ቁርኣንን ያለ ውዱእ መንካት ይቻላልን?
~
ቁርኣንን ያለ ውዱእ መንካት አይቻልም የሚለው የአራቱም የፊቅህ መዝሀቦች አቋም ነው። አልፎም ባጠቃላይ የብዙሃን ዑለማእ አቋም ነው። መረጃ የሚደግፈውም ይህንኑ ነው። ሁለት መረጃዎችን እጠቅሳለሁ:-
♻️ [መረጃ አንድ]:- ሐዲሣዊ ማስረጃ ♻️
ነብያችን ﷺ ወደ የመን በላኩት ደብዳቤ ላይ
أَنْ لَا يَمَسَّ الْقُرْآنَ إِلَّا طَاهِرٌ
"ቁርኣንን ጦሀራ የሆነ እንጂ እንዳይነካው" ሲሉ አሳስበዋል። [ሙወጦእ: 468]
ሐዲሡን ሸይኹል አልባኒይ ረሒመሁላህ "ሶሒሕ" ብለውታል። [ሶሒሑል ጃሚዕ፡ 7780]
👉🏾 ብዥታ!
~
ቁርኣንን ያለ ውዱእ መንካት ይቻላል የሚሉ ዓሊሞች ግን "የሐዲሡ መልእክት ሌላ ነው። 'ጦሀራ የሆነ እንጂ እንዳይነካው' ማለት 'ሙስሊም እንጂ እንዳይነካው' ማለት ነው" ይላሉ። ለዚህም "ሙስሊም አይንነጀስም" የሚለውን ሐዲሥ ያጣቅሳሉ።
ይሄ ግን - ወላሁ አዕለም - ልክ አይደለም። ይልቁንም መልእክቱ በቀጥታ ጦሀራ/ውዱእ የሌለው ሰው እንዳይነካው ማለት ነው። የሐዲሡ ሌሎች ዘገባዎች ይህንን መልእክት ግልፅ ያደርጉልናል። ለምሳሌ:-
✅ 1ኛ፦ የዐብዱረዛቅ ዘገባ ላይ እንዲህ የሚል እናገኛለን፦
لَا يُمَسُّ الْقُرْآنُ إِلَّا على طُهْرٍ
"በጦሀራ ላይ ተሁኖ እንጂ ቁርኣን አይንነካም።" [አልሙሶነፍ: ቁ. 1328]
✅ 2ኛ:- የኢብኑል ሙንዚር ዘገባ ላይ ደግሞ እንዲህ የሚል እናገኛለን፦
لَا تَمَسَّ الْقُرْآنَ إِلَّا على طَهورٍ
"በጦሀራ ላይ ሆነህ እንጂ ቁርኣን እንዳትነካ።" [አልአውሰጥ፡ 2/103]
▶️ ልብ በሉ! ሙስሊሙን ሰው ነው "በጦሀራ ላይ ሆነህ እንጂ ቁርኣንን እንዳትነካ" ያሉት። ይህም ሐዲሡን "ሙስሊም ያልሆነ እንዳይነካው ማለት ነው" በማለት የተረጎሙት ልክ እንዳልሆኑ ያሳያል።
♻️ [መረጃ ሁለት]:- ቁርኣናዊ ማስረጃ ♻️
በቁርኣን ውስጥም እንዲህ የሚል መጥቷል:-
{ لَّا یَمَسُّهُۥۤ إِلَّا ٱلۡمُطَهَّرُونَ }
"የተጥራሩት እንጅ ሌላ አይነካውም።" [አልዋቒዐህ፡ 79]
በርግጥ የዚች አንቀፅ ቀጥተኛ መልእክት ጥብቁን ሰሌዳ (ለውሐል መሕፉዝን) የሚገልፅ እንደሆነ አገባቡ ያሳያል። ይሁን እንጂ መልእክቱ ለቁርኣንም የሚውል እንደሆነ ጥቆማ አለው ይላሉ ሸይኹል ኢስላም ኢብኑ ተይሚያ ረሒመሁላህ። [ሸርሑል ዑምደህ: 384] ዝርዝሩን ከዚህ በላይ ላለማስረዘም ስል ስለተውኩት በቦታው ተመልከቱት።
ባይሆን ይህንን ሃሳብ የሚደግፍ አንድ የሶሐቢይ ንግግር ልጥቀስ። ሶሐቢዩ ሰልማኑል ፋሪሲይ - ረዲየላሁ ዐንሁ - ናቸው። ዐብዱረሕማን ብኑ የዚድ - ረሒመሁላህ - እንዲህ ይላሉ፦
"ከሰልማን ጋር በሆነ ጉዳይ ላይ ነበርን። እሳቸው ጉዳያቸውን ለመፈፀም (ለመፀዳዳት) ሄደው ተመለሱ። 'ውዱእ አድርግማ የዐብደላህ አባት! ምናልባት ከቁርኣን ስለሆኑ አንቀፆች ልንጠይቅህ እንችላለን' አልናቸው። በዚህን ጊዜ (ሰልማን) እንዲህ አሉ፦
فَاسْأَلُوا، فَإِنِّي لَا أَمَسُّهُ، إِنَّهُ {لَا يَمَسُّهُ إِلَّا الْمُطَهَّرُونَ}
'ጠይቁ! እኔ አልነካውም። ነገሩ {የተጥራሩት እንጅ ሌላ አይነካውም}።'
ከዚያም "ጠየቅናቸው። ውዱእ ሳያደርጉ ቀሩልን" አሉ። [ሙሶነፍ ኢብኒ አቢ ሸይባህ፡ ቁ. 1100]
መግቢያዬ ላይ እንደገለፅኩት ጦሀራ የሌለው ሰው ቁርኣንን ሊነካ አይገባም የሚለው የብዙሃን ዑለማእ አቋም ነው። ኢብኑ ዐብዲል በር እንዲህ ይላሉ፦
أجمع فقهاء الأمصار الذين تدور عليهم الفتوى وعلى أصحابهم بأن المصحف لا يمسه إلا طاهر
"ጦሀራ ላይ የሆነ ካልሆነ በስተቀር ሙስሐፍ እንደማይንነካ ፈትዋ የሚቀርብላቸው የሙስሊም ሃገራት ሊቃውንት እና ባልደረቦቻቸው ወጥ ስምምነት ላይ ደርሰዋል።" [አልኢስቲዝካር፡ 8/10]
ከኢብኑ ሁበይራም በተመሳሳይ ኢጅማዕ እንዳለበት ተጠቅሷል። [አልኢፍሷሕ፡ 1/68]
ይሄ እንግዲህ እነሱ በሚያውቁት መጠን ነው። እንጂ ጥቂቶች ቢሆኑም የተለየ ሃሳብ ያንፀባረቁ ተገኝተዋል።
የሆነ ሆኖ ቁርኣንን ያለ ውዱእ መንካት አይቻልም የሚለው ከሶሐቦች ውስጥ ከ0ሊይ፣ ከሰዕድ ብኑ አቢ ወቃስ፣ ከኢብኑ ዑመር፣ ከሰልማኑል ፋሪሲይ - ረዲየላሁ ዐንሁም - ተገኝቷል። ከሶሐቦች ውስጥ እነዚህን የተቃረነ አይታወቅም ይላሉ ነወዊይ እና ኢብኑ ተይሚያህ። [አልመጅሙዕ፡ 2/80] [መጅሙዑል ፈታዋ፡ 21/266]
ይህንን ሃሳብ አስምሩበት። ከሶሐቦች ውስጥ እነዚህን የተቃረነ አይታወቅም። ስለዚህ ውዝግቡ የመጣው ከሶሓቦች በኋላ ነው ማለት ነው። አዋቂው አላህ ነው።
ማሳሰቢያ፦ ሞባይልና መሰል 'ዲቫይሶች'ን ተጠቅሞ መቅራት እዚህ ውስጥ አይገባም። እንዲሁም ትርጉምና የተፍሲር ኪታቦችም የሙስሐፍ ብይን ስለሌላቸው ያለ ጦሀራ መንካት ይቻላል።
=
(ኢብኑ ሙነወር፣ ረመዷን 21/1444፣ ሚያዚያ 04/2015)
የቴሌግራም ቻናል፡-
https://t.me/IbnuMunewor