የሚኒስትሮች ምክር ቤት የተለያዩ ውሳኔዎችን አሳለፈ
አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 17፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የሚኒስትሮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 31ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል፡፡
ምክር ቤቱ ያሳለፋቸው ውሳኔዎች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡-
1. ምክር ቤቱ በቅድሚያ የተወያየው የወጪ ንግድ የቀረጥ ማበረታቻ ሥርዓት አዋጅን ለማሻሻል የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ ነው፡፡ ለኢንደስትሪ ልማትና ኢንቨስትመንት የሚያስፈልገውን የውጭ ምንዛሪ ግኝት ለማሳደግ፣ በወጪ ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች በማበረታታት ረገድ የታዩ ውስንነቶችን ለመቅረፍ እና የዘርፉን ተዋንያን የሚያበረታታ ሥርዓት በመዘርጋት ተወዳዳሪነት ማላቅ ይቻል ዘንድ ረቂቅ ማሻሻያ አዋጅ ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም ረቂቅ ማሻሻያ አዋጁ ላይ ከተወያያ በኋላ ግብዓቶችን በማከል ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡
2. በመቀጠል ምክር ቤቱ የተወያየው የፌዴራል ህብረት ስራ ኮሚሽን ለሚሰጣቸው አገልግሎቶች የሚያስከፍለውን የአገልግሎት ክፍያ ለመወሰን በቀረበ ረቂቅ ደንብ ላይ ነው፡፡ ኮሚሽኑ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ማስፋት፣ የአገልግሎቶቹን የጥራት ደረጃ ማሻሻል፣ ብሎም የተጠቃሚውን ማህበረሰብ አቅም ባገናዘበ መልኩ አገልግሎት ለመስጠት ያወጣውን ወጪ በከፊል መሸፈን የሚያስችል ስርዓት መዘርጋት በማስፈለጉ ረቂቅ ደንቡ ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በረቂቅ ደንቡ ላይ ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውል በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡
https://www.fanabc.com/archives/243695