Фильтр публикаций


የአባ ገብርኤል ጉዳይ የሃይማኖትና የጽድቅ ቅንአት እንዳልኾነ እኒህ ማሳያዎች ናቸው፦

- "እንኳን ማማለድ ማርያም አፍርሳ መሥራት ትችላለች" ብሎ ሄኖክ ኃይሌ ሲናገር ማንም ትንፍሽ አላለም፣
- አንዱ ጳጳስ፦ "ድንግል ማርያም ባትኖር እግዚአብሔርም ክርስቶስም የሉም"  ብለው በአደባባይ ተናግረው አንድም የኦርቶዶክስ ሊቅም ኾነ አክቲቪስት ቲክቶዶክሶች አቧራ አላቦነኑም! ለምን?
- አንዱ የነገረ መለኮት ምሩቅ ነኝ ባይ፣ "ያለ ድንግል ማርያም አማላጅነት ዓለም አይድንም" ብሎ ከኦርቶዶክስ ነገረ መለኮት ኮሌጅ ተመርቆ ሲወጣ፣ ማን መምህር፣ የቱ ኮሌጅ፣ ማንኛው ሲኖዶስ፣ የትኛው ሰንበት ተማሪና ሊቅ ስለ ክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ በአደባባይ መነቀፍ ቆረቆረው፤ ከነከነው?!
- ዘበነ ለማ፣ "ሰይጣን ከክርስቶስ ይልቅ ማርያምን ይፈራታል" ሲል እንዴት፤ በየት በኩል ማንም አላለም!
- በድጋሚ ዘበነ ለማ፣ "የዶሮ 12ቱ ብልቶች የኢየሱስ ደቀመዛሙርት ምሳሌ ነው" ብሎ ሲዘብት ማን ምን ተናገረ?!

- ምሕረተ አብ አሰፋ "ኦርቶዶክስ እንጂ ክርስቲያን አይደለንም" ብሎ ክርስትናን ሲያጥላላ፣ ማን ነበር "ኦርቶዶክስ ትምህርት እንጂ "ተቋም" አይደለም" ያለ?!
...
ብዙ ክርስቶስንና መጽሐፍ ቅዱስን የሚያዋርዱ ትምህርቶች በአደባባይ ሲሰጡ ማንም ምንም አላለም። እኒህንና ሌሎችንም አያሌ የኑ-ፋ-ቄ ትምህርቶች የሰጡ አካላት ዛሬም በኦርቶዶክስ "ዐውደ ምሕረቶች" ያለ ጠያቂ አሉ። ግና የአባ ገብርኤል ነገር መግነኗ ብዙ ጥያቄ እንድጠይቅና፣ "ኢየሱስን ማንኳሰስ ችግር የለውም፤ ማርያምና ታቦቱ እስካልተነካ" ድረስ ብለን እንድንናገር ያስደፍረናል። የሲኖዶሱን ውሳኔ እየጠበቅን፣ ኦርቶዶክስ ሆይ፤ መንፈስ ቅዱስ መመለስን እንዲሰጥሽ በብዙ እንመኛለን ማለትን አንተውም።

284 0 2 14 21

የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ለድርድርም፤ ለክርክርም አይቀርብም።

(አቡነ ገብርኤል በድጋሚ ከተናገሩት)

በድጋሚ ይህን በመናገራቸው ደስ ብሎኛል። ኹሉም ኦርቶዶክሳውያን ባይኾኑም፣ ካራ ኦርቶዶክሳውያን ግን የክርስቶስን የቤዝወትና የዕርቅ መካከለኝነት የሚጠሉትንና ነገረ ማርያምን እንዲህ ያፈቀሩበት መንገድ እንዲኹ ይቀጥላል ብዬ አላምንም። አንድ ቀን ወንጌል ጥቂት በማይባሉ ኦርቶዶክሳውያን ልብ ላይ ደምቆ ይታያል፤ የእግዚአብሔር መንግሥት ትናጠቃለች፤ ትሰፋለችም።

የእግዚአብሔር መንግሥት እውነትና የመስቀሉ ቤዝወት፣ በመግለጫም በሲኖዶስ ድምጽም አይታጎልም!


የቴሌግራም አድራሻ - https://t.me/ebenezertek


ሄኖክ ኃይሌ፣ “ሰባኪ” ከኾነ ከመጽሐፍ ለምን አይጠቅስም?


ሄኖክ ሃይሌ፣ ለጳጳሱ አባ ገብርኤል በመለሰው መልስ ውስጥ እንዲህ የሚል ንግግር አለው፣
“ያስተማሩት የታሰበበት ክህደት ነውና … ሙሴ ቤዛ በተባለበት መጽሐፍ ቅዱስ እያመኑ ድንግል ማርያም ቤዛ አትባልም ላሉት ጳጳስ ቅዱስ ሲኖዶስ ቤዛ ሲሆናቸው ማየት አንፈልግም። ጠንከር ያለ ቀኖናዊ እርምጃ እንጠብቃለን።”

ነገሩን ግልጽ ለማድረግ፣ ሙሴ “ቤዛ” የተባለበትን ዐሳብ፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ ማየቱ እጅግ መልካም ነው። በታላቁ መጽሐፍ ውስጥ በእስጢፋኖስ አንደበት፣

“ … ሙሴን በቍጥቋጦው በታየው በመልአኩ እጅ እግዚአብሔር ሹምና ቤዛ አድርጎ ላከው።” (ሐ.ሥ. 7፥35)

ተብሎ ተጠቅሶአል። ስለ ሙሴ ጥቂት እንናገር፣ ሙሴ በግብፃዊቷ ልዕልት ቤት ያደገ ዕብራዊ ሰው ነበር (ዘጸአት 2፥1-10)። ለእኛ ባልተገለጠና የመጀመሪያው ዘገባ በማይገልጠው መንገድ፣ ሙሴ ሕዝቡን ከባርነት ነፃ ለማውጣት እግዚአብሔር እንደ ላከው ያውቅ ነበር (ሐ.ሥ. 7፥25)። በመጀመሪያ ሙከራው ሙሴ ዕብራዊውን እየደበደበ ያለውን ግብፃዊ ሰው ገደለ። በማግስቱ፣ እስራኤላውያን ረድኤቱንና ሥልጣኑን አለመቀበል ብቻ ሳይሆን ግድያውን እንደሚያውቁ ተገነዘበ። ፈርዖን ሳይገድለው ሙሴ ወደ ምድያም ምድር ሸሸ (ዘጸ. 2፥11–15)።


በምድያም፣ ሙሴ የካህን ሴት ልጅ አግብቶ የአማቱን በጎች ይጠብቅ ጀመር። እሱ ከደረሰ ከአርባ ዓመታት በኋላ እግዚአብሔር በቁጥቋጥ ተገለጠለት (ዘጸ. 3፥4)፤ እስጢፋኖስ ለሙሴ የተገለጠው መልአክ እንደ ኾነ ተናገረ፣ በብሉይ ኪዳን ደግሞ “የእግዚአብሔርን መልአክ” ተብሎ በብዙ ስፍራ የተጠቀሰው፣ በኋለኛው ዘመን ሥጋ የለበሰውን ክርስቶስን እንደሚያመለክት እሙን ነው። እስጢፋኖስ ያንን እዚህ ላይ ቢያብራራ ጠቃሚ ይሆናል፤ ግን አላደረገም።

ሙሴ ወደ ምድያም ከመሸሽ በፊት፣ አንድ እስራኤላዊ “አንተን በእኛ ላይ አለቃና ፈራጅ ያደረገህ ማን ነው?” ሲል ጠየቀው። (ዘጸ. 2፥14) “አለቃ” የሚለው ቃል፣ የንጉሥ ፈርዖን ባለሥልጣንን ወይም ተወካይን ያመለክታል። “ፈራጅ - ዳኛ” ደግሞ፣ ሕጋዊ ውሳኔ ለመስጠት ሥልጣን ያለው ሰው መኾኑን። እስጢፋኖስ፣ ሙሴ እውነተኛ ገዥና የአምላክ ወኪል እንደ ነበረ ገልጾአል። ከዚህም በላይ አምላክ እስራኤላውያንን አዳኝ እንዲኾን መረጠው። ተከራካሪዎቹ እስራኤላውያን፣ ሙሴን የፈርዖን ፍርድ ቤት ተወካይ አድርጎ የሰጠውን አቋም በመሳለቅና በመቃወም አልተቀበሉትም፤ ሙሴ እነርሱን ለማዳን ከእግዚአብሔር እንደ ተላከ አላስተዋሉምና።

በርግጥ ሙሴ ለእስራኤል ዘሥጋ ታዳጊና ቤዛ ኾኖ ተልኮ ነበር፤ ዋና ዓላመውም፤ ከፈርዖን ቤት፤ ከባርነት ቀንበር ነጻ ለማውጣት ነውና። ሙሴ ራሱ ግን ፍጹም ቤዛና አዳኝ እንዳልኾነና ከርሱ የሚበልጥ ሌላ እንዳለ ሲናገር እንዲህ አለ፤ “ይህ ሰው[ሙሴ] ለእስራኤል ልጆች፦ እግዚአብሔር ከወንድሞቻችሁ እንደ እኔ ያለ ነቢይ ያስነሣላችኋል፤ እርሱን ስሙት ያላቸው ሙሴ ነው።” (ሐ.ሥ. 7፥37) አስተውሉ፤ እስጢፋኖስ ይህን እየተናገረ ያለው፣ አሻግሮ ስለ ኢየሱስ እንጂ ስለ ሙሴ እንዳልነበረ በመደምደሚያው እንዲህ አለ፣ “… በመላእክት ሥርዓት ሕግን ተቀብላችሁ ያልጠበቃችሁት እናንተም አሁን እርሱን[ክርስቶስን] አሳልፋችሁ ሰጣችሁት ገደላችሁትም።” (ሐ.ሥ. 7፥52-53) ይላል።
ሙሴ ምንም ለእስራኤል ዘሥጋ “ቤዛ” ቢባልም፣ በጥላለነት ያገለገለው እስራኤል ዘነፍስን በቤዝወቱ ነጻ ላወጣው ለኢየሱስ ነው። በሌላ ንግግር ሙሴ ያገለገለው፣ የኢየሱስን አገልግሎት በጥላነት ነው። አካሉ ሲመጣ ደግሞ ጥላው በራሱ ጊዜ ስፍራውን ለአካሉ ይለቅቃል፤ ኢየሱስ ባለበት ሙሴ ደግሞ ዘወትር ባሪያና አገልጋይ ብቻ ነው።
“ዲያቆን” ሄኖክ ግን፣ የትክክለኛውን ዲያቆን እስጢፋኖስን ንግግር እንኳ አንብ ሳያስረዳ፣ ማርያምን ከክርስቶስ በላይ እንደሚመለከታት፣ “እመቤታችን ማማለድ አይደለም አፍርሳን መሥራት ትችላለች” በሚለው ንግግሩ ይታወቃል። ለዚህ ንግግሩም ከዓመታት በፊት በጡመራ መድረኬ መልስ ሰጥቼበታለሁ። ከዚህ በዘለለ፣ በሰሞኑ በአባ ገብርኤል “ማርያም ለኀጢአታችን ቤዛ አይደለችም” በሚለው ትምህርት ዙሪያ፣ ብዙ ስድብና ዘለፋ ካቀረበ በኋላ በመቋጫው ከላይ የጠቀስሁትን ተናግሮአል።
“ዲያቆን” ሄኖክ፣ ያስተማሩት ክህደት ነው ሲል፣ ምኑ ክህደት እንደ ኾነ አይናገርም፤ የኢየሱስ ቤዛ መባልንና በትክክል መኾንን አንድም ቦታ ሳይናገር[ይህ ለአንድ ሰባኪ የሞት ያህል መራራ ነው!]፣ የሙሴን “ቤዛ” መባል ግን ዋቢ ይጠቅሳል፤ ሙሴ “ቤዛ” ቢባል፣ መሲሑን ተክቶ ለእስራኤል ደሙን አፈሰሰን? ከኀጢአት ባርነት ሕዝቡን ነጻ አወጣን? ሕዝብን ከሰው አገዛዝ ባርነት ነጻ አውጥቶ መምራቱ “ቤዛ” ቢያስብለው፣ እንደ ኢየሱስ “ቤዛችን ሙሴ ሆይ፤ ምትክ ኾነህ ሞተኽልናልና” ተብሎ ሊጠራ ነውን?

ጳጳስን “ሰንበት ተማሪ” ብሎ መሳደብ፣ አይከብድ ይኾናል፤ እንዲህ ያለ ከሰንበት ተማሪ ያነሰ ዕውቀት ይዞ “በስመ ደጋፊ ብዛትና በዕብጠት” መናገር ግን “እባብ እያስተፉ ዘንዶ የመዋጥ ያህል” ይቀፍፋል። በርግጥ እነ ዘበነ ለማና ምሕረተ አብ አሰፋ በኢየሱስና በመጽሐፍ ቅዱስ “ሲሸቅጡ”፣ ምንም ሊባሉ አይችሉም፤ ማርያምን እስካልነኩ ድረስ የሚናገራቸው አይኖርም!

የኢየሱስ ቤዝወትና አስታራቂነት ሲነገር ግን፣ ሄኖክና ባልንጀሮቹ ይንጨረጨራሉ፤ እርር ኩምትር ይላሉ፤ ምክንያቱን በትክክል ባልረዳም፣ ከጤናማ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪ የሚወጣ ባህርይ እንዳልኾነ የተገለጠ ነው። ስለ ኢየሱስ አትጻፉ፤ ማርያምንም አምልኩ፣ ግን እንዴት ስለ ኢየሱስ ሲነገር እንዲህ ይከፋችኋል?! ጌታ ይገስጻችሁ!

“ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በማይጠፋ ፍቅር ለሚወድዱ ሁሉ ጸጋ ይሁን።” (ኤፌ. 6:24) አሜን።




የጡመራ መድረክ አድራሻ - https://abenezerteklu.blogspot.com/2025/04/blog-post_24.html


"ሊቃውንቱና መምህራኑ" እንዴት ከመጽሐፉ ተራራቁ?!

ደግሜ ቤዛ ለሚለው ቃል የተሰጠ ፍቺ ልጥቀስ፣ " ... ቤዛ ማለት፦ “... ካሣ፣ የደም ቤዛ፣ አንዱ ሰው የሰውን ደም ስለሚያፈስሰው ለውጥ ወይም ዋጋን፣ ገንዘብን፣ ካሣን መስጠት ወይም መዋጀት ማለት ነው።” ይላል የከሣቴ ብርሐን መዝገበ ቃላት። (ከሣቴ ብርሃን መዝገበ ቃላት፤ 1951 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፤ ገፅ 532)። ጌታችን ኢየሱስ ስለ ቤዝወት በተናገረ ጊዜ እንዲህ አለ፣ "የሰው ልጅ ሊያገለግል ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉት አልመጣም።" (ማቴ. 20፥28፤ ማር. 10፥45) ብሎአል።

በመላው ቅዱሳት መጻሕፍት እንዲህ ብሎ የተናገረ ከኢየሱስ በቀር ሌላ የለም። ጌታችን ኢየሱስ እኛን ከኀጢአት ባርነት ነጻ ለማውጣት ምትክና ምስያ የሌለውን ሕይወቱን፣ ለእኛ ምትክ አድርጎ በቤዛነት አቅርቦአል። የወንጌላቱ ንባባት በግልጥ የሚያሳዩት፣ ክርስቶስ በእኛ ቦታ ቤዛና ዋጆ መኾኑን ነው። ቅዱስ ጳውሎስ፣ “ራሱንም ለሁሉ ቤዛ ሰጠ” (1ጢሞ. 2፥6) ብሎ ሲናገር፣ ጌታችን ኢየሱስ ለመላለሙ ቤዛ ኾኖ መሰጠቱን ያመለክታል።

በወንጌላትም ኾነ በመልዕክታት ውስጥ፣ ስለ ኀጢአት የተደረገ ቤዛነትን በተመለከተ ለኢየሱስ ብቻ እንጂ ለሌላ ለማንም አልተነገረም። ከኀጢአት ሰውን መቤዥ፣ ከኢየሱስ በቀር በሌላ መንገድ የሚቻል ቢኾን፣ ቅዱሳት መጻሕፍት ይህን እውነት ጨርሶ ባልሸሸጉ ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር የቤዝወትን መንገድ የሠራውና ያዘጋጀው በክርስቶስ መስቀል በኩል ብቻ ነው።

ዳሩ ግን በሰሞኑ የቤዝወት ትምህርት ዙሪያ፣ ኦርቶዶክሳውያን “ሊቃውንትና መምህራን”፣ ከላይ በቅዱሳት መጻሕፍት የተትረፈረፈውንና “ቤዛ ለመኾን አምላክነት ያሻል” የሚለውን የአገሬን ገበሬ አባባል፣ በመጽሐፍ ቅዱስ እውነት አጽንተው ይዘው ይገለጣሉ ብዬ እጅጉን ተስፋ አድርጌ ነበር። በተለይም የቤዝወት ትምህርት በቤተ ክርስቲያኒቱ የዳበረና በምልአት የሚነገር ትምህርት ነበር! የሰሞኑ የአባ ገብርኤል፣ “ማርያም ቤዛ አይደለችም” የሚለው ትምህርት ግን የቤተክርስቲያኒቱን "አዋቂዎች" ለትዝብት የጣለ እውነታ ኾኖአል።

ከዚህ የተረዳኹት ትልቅ እውነት፣ የክርስቶስ ቤዝወት በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ውስጥ ምን ያህል እንደ ተነቀፈና የማርያም ነገር ደግሞ ምን ያህል ከክርስቶስ በላይ እንደ ኾነ ነው። ይህ ብቻም አይደለም፣ አዋልድና ሌሎች ጽሑፎች ከቅዱሳት መጻሕፍት በላይ ምን ያህል ስፍራ እንደ ተሰጣቸውም ጭምር።

“ሐዋርያዊ መልስ” እንመልሳለን የሚሉት፣ ከጊዮርጊስ ዘጋስጫ ሌሎቹ ከያሬድ ሌሎቹም ከሌላ … ስለ ቤዝወት ለማስረዳት ይባትላሉ፤ ሌሎቹ ደግሞ አንድም የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ሳይጠቅሱ “በክርስቶስ ቤዝወት” ይሳለቃሉ። ፍካሬና ሐቲት፤ ቅኔና ግስ ደርጅቶበታል የተባለው ቤት፣ ስለ ቤዝወት እንዲህ እርጅና ሲጫጫነው ማየት ያሳዝናል። ከዚህ የሚከፋው ደግሞ ለዚኹ ጉዳይ ሲኖዶስ መቀመጡን ስንሰማ ነው። የኦርቶዶክስ ዐይን ማርያም እንጂ ክርስቶስ አለመኾንዋንም አስመስክረዋል። ኢየሱስ ግን እንዲህ ማለቱን ማስታወስ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ለሚያጠና ተማሪ ታላቅ ጥያቄም፤ መልስም ነው።

“ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል?” (ማቴ. 16፥26)

የካራ ኦርቶዶክሳውያኑን ተሳልቆና ቤዝወታዊ ነቀፋዎችን ከዚሁ ጋር ላያይዝ።

“ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በማይጠፋ ፍቅር ለሚወድዱ ሁሉ ጸጋ ይሁን።” (ኤፌ. 6:24) አሜን።

የብሎግ አድራሻ - http://abenezerteklu.blogspot.com/2025/04/blog-post_23.html


ከመስቀል ሌላ የመዳን አማራጭ አለ ብሎ ማሰብ ከእውነትና ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጭ መሆንን ያመለክታል። መስቀል አያስፈልገንም ከነ ኃጢአታችን ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ እንችላለን ማለት ዘበት ነው፤ ሐሰት ነው፤ ከእግዚአብሔር ተለይቶ መቅረት ካልሆነ በስተቀር የእግዚአብሔር የቅድስና መለኮታዊ ባህርዩ የሚያቃጥል እሳት ስለሆነ በክርስቶስ መስቀል በኩል ካልሆነ ማንም ሊድንና ወደ እግዚአብሔር ሊቀርብ አይችልም። … ደም ካልፈሰሰ የኀጢአት ሥርየት የለም (ዕብ. 9፥22)። የኀጢአት ሥርየት ከሌለ ሰው ከእግዚአብሔር አይታረቅም።

ማጠቃለያ

ከላይ በርዕስነት የመረጥኹትን “መዝሙር”፣ ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ ሳለኹ፣ “ከዘመሩ፣ ካስዘመሩ” መካከል እኔ ፊተኛው ነኝ። ባለማወቅ ለብዙዎች የመሳሳት ምክንያት ኾኜ ነበር፤ ዛሬ ላይ በአደባባይ ይህ “ዝማሬ” ስህተት እንደ ኾነ ከሚናገሩት መካከል አንዱ ነኝ። ከላይ ባስቀመጥነው ኦርቶዶክሳዊ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መዝነን የቤዛነት ትምህርት በትክክል ከተረዳን፣ “የማርያም ቤዛ አለመኾን” አይደንቀንም!

እናም ቤዛነት በክርስቶስ ብቻ የተከናወነ፣ የሰው ልጆች ኹሉ የዳኑበት ታላቅ፣ ዘላለማዊና ሕያው ሥራ ነው። ኀጢአተኞች ኹሉ በዚህ ጽድቅና ቤዛነት በመታመን ቢመጡ፣ “ከአባቶቻቸው ከወረሱት ከከንቱ ኑሮአቸው” (1ጴጥ. 1፥18-19)፣ ከኀጢአት ባርነት (ዮሐ. 8፥34)፣ ከጨለማ ሥልጣን (ቈላ. 1፥13)፣ ከሞት ፍርሃት (ዕብ. 2፥14) ነጻ በመውጣት ይድናሉ፤ ቤዛነቱ ለመላለሙ፤ መዳኑ ደግሞ ለሚያምኑበት ነውና። እንዲህ ያዳነን ጌታ ይባረክ፤ አሜን።

አባ ገብርኤል ምንም እንኳ አቀራረባቸውን በጥቂቱ ባልደግፈውም፤ በትምህርታቸው ግን ሙሉ ለሙሉ የምስማማ ነኝና፣ ትጋቱን ይጨምርልዎ ማለትን እወዳለሁ!

“ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በማይጠፋ ፍቅር ለሚወድዱ ሁሉ ጸጋ ይሁን።” (ኤፌ. 6:24) አሜን።

የቴሌግራም አድራሻ - https://t.me/ebenezertek
የጡመራ መድረክ አድራሻ - https://abenezerteklu.blogspot.com/2025/04/blog-post.html


“ነይ ነይ እምዬ ማርያም… ቤዛዊት ዓለም … ስህ-ተ-ት ነው”
(አባ ገብርኤል)

ከሰሞኑ በጣም ያከራከረ አንድ ርዕሰ ጉዳይ አለ፤ ነገረ ቤዝወት። “ቤዝወት” ታላቅ ነገረ መለኮታዊ ዕሳቤን በውስጡ የያዘ አስደናቂ ቃል ነው። በብዙዎች አንደበት የሚጠቀስ ቃል ቢኾንም፣ ቃሉ በትክክል ስፍራውንና ትርጕሙን አጊኝቷል ብዬ ግን አላምንም። ጥቂት ስለ ቃሉ እናውጋ እስኪ!

ቤዛነት ምንድር ነው?

“ቤዛ” የሚለው ቃል፣ ከግዕዝ ቋንቋ የተወሰደ ሲኾን፣ ሰውን ከባርነት ነጻ ለማውጣት የሚከፈል ዋጋ ወይም አንድን የተያዘን ወይም የተወሰደን ነገር ለማስመለስ የሚከፈል ዋጋን፣ ካሳን አመልካች ነው። ቤዛን የመክፈል ሥራ ደግሞ፣ ቤዛነት ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ ተጠቅሶአል። ቤዛነት፣ በበደለኛው ሰው የተወሰነውን ትክክለኛ ፍርድ ተመጣጣኙን ዋጋ ከፍሎ ነፃ ማውጣት ነው። ስለዚህም ቤዛ ማለት፣ “በቁሙ ዋጋ፣ ካሳ፣ ለውጥ፣ ምትክ፣ ዋቢ፣ ዋስ፣ መድን፣ ተያዥ … የመሰለው ኹሉ። [በደቂቅ አገባብ] ደግሞ፣ ስለ፣ ፈንታ፣ ምክንያት” በማለት አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ያብራሩታል። ከዚህ በመነሣት፦

1. በብሉይ ኪዳን ሰዎች እንሰሳትን ከመታረድ፣ በድኅነት ምክንያት የተሸጠውን ርስት መሬታቸውን ወይም ቤታቸውን ወይም በባርነት የተያዘባቸውን ሰው ለማስለቀቅ ተመጣጣኙን ዋጋ ይከፍሉና ይቤዡ ነበር፤ (ዘጸ. 13፥13፤ ዘሌ. 25፥24-34፤ ሩት 4፥4፤ ኤር. 32፥6)፣ ለዚህም በምሳሌነት፣ እግዚአብሔር ሕዝቡን ከግብጽና ከባቢሎን መቤዠቱን ይናገራል፤ (2ሳሙ. 7፥23፤ ነህ. 1፥10)፣

2. በአዲስ ኪዳን ግን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚያምኑበት ኹሉ፣ ቤዛና መድኀኒት ኾነላቸው፤ (ማር. 10፥45፤ ኤፌ. 1፥7፤ 1ጢሞ. 2፥5፤ ዕብ. 9፥12)፤ ይህንም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነትን ከሙታን ትንሣኤ በኋላ አረጋገጠው፤ (ሮሜ 8፥23፤ ኤፌ. 4፥30)።
ጌታችን ኢየሱስ ለምን ቤዛ ኾነን?

1. ሰው በደለኛ ስለ ኾነ፦ ሰው በደለኛና ኀጢአተኛ ስለ ኾነ፣ ለራሱ ቤዛ መኾን አይችልም። ቤዛ ለመኾን ከሚቤዥበት ነገር፣ ተቤዢው ነጻ መኾን መቻል አለበት። ከዚህ አንጻር በደል አልባ የኾነ ሰው፤ ለሰው እጅግ ያስፈልግ ነበር፤ ምክንያቱም ኹሉም የአዳም ዘር፣ ከኀጢአትና ከበደል በታች ተከስሶ ተዘግቶበት ነበር፤ (ሮሜ 3፥9)። ስለዚህም ክርስቶስ ኢየሱስ፣ “ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” (ቈላ. 1፥13-14)።

2. በኀጢአት ምክንያት የሕግ እርግማን ያገኘንን፣ እርሱ የሞትን መውጊያ ሰብሮ፣ የሲዖልን ኃይል ድል ነሥቶ ተቤዠን፤ ዋጀን፤ ዐርነትን ሰጠን። የሕጉንም እርግማን ከእኛ ላይ አስወገደው፤ (1ቆሮ. 15፥56፤ ገላ. 3፥10)። ስለዚህም ከእርሱ ተነሣ ቅዱሳንና አለነውር ኾንን።
ክርስቶስ አንዳች በደል ስለሌለበት ስለ በደላችን ብቸኛ ቤዛ ኾነልን። ራሱም ሲናገር፣ “የሰው ልጅ ሊያገለግል ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ” እንደ መጣ ተናገረ፤ (ማቴ. 20፥28፤ ማር. 10፥45)፤ እኛም በክርስቶስ በኩል በኾነው ቤዛነት፣ የበደላችንን ስርየት አገኘን፤ ከሕግ እርግማንም ዋጀን፤ (ሮሜ 3፥24፤ ኤፌ. 1፥7፤ ገላ. 3፥13)።

3. ከዚህም የተነሳ ለዋጀን ጌታ ብቻ እንኖርለታለን፤ ቤዛና ዋጆ በዐሳብ ደረጃ ተዛማጅ ትርጉም አላቸው፤ በቤዛነት ክርስቶስ የራሱ ገንዘቦች እንዳደረገን መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ በማለት ይመሰክራል፤ “በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ።”፣ “በዋጋ ተገዝታችኋል፤ የሰው ባሪያዎች አትሁኑ።” (1ቆሮ. 6፥16፤ 7፥23)።

የዳንነውና ክርስቲያን የተባልነው ወይም የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን የተጠራነው፣ ክርስቶስ ያለ አንዳች በደልና ነውር ቤዛ ኾኖ በደሙ፣ የኀጢአታችንን ዕዳ ኹሉ ስለ ከፈለልን ነው። በዋጋ የገዛን እርሱ ነውና የእርሱ ብቻ ነን! ወደፊት የምንኖረውና የምንኖርለት በክርስቶስ ለክርስቶስ ብቻ ነው። ዐርነት የወጣንበት እውነት (ዮሐ. 8፥32)፣ ጸድቀን ጻድቃን የተባልንበት ጽድቃችን ክርስቶስ ኢየሱስ ብቻ ነው፤ (1ቆሮ. 1፥30-31)።

ቤዛነትን ፍጹም በኾነ መንገድ፣ አንድን ነገር የራስ ገንዘብ ማድረግ ነው። ልክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደሙ ዋጅቶ፣ ገዝቶ፣ ተቤዥቶ የራሱ ገንዘቦችና ውድ ዕቃዎቹ እንዳደረገን እንዲህ ነው። የፈጠረንና፣ “ሁሉን በሥልጣኑ ቃል የደገፈው ክርስቶስ ኢየሱስ፥ ኃጢአታችንን ደግሞ በራሱ አንጽቶአልና” (ዕብ. 1፥3)።

ቤዛነት፣ አምላክነትን ብቻ ያይደለ፣ ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው መኾንን ይሻል። በፍጹም አምላክነቱ ዓለማትን የደገፈው ያው ጌታ፣ ከቅድስት ድንግል ተወልዶ በፍጹም ሰውነቱ አድኖናል፤ ለኀጢአታችን በደሙ ስርየት ኾኖአል፤ “መንግሥትም ለአምላኩና ለአባቱም ካህናት እንድንሆን አድርጎአልና፥ ለእርሱ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ክብርና ኃይል ይሁን፤ አሜን።” (ራእ. 1፥6)።

ቅድስት ማርያም፣ ኀጢአትን በተመለከተ ለሰው ልጆች ኹሉ ቤዛ መባል ወይም መኾን አትችልም፤ ምክንያቱም ቅድስት ማርያም ቤዛዋን ወለደች እንጂ፣ በራስዋ ቤዛ ለመኾን ፍጹም አምላክነትና ፍጹም ሰውነት ያሻታል። ቅድስት ማርያም እንዲህ ናት የሚሉ፣ ቅድስት ማርያም ለነርሱ አራተኛ “ሥላሴ” ናት ማለት ነው። ነገር ግን ለኀጢአታችን ቤዛችን ናት ማለትም፤ “እርሷ ፍጹም ሰው፤ ፍጹም አምላክ ናት” የማለት ያህል፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ የወጣ የተገለጠ ኑ-ፋ-ቄ ነው።

ከመጽሐፍ ቅዱስ በተቃራኒ ቆሞ፣ ቤዛነት ከስቅለት ጋር አይገናኝም የሚሉም፣ መጽሐፍ ቅዱስ ግን በቀጥታ ከስቅለቱና ከደሙ ጋር በማያያዝ እንዲህ ይላል፦ “በእርሱም እንደ እግዚአብሔር ጸጋ ባለጠግነት መጠን፣ በደሙ በተደረገ ቤዛነት፣ የኀጢአትን ይቅርታ አገኘን” (ኤፌ. 1፥7) ይላል። ዘበነ ሆይ! “በደሙ የተደረገ ቤዛነት” የተባለው የመስቀሉ ሥራ አይደለምን?!
ቤዛነት፣ ክርስቶስ በሰውነቱ ወይም በሥጋ ሞቱ የከፈለልን ፍጹም የመስቀሉ ሥራ ነው፤ ይህም ብቃት ያለውና አንዳች ተጨማሪ ነገር የማያሻው ነው፤ የትኛውም ኀጢአተኛ ይህን በማመን ይድናል። ይህ መንገድ ኹለተኛ ሌላ አማራጭ የለውም፤ የዳንበትና የምንድንበት የቤዛነት ሥራ አንድና አንድ ብቻ ነው። ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ እንዲህ ብለዋል፤

“አዳም መለኮታዊ ሕግን በመተላለፉ፣ በደል በመፈጸሙ የሞት ቅጣት ተፈርዶበታል፤ አዳም ከዚህ ዘላለማዊ ቅጣት ለመዳን የሚችለው በፍርድ መንገድ እንጂ በሌላ ሁኔታ መዳን አይችልም። ቅጣቱ በፍርድ እንደ ሆነ መዳኑም በፍርድ ይፈጸማል። ስለዚህ ነው ጌታ ሥጋ ለብሶ ማለት ሰው ሆኖ የአዳምን የሞት ፍርድ በራሱ ሰውነት ተቀብሎ ያዳነው፤ “ወአድኃነነ በፍትሕ ጽድቅ ወርትዕ” ተብሎ እንደ ተጻፈው መዳናችን በፍርድ እንደሆነ እናስተውል (መቅድመ ወንጌል)። ፍርድም የተፈጸመው በመስቀል ላይ ነው። እንግዲህ በመስቀል የመዳናችን ነገር አማራጭ የሌለው በእግዚአብሔር የተመረጠ ብቸኛ የጽድቅና የፍትሕ የርትዕ መንገድ እንደሆነ እናምናለን።




ፀሐይ በቆሻሻ ስፍራ ላይ እንደማትቆሽሸው፣ እንደ እኔ ያለ ዕድፋም ኀጢአተኛ ሲያነጻ የማይረክሰው የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ፍቅሩ ይደንቀኛል! ተባረክ!


ኢየሱስ ፍጹሙ ተስፋችን ባይኾን፣ ስንቱ መንገደኛና በሃይማኖት የታ*ጀለ ሰነ*ፍ በቀለደብን ነበር! ማራናታ መሲሑ!


እና ኢዩ ጩፋ ሠርቼ፤ ላቤን ጠብ አድርጌ እንኳን መኪናና ገና ጀት ገዛለኹ እያለ ነው?! ሌብ*ነትና የሐሰ*ት ትንቢት ሙያና ሽቄ ኾነ ለካ?! የስርቆሽ ውኃ አቤት አጠፋፈጡ፤ ትዕቢተኛ አቤት አፈጣፈጡ!


"እኔና ... በተራ ጫጫታ አንጠፋም"

ኢዩ ጩፋ በአንድ ወቅት "ድራማ ሠሪ ነቢይና ገንዘብ እየከፈለ፣ ሰዎች ሳይፈወሱ ተፈወሱ" አስባይ እንደ ኾነ አንድ ሰው በሚዲያ ተናገረ። ከጥቂት ቀናት በኋላ ደግሞ፣ ያው ሰው "በመከላከያ ወታደር ለባሾች ተከብቦ ተሳስቼ ነበር" አለ። ኢዩ ጩፋ ጉልቤያም(ጉልበተኛ) "ነቢይ" ነው። ሥራውን ካጋለጥክበት፣ ያለህበት ድረስ መጥቶ "ራስህን ለራስህ" በአሰቃቂ ኹኔታ ያስጋልጥሃል።

ሰውዬው የዋዛ አይደለምና፣ ከሰሞኑ ለአዋሳው "trip" አቀባበል እንዲያደርጉለት ለከተማው መስተዳድር ስድስት ሚሊየን ብር "የሻይ አስጨብጦ" ነበር አሉ።[የስድስት ሚሊየን ብር ሻይ መኖሩ አይደንቅም፤  እራቶቻችን በሚሊየን ብር ተመንድገውም አይደል]?! ግን ጩፋ የአዋሳው ነገር ደስ አላለውም። ካውንስል የተባለ አካል "ከንግዲህ በፖሊስና በማርሽ ባንድ እጀባ ይበቃል" ማለቱን ተከትሎ የጩፋ ልጅ፣ " ...ገና ካላንደር አዘጋለሁ... እኔና ... በተራ ጫጫታ አንጠፋም" ብሎ እርፍ።

ካውንስሉን "ይበለው፣ የእጁን በእጁ ይስጡት"፤ ተኩላ ከበግ ጋር ዝምድና የሌለውን ያህል፣ ትዕቢትና ማንአለብኝነትም ከቅኖች ጋር አይሄድም። ኹሌም ግን የሚደንቀኝ የስህ*ተት መምህራን፣ ከባድ ነውር ይፈጽሙና "የመንግሥት ጥላ መጠለላቸው" ይደንቀኛል! የድሎት ጌቶች፤ የትዕቢት ቁንጮ፤ የግብዝነት መገለጫ፤ የአታላይነት አባወራ ኾነው ... የጽድቅ አገልጋይ ለመምሰል ሲጨነቁ ማየት ያምማል!

ነገር ግን ዛሬ በጥሩ ድራማና ትወና ሊሸፈን የታለመ ነገር ኹሉ የሚገለጥበት አንድ የተቀጠረ ቀን አለ፣ “የማይገለጥ የተከደነ፥ የማይታወቅም የተሰወረ ምንም የለም።”(ሉቃ 12፥2) እንዲል።

ኢየሱስን የምትወዱ ኹሉ፣

"ደጉን ሰው ተመልከት፤ ቅን የሆነውንም ሰው እይ፤ ሰላም ወዳድ ሰው ዘር ይወጣለታል።" (መዝ. 37፥37 አት) አሜን።


ኢየሱስ ዳግም ሲመጣ፣ ኹሉም ነገር አዲስና ደህና ይኾናል!


ወጥረህ መንግሥትን መደገፍ ወይም መጥላት ትችላለህ፤ ነገር ግን ሰብዓዊነትን መንግሥት ይጠብቃል እንጂ መስጠትም ኾነ መንሣት አይችልም፤ የእግዚአብሔር ስጦታ ነውና! እና በርኩሰት አትዘባበቱ!


እግዚአብሔር ሆይ፤ በዓለሙ በተለይ በኢትዮጵያ ላይ እንደገና ስምህ ይቀደስ፤ ስምህ ይፈራ፤ ስምህ ይታወቅ! አሜን።


"አገር ስታምፅ፣ ገዦቿ ይበዛሉ፤ አስተዋይና ዐዋቂ ሰው ግን ሥርዐትን ያሰፍናል።" (ምሳ. 28፥2)


በአጕል ትህትና ሥጋን አትጨቁኑ!
 
መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ ቃቃል፣

“… ለዚህ ዓለም መርሕ ከክርስቶስ ጋራ ከሞታችሁ፣ ታዲያ በዚህ ዓለም እንደሚኖር ለምን ትገዙላቸዋላችሁ? “አትያዝ! አትቅመስ! አትንካ!” እንደሚሉት ዐይነት፣ እነዚህ ሁሉ በሰው ትእዛዝና ትምህርት ላይ የተመሠረቱ ስለ ሆኑ በተግባር ላይ ሲውሉ ጠፊ ናቸው። እነዚህ ነገሮች በገዛ ራስ ላይ ከሚፈጥሩት የአምልኮ ስሜት፣ ከዐጕል ትሕትናና ሰውነትን ከመጨቈን አንጻር በርግጥ ጥበብ ያለባቸው ይመስላሉ፤ ነገር ግን የሥጋን ልቅነት ለመቈጣጠር አንዳች ፋይዳ የላቸውም።” (ቈላ. 2፥21-23)

ይላል።


ለአማኞች የተሰጠው ልከኛው የመመላለሻ መንገድ ወይም የኑሮ ዘይቤ መገለጫ፣ “ጌታን ክርስቶስ ኢየሱስን እንደ ተቀበላችሁት በእርሱ ተመላለሱ፤” (ቈላ. 2፥6) የሚል ነው። ጌታችን ኢየሱስ የሚኖር ሕይወትና የሚከተሉት ትምህርት ያለው ጌታና መምህር ነው። ቅዱስ ጳውሎስ፣ አማኞች ከክርስቶስ ጋር ባላቸው ግንኙነቶች፣ ፍጹም የተቀራረበና በመንፈስ አንድነት የጐለበተ ሊኾን እንደሚገባ ደጋግሞ ይጠቅሳል፤ “ሥር ሰዳችሁ በእርሱ ታነጹ፥ እንደ ተማራችሁም በሃይማኖት ጽኑ”፣ “ራስ በሆነ በእርሱ ሆናችሁ ተሞልታችኋል።”፣ “ከዓለማዊ ከመጀመሪያ ትምህርት ርቃችሁ ከክርስቶስ ጋር ከሞታችሁ…” (ምዕ. 2፥7፡ 10፡ 20) የሚሉትና ሌሎችም ንባባት የሚያመለክቱት፣ አማኙ ከክርስቶስ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዲኖረው ነው።

አማኞች ደግሞ ይህን ሕይወት ለመኖር ዋስትና አላቸው፣ ይኸውም፦ አማኞች የሥጋውን ሰውነት በመግፈፍ ወይም ፍጹም የኾነ የኀጢአትን ይቅርታ አጊኝተዋል (ቊ. 11)፣ ከመንፈሳዊ ሞት ነቅተው ከክርስቶስ ጋር ብቻ ለመኖር ይቅርታን በማግኘት ሕያዋን ኾነዋል (ቊ. 12-13)፣  ጨቋኝና ተቃዋሚው፤ የክፍት ተጽዕኖ አድርጊው በመስቀሉ ሥራ ተጠርቆ ተወግዶላቸዋል (ቊ. 15)፣ ከዚህም ባሻገር ከዓለማዊና ከመጀመሪያ ትምህርት ወይም እንደ ሕግ ካሉ ዕዳዎች ኹሉ ነጻ ናቸው (ቊ. 15 እና 22)። አማኞች ይህን በክርስቶስ በማግኘታቸው፣ በጽድቅ ለመመላለስ ትልቅ ዋስትና አላቸው።

ነገር ግን ከዚህ በተቃራኒ ይህን እንዳናስተውል፣ የሐሰት ትምህርት በባህርይው ሳቢ ኾኖ ይቀርብልናል፣ ማስተዋል ያለብን እውነት፣ የሐሰት ትምህርት ምንም ሳቢ ቢኾን ምንጩ መለኮት አይደለም። ቅዱስ ጳውሎስ ከላይ የተጠቀሰውን ሕይወት አማኞች እንዳይኖሩት፣ ሐሰተኛ አስተማሪዎች በሚያስደንቅ መንገድ ትህትናን በማሳየት ሥጋቸውን የመጨቆን ትምህርት ያስተምራሉ በማለት ትምህርታቸውን ያጋልጣል (ቊ. 23)።  ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ያለ ትምህርትና ልምምድ ሥጋን በመቈጣጠር ወደ እግዚአብሔር እንደማያቀርብ ይናገራል፤ ነገር ግን ሰዎች ወደ እግዚአብሔር መቅረቢያቸው ክርስቶስ፤ መጽኛውና መጽናኛው መንፈስ ቅዱስ እንደ ኾነና ጾም፤ ጸሎት፤ ምጽዋት … የዚህ ውጤት መኾኑን የመጽሐፍ ቅዱሱን ክርስትና ያስተምራል!

ብዙ ሃይማኖቶች ሥጋን መጨቆንና ፈጽሞ መጥላት ወደ እግዚአብሔር እንደሚያቀርብ ያስተምራሉ፤ ከዚህ የተነሣ እግዚአብሔር በክብር የፈጠረውን ሥጋቸውን ክብረ ቢስ እንደ ኾነ በመቊጠር፣ ሲያዋርዱ፣ ሲኰንኑ፣ ሲያስጨንቁ እናስተውላለን። በርግጥ ይህ የለበስነው ሥጋ ሙሉ ለሙሉ ያልተዋጀና ፍጹም ውጅትን ገና በመቃተት የሚጠብቅ ነው (ሮሜ 8፥22)፤ ይህ ማለት ግን ሥጋ ፍጹም ርኩስ፤ የማይረባ፣ ሊቀደስ የማይችል፤ ከቅዱሱ አምላክ ጋር ምንም ኅብረት ሊያደርግ የማይችል፤ ከሰይጣን ጋር ብቻ የሚጣበቅ … ነው ማለት አይደለም፤ ቅዱሱ መጽሐፍ፣ “ለምኞቱ እንድትታዘዙ በሚሞት ሥጋችሁ ኃጢአት አይንገሥ፤” (ሮሜ 6፥12)፣ “ወንድሞች ሆይ፥ ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ሕያው ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ” (ሮሜ 12፥1)፣ “በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ።” (1ቆሮ. 6፥20)፣ “…ሥጋችሁም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጣ ጊዜ ያለ ነቀፋ ፈጽመው ይጠበቁ” (1ተሰ. 5፥23) በሚለውና በአያሌ ንባባቱ ውስጥ፣ ሥጋችንን ለእግዚአብሔር ክብር በመቀደስ ማቅረብ እንዳለብን ይነግረናል።
ሥጋን ግን በማስጨነቅ ወይም በመጨቆን ወይም ፍጹም ትህትናን እያሳዩና በመልካም ሥራ በመትጋት፣ ያለ ክርስቶስ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ አይቻልም፤ “እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” (1፥13-14) እንዲል፣ የዳንነው በልጁ በክርስቶስ ነው፤ ወደ አባቱ የምንቀርብበት ቀጥተኛውና የማያሳስተው መንገድና ጽድቃችን ክርስቶስ ኢየሱስ ነው!

“ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በማይጠፋ ፍቅር ለሚወድዱ ሁሉ ጸጋ ይሁን።” (ኤፌ. 6:24) አሜን።

My blog link - https://abenezerteklu.blogspot.com/2025/03/blog-post_23.html?m=1


ክርስትና በአሜሪካና በአውሮፓ "ሞቶ" ሕዝቡ፣ ወደ ኢ አማኒነት ከመ*ገልበ*ጡ በፊት፣ ከበሽታዎቹ ምልክት አንዱ እንዲህ ዐይነት ድሃ ጠል "ነቢያት" ተፈልፍለው ነበር። ከበርቻቻ፣ "ጋለ*ሞታ ሴት" ይመስል ብርቅርቅና ደማቅ አጀብና ቀለማቸው አስፈሪ በኾኑ ልብሶች ተጌጦ መታየት ... የሐሰተ*ኞቹ መገለጫ ነው። ከሐ*ሰተኛ አስተማሪዎች ጀርባ "ሕዝቤን ሊወርር" ያደፈጠ ኢአ*ማኒነት የ[ታሠረ-ተወጋ] ይኹን ብቻ አልልም! ቅድስት ቤተክርስቲያን ሆይ፤ መንፈስ ቅዱስ በጉበኛነቱ ይጠብቅሽ!
የቴሌግራም አድራሻ - https://t.me/ebenezertek


የእምነት እንቅሰቃሴ ቀንደኛ አስተማሪው "ፓስተር" ሮን፣ ኢየሱስ "ሰይጥኗል" ባዩና ስለ መለኮታዊ ገንዘብ አቅርቦት አስተማሪው "ሐዋርያ" ዘላለም፣ ሰው መንፈስ ነው ባዩ ጃፒ(ብዙአየሁ) ... እነዚህ ሰዎች "ሐዋርያ" ተብለው ቢጠሩም ሐዋርያት በዋሉበት አልዋሉም፤ አላደሩም፤ አያውቋቸውምም።

እናም የሊሊን ፕሮግራም አድማቂዎች እኒህ ነበሩ። ቅዱስ ጳውሎስ፣ "ነገር ግን ለሌሎች ከሰበክሁ በኋላ እኔ ራሴ ውድቅ ሆኜ እንዳልቀር፣ ሰውነቴን እየጐሰምሁ እንዲገዛልኝ አደርገዋለሁ።" (1ቆሮ. 9፥27 ዐመት) እንዲል፣ ሊሊን፤ አገልግሎ መጣል፤ ጥሩ ዘምሮና ሰብኮ በጌታ ፊት ውድቅ መኾን እንዳለ ይህን የጳውሎስ ምክር ማን በመከራት እላለኹ?!

መጽሐፍ በጥልቅ ምክሩ እንዲህ ይላል፣ "አትሳቱ፤ “መጥፎ ጓደኝነት መልካሙን ጠባይ ያበላሻል።” ወደ ሰከነ ልቦናችሁ ተመለሱ፤ ኀጢአትንም አትሥሩ፤ እግዚአብሔርን የማያውቁ አሉና፤ ይህንም የምለው ላሳፍራችሁ ነው።" (1ቆሮ. 15፥33-34) ይላል። ሊሊንም እንዲህ፣ አንቺ የዘመርሽለትን ጌታ ከማያውቁ ጋር ምን በአምልኮና በ"ዐውደ ምሕረት" አጎራበተሽ?! ...

ኢየሱስ ሰሚ ባጣ ጊዜ እንደ ተናገረው እላለኹ፣ "የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ"። ከአጀብ ተነጠሉ ከኢየሱሰ ጋር ተስማሙ፤ ከሐሰተኞች መንጋ ሽሹ፣ ኢየሱስ ከሚከብርበት ኹለትም ሰዎች ካሉበት ኅብረት ተጣበቁ፤ አትሳቱ፤ የክብር አምላክ በሰማያት በዙፋኑ አለ፤ ርሱ በጽድቅ እርሻ ውስጥ የተዘራውን እንክርዳድ ኹሉ ሳይቀር፣ ሲለቅምና ሲለይ አይሳሳትም፤ ፍጹም ጻድቅ ነውና!

ለገንዘብና ለክብር ብላችኹ ዕንቁ እምነታችሁን በዕሪያ ፊት አታስረግጡ።

የቴሌግራም አድራሻ - https://t.me/ebenezertek


ሊሊዬ "በ100 ዓመት የተፈጠረች ልዩ ክስተት" ብሎ በአደባባይና በሚሊዮን ብር ማሞገስ የቻለ አንደበት፣ ሌሎቹ "ተክለሃይማኖት ፀሐይ" ሲሉ ለምን ይከፋዋል? ክፉ ስህተት ከወደቁት አለመማር!


ወርቆቹ በብር ሲደብሱ!😢

" ... የምንበላውንና የምንለብሰውን ካገኘን ይበቃናል። ሀብታሞች ለመሆን የሚፈልጉ ግን በፈተና ይወድቃሉ፤ ሰዎችን በሚያበላሽና በሚያጠፋ ከንቱና አደገኛ በሆነ በብዙ ምኞት ወጥመድ ይያዛሉ። ይህም የሚሆነው የገንዘብ ፍቅር የክፋት ሁሉ ምንጭ ስለ ሆነ ነው። " (1ጢሞ. 6፥8-10)

የሚለው ቅዱስ ቃል እንዴት ተዘነጋ?!

የቴሌግራም አድራሻ - https://t.me/ebenezertek

978 0 17 4 32
Показано 20 последних публикаций.