ይላልና የዚህ ምሳሌ ነው። መመሳሰሉ መናው ረኀበ ሥጋን እንዳራቀ የክርስቶስ ሥጋና ደምም ከረኀበ ነፍስ ያድናልና።

▶️፮. ጥበ.18፥5 ላይ "ያለ ርኅራኄ በብዙ ውኃ አጠፋህ" ይላል። ያለ ርኅራኄ ሲል እንዴት ይተረጎማል?

✔️መልስ፦ ይህ የእግዚአብሔርን ፈታሒነት ይገልጻል። እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ሰው እንደ ጥፋቱ መጠን ልክ ይፈርድበታል። ያለ ርኅራኄ ማለት በፍርድ ጊዜ ፊት ሳያደላ፣ በደለኛውን ሳይምር እንደበደሉ አጠፋው ማለት ነው። በኋላም በምጽአት ጊዜ ኃጥኣንን ሑሩ እምኔየ ሲላቸው ፍርዱ ስለሆነ ራርቶ ወደ መንግሥተ ሰማያት ይመልሳቸዋል አንልም። በትክክል ፈራጅነቱን ለመግለጽ ያለ ርኅራኄ ተብሏል።

▶️፯. ጥበ.16፥22 እሳት እና በረድ ሳይጠፋፉ የነበሩት መቼ ነው?

✔️መልስ፦ እሳትና በረድ ሳይጠፋፉ የተባለው እግዚአብሔር በግብፃውያን ላይ መቅሠፍት ሲያመጣ በአንድ ወቅት እሳት፣ በረድ፣ ዝናም ቀላቅሎ አዝንሟልና ይህን ለመግለጽ ነው።

▶️፰. ጥበ.16፣4 ላይ "በእነዚህ ላይ ፍርድ ያለርህራሄ ይወርድ ዘንድ ግድ ነው" ይላል። በእስራኤላውያን ላይ ነው? በግብፃውያን ላይ ነው?

✔️መልስ፦ በግብፃውያን ላይ ነው።

▶️፱. ጥበ.16፣18 "የእሳት ነበልባል በዝንጉዎች ላይ የተላኩ እንስሳትን እንዳያቃጥል ለማዳን ሆነ" ይላል። ዝንጉዎች እና እንስሳት ተብለው የተገለፁት እነማንን ነው ቢብራራልኝ?

✔️መልስ፦ ከዚህ ላይ ዝንጉዎች የተባሉ ግብፃውያን ናቸው። እንስሳት የተባሉ እስራኤላውያን ናቸው። በዝንጉዎች ግብፃውያን የመጣው መከራ እስራኤላውያንን እንዳይጎዳ ማለት ነው።

▶️፲. ጥበ.፲፯፥፫ ላይ "የበደሉትን ዐስበው በውስጡ ብርሃን በሌለበት ቤት ውስጥ ከዝንጋዔ መጋረጃ በታች ተሰወሩ። እጅግም እየተደነቁ በድንጋጤ ቀለጡ። በምትሀትም ታወኩ" ይላል። ከዝንጋዔ መጋረጃ በታች ተሰወሩ እና በምትሐትም ታወኩ ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ ከዝንጋኤ መጋረጃ በታች ተሠወሩ ማለት በዝንጋኤያቸው ምክንያት ጠፉ ማለት ነው። በምትሐትም ታወኩ ማለት ራሳቸው የግብፅ ጠንቋዮች ባሳዩዋቸው ምትሐት ታወኩ ማለት ነው።


© በትረ ማርያም አበባው

✝️የዩቲዩብ ቻናሌ:- ንሕነ ዘክርስቶስ https://youtube.com/@edenawizechristos?si=6V4y-73OM3LTzhAf ነው።

🌻የፌስቡክ ገጼ Betremariam Abebaw https://www.facebook.com/profile.php?id=100075547015721 ነው።


Video is unavailable for watching
Show in Telegram
ሊቀ መዘምራን በቃሉ ብዙነህ


ለምን ወደቅን ? እንዴት እንነሣ ?
የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ "እለ ትነብሩ ተንሥኡ "የተቀመጣችሁ ተነሡ በሚል ርእስ የተዘጋጀው መጽሐፍ ባለመፈፀማቸው ምክንያት ለመንፈሳዊ እና ሥጋዊ ድቀት እያዳረጉን ያሉ የክህነት አሰጣጥና የምንኩስና ሥርዓት አለመከበር እንዲሁም የአብነት ትምህርት ትኩረት ማጣትና  የጋብቻ ሥርዓት አለመከበር  ከቅዱሳት መጻሕፍት መረጃና ማስረጃ በማቅረብ ለትንሣኤ ከሚያበቁ ከመፍትሔ ሐሳቦች ጋር በስፋት  ተዳሰውበታል በተለይም ከዲቁና ጀምሮ ያለው የክህነት አሰጣጥ ሥርዓታችን እንደ ቅዱሳን ሐዋርያትና ሊቃውንት አስተምህሮ መምራትና መፈጸም የማንችል ከሆነ አሁን ከሚታየው በላይ የቤተክርስቲያን አንድነት ጥያቄ ምልክት ውስጥ ይገባል። በመሆኑም መጽሐፉ ለቤተክርስቲያን አንድነት ቅድሚያ በመስጠት ገዳማት ለዓቅመ ምንኩስና ያልደረሱ ሰዎችን እንዳያመነኩሱ ጳጳሳት ለዓቅመ ክህነት ያልደረሱ ሰዎችን ሥልጣነ ክህነትን እንዳይሰጡ የቤተክርስቲያን አስተዳደር የአብነት መምህራንን ያካተተ እንዲሆን ምእመናን በጋብቻ ሥርዓት እንዲጸኑ ያስገነዝባል።


#Home_for_Andu's_Family
🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔺🔻🔺
የውድ ወንድማችን የዶ/ር አንዷለም ዳኘን ልጆችና ቤተሰቦች ለማገዝ እስካሁን ያደረጋችሁትን ድጋፍ እያመሰገንን የ40 ቀን መታሰቢያ ምክኒያት በማድረግ #Home_for_Andu's_Family በሚል መሪ ቃል ልዩ የድጋፍ ማሰባሰቢያ መርሀግብር ተዘጋጅቷል። ስለሆነም ሁላችሁም የምትችሉትን ድጋፍ ታደርጉ ዘንድ በትህትና እንጠይቃለን።

#የጥምር_ሂሳበ_ቁጥር_ሥም፦

1.  ዶ/ር ሀይልማሪያም አወቀ እንግዳው
2.  ዶ/ር አምሳሉ  ወርቁ መኮነን
3.  ዶ/ር መኳንንት ይመር

1. አማራ ባንክ = 9900037383825
2. የአቢሲኒያ ባንክ=218081487
3. የንግድ ባንክ = 1000676116978
4. የአዋሽ ባንክ= 013200903947800

በተጨማሪም ከስር በተቀመጠው የወገን ፈንድ ማገዝ ትችላላችሁ፦
https://www.wegenfund.com/causes/drandualem/


#የባከኑ #ዓመታት
የካቲት 29 ቀን የተወለድኩባት ቀን ናት። በቸርነቱ ብዛት እስካሁን ያቆየኝ የአባቶቻችን አምላክ ልዑል እግዚአብሔር ይመስገን።

ባለፉት ጊዜያት የረባ ሥራ ባልሠራም ወደፊት ግን በቀረኝ ዕድሜ የሚጠቅም ሥራን ሠርቼ እንዳልፍ በጸሎታችሁ አስቡኝ።


💗 መጽሐፈ ጥበብ ክፍል 4 💗

💗ምዕራፍ ፲፮፡-
-የእግዚአብሔር ቃል ሁሉን እንደሚያድን
-እግዚአብሔር በሕይወትና በሞት ላይ ሥልጣን እንዳለው

💗ምዕራፍ ፲፯፡-
-የእግዚአብሔር ፍርድ ታላቅ እንደሆነ

💗ምዕራፍ ፲፰፡-
-በጻድቃን ዘንድ ታላቅ ብርሃን እንደነበር

💗ምዕራፍ ፲፱፡-
-እግዚአብሔረ በታላላቅ ተአምራት እስራኤልን ከግብፅ እንዳወጣ

💗የዕለቱ ጥያቄ💗
፩. ከሚከተሉት ውስጥ ትክክል ያልሆነው የትኛው ነው?
ሀ. እግዚአብሔር በሕይወትና በሞት ላይ ሥልጣን አለው
ለ. እግዚአብሔር ሁሉን ያድናል
ሐ. ሀ እና ለ
መ. መልስ የለም

https://youtu.be/3byPjY5ktVI?si=xvHbaxhqzJ2m_cXh


💙 የጥያቄዎች መልስ ክፍል 156 💙

▶️፩. "ክፉ አሳብ የሰው ጥበብ ፍሬ የሌለው የማስጌጥ ድካም ወይም ቀለም በመቀባት መልካቸው የሚለወጥ ሥራዎች አያስቱንምና" ይላል (ጥበ.15፥4)። ስለ cosmetic አጠቃቀም የቤተክርስቲያን ትምህርቷ ምንድን ነው? ራስን ከመጠበቅና በሌላው መካከል ያለው balance የት ላይ ነው? ከዚህ ጋር አያይዤ አርቲፊሻል ፀጉር፣ ለውበት ሲባል የአካል ቀዶ ጥገና ፀጉር የማስተካከል እና መሰል ከውበት መጠበቅ ጋር በሚያያዙ ነገሮች ዙሪያ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ውበትን የመረዳት አቅማችን ዝቅተኛ ሆኖ ነው እንጂ የሰው ልጅ በተፈጥሮው ራሱ ውብ ነው። እግዚአብሔር የሰጠውን መልክ ንቆ መልኩ ባልሆነ ነገር መገለጥ ግን ከማንም አይጠበቅም። ይህ የውሸት ሌላ ገጽታ ነውና። ራስን መጠበቅ ማለት የተሰጠንን ውበት መጠበቅ ማለት ነው እንጂ ያልሆንነውን መስሎ መታየት አይደለም። ለውበት ሲባል ቀዶ ጥገናም ተገቢ አይደለም። በተሰጠን እግዚአብሔርን ማመስገን እንጂ ያልተሰጠንን መሻት አይገባምና። ራስን መጠበቅ ሰውነትን በውሃ በመታጠብ ንጽሕናን መጠበቅ ነው። ከዚህ ውጭ የእኛ ያልሆነን ጸጉር የእኛ አስመስለን ብናደርገው የውሸት ሌላ ገጽታ ስለሆነ አይገባም።

▶️፪. ስለ ጣዖት ውጤት ሲናገር "ሰውነትን ከማስተዳደፍ ጋር ፍጥረትንም ከመለወጥ ጋር" ይላል (ጥበ.14፥26)። "ፍጥረት መለወጥ" የሚለው ላይ በዚያን ሰዓት የፆታ መቀያየር ነበር? ከዚህ ጋር አያይዤ በሕክምና ፆታን ስለመቀየር የቤተክርስቲያን ትምህርቷ ምንድን ነው? ሁለት ፆታ ይዘው ስለሚወለዱ ሰዎችስ?

✔️መልስ፦ ፍጥረትን መለወጥ የሚለውን ግእዙ "ሙያጤ ልደት" ብሎታል። በአንዱ ማኅፀን ያለውን ወደ ሌላ ማኅፀን መገልበጥ ብለው ሊቃውንቱ ተርጉመውታል። የፆታ መቀያየር ሳይሆን ከተፈጠረልን ነገር ማፈንገጥን ለመግለጽ የመጣ ነው። በሕክምና ፆታን መቀየር በክርስትና አይፈቀድም። ሁሉም እግዚአብሔር በሰጠው ጾታ መኖር አለበት እንጂ ጾታን መቀየር እግዚአብሔርን ሲፈጥረን ተሳስቷል እንደማለት ስለሆነ ተገቢ አይደለም። ሁለት ጾታ ይዘው የሚወለዱ ሰዎች ካሉ በጥምቀት ጊዜ በሚሸኑበት ጾታ መሠረት ይጠመቃሉ። በወንዱ ጾታ የሚሸና ሰው በ40 ቀን፣ በሴት ጾታ የሚሸና ካለ በ80 ቀን ይጠመቃል።

▶️፫. "ልጁ ሕፃን ሳለ ፈጥኖ በሞት ስለ ተነጠቀ አባቱ ለአንድ ልጁ ይጨነቅና ያለቅስ ነበርና ቀድሞ ለሞተው ልጁ ምስል ሠራለት። ዛሬ ግን እንደ አምላክ አድርገው አከበሩት። ለኀጢአት የተገዙ ሰዎችም በስውር በዓል አደረጉለት። የምሥጢር መሥዋዕትንም ሠዉለት" ሲል እነዚህ አባትና ልጅ እነማን ናቸው?

✔️መልስ፦ አባት የተባለው ሴሩህ ሲሆን ልጅ የተባለው ብኑ ነው። ሴሩህ ብኑ የሚባል ልጅ ነበረው። ብኑ በሕፃንነቱ ሞተ። ሴሩህ ከኀዘን ጽናት የተነሣ እህል አልቀምስም ውሃም አልጠጣም አለ። ከዚያ ዘመዶቹ እንጨት ጠርበው የሞተውን ብኑን አስመስለው ቀርጸው ቀለም ቀብተው ልጅህ ብኑ ተነሣ አሉት። ሴሩህም መጥቶ ልጄ ብኑ ነህ ሲለው በጣዖቱ ያደረ ሰይጣን አዎ ነኝ አለ። ከዚህ በኋላ ሰይጣን በጣዖቱ እያደረ አምላክ ነኝ እያለ ሲያታልል ኖሯል። ይህን ለመግለጽ የተነገረ ነው።

▶️፬. "የዝሙት መጀመሪያዋ ጣዖትን የመሥራት ዐሳብ ነውና። እርሱንም ማግኘት የሕይወት ጥፋት ነው" ሲል በዚህ አገብብ የዝሙት ትርጕሙ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ዝሙት የሚባለው ሴትና ወንድ በመኝታ የሚያደርጉት ብቻ አይደለም። እግዚአብሔርን ትቶ ጣዖትን ማምለክም ከዝሙት የሚቆጠርበት አግባብ አለ። ከዚህ የተገለጸው ይህ ነው።

▶️፭. "እርሷ በውዱሱ ነቢይ እጅ ሥራቸውን አቃናች" ይላል (ጥበ.11፥1)። ውዱሱ ነቢይ የተባለው ማን ነው?

✔️መልስ፦ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ነው።

▶️፮. "የተሠራው ሥራ ከሠሪው ጋራ ይፈረድበታልና" ይላል (ጥበ.14፥9)። እንዴት ግዑዝ የሆነ ነገር ይፈረድበታል?

✔️መልስ፦ ጣዖቱን የሠራው ሰው እንደሚፈረድበት የሚያመለክት ቃል ነው። ሥራው ይፈረድበታል ያለው ጣዖቱ ይፈረድበታል ለማለት ነው። አሁን ጣዖት ግዕዛን ያለው ሆኖ ለፍርድ የሚቆም ሆኖ አይደለም። በጣዖቱ አድረው ሳይፈጥሩ ይመለኩ በነበሩ አጋንንት ይፈረድባቸዋል ማለት ነው።

▶️፯. "ማንም ማን ወዳልኖረበት ምድረ በዳ ሄደው ኖሩ። ያልተረገጠች ቦታም የድንኳኖቻቸውን ካስማ ተከሉ" ይላል (ጥበ.11፥2)። ከምድረ በዳ ሄደው ኖሩ የተባሉት እነማን ናቸው?

✔️መልስ፦ እስራኤላውያን ናቸው። ከግብፅ ወጥተው ከነዓን እስከሚገቡ ድረስ ለአርባ ዓመት በምድረበዳ ኖረዋልና።

▶️፰. "ይህም ባይሆን ድንገት የተፈጠሩ የማይታወቁ የሚያላልብና የሚፋጅ እሳትን የሚተነፍሱ ይህም ባይሆን የሚከረፋ የጢስ መዓዛን የሚተነፍሱ ይህም ባይሆን ክፉ ከሚሆን ዓይናቸው የብረት ፍንጣቂ የመሰለ ቦግ ቦግ የሚያደርጉ መዓትን የተመሉ አውሬዎችን ላክህባቸው" ይላል (ጥበ.11፥19)። እነዚህ አውሬዎች የተባሉት እንደምን ዓይነት እንስሳት ናቸው? ምሳሌ ቢጠቀስልን።

✔️መልስ፦ እነዚህ አውሬዎች ግሩማን አራዊት ይባላሉ። ከአስፈሪነታቸው የተነሣ ሰው እነርሱን ካየ ነፍሱ ከሥጋው እንደሚለይ ይነገራል። ስለዚህ በዚህ ዓለም ቢኖሩም ከሰባቱ የመሬት ክፍሎች በአንዱ የሚገኙ ስለሆነ አናያቸውም።

▶️፱. ጥበ.፲፬፥፳፯ ላይ "ስም የሌላቸው ጣዖቶችን ማምለክ የክፋት ሁሉ መጀመሪያ ነውና። የፍጻሜውም ምክንያት ነውና" ይላል። ስም የሌላቸውን ሲል ስም ልዩነት ያመጣል እንዴ?

✔️መልስ፦ የክፋት ሁሉ መጀመሪያ ያሰኘው ጣዖቱን ማምለኩ ነው እንጂ ለጣዖቱ ስም አለመኖሩ አይደለም። አንድ ሰው ጣዖት ካመለከ ለጣዖቱ ስም ይኑረውም አይኑረውም ያው ክፋት ስለሆነ ፍዳውን መቀበሉ አይቀርምና።

▶️፲. መጽሐፈ ጥበብና መጽሐፈ ተግሣጽ በግእዙና በአማርኛው የምዕራፉ ብዛት የተለያየ ሆኖ ይታየኛል። ልዩነቱ የተፈጠረበትን ሁኔታ ቢያስረዱን።

✔️መልስ፦ ለመጻሕፍት አርእስት የሰጡ የኋላ ሊቃውንት ናቸው። ለአጠናን እንዲያመች ምዕራፍና ቁጥር የሰጡት ደግሞ ልዩ ልዩ ሊቃውንት ናቸው። ስለዚህ ሐሳቡ በሁሉም በምልአት የተቀመጠ ነው። የምዕራፉና ቁጥሩ መብዛትና ማነስ ሐሳቡን አይቀንሰውም። ይህ ልዩነት የሚፈጠር ቁጥሩን የተለያዩ ሊቃውንት ስለሰጡት ነው።

▶️፲፩. ጥበ.15፥2 ላይ "ኃይልህን እያወቅን ብንበድል የአንተ ነን" ሲል ሰው እያወቀ (intentionally) ኃጢአት ቢሠራ የዲያብሎስ የግብር ልጅ ቢሆን እንጂ እንዴት የጌታ ይሆናል?

✔️መልስ፦ ብንበድልም ባንበድልም የአንተ ነን ማለት በተፈጥሮ ማንኛውም ፍጡር የእግዚአብሔር ገንዘብ መሆኑን የሚያመለክት ነው። ሰው ኃጢአት ሲሠራም ቢሆን በግብሩ የሰይጣን ልጅ ቢሆን በተፈጥሮ ግን የእግዚአብሔር ፍጥረት ነውና።


© በትረ ማርያም አበባው


✝️የዩቲዩብ ቻናሌ:- ንሕነ ዘክርስቶስ https://youtube.com/@edenawizechristos?si=6V4y-73OM3LTzhAf ነው።

🌻የፌስቡክ ገጼ Betremariam Abebaw https://www.facebook.com/profile.php?id=100075547015721 ነው።

20 last posts shown.