ቅኔ ሚስጥር ትርጉም
ዘመን ግብሩን ላይለቅ የሚሆነዉ ላይቀር
ከሰዉነት መጉደል ከጨቋኝ ጋር ማበር
በእንቶ ፈንቶ ፍቅር ባለየ ጥላቻ
እናንተ ሙቱልን እኛ እንብላ ብቻ
በሆነበት ዘመን ነፍስ እየቀጨጨ ስጋ እየገዘፈ
ለጥቅማቸዉ ሲሉ ካስቀመጡን ቦታ እኛ ሳንፈልግ ሽ ዓመት ከነፈ፡፡
በሽ አመቱ መሀል ከቀን ቀን ሳይጎድሉ ሁሌም የሚሰሙ
ወጀብ ማዕበሉ ያላናወጣቼዉ ለወሬ ያልቆሙ
ማይነቃቀፉ ማይረባበሹ የማይገፋፉ
ለየብቻ ቆመዉ በአንድ የተሰለፉ
ግብራቼዉ አንድነት ፍፃሜያቸዉ ፍቅር
ስጋቸው ሰው መሆን ነፍሳቸውም ሀገር
አሏህ አከብር ሲባል በስመአብ ቅዱስ ብሎ
ከሰማይ ሰማያት ለሚኖር አምላኩ ምስጋናን አድሎ
ኑረዋል ለሽ ዓመት…..
የአንደኛው ሲጎድል አንዱ እየሞላለት
በሽ ዓመቱ መሀል….
ጨለማ ላይ ቆሞ መንጋትን አላሚ
ብርሀን የናፈቀው የድል ዜና አሰሚ
ግፍ ያንሰፈሰፈው ለነፍስያው ቋሚ
የአገር ደጅን ጥላ እውነትን ተላሚ
ሲደላው ገበሬ ሲከፋው ወታደር
አማኝ ፅኑ ታጋሽ ታሪክ የሚዘክር
መሞት ሽልማቱ መድማት መቁሰል ጌጡ
ነበልባል ነው ክንዱ በሀገሩ ለመጡ
አፈር ላይ ተኝቶ አይከፋው አይጨንቀው
ድንጋይ ተንተርሶ አይበርደው አይሞቀው
ብቻ አገር አለችው ሰርክ የሚጠብቃት
መጥፋቷን በሞቱ የሚቀይርላት
በሽ ዓመቱ መሀል….
ለቅሶና ዳንኬራ ከአንድ ቤት ተከብሯል
በአባት ሬሳ ላይ ልጅ እየጨፈረ በወኔ ፎክሯል
ለአንድ ሀገር ሳይሆን ሽ ክልል መስርቷል
በኔ እነት አለም ውስጥ እኛነት ተረስቷል፡፡
በሽ ዓመቱ መሀል….
ሀገር ይሏት ነገር በእፍኝ ተጠቅልላ
የሽ ዓመትነቷን ወደኋላ ጥላ
ትላንት ገተገኘው ድንገት ተንጠልጥላ
ታሪክ ገሌ መሌ ባህል ቅብርጥሴ
ቀደምት ስልጣኔ በአክሱም ላሊበላ የታወቀው ቅርሴ
የኔነት አይገልጥም ብላለች በልጇ
ዘመን ላላወቁ ጥበብ ላልገባቸው አዋጅ አሳውጃ….
የዚህ ሁሉ ተንኮል ይሄ ሁሉ በደል
ኢትዮጲያን ለማፍረስ እኛኑ ለማጉደል
ወርቅ እየዘረፉ ቁራሽ ዳቦ ማደል
ታሪኩ ተረት ሆኖ ለፊልም መጋደል….
ሀገር አልባ ተውልድ ለመፍጠር የለፋ
ሀገራችን አለች እኛም አለን እሄው እንሱ ግን ጠፉ…
ቅኔናት ሀገሬ ደረሳ ማትፈታ
ሚስጥር ናት ሀገሬ በሞኞክ ልኬታ ቀድማ ማትረታ
ትርጉም ናት ሀገሬ ውስጧ የከረረ
ደንበሯ ነበልባል በእሳት የታጠረ
ገጣሚ ስንታየሁ ስንሻው ከባህርዳር
ሰኞ እና መስከረም ከተሠኘው መጽሐፌ የተወሰደ
@ebchager1