ሄኖክ ኃይሌ፣ “ሰባኪ” ከኾነ ከመጽሐፍ ለምን አይጠቅስም?
ሄኖክ ሃይሌ፣ ለጳጳሱ አባ ገብርኤል በመለሰው መልስ ውስጥ እንዲህ የሚል ንግግር አለው፣
“ያስተማሩት የታሰበበት ክህደት ነውና … ሙሴ ቤዛ በተባለበት መጽሐፍ ቅዱስ እያመኑ ድንግል ማርያም ቤዛ አትባልም ላሉት ጳጳስ ቅዱስ ሲኖዶስ ቤዛ ሲሆናቸው ማየት አንፈልግም። ጠንከር ያለ ቀኖናዊ እርምጃ እንጠብቃለን።”
ነገሩን ግልጽ ለማድረግ፣ ሙሴ “ቤዛ” የተባለበትን ዐሳብ፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ ማየቱ እጅግ መልካም ነው። በታላቁ መጽሐፍ ውስጥ በእስጢፋኖስ አንደበት፣
“ … ሙሴን በቍጥቋጦው በታየው በመልአኩ እጅ እግዚአብሔር ሹምና ቤዛ አድርጎ ላከው።” (ሐ.ሥ. 7፥35)
ተብሎ ተጠቅሶአል። ስለ ሙሴ ጥቂት እንናገር፣ ሙሴ በግብፃዊቷ ልዕልት ቤት ያደገ ዕብራዊ ሰው ነበር (ዘጸአት 2፥1-10)። ለእኛ ባልተገለጠና የመጀመሪያው ዘገባ በማይገልጠው መንገድ፣ ሙሴ ሕዝቡን ከባርነት ነፃ ለማውጣት እግዚአብሔር እንደ ላከው ያውቅ ነበር (ሐ.ሥ. 7፥25)። በመጀመሪያ ሙከራው ሙሴ ዕብራዊውን እየደበደበ ያለውን ግብፃዊ ሰው ገደለ። በማግስቱ፣ እስራኤላውያን ረድኤቱንና ሥልጣኑን አለመቀበል ብቻ ሳይሆን ግድያውን እንደሚያውቁ ተገነዘበ። ፈርዖን ሳይገድለው ሙሴ ወደ ምድያም ምድር ሸሸ (ዘጸ. 2፥11–15)።
በምድያም፣ ሙሴ የካህን ሴት ልጅ አግብቶ የአማቱን በጎች ይጠብቅ ጀመር። እሱ ከደረሰ ከአርባ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር በቁጥቋጥ ተገለጠለት (ዘጸ. 3፥4)፤ እስጢፋኖስ ለሙሴ የተገለጠው መልአክ እንደ ኾነ ተናገረ፣ በብሉይ ኪዳን ደግሞ “የእግዚአብሔርን መልአክ” ተብሎ በብዙ ስፍራ የተጠቀሰው፣ በኋለኛው ዘመን ሥጋ የለበሰውን ክርስቶስን እንደሚያመለክት እሙን ነው። እስጢፋኖስ ያንን እዚህ ላይ ቢያብራራ ጠቃሚ ይሆናል፤ ግን አላደረገም።
ሙሴ ወደ ምድያም ከመሸሽ በፊት፣ አንድ እስራኤላዊ “አንተን በእኛ ላይ አለቃና ፈራጅ ያደረገህ ማን ነው?” ሲል ጠየቀው። (ዘጸ. 2፥14) “አለቃ” የሚለው ቃል፣ የንጉሥ ፈርዖን ባለሥልጣንን ወይም ተወካይን ያመለክታል። “ፈራጅ - ዳኛ” ደግሞ፣ ሕጋዊ ውሳኔ ለመስጠት ሥልጣን ያለው ሰው መኾኑን። እስጢፋኖስ፣ ሙሴ እውነተኛ ገዥና የአምላክ ወኪል እንደ ነበረ ገልጾአል። ከዚህም በላይ አምላክ እስራኤላውያንን አዳኝ እንዲኾን መረጠው። ተከራካሪዎቹ እስራኤላውያን፣ ሙሴን የፈርዖን ፍርድ ቤት ተወካይ አድርጎ የሰጠውን አቋም በመሳለቅና በመቃወም አልተቀበሉትም፤ ሙሴ እነርሱን ለማዳን ከእግዚአብሔር እንደ ተላከ አላስተዋሉምና።
በርግጥ ሙሴ ለእስራኤል ዘሥጋ ታዳጊና ቤዛ ኾኖ ተልኮ ነበር፤ ዋና ዓላመውም፤ ከፈርዖን ቤት፤ ከባርነት ቀንበር ነጻ ለማውጣት ነውና። ሙሴ ራሱ ግን ፍጹም ቤዛና አዳኝ እንዳልኾነና ከርሱ የሚበልጥ ሌላ እንዳለ ሲናገር እንዲህ አለ፤ “ይህ ሰው[ሙሴ] ለእስራኤል ልጆች፦ እግዚአብሔር ከወንድሞቻችሁ እንደ እኔ ያለ ነቢይ ያስነሣላችኋል፤ እርሱን ስሙት ያላቸው ሙሴ ነው።” (ሐ.ሥ. 7፥37) አስተውሉ፤ እስጢፋኖስ ይህን እየተናገረ ያለው፣ አሻግሮ ስለ ኢየሱስ እንጂ ስለ ሙሴ እንዳልነበረ በመደምደሚያው እንዲህ አለ፣ “… በመላእክት ሥርዓት ሕግን ተቀብላችሁ ያልጠበቃችሁት እናንተም አሁን እርሱን[ክርስቶስን] አሳልፋችሁ ሰጣችሁት ገደላችሁትም።” (ሐ.ሥ. 7፥52-53) ይላል።
ሙሴ ምንም ለእስራኤል ዘሥጋ “ቤዛ” ቢባልም፣ በጥላለነት ያገለገለው እስራኤል ዘነፍስን በቤዝወቱ ነጻ ላወጣው ለኢየሱስ ነው። በሌላ ንግግር ሙሴ ያገለገለው፣ የኢየሱስን አገልግሎት በጥላነት ነው። አካሉ ሲመጣ ደግሞ ጥላው በራሱ ጊዜ ስፍራውን ለአካሉ ይለቅቃል፤ ኢየሱስ ባለበት ሙሴ ደግሞ ዘወትር ባሪያና አገልጋይ ብቻ ነው።
“ዲያቆን” ሄኖክ ግን፣ የትክክለኛውን ዲያቆን እስጢፋኖስን ንግግር እንኳ አንብ ሳያስረዳ፣ ማርያምን ከክርስቶስ በላይ እንደሚመለከታት፣ “እመቤታችን ማማለድ አይደለም አፍርሳን መሥራት ትችላለች” በሚለው ንግግሩ ይታወቃል። ለዚህ ንግግሩም ከዓመታት በፊት በጡመራ መድረኬ መልስ ሰጥቼበታለሁ። ከዚህ በዘለለ፣ በሰሞኑ በአባ ገብርኤል “ማርያም ለኀጢአታችን ቤዛ አይደለችም” በሚለው ትምህርት ዙሪያ፣ ብዙ ስድብና ዘለፋ ካቀረበ በኋላ በመቋጫው ከላይ የጠቀስሁትን ተናግሮአል።
“ዲያቆን” ሄኖክ፣ ያስተማሩት ክህደት ነው ሲል፣ ምኑ ክህደት እንደ ኾነ አይናገርም፤ የኢየሱስ ቤዛ መባልንና በትክክል መኾንን አንድም ቦታ ሳይናገር[ይህ ለአንድ ሰባኪ የሞት ያህል መራራ ነው!]፣ የሙሴን “ቤዛ” መባል ግን ዋቢ ይጠቅሳል፤ ሙሴ “ቤዛ” ቢባል፣ መሲሑን ተክቶ ለእስራኤል ደሙን አፈሰሰን? ከኀጢአት ባርነት ሕዝቡን ነጻ አወጣን? ሕዝብን ከሰው አገዛዝ ባርነት ነጻ አውጥቶ መምራቱ “ቤዛ” ቢያስብለው፣ እንደ ኢየሱስ “ቤዛችን ሙሴ ሆይ፤ ምትክ ኾነህ ሞተኽልናልና” ተብሎ ሊጠራ ነውን?
ጳጳስን “ሰንበት ተማሪ” ብሎ መሳደብ፣ አይከብድ ይኾናል፤ እንዲህ ያለ ከሰንበት ተማሪ ያነሰ ዕውቀት ይዞ “በስመ ደጋፊ ብዛትና በዕብጠት” መናገር ግን “እባብ እያስተፉ ዘንዶ የመዋጥ ያህል” ይቀፍፋል። በርግጥ እነ ዘበነ ለማና ምሕረተ አብ አሰፋ በኢየሱስና በመጽሐፍ ቅዱስ “ሲሸቅጡ”፣ ምንም ሊባሉ አይችሉም፤ ማርያምን እስካልነኩ ድረስ የሚናገራቸው አይኖርም!
የኢየሱስ ቤዝወትና አስታራቂነት ሲነገር ግን፣ ሄኖክና ባልንጀሮቹ ይንጨረጨራሉ፤ እርር ኩምትር ይላሉ፤ ምክንያቱን በትክክል ባልረዳም፣ ከጤናማ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪ የሚወጣ ባህርይ እንዳልኾነ የተገለጠ ነው። ስለ ኢየሱስ አትጻፉ፤ ማርያምንም አምልኩ፣ ግን እንዴት ስለ ኢየሱስ ሲነገር እንዲህ ይከፋችኋል?! ጌታ ይገስጻችሁ!
“ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በማይጠፋ ፍቅር ለሚወድዱ ሁሉ ጸጋ ይሁን።” (ኤፌ. 6:24) አሜን።
የጡመራ መድረክ አድራሻ -
https://abenezerteklu.blogspot.com/2025/04/blog-post_24.html