"ማህበራዊ ሚዲያ የልጆቻችንን የማሰብ ችሎታ እያቀጨጨ በመሆኑ የእጅ ስልክ ክልከላ ለማድረግ እየተወያየን ነው" - ፕ/ር ብርሃኑ
በትምህርት ላይ ያሉ ልጆቻችን ከዘመኑ እኩል እንዲራመዱ በማለት የምንሰጣቸው የእጅ ስልክና እና የሚጠቀሟቸው ማህበራዊ ሚዲያዎች የማሰብ ችሎታቸው እንዳይዳብር እያደረጉ ነው ሲሉ የትምህርት ሚኒስትር ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ገልጸዋል፡፡
የተማሪዎች የእጅ ስልክ ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል፤ የማያነብ እና የማሰብ ችሎታው የተገታ ዜጋ እንድናፈራ የሚያደርግ መሰናክል መሆኑን ልብ ልንል ይገባል ብለዋል፡፡
“ተማሪ ከትምህርት ተቋማት እውነትን ሊሻ ይገባል!” ያሉት ሚኒስትሩ፤ የማሰብ ችሎታው የዳበረና ምክንያታዊ የሆነ ትውልድን ማብቃት ማህበራዊ ኃላፊነት መሆኑን በኢቢሲ የዛሬይቱ ኢትዮጵያ መሰናዶ ላይ ገልጸዋል።
በመሰናዶው የዘርፉ ምሁራን እና የሚመለከታቸው አካላትን ያሳተፈው መድረኩ ‘የትምህርት ጥራትን እንዴት እናስጠበቅ?’፤ ‘ከገባንበት ስብራትስ በምን መልኩ እንጠገናለን?’ የሚል ሃሳብ ተነስቷል።
ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ የተማሪዎችን የትምህርት አቀባበል ሊረብሽ የሚችል በመሆኑ የእጅ ስልክ ክልከላ እስከማድረግ የደረሰ ቁጥጥር እንደሚደረግ በውይይቱ ላይ ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል ከትምህርት ሥርዓቱ ጋር በተያያዘ የመምህርነት ሙያን እንደቀደመው ጊዜ የሚከበር ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ሚኒስትሩ አመላክተዋል፡፡
"ይህን በማድረግ ሂደት ውስጥ ግን የመምህራንን መሰረታዊ ችግር መፍታት እንዳለብን አልዘነጋንም፤ እርሱ ላይ እየሰራን ነው" ሲሉም አክለዋል፡፡
በሌላ በኩል ትርፍን ብቻ ፈልገው ወደ ዘርፉ የሚገቡ የግል የትምህርት ተቋማት መስፋፋት ለዘርፉ ማሽቆልቆል የራሳቸውን አስተዋጽኦ አድርገዋል ነው ያሉት፡፡
በዓለም አቀፍ ደረጃ ኃያል የሚባሉ ሀገራት በዋናነት ትርፍ ላይ ያተኮሩ የግል የትምህርት ተቋማት እንደሌላቸውም አያይዘው አንስተዋል፡፡
በትምህርቱ ዘርፍ ከገባንበት ማጥ ለመውጣት የምናደርገው ማስተካከያ ውጤት በቅርብ ዓመታት ውስጥ ይመጣል ብሎ መጠበቅ የዋህነት ነው ያሉት ሚኒስትሩ፤ ትውልድ ተኮር ለውጥ በመሆኑ በርካታ ዓመታትን እንደሚወስድ አስረድተዋል፡፡
ትምህርት ለግለሰቡ ከሚሰጠው ጥቅም ይልቅ ለማህበረሰቡ ያለው አስተዋፅኦ አያሌ በመሆኑ ሁሉም ሰው ለዘርፉ እድገት የበኩሉን አስተዋጽኦ ሊያበረክት ይገባል ብለዋል፡፡
@Ethiopian_Digital_Library@Ethiopian_Digital_Library