አባ በርናባስና “ጳጳስ” ሕዝቅኤል - ተቃራኒ ጳጳሳት!
አቡነ በርናባስ አስደናቂ የወንጌልን መልእክትን ያለ ፍርሃት የሚያቀርቡ፤ ያልገባቸውንና ተንኰል አዘል በኾነ መንገድ የተቀየረውን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ደግሞ፣ በቀናነትና በቀጥተኛነት የሚጠይቁ የሚሞግቱ ናቸው። በቃለ መጠይቃቸው ላይ እንደሚስተዋለው፣ አቡኑ ጠንቃቃና ሙግታቸውን በምን መንገድ እንደሚያቀርቡ በትክክል የሚያስተዋሉ፣ ሲያስረዱም መስመር የማይስቱ፣ የተረጋጉ፣ በትህትና የተመሉ፣ ያመኑበትን የትኛውንም ትምህርት በድፍረት ለመናገር የማያፍሩም፤ የማይፈሩም አባት ናቸው።
ከዚህ ቀደም እንደ ተናገርኹት፣ በዕድሜዬ፣ ስለ ክርስቶስ ምልጃና አስታራቂነት እንደ እርሳቸው ደፍሮ በአደባባይ የመጽሐፍ ቅዱስን ዕውነት መሠረት ባደረገ መንገድ የተናገረ ጳጳስ አላስታውስም። ክርስቶሳዊ ትምህርታቸው ርቱዕ ኦርቶዶክሳዊና እንከን የማይገኝበት ነው። መጽሐፍ ቅዱሳዊውን ክርስትናና ክርስቶስን ሲናገሩ በትክክልና ለእውነት ወግነው ነው።
ስለ ክርስቶስ ሊቀ ካህናትነት ሲናገሩ፣
“ … ወደ አባቱ ሲጸልይ እምቢ የማይባል ጸሎት ነው፣ ለምን? አንደኛ ያለ ኃጢአት የተገለጠ ካህን ነው፣ ንጹሕ ነው፤ ኹለተኛ ደግሞ በአምላክነቱ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ጩኸት ሰሚ ነው፣ አየህ ራሱ ለማኝ ነው፣ ራሱ ደግሞ ተለማኝ ነው። ራሱ ሰሚ ነው፣ ራሱ ፈራጅ ነው፣ ስለዚህ አኹን እርሱ አባቱን ሲለምን በሰውነቱ ነው ማለቴ ነው፣ በሰውነቱ ስል ሥግው ቃል ነው፣ በሰውነቱ የሚናገረው ራሱ ቃል ነው፣ ወልድ ነው። ተግባብተናል? መለኮት ነው፣ ፈጣሪ ነው፣ ፈጣሪ ግን ወደ ፈጣሪ መለመን አይችልም አይደል? አምላክ ወደ አምላክ መለመን አይችልም።
ግን መለመን እንዲችል ያደረገው ሰውም ስለኾነ ነው። በሰውነቱ ነው፣ በተዋሐደው አካል ነው የሚለምነው። እና ምንድነው ያለው? እነዚህ የምታያቸው የአንተ ደቀ መዛሙርት፣ የእኔ ደቀ መዛሙርት፣ ስለ እነርሱ እለምንሃለሁ፣ ቅዱስ አባት ሆይ! በስምህ ቀድሳቸው፣ “ኦ አባ እቀቦሙ በስምከ ወበኃይልከ፣ ከመ ይኩኑ አሐደ ብነ ከማነ”፣ “እኔና አንተ አንድ እንደ ኾንን አንድ እንዲኾኑ በስምህ ቀድሳቸው፣ አንድ አድርጋቸው” ይላል። እምቢ የማይባል ነው አኹን፣ ስለ እነርሱ ብቻ አይደለም የምልህ አለ፣ በልባቸው አምነው በቃላቸው ስለ መሰከሩ እስከ ዐለም ፍጻሜ ስለሚኖሩት፣ ለምን? በስሜ አምነው የሚጠመቁ ሁሉ እንደነዚህ ናቸው ብሎ፣ እስከ ዕለተ ምጽዓት ማለት ነው፣ …”
ይህ የአባ በርናባስ ትምህርት እጅግ አስደናቂ፣ የፍጡራን ምልጃና አስታራቂነት ገንኖ ላለበት ቤት አዲስና ያልተለመደ አስደናቂ ትምህርት ነው። አዎን፤ ክርስቶስ እስከ ዕለተ ምጽዓት ለሚታመኑበት ኹሉ አስታራቂና ሊቀ ካህናታቸው ነው!
እጅግ በሚያሳዝን መንገድ፣ “ጳጳስ” ሕዝቅኤል የተባሉ አባት ደግሞ ሌላ የኑ-ፋ-ቄ ትምህርት በአደባባይ[በአዲስ አበባ ምስካየ ኅዙናን መድኃኒ ዓለም ቤተ ክርስቲያን] ያስተምራሉ፤ ሳያፍሩ በድፍረት ተመልተው እንዲህ ይላሉ፣
“ … በቀራንዮ የፈሰሰው ደም የማን ነው? እንዴ! ሥጋን የለበሰ ከእሷ ነው፣ የእሷ ደም ፈሷል፣ የእሷን ሥጋ አይደለ እንዴ የተዋሐደው? እምንበላው የምንጠጣው ሥጋ የማን ነው? የእሷ ነው። … ”
ሰው ምንም ያህል ማርያምን ቢያፈቅርና ቢያመልክ በዚህ ልክ ሊሳሳት ይችላል ብዬ አላስብም። ስህተቱ ደግሞ በጳጳስ ደረጃ ሲኾን እጅግ ግር ያሰኛል። የራሱ የክርስቶስን ሥጋ የማርያም ነው ብሎ መሞገት ምን የሚሉት እንግዳ ትምህርት ነው? የኢየሱስን ሥጋ ለሌላ መስጠትና ባለቤቱን ለሌላ አሳልፎ መስጠት እጅግ አሳዛኝ ስ-ህ-ተ-ት ነው። ይህ የማያውቁ ጳጳሳት በመንበረ ጵጵስና መቀመጣቸው በራሱ ያሳፍራል። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ፈሰሰው ደምና ስለተሠዋው ሥጋ ሲናገር፣
“በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ… ” (ሐ.ሥ. 20፥28)
“…እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ አቆመው …” (ሮሜ 3፥25)
“እንግዲህ አሁን በደሙ ከጸደቅን በእርሱ ከቍጣው እንድናለን።” (ሮሜ 5፥9)
“የዘላለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ እንጂ በፍየሎችና በጥጆች ደም አይደለም።” (ዕብ. 9፥12)
“ … ኢየሱስ ደግሞ በገዛ ደሙ ሕዝቡን እንዲቀድስ ከበር ውጭ መከራን ተቀበለ።” (ዕብ. 13፥12)
“ … ለወደደን ከኃጢአታችንም በደሙ ላጠበን፥…” (ራእ. 1፥5)
“… በፊት የተለያችሁትን ክፉ ሥራችሁንም በማድረግ በአሳባችሁ ጠላቶች የነበራችሁትን አሁን በሥጋው ሰውነት በሞቱ በኩል አስታረቃችሁ።” (ቈላ. 1፥21-22)
“ …በመረቀልን በአዲስና በሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት ስላለን፥ …” (ዕብ. 10፥19-20)
“እርሱ[ክርስቶስ] ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ” (1ጴጥ. 2፥24)
እንግዲህ ክርስቶስ ያዳነንና የዋጀን በገዛ ደሙ፤ በራሱ ሥጋው ብቻ ነው፤ ከእኛ የነሣው ሥጋ የራሱ ገንዘቡ እንጂ የማርያም ነው አንልም፤ ቅዱሳት መጻሕፍት ይህን በግልጥ ይመሰክራሉ። ርሱ ፍጹም ሰው፤ ደግሞም ፍጹም አምላክ ነውና። ኦርቶዶክሳዊት ኹለት ተቃራኒ ጳጳሳትን በአንድ መንበረ ጵጵስና የማታስተናግድበት ዘመን መምጣቱ ወይም እውነተኞቹ ጳጳሳት በመ-ና-ፍ-ቃ-ን ጳጳሳት መባረራቸው አይቀሬ ይመስላል!
“ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በማይጠፋ ፍቅር ለሚወድዱ ሁሉ ጸጋ ይሁን።” (ኤፌ. 6:24) አሜን።
My blog link -
https://abenezerteklu.blogspot.com/2025/05/blog-post_8.html