ለጠ/ሚው መልእክት የህወሓት ምላሽ
የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስቴር ለትግራይ ክልል ሕዝብ በተለይም ለትግራይ ልሂቅ በማለት በትግርኛ ላሰራጩት መልእክት ምላሽ የሰጡት የህወሓት ከፍተኛ አመራር ወይዘሮ ፈትለወርቅ ገብረ እግዚአብሔር፥ የጠቅላይ ሚኒስቴሩ መልአክም በጥሩ ቃላት የቀረበ እንኳን ቢሆንም የትግራይን ሕዝብ ለማስፈራራት ያለመ ሲሉ ኮንነውታል።
ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አሕመድ በጽሑፍ መልእክታቸው ባለፉት 100 አመታት ከማዕከላዊ መንግሥት ጋር በተለያዩ ምክንያቶች ባጋጠሙ ቅሬታዎች፥ የትግራይ መሬት የጦርነት ምድር ሆኖ ቆይቷል ያሉ ሲሆን የህወሓት ጽሕፈት ቤት ሐላፊ የሆኑት ወይዘሮ ፈትለወርቅ ገብረእግዚአብሔር ግን በምላሻቸው፥ የትግራይ ሕዝብ ባለፉት መቶ ዓመታት ወራሪዎችን መክቷል፣ ጨቋኞችን ታግሏል እንጂ የሆነ አካል ላይ ጦርነት የከፈተበት አጋጣሚ የለም ሲሉ ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ የህወሓት ከፍተኛ አመራር ወይዘሮ ፈትለወርቅ፥ ያሉንን ጥያቄዎች እናቀርባለን ይህ ደግሞ ጦርነት መሻት አይደለም ብለዋል።
ወይዘሮ ፈትለወርቅ «ልዝብ የሚመስል ግን ደግሞ በውስጡ ተጠንቀቁ የሚል ማስፈራርያ ያለው ስለሆነ ወደጦርነት ያስገባል የሚል ስጋት በሕዝብ ዘንድ ፈጥሯል። ይህ ሆን ተብሎ የተደረገ ነው። ሕዝብ እንዲሸበር እየተደረገ ነው። ይህ በትግራይ ሕዝብ ላይ እየደረሰ ያለው በደል አካል አድርገን ነው የምንወስደው። የትግራይ ሕዝብ ይህ አይገባውም፣ ማስፈራራት አይገባውም። በመላው ትግራይ ያለው ሁኔታ ለጦርነት የሚጋብዝ ነገር የለም። መብታችን ይከበር፣ ማንነታችን ይከበር፣ በፕሪቶሪያ ውል መሠረት ሁሉ ነገር ይፈፀም ማለት ግን ጥያቄያችን ነው። ይህ ግን ወደ ጦርነት የሚያስገባ አይደለም» ብለዋል።
ከዚህ በተጨማሪ 50 ዓመት የምስረታ በዓሉን ሊያከብር ቀናት የቀሩት ሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ፥ በታሪክ የከፋ የተባለ ክፍፍል ላይ ይገኛል። የምስረታ በዓሉን ለማክበር ሁለቱ የህወሓት ቡድኖች የየራሳቸውን የተለያዩ ዝግጅቶች እያደረጉ ሲሆን፥ የየራሳቸውን የተለያዩ መፈክሮችም ይዘው ቀርበዋል። በትናንትናው ዕለት በዶክተር ደብረፅዮን የሚመራው የህወሓት ክንፍ በመጪው የካቲት 11 የሚከበረው የህወሓት ምስረታ 50ኛ ዓመት ለማክበር ዝግጅት ላይ መሆኑን ሲገልጽ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደርን የሚመሩት ፕሬዝደንት ጌታቸው ረዳ፥ የካቲት 11ን ለማክበር ኮሚቴዎች ተቋቁመዋል ብለዋል። በዚሁ መድረክ ስለወቅታዊ ሁኔታ የተናገሩት ፕሬዝዳንት ጌታቸው ረዳ፥ የትግራይ ፖለቲካዊ ሁኔታ በከፋ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ እና በሆነ ቅፅበት ግጭት ሊነሳ ይችላል ሲሉ ተደምጠዋል።
አቶ ጌታቸው «በመጥፎ ሁኔታ ውስጥ ነን ያለነው። በሆነች ደቂቃ በአንድ ሰው ስህተት ወደ ግጭት የምንገባበት ዕድል የሰፋ ነው። እየሄድን ያለነው ወደ ጥፋት ስለሆነ ቢያንስ ይህ በዓል ቆም የምንልበት እናድርገው ነው እያልን ያለነው» ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አሕመድ ባለፈው ሰኞ ለትግራይ ብለው አስተላልፈውት በነበረ መልእክት የትግራን ልሂቃን የውስጥ ችግራቸው እንዲፈቱ እና ቀጥሎም ከፌደራል መንግሥቱ ጋር እንዲነጋገሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ዶቼ ቬሌ
@Yenetube @Fikerassefa