በትረማርያም አበባው Betremariam Abebaw


Channel's geo and language: Ethiopia, Amharic
Category: Religion


አቀድም አእኵቶቶ ለእግዚአብሔር

Related channels  |  Similar channels

Channel's geo and language
Ethiopia, Amharic
Category
Religion
Statistics
Posts filter


© ሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ እንደጻፉት

በጉባኤ ቤት መኖር ደስ የሚያሰኘው በየዕለቱ አዲስ አዲስ ሰው ተፈጥሮ ስለሚያድር ነው። በአትክልት ስፍራ ብትኖሩ በየጊዜው ፍሬ የሚሰጡ፣ በመዓዛቸው ልብን የሚመስጡ ዕፀዋትን ልትመለከቱ ትችላላችሁ በዚህ ከምትደሰቱት በላይ በየዕለቱ እግዚአብሔር ሰው ሲሠራ የምትመለከቱበት ቦታ ስለሆነ በጉባኤ ቤት የመኖርን ጣዕም ብትቀምሱት ደግሞ ከዚህ በላይ በጣም ትወዱታላችሁ።

እኛ የተከልነውን፣ ያጠጣነውን እግዚአብሔር ደግሞ ዕለት ዕለት ያሳድግ ነበርና ይኸው ዛሬ ማደጉን የሚያስረዳ ፍሬውን አንዥርግጎ መታየት ከጀመረ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። በመገብተ ኦሪት የቀመስነውን ፍሬ ደግመን እንድናጣጥመው ይዞልን ብቅ ብሏል።

እንደ አባቶቹ ወምበር ተክሎ ጉባኤ አስፍቶ ያስተማረ በዐውደ ምሕረትም አንደበቱ የሚጣፍጥ የተወደደው ወንድማችን መምህር ምሥጢሩ ታየ ዛሬ በነገረ እግዚአብሔር ላይ ከመምህራን አፍ፣ ከከርሠ መጽሐፍ የሰበሰበዉን ቤተ ክርስቲያን ስለ ነገረ እግዚአብሔር የምትሰብከዉን ቃል በመጽሐፍ ይዞልን በመምጣቱ እያመሰገንሁ ለአንባብያን ደግሞ ቆላ ሳንወርድ ደጋ ሳንወጣ በቆላና በደጋ በሩቅና በቅርብ ያሉ መምህራን ያስተማሩትን በልዩ ልዩ ቋንቋ የተጻፉ መጻሕፍት ለዘመናት በውስጣቸው የተሸከሙትን የሕይወት ቃል ቤታችን ድረስ ስለመጣልን በምስጋና ሁሉም እንዲያነበው እጋብዛለሁ።

ጣዕም የሕይወት ስንቅ ይዞልን ስለመጣ ሁላችንም እጃችንን ዘርግተን እንድንቀበለው እጠይቃለሁ!

© ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ


▶️፴፩. ምሳ.24፥54 ላይ "ለአልቅት" ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ አልቅት የሚባለው በወንዝ አካባቢ የሚገኝ ከብቶች ውሃ ሲጠጡ ከውሃው ጋር አብሮ ወደ ሰውነታቸው ገብቶ ደማቸውን የሚመጥ ተሳቢ የሚያሙለጨልጭ ፍጥረት ነው።

▶️፴፪. ምሳ.22፥1 ላይ "መልካም ስም ከብዙ ባለጠግነት ይሻላል" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ ብዙ ባለጠግነት ካላበሉበት ካላጠጡበት ኃላፊ ነው። ሰው ግን ባለጠጋ ሆኖ ነዳያንን ቢያበላበት፣ ቢያጠጣበት እርሱማ በጎ ሰው ነው፣ በጎ ሰው ነበር እየተባለ በመልካምነት ስሙ ይጠራል ይወሳል ይነገራል ማለት ነው።

▶️፴፫. ምሳ.24፥73 ላይ ሰሎሞን ልጁን እንዴት የማኅፀኔ ልጅ ይላል? ሴት አይደለምና።

✔️መልስ፦ ማኅፀን ያላት ሴት ናት እንጂ ወንድ ማኅፀን እንደሌለው የታወቀ ነው። ከዚህ ላይ ሰሎሞን የማኅፀኔ ልጅ ያለው ግን ከባሕርይዬ የምትወለድ የባሕርዬ ልጅ ለማለት ነው። ማኅፀን ያለው ባሕርይውን ነው።

▶️፴፬. "ጥበብ ወይም ማስተዋል ወይም ምክር በእግዚአብሔር ላይ የለም" ይላል (ምሳ.21፥30) ምሥጢሩ ምንድን እንደሆነ ቢብራራልን።

✔️መልስ፦ ግእዙ የተሻለ አድርጎ ገልጾታል። "አልቦ ጥበብ ወአልቦ እዘዝ በኀበ ዐብድ ወአልቦ ምክር በኀበ ረሲዕ" ይላል። ትርጉሙም በሰነፍ ሰው ጥበብ ማስተዋል (ሥልጣን) የለም። እግዚአብሔርን በዘነጋ ሰውም ምክር የለም ብሎታል። ጥበብ፣ ምክር፣ ማስተዋል በእግዚአብሔር ላይ የለም ማለት እግዚአብሔርን የሚቃወም ጥበብ፣ ምክር፣ ማስተዋል የለም ማለት ነው። በዚህም እንግሊዘኛው ከአማርኛው ጋር ተቀራራቢ አገላለጽ ቢጠቀምም "በ...ላይ" የሚለው ቃል ግን "Against" ብሎ ተቃውሞን አመላክቶ ከአማርኛው ሻል ያለ አገላለጽን ተከትሏል። "There is no wisdom nor understanding nor counsel against the LORD" ይላል።


© በትረ ማርያም አበባው


✝️የዩቲዩብ ቻናሌ:- ንሕነ ዘክርስቶስ https://youtube.com/@edenawizechristos?si=6V4y-73OM3LTzhAf ነው።

🌻የፌስቡክ ገጼ Betremariam Abebaw https://www.facebook.com/profile.php?id=100075547015721 ነው።


▶️፲፯. "ኋላ እንዳትፀፀት ገንዘብህን፣ ልብህንና ጉልበትህን ለሴቶች አትስጥ" ይላል (ምሳ.24፥60)። ይህ ሴቶች አይታመኑም ለማለት ነው? ገንዘብን በተመለከተ አንድ ባል ከሚስቱ ጋር እንዴት ይኑር?

✔️መልስ፦ ደጋግ ሴቶች ለባሎቻቸው ታማኝ ናቸው። ይህ ስለክፉ ሴት የተነገረ ነው። ለክፉ ሴት አንቺ አስተዳድሪኝ ብሎ ገንዘብን መስጠት አይገባም ማለት ነው። ገንዘቡን አጥፍታ ባልሰጣት ኖሮ ብሎ እንዲጸጸት ታደርገዋለችና። ባልና ሚስት አንድ አካል ስለሆኑ በምክክር በፍቅር ራሳቸውን ማስተዳደር ይገባቸዋል።

▶️፲፰. "ታካች ሰው አንበሳ በሜዳ ነው። በመንገዱ ላይ እሞታለኹ ይላል" ይላል (ምሳ.22፥13)። በመንገዱ ላይ እሞታለኹ ብሎ ማሰቡ ከመጠንቀቅ አንጻር ትክክል አይደለም?

✔️መልስ፦ አንበሳ በሜዳ መኖሩን ሳያውቅ አንበሳ በሜዳ አለ ብሎ በሌለ ነገር ከሥራ መቅረት ትልቅ ስንፍና ነው። በሌለ ነገር እሞታለሁ ብሎ ማሰብ ስንፍና ነው። ስለዚህ ይህ ከመጠንቀቅ አንጻር የተነገረ አይደለም። ላለመሄድ ሰነፍ ሰው በራሱ የፈጠረው ምናባዊ ፍርሀት (Imaginary fear) ነውና።

▶️፲፱. "ሰውነትኽም ቢሣሣ በጕረሮኽ ላይ ካራ አድርግ" ይላል (ምሳ.23፥2)። ካራ አድርግ ያለው በተግባር ነው?

✔️መልስ፦ ይህ ምሳሌያዊ አነጋገር ነው እንጂ ቀጥታ የሚተገበር አይደለም። ሰውነትህ ቢሳሳ ሰውነትህ ላይ ካራ አድርግ ማለት ካራ እንደሚጎዳ ስስትም እንደሚጎዳ አስብ ማለት ነው።

▶️፳. "ባለጠጋ ለመኾን አትድከም። የገዛ ራስኽን ማስተዋል ተው። በእርሱ ላይ ዐይንኽን ብታዘወትርበት ይጠፋል። ባለጠግነት ወደ ሰማይ እንደሚበር እንደ ንስር ለራሱ ክንፍ ያበጃልና" ይላል (ምሳ.23፥4-5)። የገዛ ራስኽን ማስተዋል ተው ሲል ምን ማለት ነው? ክንፍ ያበጃልና ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ የገዛ ራስህን ማስተዋል ተው ማለት ባለጠጋ ለመሆን ከመድከም ተው ራቅ ማለት ነው። ይኸውም በክፋት ከሚደረግ ባለጠግነት መሸሽ እንደሚገባ የሚያመለክት ነው። ንስር በክንፉ ከፍ ብሎ ርቆ እንደሚበር ሁሉ ባለጠግነትም በምኞት ብቻ የማይገኝ ሩቅ ነው ማለት ነው።

▶️፳፩. "አንዳንድ መጻሕፍት መጽሐፈ ምሳሌን 31 ምዕራፍ ያደርጉታል አንዳንዱ ደግሞ 24 ምዕራፍ ያደርገዋል ለምንድን ይሆን?

✔️መልስ፦ መጽሐፈ ምሳሌን 31 ምዕራፍ የሚያደርጉት መጽሐፈ ተግሣጽ የሚል ተጨማሪ መጽሐፍ የላቸውም። 24 የምንል እኛ ደግሞ ከምሳሌውም ተግሣጽ ላይ የሚያተኩሩት ለብቻቸው ተጽፈው መጽሐፈ ተግሣጽ ተብለው ለብቻው ስለሚሰጡ ስለሆነ ምንም ዓይነት የምሥጢር ልዩነት አያመጣም።

▶️፳፪. ምሳ.፳፩፥፲፰ ላይ "ከነዝናዛ ሴት ጋር ከመቀመጥ ይልቅ በምድረበዳ መቀመጥ ይሻላል" ይላል። ትርጓሜው ምንድን ነው? ይች ሴት የገጠመችው ሰው/ሴቷም እንዲሁ የገጠማት በሐዲስ ኪዳን ሲመዘን መፍትሔው ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ነዝናዛ ሴት በነፍስም በሥጋም ጉዳትን ታመጣለች። በምድረበዳ ብንቀመጥ ግን ግፋ ቢል የሚያገኙን አራዊት ናቸው። አራዊት ደግሞ በሥጋ ጉዳትን ቢያመጡብን እንጂ በነፍስ ጉዳትን አያመጡብንምና ይሻላል ማለቱ ለዚህ ነው። በሐዲስ ኪዳን በቁርባን ላይፋቱ ቃል ኪዳን ተጋብተው ስለተጋቡ በተቻለ መጠን ተቻችሎ በፍቅር መኖር ነው። በዝሙት ምክንያትና ሌሎች ፍች በሚፈቀድባቸው ጉዳዮች ካልሆነ በቀር ተስማምቶ በአንድ ላይ መኖር ነው።

▶️፳፫. ምሳ.፳፩፥፲፭ ላይ "ጻድቅ ሰው ግን ክፉ በሚሠሩ ዘንድ የረከሰ ነው" ሲል እንዴት የረከሰ ነው?

✔️መልስ፦ ጻድቅ ሰው የክፉ ሰዎችን ክፋት በጽድቁ ስለሚገልጥባቸው ክፉ ሰዎች ይጠሉታል። ጻድቅ ሰው ክፉ በሚሠሩ ዘንድ የረከሰ ነው ማለት እንደ ርኩስ ይታያል ማለት ነው። ይህ ማለት ደግሞ ጻድቅ ሰው በክፉዎች ዘንድ አይወደድም ማለት ነው።

▶️፳፬. ምሳ.፳፩፥፲፯ ላይ "የወይን ጠጅንና ዘይትን የሚወድድም ባለጠጋ አይሆንም" ይላል። በዚህ አገባብ ዘይት ከተፈጥሮው በተለየ ትርጕም አለውን? ዘይትን መውደድ ባለጠግነትን እንዴት ይቃወማል?

✔️መልስ፦ ዘይት የሚለው ለምግብነት የሚያገለግለን ነው። ሰው ገንዘቡን ሁሉ አብዝቶ ወይን በመጠጣትና አብዝቶ ዘይት በመግዛት የሚያጠፋ ከሆነ ባለጸጋ አይሆንም ማለት ነው። በመጠኑ የሚጠቅመውን ያህል ይጠቀም ማለት ነው። ወይንንም በመጠኑ ይጠጣ፣ ዘይትንም በመጠኑ ይጠቀም ለማለት ነው።

▶️፳፭. ምሳ.፳፩፥፳፬ ላይ "የችኩል የነዝናዛና የነገረኛ ሰው ስሙ ቸነፈር ነው" ሲል አልገባኝም።

✔️መልስ፦ ቸነፈር የሚባለው ድንገታዊ ሕመም ሆኖ በአጭር ጊዜ ብዙ ሰው የሚገድል ነው። ችኩል ሰውና ነገረኛ ሰውም በአጭር ጊዜ ብዙ ጥፋት ያጠፋልና ቸነፈር መባል ይገባዋል በግብር ይመሳሰላሉና ማለት ነው።

▶️፳፮. ምሳ.፳፪፥፱ ላይ "መማለጃን የሰጠ ሰው ድል መንሣትንና ሞገስን ያገኛል። ነገር ግን የተቀበለውን ነፍስ ያጠፋል" ይላል። በዚህ አገባብ መማለጃ ጉቦ ከሆነ ሰጭው ጸድቆ ተቀባዩ እንዴት ይፈረድበታል? ቢብራራ።

✔️መልስ፦ መማለጃን የሚሰጥ ሰው ድል መንሣትንና ሞገስን ያገኛል የተባለው በሰጠው ሰው ዘንድ ነው እንጂ በእግዚአብሔር ዘንድ አይደለም። አንዳንድ ሰው መማለጃ ሰጥቶ ከእስር ቤት ወይም ከሌላ ችግር ሊያመልጥ ይችላል። ይህን ከድል መንሣትና ከሞገስ ቆጥሮት ነው እንጂ በእግዚአብሔር ዘንድስ መማለጃን መስጠትም መቀበልም ታላቅ ኃጢአት ነው።

▶️፳፯. ምሳ.፳፫፥፳፯ ላይ "አመንዝራ ሴት የተነደለች ማድጋ ናት። ሌላዪቱም ሴት የጠበበች ጕድጓድ ናት" ይላል። ትርጓሜው ምንድን ነው።

✔️መልስ፦ የተነደለ ማድጋ ውሃ መያዝ እንደማይችል አመንዝራ ሴትም ከብዙ ወንድ ጋር ትተኛለችና ዘር አትቋጥርም ማለት ነው። የጠበበች ጉድጓድ እንደምታስጨንቅ አመንዝራ ሴትም ታስጨንቃለች ማለት ነው።

▶️፳፰. ምሳ.፳፬÷፳፬ ላይ "ከንጉሥ አንደበት ምንም ሐሰት ይነገራል አይባልም። ከአንደበቱም የሚወጣ ሐሰት የለም" ይላል። ከዚህ ላይ ንጉሥ ለምድራዊ ሰው የተሰጠ ከሆነ የዚህ ጽሑፍ እውነትነቱ አልታየኝምና ቢብራራ?

✔️መልስ፦ ይህ በባሕርይው ንጉሥ ለሆነ ለልዑል እግዚአብሔርም ይነገራል። በጸጋ ንጉሥ ለሆነ ስለ ደግ ንጉሥም ይነገራል። ከደግ ንጉሥ አንደበት ሐሰት አይገኝም ማለት ነው። ምድራዊ ሰውም ከተጠነቀቀ አንደበቱን ከሐሰት ከልክሎ መኖር ይቻለዋልና ነው።

▶️፳፱. ምሳ.፳፬፥፸፮ ላይ "ከምክር ጋር ወይን ጠጣ" ይልና ምሳ.፳፩፥፲፯ ላይ ደግሞ ባለጠግነትን እንደሚከለክል ይገልጻል። ይህ እንዴት ይታረቃል?

✔️መልስ፦ ከምክር ጋር ወይን ጠጣ የሚለው በመጠን ወይንን መጠጣት የተፈቀደ ስለሆነ ነው። መጽሐፍ የከለከለው ስካርን ነው እንጂ መጥኖ ጥቂት ወይን መጠጣትን አይከለክልምና። ምሳ.21፥17 ላይ ባለጠግነትን ይከለክላል የተባለው ከመጠን በላይ በየቀኑ የሚጠጡ ከሆነ ገንዘብን ይጨርሳል ድኻም ያደርጋል ለማለት ነው።

▶️፴. ምሳ.24፥21 ላይ "ልጄ ሆይ እግዚአብሔርንና ንጉሥን ፍራ። ከዓመፀኞችም ጋር አትደባለቅ" ይላል። ንጉሥን ፍራ ሲል እንዴት ይተረጎማል? እግዚአብሔርን በምንፈራበት መንገድ ንጉሥን መፍራት ይገባናል?

✔️መልስ፦ እግዚአብሔርን በምንፈራበት መንገድ ሥጋዊ ንጉሥን መፍራት አይገባም። እግዚአብሔርን የምንፈራው ብናጠፋ በነፍስም በሥጋም የሚቀጣን በባሕርይው ፈራጅ በባሕርይው ንጉሥ ስለሆነ ነው። ስለዚህ እግዚአብሔርን ፍራ ማለት ሕጉን ጠብቅ እርሱንም ውደደው ማለት ነው። ንጉሥን መፍራት የሚገባው በጸጋ ይፈርድ ይገዛ ዘንድ ሥልጣን የተሰጠው በመሆኑ ንጉሥን የጸጋ ክብር ማክበር ይገባል ማለት ነው።


💙 የጥያቄዎች መልስ ክፍል 152 💙

▶️፩. ምሳ.21፥14 ላይ "የብብትም ውስጥ ጉቦ ጽኑ ቁጣን ታበርዳለች" ይላል። ጉቦ የሚላት ምጽዋትን ነው ወይስ ሙስና? ሙስና ከሆነ እንዴት ቁጣን ታበርዳለች?

✔️መልስ፦ የአማርኛ መተርጉማን ጉቦ ብለው መተርጎም አልነበረባቸውም። ግእዙንም እንግሊዘኛውንም ሳየው እንደዚያ አይልም። ግእዙ የሚለው "ሀብት ዘበጽሚት ይገፍዕ መዓተ። ወዘሰ ይምሀክ ሀብተ ያነሥእ ጽኑዐ መዓተ" ነው። ግእዙ "ሀብት" የሚለው "ወሀበ" ሰጠ ከሚለው የግእዝ ቃል የሚወጣ ምዕላድ ነው። ትርጉሙ ስጦታ ማለት ነው። ስጦታ ደግሞ የፍቅር ምልክት ነው። ሰው ስጦታ ሲሰጥ ፍቅሩን እየገለጸ ስለሆነ የሌላውን ቁጣ ያርቃል ማለት ነው። እንጂ ከጉቦ ጋር አይገናኝም። እንግሊዘኛውም "A gift in secret pacifieth anger: and a reward in the bosom strong wrath" ነው የሚል (King James Version)። በዚህ አገባብ Gift (ስጦታ) ተብሎና Reward (ሽልማት) ተብሎ ተገልጿል። ሁለቱም ከጉቦ ጋር አይገናኙም።

▶️፪. ምሳ.21፥4 ላይ "ትዕቢተኛ ዓይንና ደፋር ልብ የኃጥኣንም እርሻ ኃጢአት ነው" ይላል። ትዕቢተኛ ዐይን ምትባለው ግን ምን ዓይነት ናት?

✔️መልስ፦ ትዕቢተኛ ዓይን የሚባለው ከፍ ዝቅ አድርጎ በንቀት የሚያይና ገላማጭ ዓይን ነው።

▶️፫. ምሳ.፳፬፥፷-፷፪ ላይ "በሦስት ነገር ምድር ትናወጣለች። አራተኛውንም ልትሸከመው አትችልም። ባሪያ በነገሠ ጊዜ፣ ሰነፍም እንጀራን በጠገበ ጊዜ፣ የተጣለች ሴት ቸር ባል ባገኘች ጊዜ፣ ሴት ባሪያም እመቤቷን በወረሰች ጊዜ" ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ክፉ ባሪያ በነገሠ ጊዜ፣ ሰነፍ ሰው እንጀራን በጠገበ ጊዜ፣ የተጣለች ክፉ ሴት ቸር ባል ባገኘች ጊዜ፣ ክፉ ሴት ባሪያ እመቤቷን በወረሰች ጊዜ የሚለው ሁሉም የነበሩበትን ዘንግተው ትዕቢተኛ እንደሚሆኑና ብዙ ጥፋትን እንደሚያጠፉ ለማመልከት ነው።

▶️፬. ምሳ.፳፫፥፳፫ ላይ "እውነትን ግዛ አትሽጣትም። ጥበብንና ተግሣጽን ማስተዋልንም" ሲል እውነት ሊገዛ ይችላል ወይ?

✔️መልስ፦ እውነትን ግዛ ማለት እውነትን ገንዘብ አድርግ ማለት ነው። የገዙት ነገር ገንዘብ እንደሚሆን ሁሉ አንተም እውነትን ገንዘብ አድርግ ማለት ነው። እውነትን አትሽጣት ማለት የተሸጠ ነገር ባለቤትነቱ ለሌላ እንደሚሆን እውነትን አትተዋት ማለት ነው።

▶️፭. ምሳ.፳፩፥፲፮ ላይ "ከጽድቅ መንገድ የሚሰስት ሰው በረዐይት ጉባኤ ያርፋል" ሲል የረዐይት ጉባኤ ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ረዐይት የሚባሉት ከደቂቀ ሴትና ከደቂቀ ቃኤል ተዳቅለው የተወለዱና ክፉዎች በመሆናቸው በማየ አይኅ የጠፉ ሰዎች ናቸው። የሚሰስት ሰው በረዐይት ጉባኤ ያርፋል ማለት ረዐይት እንደጠፉ እርሱም ይጠፋል ማለት ነው።

▶️፮. ምሳ.፳፩፥፯-፰ ላይ "የኃጥኣን ጥፋት ከሩቅ ይመጣል። እግዚአብሔር ለጠማሞች ጠማማ ሥራ ይልክባቸዋል" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ የኃጥኣን ጥፋት ከሩቅ ይመጣል ማለት በበደላቸው ምክንያት ደርሶባቸው የማያውቅ መከራ ይደርስባቸዋል ማለት ነው። እግዚአብሔር ለጠማሞች ጠማማ ሥራ ይልክባቸዋል ማለት መከራን ያመጣባቸዋል ማለት ነው። ጠማማነቱ ለእነርሱ ነው እንጂ ለእግዚአብሔርማ በእነርሱ ላይ ያመጣው ርቱዕ ፍርዱ ነው።

▶️፯. ምሳ.፳፪፥፯ ላይ "ድኾች ባለጠጎችን ይገዛሉ። አገልጋዮችም ለጌቶቻቸው ያበድራሉ" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ ብልህ ድኾች ሰነፍ ባለጠጎችን ይገዛሉ። ለምሳሌ ዮሴፍ ፈርዖንን በአስተዳደሩ ገዝቶታል። ማለት በዮሴፍ የአስተዳደር ጥበብ ፈርዖን ተመርቷል። አገልጋዮችም ለጌቶቻቸው ያበድራሉ ያለው ይህንኑ ነው። ዮሴፍ ለፈርዖን በአስተዳደሩ ማበደሩን ያመለክታል።

▶️፰. ምሳ. ፳፪፥፳ ላይ "ለዕውቀትና ለምክር ይኾኑኽ ዘንድ ሦስት ነገሮችን እነኾ ጻፍኹልኽ። አንተም በልብኽ ሰሌዳነት ጻፋቸው" ሲል ሦስቱ ነገሮች እነማን ናቸው?

✔️መልስ፦ ሦስቱ ነገሮች የተባሉት ከዚሁ ቀጥለው የተጠቀሱት ድኻን አለመናቅና አለመቀማት፣ ከቁጡ ሰው ጋር ተባባሪ አለመሆን፣ አባቶች ያኖሩትን ድንበር አለማፍረስ ናቸው።

▶️፱. ምሳ.፳፬፥፲፭ ላይ "ኃጥኣንን ወደ ጻድቃን ቦታ አትውሰድ" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ ኃጥኣንን ወደ ጻድቃን ቦታ አትውሰዳቸው ማለት ጻድቃን ናቸው አትበላቸው ማለት ነው። ኃጥእን ጻድቅ፣ ጻድቅን ኃጥእ ማለት አይገባምና።

▶️፲. "በስውር ያለ ስጦታ ቁጣን ይመልሳል። ስጦታን የሚሸልግ ግን ጽኑ ቁጣን ያመጣል" ይላል (ምሳ.21፥14)። የሚሸልግ ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ የሚሸልግ ማለት ስጦታን ላለመስጠት የሚሳሳ፣ ወይም ሰጥቶ የሚያዝን ሰው ማለት ነው።

▶️፲፩. ምሳ.24፥16 ላይ "ጻድቅ ሰባት ጊዜ ይወድቃልና ይነሣማል። ኃጥኣን ግን በክፉ ላይ ይወድቃሉ" ሲል ምን ለማለት ነው ቢያብራሩልኝ?

✔️መልስ፦ ጻድቅ ሰባት ጊዜ ቢወድቅ ማለትም ፈጽሞ ቢወድቅ ይነሣል ማለት በንስሓ ከበደሉ ወጥቶ የቅድስና ሥራ ይሠራል ማለት ነው። ኃጥኣን ግን በክፉ ሥራ ጸንተው ይኖራሉ ማለት ነው።

▶️፲፪. ምሳ.22፥8 ላይ "ኃጢአትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል። የቍጣውም በትር ይጠፋል" ይላል። የቁጣውም በትር ይጠፋል ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ አማርኛው ትርጉም አሻሚ ስላደረገው ነው እንጂ ኃጢአትን የሚሠራ ሰው በመቅሠፍት ይጠፋል ማለት ነው። ግእዙ ደህና ገልጾታል። "ወዘይዘርዕሰ ኅብለ የዐርር እከየ። ወመቅሠፍተ ምግባሪሁ ይፌጽም" ይላል።

▶️፲፫. ምሳ.22፥14 ላይ "የጋለሞታ ሴት አፍ የጠለቀ ጕድጓድ ነው። እግዚአብሔር የተቈጣው በእርሷ ይወድቃል" ይላል። እግዚአብሔር የተቆጣው በእርሷ ይወድቃል ሲል እግዚአብሔር በሴቷ ፈቅዶ እንደሚያሰናክለው (እንደሚቀጣው) ለማለት ነው? እግዚአብሔር ከተቆጣን በሌላ ኃጢአት እንድንወድቅ ያደርጋል ማለት ነው? ግን እግዚአብሔር መውደቃችንን አይፈልግም ከተባለ ከዚህ ጋር እንዴት ይታረቃል?

✔️መልስ፦ እግዚአብሔር የተቆጣው ተብሎ የተገለጸው እግዚአብሔር ረድኤቱን የነሣው ለማለት ነው። ሰው ኃጢአትን ሲሠራ እግዚአብሔር ረድኤቱን ይነሣዋል። በዚህ ጊዜ ሰው በጥፋት ላይ ጥፋት ይሠራል። ይህን ለመግለጽ የተነገረ ነው። እግዚአብሔር መውደቃችንን አይፈልግም። ግን ደግሞ የነጻነት አምላክ ስለሆነ አስገድዶ አያጸድቀንም። ሰው ነጻ ፈቃዱን ተጠቅሞ ከበደለ በራሱ ጥፋት ይወድቃል።

▶️፲፬. ምሳ.23፥16 ላይ "ከንፈሮችህም በቅን ቢናገሩ ኵላሊቶቼ ደስ ይላቸዋል" ይላል። ኩላሊቶቼ ያላቸው እነማን ናቸው?

✔️መልስ፦ በኵላሊት መላውን አካል መናገር ነው። ሰው አንደበቱ ቅን ነገርን ሲናገር ሕዋሳቶቹ ደስ ይላቸዋል ማለት ነው።

▶️፲፭. ምሳ.23፥34 ላይ "በባሕር ውስጥ እንደ ተኛ ትሆናለህ። በደቀልም ላይ እንደ ተኛ" ይላል። ደቀል ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ደቀል የሚባለው የመርከብ ጫፍ ማለት ነው። በዚያ የተኛ ሰው ማዕበል ሞገድ በተነሣ ጊዜ ፈጥኖ እንደሚወድቅ እንዲህ ትሆናለህ ማለት ትወድቃለህ ማለት ነው።

▶️፲፮. "ኃጥእም የጻድቅ ቤዛ ነው" ይላል (ምሳ.21፥18)። ትርጓሜ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ቤዛ ማለት ምትክ ማለት ነው። በዚህ አግባብ ኃጥእ የጻድቅ ቤዛ ነው ማለት በጻድቁ ምትክ መከራን የሚቀበል ነው ማለት ነው። በግ የይስሐቅ ቤዛ ሆነ ማለት በይስሐቅ ፈንታ ተሠዋ ማለት ነው። ስለዚህ ጻድቃን ከመከራ ሲድኑ በኃጥኣን መከራ እንደሚመጣ ለማመልከት የተነገረ ነው።


“ትምህርተ እግዚአብሔር ዘኦርቶዶክስ”

በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓተ ጽሕፈት ውስጥ ዶግማ ነክ መጻሕፍትን ማዘጋጀት ከባዱ ነገር ሆኖ አግኝቼዋለሁ። ለሚዘጋጁ መጻሕፍት እውነትም፣ እምነትም እንዳይጎድላቸው የሚራዱ ጥንተ ቀራቦች ሲኖሩ ደግሞ ዐቅም ይወለዳል።

“ትምህርተ እግዚአብሔር” ዘመኑን ተንተርሰው ልደታቸውን ላገኙ፣ ያልበረታ አድካሚ ሆነው ለተገለጡ ጥያቄዎች መልስ ከሰጠሁ ብየ በማሰብ ጥቂት የደከምኩበት ዝግጅት ነው።

ባለንበት ዘመን እግዚአብሔር በብዙዎች ዘንድ የጥያቄ ማእከል ሆኗል። የሚሉ እና ሌሎች ጥያቄዎች ይነሡበታል።

በዚህ መጽሐፍ ከላይ ያነሣኋቸውን ጥያቄዎች ከእኔ የተሻሉ በቃለ እግዚአብሔር የበረቱ ሊቃውንት አስፍተውና አጉልተው መልስ እስኪሰጡባቸው ድረስ እንደመቆያ ይሆን ዘንድ ነው ዝግጅቱ። ወዲህም ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን ስለ እግዚአብሔር አምላክነት የተቀበለችውን እውነት ለማስረዳት ሞክሪያለሁ።

በዚህ መጽሐፍ ዝግጅት ብዙዎች እንደ ግድግዳና ተረዳ ሆነውኝ ለሕትመት በቅቷል። ቀሪው ጊዜ መጻሕፍትን በማንበብ አእምሯቸውን ለሚያሰፉ አንባብያን ነው። ሐሙስ የካቲት 27 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በኢትዮፋጎስ መጻሕፍት ማከፋፈያ በኩል ለመጽሐፍ መደብሮች ይደርሳል።


🌻 መጽሐፈ ተግሣጽ 🌻

🌻ምዕራፍ ፩፡-
-የእግዚአብሔር ክብር ነገርን እንደሚሰውር
-በእግዚአብሔር ፊት መመጻደቅ እንደማይገባ
-ጸጋና ወንድማማችነት ነጻ እንደሚያደርግ
-የብልህ ነገር በሚሰማ ሰው ጆሮ ያማረ እንደሆነ
-የሕይወት ውበት በትዕግሥት እንደምትነግሥ
-እንዳይጠላንና እንዳይሰለቸን እግራችንን ወደባልንጀራችን ቤት አለማዘውተር እንደሚገባ
-የክፉ መንገድና የኀጢአተኛ እግር በክፉ ቀን እንደሚጠፉ
-ጠላታችን ቢራብ ማብላት ቢጠማ ማጠጣት እንደሚገባና ይህንን ያደረግን እንደሆነ እግዚአብሔር መልካም ዋጋን እንደሚመልስልን
-የራስን ክብር መፈለግ እንደማያስከብር

🌻ምዕራፍ ፪፡-
-ከንቱ ርግማን በማንም ላይ እንደማይደርስ
-ኃጢአትን የምታመጣ ኀፍረት እንዳለች ክብርንና ጸጋን የሚያመጣ ኀፍረትም እንዳለ
-በእንጨት መታጣት እሳት እንደሚጠፋ በእንጨት ብዛትም እሳት እንደሚነድ
-ቁጡ በሌለበት ጸብ ጸጥ እንደሚል
-ጠላትነቱን የሚሸሽግ ተንኮልን እንደሚሰበስብ
-ጉድጓድን ለባልንጀራው የሚምስ ራሱ ይወድቅበታል
-ሐሰተኛ ምላስ እውነትን እንደምትጠላ ዝም የማይል አፍ ክርክርን እንደሚያመጣ

🌻ምዕራፍ ፫፡-
-ለቁጡና ቁጣን ለሚያፋጥን ምሕረት እንደሌለው
-ከጠላት መልካም አሳሳም የወዳጅ ንክሻ እንደሚሻል
-የቀረበ ወዳጅ ከራቀ ወንድም እንደሚሻል
-የሽሙጥን ቃል ማራቅ እንደሚገባ
-ብረት ብረትን እንደሚስለው ሰውም ባልንጀራውን እንደሚስል
-በዐይኑ የሚገላምጥ በእግዚአብሔር ዘንድ ርኩስ እንደሆነ

🌻ምዕራፍ ፬፡-
-ኃጥእ ማንም ሳያሳድደው እንደሚሸሽ
-ጻድቅ ግን እንደ አንበሳ ተማምኖ እንደሚኖር
-በክፉዎች በደል መቅሠፍት እንደሚነሣ
-ከሐሰተኛ ባለጠጋ በእውነት የሚሄድ ድሃ እንደሚሻል
-በጻድቃን ረድኤት ብዙ ክብር እንዳለ
-ግፍን የሚጠላ ብዙ ዘመን እንደሚኖር

🌻ምዕራፍ ፭፡-
-በጻድቃን መመስገን ሕዝቦች ደስ እንደሚላቸው
-ጥበብን በሚወድ ልጅ አባቱ ደስ እንደሚለው
-እውነተኛ ንጉሥ ሀገሩን እንደሚያጸና ዐመፀኛ ሰው ግን እንደሚያፈርስ
-ጻድቅ በደስታና በሐሴት እንደሚኖር
-ጠቢባን ቁጣን እንደሚመልሱ
-ለድሆች በእውነት የሚፈርድ ንጉሥ ዙፋኑ ለዘለዓለም እንደሚጸና
-ትዕቢት ሰውን እንደሚያዋርደው

🌻ምዕራፍ ፮፡-
-ልባም ሴት ዋጋው ብዙ ከሆነ ከከበረ ዕንቊ እጅግ የከበረች እንደሆነች
-ልባም ሴት እድሜዋን ሁሉ በበጎ ላይ በጎ እየሠራች ባሏን እንደምትረዳው
-ብልህ ሴት እንደምትባረክ

🌻የዕለቱ ጥያቄዎች🌻
፩. ከሚከተሉት ውስጥ ትክክል ያልሆነው የቱ ነው?
ሀ. ሐሰተኛ ምላስ እውነትን ትጠላለች
ለ. የሕይወት ውበት በትዕግሥት ትነግሣለች
ሐ. ጠላታችን ቢራብ አለማብላት ቢጠማ አለማጠጣት ይገባል
መ. ሀ እና ለ
፪. ከሚከተሉት ውስጥ ስለጻድቅ ሰው ትክክል የሆነው የቱ ነው?
ሀ. ጻድቅ እንደ አንበሳ ተማምኖ ይኖራል
ለ. ጻድቅ ሰው በእግዚአብሔር ሕግ አይመራም
ሐ. ጻድቅ ሰው ጥልን ይወዳል
መ. ለ እና ሐ
፫. ስለ ልባም ሴት ትክክል ያልሆነው የቱ ነው?
ሀ. ልባም ሴት ከከበረ ዕንቊ ይልቅ የከበረች ናት
ለ. በበጎ ላይ በጎ እየሠራች ባሏን ትረዳዋለች
ሐ. ደግ ሴት ለቤተሰቦቿ ምግባቸውን አትሰጣቸውን
መ. ሀ እና ለ

https://youtu.be/A9YmiVFJEkc?si=rjjFObMgQIsv230u




PDF በኋላ በዚሁ የቴሌግራም ቻናል ይለቀቃል


6ቀን ብቻ ቀረው! ቀጠሮ ይዘዋል?
"ወደ ቀደመው ነገር እንመለስ"
ልዩ የአባላት የቃል ኪዳን ማደሻ መርሐ ግብር
በጎንደር ከተማ እና አካባቢዋ ለሚገኙ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት በሙሉ የተዘጋጀ ልዩ የአገልግሎት ቃል ኪዳን ማደሻ መርሐ ግብር
በዕለቱም፦
1. የአባላት ተቋማዊ ለውጥ ትግበራ በተመለከተ ይቀርባል
2. በተቋማዊ ለውጡ ለአባላት የተዘጋጁ የአገልግሎት አማራጮች ጥናት ይቀርባል
3. አባላት የአገልግሎት ቃል ኪዳናቸውን ያድሳ
4. ስብከተ ወንጌል እና ያሬዳዊ መዝሙር
እንዲሁም ሌሎች ከአባላት ጋር የተያያዙ መርሐ ግብራት ይከናወናሉ።
እርስዎም በማኅበሩ ምሥረታ ጀምሮ በየትኛውም ወቅት በአባልነት ሲሳተፉ ከነበሩ በዚህ መርሐ ግብር ላይ እንዲሳተፉ ተጋብዘዋል።
መረጃውን ለሌሎች አባላት በማጋራት የአገልግሎት ግዴታዎን ይወጡ!
ቀን፦ የካቲት 30/2017 ዓ.ም
ሰዓት፦ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ
ቦታ፦ጎንደር ማእከል - ማራኪ ጎንደር ዩኒቨርስቲ ዝቅ ብሎ
የመግቢያ ዋጋ፡- ሌሎችን አባላትን ይዞ መምጣት!
ለተጨማሪ መረጃ፡- 0908080202/ 0925505454
ወደ ቀደመው ነገር እንመለስ"
አዘጋጅ፡- የጎንደር ማእከል፣ የጎንደር እና የአዘዞ ወረዳ ማእከላት


❤ መጽሐፈ ምሳሌ ክፍል 5 ❤

❤ምዕራፍ ፳፩፡-
-ሰው ሁሉ ለራሱ ጻድቅ መስሎ እንደሚታይ
-ክፉ ሰው ሲዋረድ የዋህ ሰው አዋቂ እንደሚሆን
-ከነዝናዛና ከነገረኛ ሴት ጋር ከመቀመጥ በምድረ በዳ መቀመጥ እንደሚሻል
-አፉንና ምላሱን የሚጠብቅ ነፍሱን ከመከራ እንደሚጠብቅ
-የኃጥኣን መሥዋዕት በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊ እንደሆነ
-ረድኤት ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደሆነ

❤ምዕራፍ ፳፪፡-
-ከብዙ ባለጠግነት መልካም ስም እንደሚሻል
-ሐሰትን የሚዘራ መከራን እንደሚያጭድ
-እግዚአብሔር ደስ ብሎ የሚሰጥ ሰውን እንደሚወድ
-እግዚአብሔር የልብን የዋሃት እንደሚወድ
-ከቁጡ ሰው ጋር ባልንጀራ መሆን እንደማይገባ

❤ምዕራፍ ፳፫፡-
-ድሃ ስትሆን ከባለጠጋ ጋር መወዳደር እንደማይገባ
-ከስስታም ሰው ጋር መመገብ እንደማይገባ
-የነገርህን ጥበብ እንዳይንቅብህ በሰነፍ ጆሮ አንዳች ነገር መናገር እንደማይገባ
-አባቶች ያኖሩትን የድንበር ምልክት ማፍለስ እንደማይገባ
-ሕፃናትን ከመቅጣት ቸል ማለት እንደማይገባ
-ሰካራምና አመንዝራ እንደሚደኸይ
-የወለደንን አባት መስማት እንደሚገባና እናትም ባረጀች ጊዜ መናቅ እንደማይገባ
-ጻድቅ አባት በመልካም እንደሚያሳድግ

❤ምዕራፍ ፳፬፡-
-በክፉ ሰዎች መቅናት እንደማይገባና ከእነርሱ ጋር መኖርን አለመውደድ እንደሚገባ
-ከታላቅ ርስት ይልቅ ዕውቀት ያለው ሰው እንደሚበልጥ
-ብልሆች ከእግዚአብሔር ቃል እንደማይርቁ
-እግዚአብሔር የሁሉን ልብ እንደሚያውቅ
-ጻድቅ ሰባት ጊዜ ቢወድቅ ሰባት ጊዜ እንደሚነሣ
-ጠላትህ ቢወድቅ ደስ አይበልህ እንደተባለ
-እግዚአብሔርንና ንጉሥን መፍራት እንደሚገባ
-ክፉ ልጅ አባቱን እንደሚረግምና እናቱንም እንደማያመሰግን
-ነገርን መጎተት ጭቅጭቅንና ቅጣትን እንደሚያመጣ
-አፍን በእግዚአብሔር ቃል መክፈት እንደሚገባ

❤ የዕለቱ ጥያቄ ❤
፩. ከሚከተሉት ውስጥ ትክክል የሆነው የቱ ነው?
ሀ. የኃጥኣን መሥዋዕት በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊ ነው
ለ. ረድኤት ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው
ሐ. እግዚአብሔር የልብን የዋሃት ይወድዳል
መ. ሁሉም

https://youtu.be/7dzjOX24AZ4?si=V9XD7Q0jUAE9c_eU


✔️መልስ፦ በጥልቀት ተቆፍሮ የወጣ ጉድጓድ በበጋም በክረምትም ከውሃ እንደማይደርቅ ሁሉ ጥልቅ ጥበብም በብልህ ሰው ልቡና ይኖራል ማለት ነው። ፈሳሽ ወንዝ ሲፈስስ ደስ እንደሚያሰኝ ጥበብም ከጥበበኛ አፍ ስትነገር ደስ ታሰኛለች ማለት ነው።

▶️፲፮. "የሰው ሆድ ከአፉ ፍሬ ይሞላል። ከንፈሩም ከሚያፈራው ይጠግባል" ይላል (ምሳ.18፥20)። የሰው ሆድ ከአፉ ፍሬ ይሞላል ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ በሆድ ሁሉንም ሕዋሳት መናገሩ ነው እንጂ ሰው ከአፉ ፍሬ ማለት በአፉ ጸልዮ ከሚያገኘው ጸጋ፣ በከንፈሩም በጸለየው ጸሎት ሁለንተና ሰውነቱ ጸጋን፣ ክብርን ያገኛል ማለት ነው።

▶️፲፯. "የሚገዛ ሰው ክፉ ነው ክፉ ነው ይላል። በኼደ ጊዜ ግን ይመካል" ይላል (ምሳ.20፥14)። ለማለት የተፈለገው ሀሳብ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ እህልን ወይም ሌላ ነገርን የሚገዛ ሰው ዋጋው እንዲረክስለት ነገሩን ያክፋፋዋል ማለት ነው። ከገዛው በኋላ ግን ጥሩ ነገር ገዛሁ እያለ ለሁሉ ያወራል ማለት ነው። የሚገዛ የሚለው እህልን የሚገዛ ለማለት ነው እንጂ ሰውን የሚያስተዳድር ለማለት አይደለም። እንግሊዘኛው ለይቶታል Buyer ይለዋል። ለሰው ቢሆን Governor ይል ነበርና። ሙሉው “It is not good, it is not good” says the buyer; then off he goes and boasts about his purchase ይላል።

▶️፲፰. "ዐሳብ በምክር ትጸናለች። በመልካምም ምክር ሰልፍ አድርግ" ይላል (ምሳ.20፥18)። በመልካምም ምክር ሰልፍ አድርግ ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ በመልካም ምክር ሰልፍ አድርግ ማለት ንጉሥ በጠላቶቹ ላይ ጦርነትን ሲያውጅ በተጠና ምክር ሊሆን ይገባል ማለት ነው። አጋንንትን ስንገጥምም በጥሩ ምክር ሆነን በፈሊጥ በጥበብ መዋጋት እንደሚገባን የሚያመለክት ቃል ነው።

▶️፲፱. "ዘዋሪ ሐሜተኛ ምሥጢርን ይገልጣል። ከንፈሩን የሚያሞጠሙጥ ሰውን አትገናኘው" ይላል (ምሳ.20፥19)። ዘዋሪ የተባለው ወዴት የሚዞር ነው?

✔️መልስ፦ ዘዋሪ ሐሜተኛ ማለት በየመንደሩ እየዞረ (እያውደለደለ) ሰውን የሚያማ ማለት ነው። እገሌማ እንዲህ አደረገ፣ እገሌማ እንዲህ ነው እያለ ምሥጢር የሚያወጣ ማለት ነው።

▶️፳. "ጠቢብ ንጉሥ ኃጥኣንን በመንሽ ይበትናቸዋል። መንኰራኵሩንም በእነርሱ ላይ ያንኰራኵርባቸዋል" ይላል (ምሳ.20፥26)። ለማለት የተፈለገው ሀሳብ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ መንሽ ገለባውን ከፍሬው እንደሚለይ ሁሉ ጠቢብ ንጉሥም ወንጀለኛውን ሰውና ንጹሕ ሰውን በፍርዱ ይለያቸዋል ማለት ነው። መንኰራኵር ማለት እንደመኪና የሚገለባበጥ ነገር ነው። ወንጀለኞችን በዚህ ይቀጣቸዋል ማለት ነው።

▶️፳፩. ምሳ.16፥4 ላይ "በዐመፃ እጅን በእጅ የሚመታ አይነጻም" ይላል። ንባቡን ቢያስረዱን።

✔️መልስ፦ እጅን በእጅ መምታት የመሐላ ምልክት (ትእምርተ መሐላ) ነው። ስለዚህ ሰዎች ሌላውን ለመጉዳት በዐመፅ መማማል አያነፃም ማለት በደለኛ ተብሎ በእግዚአብሔር ይፈረድበታል ማለት ነው።

▶️፳፪. "ኀጥእ ለክፉ ቀን ይጠበቃል" ይላል (ምሳ.16፥9)። ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ኃጥእ ለክፉ ቀን ይጠበቃል ማለት ኃጥእ ሰውን ክፉ ቀን ያገኘዋል ማለት መከራ ይገጥመዋል ማለት ነው። መከራ ሥጋ መከራ ነፍስ ይገጥመዋል ማለት ነው።

▶️፳፫. ምሳ.20፥16 ላይ "ለማያውቀው ከተዋሰ ሰው ልብሱን ውሰድ። ለእንግዳ የተዋሰውንም እርሱን አግተው" የሚለው ሀሳቡ ምን እንደሆነ አልገባኝም።

✔️መልስ፦ አንድ ሰው ለማያውቀው ሰው ዋስ ሆኖ ሳለ የተዋሰው ሰው መልሶ ወንጀል ሠርቶ ቢጠፋ የተዋሰው ሰው መክፈል ይገባዋልና ይህን ለመግለጽ ልብሱን ውሰድ ይላል። ለእንግዳ የተዋሰውንም እርሱን አግተው ማለት እንግዳው ቢጠፋ እንግዳው ሊከፍለው የሚገባውን ነገር ዋሱ ይክፈል ማለት ነው።

▶️፳፬. ምሳ.17፥9 ሌሎች የሠሩትን በደል የሚሰውር እንጅ የራሱን በደል የሚሰውር (ንስሓ የማይገባ) እንዴት ነው እርቅን የሚሻ?

✔️መልስ፦ እውነት ነው የራሱን በደል ከንስሓ አባቱ የሚሰውር ሰው በደል ይሆንበታል። ነገር ግን ከዚህ የተጠቀሰው ሌላ ሰው በድሎት እያለ ለዕርቅ ብሎ በደሉን ትቶ ተበድሎ ሳለ አልተበደልኩም የሚል ዕርቅን ይወዳል ለማለት ነው።

▶️፳፭. ምሳ.16፥10 ሰው የሆነ ንጉሥ እንዴት የማይሳሳት (infallible) ይሆናል? የቱንም ያህል ጥበብ ቢኖረው በፍርድ አይሳሳትምን? his mouth does not err in judgment ይላልና።

✔️መልስ፦ ሥጋዊ ንጉሥ ፍጹም ስላልሆነ ሊሳሳት ይችላል። ፍርዱም ፍጹም እውነት ነው የሚባል አይደለም። ይህ የሚነገር ለእግዚአብሔር ብቻ ነው። በተቻለ አቅም ግን ተቀብቶ የሚነግሥ ንጉሥ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ስለሚያድርበት ከሌላው በተሻለ ጥሩ ፍርድ ይፈርዳል ማለት ነው። his mouth does not err in judgment ማለቱም በፍጹም ሳይሆን በአንጻራዊ ነው።

▶️፳፮. ምሳ.18፥22 ላይ "ሚስትን ያገኘ በረከትን አገኘ" ይላል። ይህ እንዴት ይታያል? የሁሉ ሚስት አንድ ይሆናል እንዴ?

✔️መልስ፦ ሚስት ያገባ ሁሉ በረከትን አገኘ አይባልም። ደግ ሴትን ያገኘ ሰው በረከትን ያገኛል ማለት ነው። ግእዙ የተሻለ ገልጾታል። "ዘረከበ ብእሲተ ኄርተ ረከበ ሞገሰ" ይላል።

▶️፳፯. ምሳ.18፥14 ላይ "የሰው ነፍስ ሕመሙን ይታገሣል። የተቀጠቀጠን መንፈስ ግን ማን ያጠነክረዋል" ይላል። የተቀጠቀጠ ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ የተቀጠቀጠ ነገር ደካማ እንደሚሆን ሁሉ ደካማ ልብ ያለው ሰው ለማለት ነው። መንፈስ ያለው ከዚህ ልብን ነው። የተቀጠቀጠ መንፈስ ያለው ሰው ማለት ልበ ደካማ፣ አእምሮ ደካማ ሰው ማለት ነው።

▶️፳፰. ምሳ.20፥30 ላይ "የሰንበር ቁስል ክፉዎችን ያነጻል" ይላል። የሰንበር ቁስል ማለት ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ክፉዎችን ያነጻል ማለት ይጥላል ማለት ነው። ያነጻል ከዚህ ይጥላል ተብሎ ይተረጎማል። የሰንበር ቁስል ማለት የሆድ ቁስል፣ የጨጓራ ቁስል ማለት ነው። ይህ ከባድ በሽታ ስለሆነ ይጥላል ማለት ነው።

▶️፳፱. መዝ.17፥12 ላይ "ሰነፍን በስንፍናው ከመገናኘት ልጆቿ የተነጠቁባትን ድብ መገናኘት ይሻላል" ይላል። ልጆቿ የተነጠቁባት ድብ እንዴት ያለች ናት?

✔️መልስ፦ ልጆቿ የተነጠቁባት ድብ በጣም ቁጡ ስለሆነች ትገድላለች። ነገር ግን ሰነፍ ሰውን በስንፍናው ከማግኘት እርሷን መገናኘት ይሻላል አለ። ቁጡ ድብ ብትጎዳን ሥጋችንን ነው። ሰነፍ ሰው ግን ሥጋንም ነፍስንም ይጎዳልና ይህን ለመግለጽ ነው።


© በትረ ማርያም አበባው


✝️የዩቲዩብ ቻናሌ:- ንሕነ ዘክርስቶስ https://youtube.com/@edenawizechristos?si=6V4y-73OM3LTzhAf ነው።

🌻የፌስቡክ ገጼ Betremariam Abebaw https://www.facebook.com/profile.php?id=100075547015721 ነው።


💙 የጥያቄዎች መልስ ክፍል 151 💙

▶️፩. ምሳ.፲፮፥፫ ላይ "ኃጥኣን ግን በክፉ ቀን ይጠፋሉ" ይላል። ክፉ ቀን የተባለችው ማን ናት? የቀንስ ክፉ አለወይ?

✔️መልስ፦ ሁሉም ቀኖች በራሳቸው መልካሞች ናቸው። ነገር ግን ሰው የተጎዳበትን ቀን ክፉ ቀን ማለቱ የተለመደ ስለሆነ በዚህ አግባብ የተነገረ ነው። ለምሳሌ የምጽአት ቀን ለጻድቃን የደስታ ቀን ስትሆን ለኃጥኣን ክፉ ቀን ናት። ቀኒቱ በራሷ ክፉ ሆና አይደለም። ዘለዓለማዊ የገሀነም ኑሮ የሚፈረድባቸው ስለሆነ ክፉ ተባለች እንጂ።

▶️፪. "እግዚአብሔር ሁሉን ለእርሱ ለራሱ ፈጠረ። ኃጥእን ደግሞ ለክፉ ቀን" ይላል (ምሳ.16፥4)። ይህ ቅድመ ውሳኔ (predestination) አይሆንም?

✔️መልስ፦ አይሆንም። እግዚአብሔር እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚሆነውን ነገር ዓለምን ከመፍጠሩ በፊት ጀምሮ ያውቃል። ስለዚህ ኃጥኣን ክፉ ነገር እንደሚደርስባቸው አውቆ ተናገረ እንጂ ክፉ ነገርን እንዲያደርጉ አላደረገም። ክፉ ነገር የደረሰባቸው በተሰጣቸው ነጻ ፈቃድ መርጠው እንጂ ተገደው አይደለምና።

▶️፫. "ከዐስበ ደነስ ጋር የሚቀርብ ስእለትም ንጹሕ አይደለም" ይላል። ዐስበ ደነስ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ዐስበ ደነስ ማለት የኃጢአት ደመወዝ ማለት ነው። ይኸውም ዝሙት ሠርተው፣ ሰርቀው፣ በጠቅላላው ኃጢአት ሠርተው የሚያገኙት ገንዘብ ነው። ስለዚህ ኃጢአት ሠርተው የሚያገኙትን ገንዘብ ለስእለት መስጠት አይገባም ማለት ነው።

▶️፬. "ብርና ወርቅ በከውር እንዲፈተን የተመረጡ ሰዎች ልብም በእግዚአብሔር ዘንድ እንዲሁ ነው" ይላል (ምሳ.17፥3)። በከውር ማለት ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ከውር ማለት ማቅለጫ ማለት ነው። ይኸውም ብረትን፣ ብርትን፣ ብርን፣ ወርቅን የሚያቀልጥ ነው።

▶️፭. ምሳ.፲፱፥፲፰ ላይ "ለተስፋ ይኾንኽ ዘንድ ልጅኽን ግረፍ። ለመሳደብ ግን እጅኽን አታንሣ" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ ልጅን ሲያጠፋ መቅጣት መግረፍ ይገባል። ነገር ግን ስንገርፈው እንዳይሞትብን ፊታችንን አማትበን፣ በጉልበታችን ፈትነን ሊሆን ይገባል። ለመሳደብ እጅህን አታንሣ ማለት አካሉን አጉድለህ ዕ*ውር፣ አንካ*ሳ ወዘተ ተብሎ ይሰደብ ዘንድ በኃይል አትምታው ማለት ነው።

▶️፮. ምሳ.፲፮፥፲፩ ላይ "የእግዚአብሔር ፍርድ እንሚዛን ውልብልቢት ነው። ሥራውም የከረጢት ድንጋይ ነው" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ የሚዛን ውልብልቢት የምትባለው የእህል ሚዛን ላይ የእህሉን ክብደት ለመለየት መካከል ላይ ወደ ግራና ወደቀኝ የምታዘነብል ናት። ሚዛኑ ግራ ቀኝ እኩል ሆኖ እርሷ ካረፈችበት ላይ ያለው ቁጥር የነገሩን ክብደት በኪሎ ግራም ያሳውቀናል። ሥራውም የከረጢት ድንጋይ ነው ማለት ደግሞ አንድን ነገር መዝነው በከረጢት ያስቀምጡታል። ያ ለሌሎች ሚዛን ሆኖ ያገለግላል። ስለዚህ ሥራውም የከረጢት ድንጋይ ነው ማለት በዚያ እየተመዘነ ያልፋል ማለት ነው። ፍሬ ነገሩ ሰው በእግዚአብሔር ፍርድ እየተመረመረ ዋጋውን ያገኛል ማለት ነው።

▶️፯. ምሳ.፲፮፥፲፭ ላይ "የንጉሥ ልጅ እንደ ሕይወት ብርሃን ነው። ለማያስደስቱትም የማታ ደመና ነው" ሲል የማታ ደመና ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ የሕይወት ብርሃን ደስ እንደሚያሰኝ ሁሉ የንጉሥ ልጅም ለሚቀርቡትና ለሚወዱት ሰዎች ደስ ያሰኛል። አንድም የሚቀርቡትንና የሚያስደስቱትን ደስ ያሰኛል ማለት ነው። ለማያስደስቱት የማታ ደመና ነው ማለት በጨለማ ላይ ደመና ሲታከል የበለጠ እንደሚጨልም የንጉሥ ልጅም በማያስደስቱት ሰዎች ላይ መከራን ያመጣል ማለት ነው።

▶️፰. ምሳ.፲፯፥፭ ላይ "ለሚያምን በዓለም ያለው ገንዘቡ ነው። ለማያምን ግን መሐለቅ የለውም" ሲል መሐለቅ ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ መሐለቅ ከመዓድናት የሚሠራ እንደ ብር እንደ ሳንቲም ያለ የገንዘብ ዓይነት ነው።

▶️፱. "የልብ መዘጋጀት ከሰው ነው። የምላስ መልስ ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው" ይላል (ምሳ.16፥1)። የምላስ መልስ ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሰው በልቡ ይዘጋጃል። የምላስ መልስ ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው መባሉ ነገሩ በሌሎች ዘንድ ተወዳጅ እንዲሆንና ሞገስ እንዲኖረው የሚያደርግለት ግን እግዚአብሔር ነው ማለት ነው። በሞሥጢር ጌታ ሐዋርያትን ስለምትናገሩት አትጨነቁ ካላቸው ጋር ይመሳሰላል።

▶️፲. "የእግዚአብሔር ብይን በንጉሥ አፍ ነው። አፉም በፍርድ አይስትም። እውነተኛ ሚዛንና መመዘኛ የእግዚአብሔር ናቸው" ይላል (ምሳ.16፥10-11)። በንጉሥ አፍ ነው ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ የእግዚአብሔር ፍርድ በንጉሥ አፍ ነው ማለት እግዚአብሔር በባሕርይው የሚገዛውንና የሚፈርደውን ፍርድ ምድራዊ ንጉሥ ደግሞ በጸጋ የሚገዛና የሚፈርድ ነው ማለት ነው።

▶️፲፩. "የንጉሥ ቍጣ እንደ ሞት መልእክተኛ ነው። ጠቢብ ሰው ግን ያቈላምጠዋል" ይላል (ምሳ.16፥14)። ንጉሥን ከሌላው ሰው ለይቶ ማቆላመጥ ተገቢ ነው?

✔️መልስ፦ ንጉሥ ሀገርን ያስተዳድር ዘንድ በእግዚአብሔር ፈቃድ የነገሠ ስለሆነ ከሌላው ሰው በተለየ እንደ ንጉሥነቱ ንጉሥን ማክበር ተገቢ ነው። ማቆላመጥ ትእምርተ ፍቅር (የመውደድ የማክበር ምልክት) ነው። ጠቢብ ሰው ንጉሥን ያቆላምጠዋል ማለት የሚገባውን ክብር ይሰጠዋል ማለት ነው።

▶️፲፪. "ዐይኑን የሚዘጋ ጠማማ ዐሳብን ያስባል። ከንፈሩን የሚነክስ ክፋትን ይፈጽማል። የሸበተ ጠጕር የክብር ዘውድ ነው። እርሱም በጽድቅ መንገድ ይገኛል" ይላል (ምሳ.16፥30-31)። ዐይኑን የሚዘጋ ጠማማ ዐሳብን ያስባል ሲል ለማለት የተፈለገው ምንድን ነው? የሸበተ ጠጕር የሚገኘው በጽድቅ መንገድ ነው?

✔️መልስ፦ ዐይኑን የሚዘጋ ማለት በክፉ አተያይ በዐይኖቹ የሚያይ ሰው ጠማማ ሐሳብን ያስባል ማለት ነው። የጠማማ አተያይ ምንጩ ጠማማ ሐሳብ መሆኑን ለመግለጽ ነው። የሽማግሌ ክብሩ የሸበተ ጸጉሩ ነው። በበጎ መንገድ የሄዱ ሰዎች ሽበት የተከበረ ነው ለማለት ነው። በበጎዎቹ ተናግሮ ነው እንጂ ክፉ ሰዎችም ሊሸብቱ ይችላሉ። ስለዚህ መሸበት ብቻውን የጽድቅ መንገድ አይደለም። የሸበተ ጸጉር ሁሉ በጽድቅ መንገድ የተገኘ አይደለም።

▶️፲፫. "በሰነፍ እጅ የጥበብ መግዣ ገንዘብ መኖሩ ስለ ምንድን ነው? ጥበብን ይገዛ ዘንድ አእምሮ የለውምና" ይላል (ምሳ.17፥16)። የጥበብ መግዣ ገንዘብ መኖሩ ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ጥበብ በዕውቀት እና በመልካም ሥራ ይገኛል እንጂ ሰነፍ ሰው ጥበብን በገንዘብ መግዛት አይችልም ማለት ነው። በሌላ መንገድ ሰነፍ ሰው ገንዘብ ቢኖረውም እንኳ ከገንዘቡ መጽውቶ ጥበብን ማግኘት እየቻለ የጥበብ መግዣ (ማግኛ) ገንዘብ እያለው ባለመመጽወቱ ጥበብን አያገኝም ማለት ነው።

▶️፲፬. "መለየት የሚወድ ምኞቱን ይከተላል። መልካሙንም ጥበብ ዅሉ ይቃወማል" ይላል (ምሳ.18፥1)። ከምን መለየት የሚወድ ነው?

✔️መልስ፦ ከወዳጆቹ መለየትን የሚወድ ጥበብን ይቃወማል ማለት ነው። ግእዙ በግልጽ አስቀምጦታል። "ምክንያተ የኀሥሥ ብእሲ ዘይፈቅድ ይትፈለጥ እምአዕርክቲሁ" ይላል።

▶️፲፭. "የሰው አፍ ቃል የጠለቀ ውሃ ነው። የጥበብም ምንጭ ፈሳሽ ወንዝ ነው" ይላል (ምሳ.18፥4)። የጠለቀ ውሃ ነው ሲባል ምን ማለት ነው? የጥበብም ምንጭ ፈሳሽ ወንዝ ነው ሲባልስ ምን ማለት ነው?




✔️መልስ፦ ጻድቅነት አንጻራዊ ነው። አንድ ጻድቅ ጥቂት በደል ካለችበት የዚያች በደል ፍዳ በዚህ ምድር ይከፈለዋል። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደተናገረው አልዓዛር ጻድቅ የነበረ ቢሆንም በነበረችበት ጥቂት በደል ምክንያት በምድር ድኻና በሽተኛ ሆኖ ኖረ። ነዌ ክፉ የነበረ ቢሆንም ጥቂት መልካምነት ስለነበረው በነበረችው ጥቂት መልካምነት በምድር ሀብታም እንዲሆን ሆኖ ተከፈለው ይላል። ጻድቅን መከራ አያገኘውም ማለት በሲኦል መከራ አያገኘውም ማለት ነው። እንጂ በምድርማ ብዙ ቅዱሳን መከራ እንደገጠማቸው አንብበናል ተምረናል።

▶️፴፩. “የጎመን ወጥ በፍቅር መብላት የሰባ ፍሪዳን ጥል ባለበት ዘንድ ከመብላት ይሻላል” ይላል (ምሳ.15፥17)። ትርጉሙ ቢብራራልኝ?
ቁጥር 27 ላይ “ትርፍ ለማግኘት የሚሳሳ ሰው የራሱን ቤት ያውካል" ሲልስ ነግዶ ከማትረፍ ጋር እንዴት ይታያል?

✔️መልስ፦ የሰባ ፍሪዳ ከጎመን ይልቅ የተወደደ ነው። ነገር ግን ተጣልተው የተወደደውን ፍሪዳ ከመብላት ይልቅ በፍቅር ሆነው የተናቀውን ጎመን መብላት ይበልጣል ማለት ነው። በጥላቻ ሆነን ከምናገኘው ብዙ በፍቅር ሆነን የምናገኘው ጥቂት ይሻላል ማለት ነው። ነግዶ በሚገባ ማትረፍ ኃጢአት አይሆንም ንግድ ለምእመናን የተፈቀደ ሥራ ነውና። ነገር ግን ትርፍ ለማግኘት ብሎ ሰው መሳሳት የለበትም። ከዚህም መንቀፍ የፈለገው መሳሳት መልካም እንዳይደለ ነው።


© በትረ ማርያም አበባው


✝️የዩቲዩብ ቻናሌ:- ንሕነ ዘክርስቶስ https://youtube.com/@edenawizechristos?si=6V4y-73OM3LTzhAf ነው።

🌻የፌስቡክ ገጼ Betremariam Abebaw https://www.facebook.com/profile.php?id=100075547015721 ነው።


▶️፲፯. "የወርቅ ቀለበት በዕሪያ አፍንጫ እንደ ሆነ ከጥበብ የተለየች ቈንዦ ሴትም እንዲሁ ናት" ይላል (ምሳ.11፥22)። ምሥጢሩ ምንድን ነው? በዕሪያ አፍንጫ የወርቅ ቀለበት እንዴት ሊገኝ ይችላል?

✔️መልስ፦ ምሥጢሩ ከጥበብ የተለየች፣ ጥበብ የሌላት ሴት አትጠቅምም አንድም አትጠቀምም ማለት ነው። ሴት ከቁንጅናዋ በተጨማሪ ጥበብ ሊኖራት ይገባል ማለት ነው። ዓረፍተ ነገሩ በዕሪያ አፍንጫ ወርቅ ይገኛል አይልም። ቢሆን ተብሎ የተገለጸ ነው። ይህም ማለት የወርቅ ቀለበት በዕሪያ አፍንጫ እንደሆነ ማለት ወርቅ በዕሪያ አጠገብ ብናስቀምጥ የወርቁ ጥራት የዕሪያውን መልክ ያሳየዋል። በዚህ ጊዜ ዕሪያው ደንግጦ ወርቁን ይረግጠዋል። በአጭሩ ፍሬ ነገሩ ለዕሪያ ወርቅ እንደማይጠቅመው ሁሉ ለቆንጆ ሴትም ጥበብ ከሌላት ቁንጅናዋ አይጠቅማትም ማለት ነው።

▶️፲፰. "ያለውን የሚበትን ሰው አለ ይጨመርለታልም። ያለቅጥ የሚነፍግ ሰውም አለ ይደኸያልም" ይላል (ምሳ.11፥24)። ያለውን የሚበትን ሰው እንዴት ሊጨመርለት ይችላል? ቆጥቦ መጠቀም፣ ራስን ማስተዳደር ያስኮንናል እንዴት?

✔️መልስ፦ ያለውን የሚበትን ሰው የተባለ ካለው በተቻለው መጠን የሚመጸውት ሰው ለማለት ነው። ንፉግ ሰው ግን መመጽውት ሲገባው ባለመመጽወቱ ይደኸያል ማለት ነው። ራስን ማስተዳደር፣ የዓመት ልብስን የዕለት ጉርስን ቆጥቦ መጠቀምም አያስኮንንም። ከላይ የተነገረው እየተቻለው መመጽወት የማይችል ሰው በእግዚአብሔር እንደሚቀጣ ለማመልከት ነው።

▶️፲፱. "ለራሱ ባሪያ ሆኖ የተጠቃ ሰው እንጀራ ጎድሎት ራሱን ካከበረው ሰው ይሻላል" ይላል (ምሳ.12፥9)። ለራሱ ባሪያ ሆኖ ሲልና እንጀራ ጎድሎት ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ለራሱ ባሪያ ሆኖ የተጠቃ ሰው ማለት ምንም ስለሌለው ለሌሎች ባሪያ ሆኖ የሚያገለግል ሰው የአገልግሎቱን ዋጋ ስለሚያገኝ አይቸገርም ማለት ነው። እንጀራ ጎድሎት ራሱን ካከበረው የተባለው ደግሞ እኔ የመኳንንቱ፣ የነገሥታቱ፣ የታላላቆች ሰዎች ዘር ነኝ እያለ ኮርቶ የሚበላው እስከሚያጣ የሚደርስ ሰው ነው።

▶️፳. "ጻድቅ ሰውነቱ እስክትጠግብ ድረስ ይበላል የኃጥኣን ሆድ ግን ይራባል" ይላል (ምሳ.13፥25)። የጻድቅ ሰውነት እስክትጠግብ የሚበላው ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ከዚህ ጻድቅ የተባለ እያረሰ፣ እየቆፈረ፣ እየሠራ የሚኖር ሰው ነው። በደንብ የሠራ ሰው ምግቡን በደንብ ስለሚያገኝ እስኪጠግብ ይበላል ማለት ነው። በሌላ መልኩ ጻድቅ በእግዚአብሔር ጸጋ ደስ ብሎት ይኖራል ማለት ነው። የኃጥኣን ሆድ ግን ይራባል ያለው ኃጥኣን ያላቸው ከዚህ ሰነፎችን ነው። ሰነፎች ስለማይሠሩ ብዙ ንብረትና እህል አያገኙም በዚህ ምክንያት እስኪጠግቡ አይበሉም ማለት ነው። በሌላ መልኩ ኃጥኣን ሕገ እግዚአብሔርን ስለማይጠብቁ ከጸጋ እግዚአብሔር ተራቁተው ይኖራሉ ማለት ነው።

▶️፳፩. "ሁለት ምሥጢር ያለው የጉባኤ ምሥጢር ይገልጣል" ማለት ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሁለት ምሥጢር ያለው ማለት ለአንዱ ሌላ፣ ለሌላው ሌላ የሚናገር ሰው የጉባኤውን ምሥጢር አሳልፎ ለሌሎች ያወጣል ማለት ነው። አለመታመኑን ለመግለጽ ነው። ታማኝ ሰው ለማኅበሩ ምሥጢር ብቻ ይገዛል እንጂ ለሌላው ስለማይገዛ ሁለት ምሥጢር አይኖረውም። ከሓዲ ሰው ግን ታማኝነት ስለሌለው የሌላውን ምሥጢር ለሌላው በመናገሩ ከዚህ ሁለት ምሥጢር ያለው ተብሏል።

▶️፳፪. "ስንዴውን የሚያደልብ ለአሕዛብ ይተወዋል" ማለት ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ስንዴውን የሚያደልብ ማለት መመጽወት ሲገባው ምጽዋቱን ትቶ የሚያከማች ሰው ለአሕዛብ ይተወዋል ማለት እርሱ ሞቶ ሌሎች ይወርሱታል ማለት ነው። እንዲሁም የማይመጸውትን ሰው አጋንንት ይወርሱታል ማለት ነው።

▶️፳፫. "ክፉዎች በደጎች ፊት ይሰናከላሉ። ኃጥኣን በጻድቃን በር ያገለግላሉ" ሲል ምን ለማለት ነው? (ምሳ.14፥19)።

✔️መልስ፦ ክፉዎች በደጎች ፊት ይሰናከላሉ ማለት በደጋጎች ሰዎች ፊት ኃጢአትን በደልን ይሠራሉ ማለት ነው። ሰብአ ትካት በኖኅ ፊት ኃጢአት እንደሠሩና በኋላ ግን በማየ አይኅ እንደጠፉ ማለት ነው። ኃጥኣን በጻድቃን በር ያገለግላሉ ማለት በጻድቃን ሰዎች ይገዛሉ ማለት ነው።

▶️፳፬. ምሳ.፲፬፥፲፫ ላይ "ከደስታ ጋር ኀዘን አይቀላቀልም። የደስታ ፍጻሜ ግን ወደ ኀዘን ይመለሳል" ሲል ምሥጢሩ ቢብራራ።

✔️መልስ፦ ደስታና ኀዘን ሁለት ተቃራኒ ነገሮች ስለሆኑ አይቀላቀሉም ማለት ነው። የደስታ ፍጻሜ ወደ ኀዘን ይመለሳል የሚለው የዚህችን ዓለም ደስታ ነው። የሥጋዊ ተድላ ደስታ ፍጻሜው ኀዘን ነው ማለት ሑሩ እምኔየ (ከእኔ ሂዱ) ተብሎ ዘለዓለማዊ ኀዘን ወዳለበት ወደ ገሀነም መግባት ነው ማለት ነው።

▶️፳፭. "ልበ ጠማማዎች በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊዎች ናቸው። በመንገዳቸው ፍጹማን የሆኑ ግን የተወደዱ ናቸው" ይላል (ምሳ.11፥20)። እግዚአብሔር ልበ ጠማሞችን ለምን ይጠላል? ሰውስ ፍጹም መሆን ይቻለዋልን?

✔️መልስ፦ እግዚአብሔር በባሕርይው ፍቅር ነው። ስለዚህ እርሱ ፍጥረታትን ምንም ቢያደርጉ አይጠላቸውም። ነገር ግን ሰዎች ቢበድሉ በበደላቸው ምክንያት ፈርዶ ወደ ሲዖል ወደ ገሀነም የሚያስገባቸው በመሆኑ ፍርዱን በሰውኛ ከመጥላት ቆጥሮት ነው። ሰውን ፍጹም ባለመሆኑ እግዚአብሔር አይጠላውም። ሰው ወደ ፍጹምነት ለማደግ መልካም ሥራን አብዝቶ መሥራት ግን ይገባዋል።

▶️፳፮. ምሳ.12፥13 ላይ "ድንገት በበር የሚገናኝ" ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ ድንገት በበር የሚገናኝ ያለው በጠብ ወይም በጥል የሚገናኝ ለማለት ነው። በር መተላለፊያ ነው። ጠላት በመተላለፊያ ሲገናኝ ያስደነግጣልና ነው። ግእዙ የተሻለ ገልጾታል። "ወዘሰ ይዳደቅ በአናቅጽ ያመነድብ ነፍሳተ" ይላል። ግንኙነቱ በጥል (በድድቅ) ነው።

▶️፳፯. ምሳ.12፥25 ጻድቅ ሰው በሰማው ክፋት እንዴት ይደነግጣል? በእግዚአብሔር አይተማመንምን?

✔️መልስ፦ ሰው ምንም ያህል ጻድቅ ቢሆን ድንጋጤ ይስማማዋል። ከፍጥረታት ሁሉ በላይ የሆነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንኳ ሄሮድስ ሲያሳድዳትና ወታደሮች በመንገድ ሲያገኟት ትደነግጥ ነበርና። ይህ በእግዚአብሔር ከመተማመን ጋር አይገናኝም። አዳም ከወደቀ በኋላ የሰው ልጅ ድንጉጥ ሆኗልና።

▶️፳፰. ምሳ.14፥10 የአዋቂ ሰው ልብ ለሰውነቱ ደስታ እንጅ ኀዘን ነውን?

✔️መልስ፦ አዋቂ ሰው በዚህ ምድር ሳለ በአላዋቂዎች ንግግርና ድርጊት ማዘኑ አይቀርም። ይህን ለመግለጽ ነው። ሰው እያወቀ ሲመጣ በዚህች ምድር በሥጋው ኀዘንተኛ ነው የሚሆነው።

▶️፳፱. ምሳ.፲፩፥፲፰ ላይ "የኀጥእ ሰው ሙያ ሐሰተኛ ነው" ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ኃጢአተኛ ሰው የሚሠራው ሥራ (ሙያ) ሐሰተኛ ነው ማለት ክፉ ሥራን ይሠራል ማለት ነው። በክርስትና አንድ ነገር ሐሰት ነው የሚባለው ከእግዚአብሔር ሕግ በተቃራኒ ከተተገበረ ነውና።

▶️፴. ምሳ.፲፩፥፴፩ ላይ "እነሆ ጻድቅ በምድር ላይ ፍዳውን የሚቀበል ከሆነ" የሚለው ላይ ምን ማለት እንደፈለገ ቢያብራሩልን? ጻድቅ እንዴት ፍዳ ይቀበላል? ምሳ.፲፪፥፳፩ ደግሞ "ጻድቅን መከራ አያገኘውም" ይላል። ሁለቱ ጥቅሶች እንዴት ይታረቃሉ?


💙 የጥያቄዎች መልስ ክፍል 150 💙

▶️፩. ምሳ.11፥15 ላይ "ለማያውቅ የሚዋስ ክፉ መከራን ይቀበላል። ዋስነትን የሚጠላ ግን ይድናል" ይላል። ዋስነትን የሚጠላ ሲል ከ6ቱ ቃላተ ወንጌል አንዱ ብታሰር ጠይቃችሁኛል የሚለው ነው። ከዚህ አንጻር እንዴት ይታረቃል?

✔️መልስ፦ የታሰረን መጠየቅና ዋስ መሆን ይለያያል። የታሰሩ ሰዎች ካሉ ከገንዘባችን አውጥተን፣ የሚበላ አዘጋጅተን እግዚአብሔር ያስፈታችሁ ማለት ይገባል። ዋስ ያልሆነ ቅጣታቸውንም የሚከፈለውን ከፍለን ከታሰሩበት ማስፈታት የጽድቅ ሥራ ነው። በተጨማሪም የሰዎቹ ደግነት የታወቀ ከሆነ ለእነርሱ ዋስ ሆኖ ማስፈታት ይቻላል። ለክፉ ሰው ዋስ መሆን ግን በእርሱ ምትክ እኔ ልታሰር ማለት ስለሆነና ዋስነቱ ወንጀለኛውንም ከወንጀሉ የማያቆመው ስለሆነ አይገባም ተብሏል። ከዚህ የተገለጸው ለክፉ ሰዎች ዋስ መሆን እንደማይገባ ነው።

▶️፪. ምሳ.፲፪፥፲ ላይ "የኃጥኣን ምሕረት ግን አለመመጽወት ነው" ይላል። በዚህ አገባብ ምሕረት ምን ለማለት ነው? አለመመጽወት ምሕረት ነው እንዴ?

✔️መልስ፦ አይደለም። በዚህ አግባብ ምሕረት የሚለው ምጽዋትንና ለተቸገረ ሰው የሚደረግ ርኅራኄን ነው። የኃጥኣን ምሕረት አለመመጽወት ነው ማለት ኃጥኣን ሰርቀው ቀምተው ቢመጸውቱ ምጽዋታቸው ከምጽዋት ስለማይቆጠር አለመመጽወት ነው ተብሏል። ምጽዋት መስጠት የሚገባው ጥረን፣ ግረን፣ ለፍተን ካገኘነው ገንዘብ ነው ለማለት ነው።

▶️፫. "በጻድቃን ደግነት ከተማ ትቀናለች" ሲል ከተማ የተባለው ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ከተማ የሚለው ሀገር ለማለት ነው። በመዲናዋ ሀገሪቱን ለመግለጽ የመጣ ነው። በጻድቃን ደግነት ሀገር ትቀናለች ማለት ሰላም ትሆናለች ማለት ነው።

▶️፬. "ተግሣጽን የሚወድ ዕውቀትን ይወዳል ዘለፋን የሚጠላ ግን ደን*ቈሮ ነው" ይላል (ምሳ.12፥1)። ዘለፋ የሚለው ቃል በአሁን ሰዓት ስድብን የሚያመለክት ነው?

✔️መልስ፦ በእርግጥ ዘለፈ ብሎ ሰደበ ይላል። ይኸውም ሰው ከነበረበት ከክፉ ሥራው ይመለስ ዘንድ ክፉ ሥራውን በአደባባይ መግለጽ ማለት ነው። ለምሳሌ የሚሰርቅን ሰው ሌባ ማለት ዘለፋ ነው። ነገር ግን ይህ ዘለፋ መሠረቱ እውነትና ፍቅር ነው። ሰው ያልሆነውን ነህ ማለት ግን ታላቅ ኃጢአት ነውና ይህኛው ዘለፋ ሳይሆን የቅንዐት የምቀኝነት ውጤት የሆነው ስድብ ነው።

▶️፭. "ለሰው ቅን የምትመስል መንገድ አለች። ፍጻሜዋ ግን የሞት መንገድ ነው" ይላል (ምሳ.14፥12)። ይህች መንገድ ምንድን ናት?

✔️መልስ፦ ከዚህ መንገድ የተባለች ይህች ዓለም ናት። ለሰው ብዙ ዘመን የምትኖር መስላና መልካም ዓለም መስላ ትታያለች። ነገር ግን የዚህች ዓለም ኑሮ በሞት የሚደመደምና ምንም የማይጠቅም ነው።

▶️፮. "አባይ ሚዛን በእግዚአብሔር ፊት አስጸያፊ ነው። እውነተኛ ሚዛን ግን ደስ ያሠኘዋል" ይላል (ምሳ.11፥1)። አባይ ማለት ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ አባይ ማለት ሐሰተኛ ማለት ነው። ሐሰተኛ ሚዛን ማለት የሚያደላ፣ ብዙ ተቀብሎ ትንሽ የሚሰጥ፣ ትንሽ ሰጥቶ ብዙ የሚቀበል ማለት ነው።

▶️፯. "ቤቱን የሚያውክ ሰው ነፋስን ይወርሳል። ሰነፍም ለጠቢብ ተገዢ ይኾናል" ይላል (ምሳ.11፥29)። ነፋስን ይወርሳል ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ቤቱን የሚያውክ ሰው ነፋስን ይወርሳል ማለት ነፋስ ቤቱን አፍርሶበት በነፋስ ይጎዳል ማለት ነው። በምሥጢር ነፋስ የተባለ ዲያብሎስ ነው። ቤተ ነፍሱን የማይጠብቅ ሰው ዲያብሎስ ያፈርስበታል ማለት ነው።

▶️፰. "ምድሩን የሚሠራ ሰው እንጀራ ይጠግባል። ለከንቱ ነገር የሚሮጥ ግን አእምሮ የጎደለው ነው" ይላል (ምሳ.12፥11)። ምድሩን የሚሠራ ሰው እንጀራ ይጠግባል ሲባል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ ምድሩን የሚሠራ ሰው ማለት ምድርን አርሶ፣ ቆፍሮ የሚዘራ ሰው እህል አግኝቶ እንጀራ ያገኛል ይጠግባል ማለት ነው።

▶️፱. "የሰነፍ መንገድ በዐይኑ የቀናች ናት። ጠቢብ ግን ምክርን ይሰማል" ይላል (ምሳ.12፥15)። በዐይኑ የቀናች ናት ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ የሰነፍ መንገድ በዐይኑ የቀናች ናት ማለት ክፉ ሰው የሚሠራው ክፉ ሥራ ለእርሱ የቀናና ደግ ሥራ ይመስለዋል ለማለት ነው። በሌላው ዘንድ ግን የእርሱ ሥራ ክፉ መሆኑ ይታወቃል።

▶️፲. "በችኰላ የምትከማች ሀብት ትጎድላለች። ጥቂት በጥቂት የተከማቸች ግን ትበዛለች" ይላል (ምሳ.13፥11)። በችኰላ ሲል ምን ለማለት ነው?

✔️መልስ፦ በችኮላ ያለው ሰርቆ፣ ቀምቶ ቶሎ ሀብታም ለመሆን የሚፈልግ ሰው ያነሰ ይሆናል ለማለት ነው። በጽድቅ በፍጥነት የሚሠራ ሰው ግን ኃጢአት አይሆንበትም። ያነሰም አይሆንም።

▶️፲፩. "በድኻዎች እርሻ ላይ ብዙ ሲሳይ አለ። ከፍርድ መጕደል የተነሣ ግን ይጠፋል" ይላል (ምሳ.13፥23)። ሲሳይ ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሲሳይ ግእዝ ቀመስ አማርኛ ነው። ሴሰየ መገበ ከሚለው ቃል ሲሳይ የሚል ቃል ይወጣል ምግብ (እንጀራ) ማለት ነው።

▶️፲፪. "ፌዘኛ ሰው ጥበብን ይፈልጋል አያገኛትም። ለአስተዋይ ግን ዕውቀትን ማግኘት አያስቸግረውም" ይላል (ምሳ.14፥6)። ፌዘኛ ሰው ከፈለጋት ያላገኛት ለምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ፌዘኝነት ራሱ የጥበብ ተቃራኒ ስለሆነች ነው። ሰው ጥበብን ለማግኘት መጀመሪያውንም ከፌዘኝነት መላቀቅ አለበት። ከፌዘኝነት መላቀቅ ራሱ አንዱ የጥበብ መንገድ ነውና። ፌዝን ይዞ ጥበብን መፈለግ ማለት ከሰረቀን ሌባ ጋር የጠፋንን ዕቃ እንደመፈለግ ያለ ነውና።

▶️፲፫. "የንጉሥ ክብር በሕዝብ ብዛት ነው። በሰው ጥቂትነት ግን የገዢ ጥፋት አለ" ይላል (ምሳ.14፥28)። በሰው ጥቂትነት ግን የገዢ ጥፋት አለ ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ንጉሥ ያለ ሕዝብ፣ ንጉሥ ያለ ሠራዊት መኖር አይችልም ማለት ነው። ጥቂት ሕዝብ ያለውን ንጉሥ ብዙ ሕዝብ ብዙ ሠራዊት ያለው ንጉሥ ያጠፋዋልና ነው።

▶️፲፬. "የታካች መንገድ እንደ እሾኽ ዐጥር ናት። የጻድቃን መንገድ ግን የተደላደለች ናት" ይላል (ምሳ.15፥19)። እንደ እሾኽ ዐጥር ናት እና የተደላደለች ናት ማለት ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ የእሾህ አጥር እንደማይመችና እየወጋ እንደማያሳልፍ ሁሉ የሰነፍ መንገድም እንዲሁ አይመችም ማለት ነው። በሌላ አገላለጽ ጌታ አዳም በበደለ ጊዜ እሾህ ይብቀልብህ ብሎት ነበር። እኩያት ፍትወታት ኃጢአት ይሰልጥኑብህ ማለቱ ነው። ስለዚህ የታካች መንገድ እንደእሾህ አጥር ናት ማለት ኃጢአት ናት ማለት ነው። የጻድቅ መንገድ የተደላደለ ነው ማለት የተመቸ የሚመች ነው ማለት ነው። ይኸውም ኃጢአት የለበትም ማለት ነው።

▶️፲፭. "የጻድቅ ልብ መልሱን ያስባል። የኃጥኣን አፍ ግን ክፋትን ያፈልቃል" ይላል (ምሳ.15፥28)። መልሱ የተባለው ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ መልስ የተባለች ሃይማኖት ናት። ግእዙ በግልጽ አስቀምጦታል። ልበ ጻድቃን ይትሜሀር ሃይማኖተ እንዲል። በተጨማሪም የኃጥኣን አፍ ግን ክፋትን ያፈልቃል በሚለው አንጻር የጻድቅ ልብ መልሱን ያስባል ማለቱ ጽድቅን ያስባል ማለት ነው።

▶️፲፮. "እግዚአብሔርን መፍራት የጥበብ ትምህርት ነው። ትሕትናም ክብረትን ትቀድማለች" ይላል (ምሳ.15፥33)። ትሕትናም ክብረትን ትቀድማለች ሲባል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ትሕትና ክብረትን ትቀድማለች ማለት ሰውን ወደ ክብር የምታወጣው ትሕትና ናት ማለት ነው። ወይም በሌላ አገላለጽ ሰው ትሑት ሲሆን ክቡር ይሆናል ማለት ነው።


🧡 መጽሐፈ ምሳሌ ክፍል 4 🧡

🧡ምዕራፍ ፲፮፡-
-እግዚአብሔርን መፍራት በጎ ዕውቀትና ጥበብ እንደሆነ
-የዋሃንን ክብር እንደምትከተላቸው
-የትሑት ሰው ሥራ ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ እንደሆነ
-በልቡ የታበየ ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ ርኩስ እንደሆነ
-የደግ ነገር መጀመሪያ እውነት መሥራት እንደሆነ
-ቅንነትን የሚሹ ሰላምን እንደሚያገኙ
-የእግዚአብሔር ሥራ ሁሉ ከእውነት ጋር እንደሆነ
-የሕይወት መንገዶች ከክፉ እንደሚያርቁ
-በእግዚአብሔር የታመነ ብፁዕ እንደሆነ
-ያማረ ቃል የማር ወለላ እንደሆነ
-መልካም ሽምግልና የክብር አክሊል እንደሆነ

🧡ምዕራፍ ፲፯፡-
-ጻድቅ የሐሰት ከንፈሮችን እንደማይመለከት
-የልጆች ክብር አባቶቻቸው እንደሆኑ
-የጽድቅ መጀመሪያ በነገር መሠልጠንን እንደሚሰጥ
-ኃጥኡን ጻድቅ ጻድቁን ኃጥእ ብሎ መፍረድ በእግዚአብሔር ዘንድ የረከሰ እንደሆነ
-ጠማማ ልብ ያለው መልካም ነገርን እንደማያገኝ
-ሻካራ ቃልን ከመናገር የሚከለከል ዐዋቂ እንደሆነ
-ትዕግሥተኛ ሰው ብልህ እንደሆነ

🧡ምዕራፍ ፲፰፡-
-በፍርድ ጊዜ እውነትን ማራቅ መልካም እንዳይደለ
-የእግዚአብሔር ስም ታላቅ እንደሆነና ጻድቃን እርሱን በመከተል ከፍ ከፍ እንደሚሉ
-የብልህ ልብ ዕውቀትን ገንዘብ እንደሚያደርግ
-ደግ ሚስትን ያገኘ ሞገስን እንዳገኘና ደግ ሴትን የፈታ ደስታን እንዳጣ

🧡ምዕራፍ ፲፱፡-
-ነፍስ ዕውቀት የሌለባት ትሆን ዘንድ መልካም እንዳይደለ
-ማስተዋልን የሚጠብቅ መልካም ነገርን እንደሚያገኝ
-ሐሰተኛ ምስክር ከቅጣት እንደማይድን
-ይቅር ባይ ሰው ታጋሽ እንደሆነ
-እግዚአብሔርን መፍራት ሕይወት እንደሆነ
-አስተዋይን ሰው ብትገሥጸው ዕውቀትን እንደሚያገኝ

🧡ምዕራፍ ፳፡-
-ለተሳዳቢና ለሰካራም ወይን ክፉ እንደሆነ
-የሰው ክብሩ ከስድብ መከልከል እንደሆነ
-ይቅር ባይ ሰው ታላቅና ክቡር እንደሆነ
-ቸርነትና እውነት ንጉሥን እንደሚጠብቁት

🧡 የዕለቱ ጥያቄዎች 🧡
፩. ከሚከተሉት ውስጥ ትክክል ያልሆነው የቱ ነው?
ሀ. የትሑት ሰው ሥራ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ ነው
ለ. በልቡ የታበየ ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ የተከበረ ነው
ሐ. የደግ ነገር መጀመሪያ እውነትን መሥራት ነው
መ. ሀ እና ሐ
፪. ስለ ብልህ ሰው ትክክል የሆነው የቱ ነው?
ሀ. የብልህ ሰው ልብ የሕይወት ምንጭና ፈሳሽ ወንዝ ነው
ለ. የብልህ ሰው ልብ ዕውቀትን ገንዘብ ያደርጋል
ሐ. ሀ እና ለ
መ. መልስ የለም
፫. ስለይቅር ባይ ሰው ትክክል ያልሆነው የቱ ነው?
ሀ. ይቅር ባይ ሰው ታላቅና ክቡር ነው
ለ. ይቅር ባይ ሰው ታጋሽ ነው
ሐ. ይቅር ባይ ሰው በእግዚአብሔር ይጠላል
መ. ሀ እና ለ

https://youtu.be/jJ3uKRxDIfw?si=WIv23ne-ANWFzsZy


የጎንደር ደብረ ኃይል ወደብረ ጥበብ በዓታ ለማርያም ካቴድራል ሰንበት ትምህርት ቤት ሁልጊዜም እሑድ ከ9፡00 ጀምሮ እስከ 11፡30 የግእዝ ትምህርትን ይሰጣል። ስለዚህ በቦታው ተገኝተው ይማሩ።

ትምህርቱ የሚሰጠው ከካቴድራሏ ግቢ ውስጥ በሚገኘው ፈለገ ጥበብ በዓታ ለማርያም አካዳሚ ውስጥ ነው።

በቦታው ተገኝተው ትምህርቱን መማር ለሚፈልጉ ሁሉ መረጃው ይደርስ ዘንድ share በማድረግ ይተባበሩ።


ለነገው ጥያቄ ለመጠየቅ ከአሁን ጀምሮ እስከ ነገ ከቀኑ 10፡00 ሰዓት ድረስ ጠይቁ።


▶️፰. ምሳ.6፥16 ላይ "እግዚአብሔር የሚጠላቸው ስድስት ነገሮች ናቸው። ሰባትንም ነፍሱ አጥብቃ ትጸየፈዋለች" ይላል። ስድስት ነገሮች እና ሰባትንም የተባሉ ምን ምን ናቸው?

✔️መልስ፦ ከቁጥር 17 ጀምሮ የጠቀሳቸው ናቸው። እነዚህም የሚከተሉት ናቸው።
1ኛ፦ ከፍ ዝቅ እያደረገ የሚያይ ዐይን
2ኛ፦ ሐሰተኛ አንደበት
3ኛ፦ የጻድቁን ደም የሚያፈስ እጅ
4ኛ፦ ክፉ ሐሳብን የምታስብ ልቡና
5ኛ፦ ክፉ ነገር ለማድረግ የሚሄድ እግር
6ኛ፦ በሐሰት የሚመሰክር ሰው
7ኛ፦ በወንድሞች መካከል ጸብን የሚያመጣ

▶️፱. ምሳ.8፥30 ላይ "የዚያን ጊዜ እኔ በእርሱ ዘንድ ዋና ሠራተኛ ነበርኹ። ዕለት ዕለት ደስ አሠኘው ነበር። በፊቱም ዅልጊዜ ደስ ይለኝ ነበር" ይላል። እኔ ያለው ማን ነው?

✔️መልስ፦ ከዚህ እኔ እያለች የምትናገረዋ ተናጋሪ ጥበብ ናት።

▶️፲. "እግዚአብሔር በሚጠላቸው ሁሉ ደስ ይለዋልና። ስለ ነፍሱ ርኩሰትም ይደቅቃልና" ይላል (መዝ.6፥16)። የዚህ ንባብ ትርጓሜ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ይህ የተነገረ ስለ ክፉ ሰው ነው። ክፉ ሰው እግዚአብሔር የሚጠላውን ሥራ ይሠራል ማለት ነው። ስለነፍሱ ርኵሰትም ይደቅቃልና ማለት ክፉ ሰው በሚሠራው ክፉ ሥራ ራሱ ይጎዳል ማለት ነው።

▶️፲፩. "የአመንዝራ ሴት ክብር እስከ አንዲት እንጀራ ነው" ይላል (ምሳ.6፥26)። እስከ አንዲት እንጀራ ነው ሲል ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ እስከ አንዲት እንጀራ ናት ማለት አመንዝራ ሴትን መውደድ አንዲት እንጀራን እስከ ማሳጣት ያደርሳል ማለት ነው። አመንዝራ ሴት ሀብትን ትበዘብዛለች ማለት ነው።

▶️፲፪. ምሳ.7፥16 "በአልጋዬ ላይ ማለፊያ ሰርፍ ዘርግቼበታለሁ። የግብፅንም ሽመልመሌ ለሀፍ" ይላል። ሽመልመሌ ለሀፍ ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሸመልመሌ ለሐፍ የሚለው የልብስ ዓይነት ነው። የተዝጎረጎረ ልብስ ማለት ነው።

▶️፲፫. ምሳ.9፣7 ላይ "ክፉዎችን የሚያስተምር ለራሱ ውርደትን ይቀበላል። ኃጥኣንንም የሚገሥጽ ራሱን ያዋርዳል" ሲል ክፉዎችንና ኃጥኣንን መገሠጽ አይገባም ማለት ነው?

✔️መልስ፦ አይደለም። ክፉዎችን ሰዎች ከክፋታቸው እንዲመለሱ ማስተማርና መገሠጽ አስፈላጊ ነው። እነዚህን ለማስተማር የተዘጋጀ ሰው ግን ሥጋዊ ውርደት ይገጥመዋል ማለት ሊንቁት፣ ሊዘልፉት፣ ሊያቃልሉት ይችላሉ። በነፍሱ ግን ክብርን ያገኝበታል ለማለት ነው። በተጨማሪም በተደጋጋሚ ተመክሮ አልመለስ ያለን ሰው መራቅ እንደሚገባ የሚያመለክት ቃል ነው።

▶️፲፬. ምሳ.፯፥፲፩ ላይ "ሁከተኛና አበያ ናት" ይላል። ሁከተኛ እና አበያ ማለት ምን ማለት ነው?

✔️መልስ፦ ሁከተኛ ማለት በጥባጭ ማለት ነው። አበያ ማለት ደግሞ ሰነፍ ማለት ነው። ክፉና አመንዝራ ሴት ሰነፍና በጥባጭ ናት ማለት ነው።

▶️፲፭. "ሌባ በተራበ ጊዜ ነፍሱን ሊያጠግብ ቢሰርቅ ሰዎች አይንቁትም" ይላል (መዝ.6፥30)። ሌባውን ሰዎች ቢሰርቅ አይንቁትም ሲል ምን ማለቱ ነው?

✔️መልስ፦ አይንቁትም የተባለው አንጻራዊ ንቀት ነው። ሌባ ከአመንዝራ ይሻላል ማለቱ ነው። ይኸውም የሰረቀ የሚበላው ቢያጣ ነው ብለው ሰዎች ያስቡለታል ለማለት ነው እንጂ ሁለቱም ገሀነም የሚያስገቡ ክፉ ሥራዎች ናቸው። እጅ ከፍንጅ ሲያዝ የሰረቀውን ሰባት እጥፍ እንዲከፍል ቀጥሎ ቁጥር 31 ላይ ተገልጿልና። ስለዚህ በአንጻር ተናገረ እንጂ ሌብነትም ማመንዘርም ሁለቱም ታላላቅ ኃጢአቶች ስለሆኑ መጠንቀቅ ይገባናል። ብንቸገር እንኳ መለመን እንጂ መስረቅ አይገባንም።

▶️፲፮. "የስርቆት ውሃ ይጣፍጣል። የተሸሸገም እንጀራ ደስ ያሠኛል" ይላል (መዝ.9፥17)። ምሥጢሩ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ የተጠማ ሰው ውሃ ሰርቆ ሲጠጣ ደስ ይለዋል። ማለት ጥሙን ያስወግድበታል። በዚህ ጊዜ ምሥጢሩን በጥንቃቄ መረዳት አስፈላጊ ነው። ከዚህ ደስ ያሰኛል ያለው ጥሙን ስላራቀለትና ስለሚያርቅለት እንጂ በመሰረቁ አይደለም። ስርቆት ታላቅ ኃጢአት ነውና። የተሸሸገም እንጀራ ደስ ያሰኛል መባሉ የተራበ ሰው በልቶት ከረኀቡ ይላቀቃልና ረኀቡን በማስለቀቁ የተነገረ ነው።

▶️፲፯. ምሳ.6፥5 ላይ "እንደ ወፍ ከጭራ ወጥመድ" ሲል የጭራ ወጥመድ ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ የጭራ ወጥመድ ማለት ከጭራ የሚሠራ ወጥመድ ማለት ነው። ጭራውን ጎንጉነው ወይም ፈትለው ወፍን ለመያዝ ያጠምዱታልና ስለዚህ የተነገረ ነው።

▶️፲፰. መዝ.6፥12 ላይ "በዐይኑ ይጠቅሳል፣ በእግሩ ይናገራል፣ በጣቱ ጥቅሻ ያመለክታል" ይላል። ትርጓሜው ምንድን ነው?

✔️መልስ፦ ይህ ስለአመፀኛ ሰው የተነገረ ነው። አመፀኛ ሰው ክፉ ሥራን ለመሥራት በዐይኑ ይጠቅሳል ማለት ክፉ ነገርን በዐይኑ ጠቅሶ ያሳያል ማለት ነው። በእግሩ ይናገራል ማለት በእግሩ ጎሰም አድርጎ ያሳያል ማለት ነው ማሳየቱን መናገር ብሎት ነው። በጣቱ ጥቅሻ ያመለክታል አለ ክፉ ሥራን ያሳያል ማለት ነው።

▶️፲፱. "በዐይኑ የሚጠቅስ መከራን ያመጣል። ደፍሮ የሚገሥጽ ግን ሰላምን ያደርጋል" ይላል (ምሳ.10፥10)። በዐይን መጥቀስ ኀጢአት ነው?

✔️መልስ፦ በዐይን መጥቀስ ብቻውን ኃጢአት አይደለም ኃጢአትም አይሆንም። ነገር ግን ለክፉ ነገር በዐይን መጥቀስ ኃጢአት ይሆናል። ከዚህ ምዕራፍ የተገለጸውም ለክፉ ነገር መጥቀስ እንደማይገባ ነው።

▶️፳. "የጻድቅ ምላስ የተፈተነ ብር ነው" ይላል (ምሳ.10፥20)። የጻድቅ ምላስ የተፈተነ ብር ነው የተባለው ከምን አንጻር ነው?

✔️መልስ፦ ከዚህ ላይ ብር የተባለው የወረቀቱ ብር ሳይሆን የመዓድኑ ብር ነው። በተለምዶ ሁለተኛ ደረጃ የሆኑ ተሸላሚዎች የሚሸለሙት መዓድን ነው። ወርቅን በእሳት በማቅለጫ ሲፈትኑት ማለት ሲያቀልጡት ጥራቱ እየጨመረ እንደሚሄድ ሁሉ የጻድቅ ሰው ምላስም የተፈተነ ነው ማለት ሐሜትና ቧልት በጠቅላላ ክፉ ነገርን የማይናገር የጠራ ነው ማለት ነው።


© በትረ ማርያም አበባው


✝️የዩቲዩብ ቻናሌ:- ንሕነ ዘክርስቶስ https://youtube.com/@edenawizechristos?si=6V4y-73OM3LTzhAf ነው።

🌻የፌስቡክ ገጼ Betremariam Abebaw https://www.facebook.com/profile.php?id=100075547015721 ነው።

20 last posts shown.