ለሙት አንሳ ማር ቅዱስ ሚካኤል አንድነት ገዳም 11 ሚሊዮን ብር መሰብሰቡ ተገለፀ
I በማዕከላዊ ጎንደር ሐገረ ስብከት በምስራቅ በለሳ ወረዳ ቤተክህነት የሚገኘው ሙት አንሳ ማር ቅዱስ ሚካኤል አንደነት ገዳም፣ ከዘጠና በላይ መነኮሳትና በመቶ የሚቆጠሩ ፀበልተኞች የሚገኙበት ታሪካዊ የአንድነት ገዳም ቢሆንም መነኮሳቱ በአሁኑ ወቅት ትልቅ ችግር ተጋርጦባቸው እንደሚገኝ ተነግሯል።
ገዳማዊያኑ የሚቀምሱት እህል፣ የሚለብሱት ልብስ በመጠኑ የተሟላላቸው ቢሆንም ከጾም፣ ጸሎት መልስ ስጋቸውን የሚያሳርፉበት ቤት የላቸውም፣ በአንድ ደሳሳ ጎጆ ቤት ውስጥ ለሶስት ለአራት የሚያድሩበት በጣም አሳዛኝ ሁኔታ ዉስጥ እንደሚገኙ ነው የተገለፀው።
ገዳማዊያኑን ከነዚህ ችግሮች እንዲወጡና በቀጣይም ገዳሙ ራሱን እንዲችል ለማድረግ፣ በጠቅላይ ቤተክህነት እውቅና እና በሐገረ ስብከቱ ፍቃድ ገዳሙ ብቻ የሚጠቀመው በገዳሙ ስም የተከፈቱ የባንክ አካውንቶች ይፋ ተደርገው፣ በሕዝበ ክርስቲያኑ በሚደረገው ድጋፍ ስራዎች እየተሰሩ ሲሆን፣ ገዳሙም የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በወረዳ ቤተ-ክህነት፣ በሐገረ ስብከትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጸድቆ በሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬና የቅርብ ክትትል እየተደረገበት በመሰራት ላይ ይገኛል ተብሏል።
ገዳሙ ያለበትን አሁናዊ ሁኔታ የሚገልጹ እና የሚያሳዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ዶግማ፣ ቀኖና እንዲሁም ትሁፊት በጠበቀ መልኩ በቴሌቪዥን፣ በሬዲዮ፣ በማህበራዊ ሚዲያ ማስታወቂያዎችን በማስተላለፍ ሕብረተሰቡ መረጃዉ ኖሮት የተቻለውን ድጋፍ እንዲያደርግ ተደርጎ በዚህም እስካሁን 11,000,000 (አስራ አንድ ሚሊዮን) ብር የሚያህል የገንዘብ ድጋፍ እንዲሁም 1,200,000 (አንድ ሚሊዮን ሁለት መቶ ሺህ) ብር የሚሆን የአይነት ድጋፍ ማሰባሰብ እንደተቻለ ተገልጿል።
ፕሮጀክቱ ከተጀመረ 11 (አስራ አንድ) ወራትን ያስቆጠረ ሲሆን በነዚህ ጊዜያት በመጀመሪያው ምዕራፍ በርካታ ስራዎች ተከናውነዋል።
ከተሰሩ ስራዎች መካከል ፡-
❖ የእናቶች በዓት ወይም ቤት በጥሩ ሁኔታ ተሰርቷል።
❖ 170 ሜትር ተራራ ተቦርቡሮ ለእናቶችም ለአባቶችም ለእንቅስቃሴ አስቸጋሪ የነበረው ቦታ በአርማታ ደረጃ ተሰርቶለት ለገዳማዊያን እንቅስቃሴ ምቹ እንዲሆን ተደርጓል።
❖ በአካባቢው ምንም አይነት የመብራት አገልግሎት ያልነበረ ሲሆን አሁን የሶላር መብራት ተሟልቶ የመብራት ተጠቃሚ ለማድረግ ተችሏል።
❖ ቤተ-እግዚአብሔር ወይም ማዕድ ቤት ተሰርቷል፤ የሚያስፈልጉ ሙሉ ቁሳቁሶችም ተሟልቷል።
❖ ገዳማዊያኑ በተደጋጋሚ የሚያጋጥማቸውን የምግብ አቅርቦት ችግር እና የአቅም ውስንነት በዘላቂነት ለመቅረፍ ጥረት እየተደረገ ይገኛል።
❖ ለገዳማዊያኑ የእደ-ጥበባት ውጤቶችን ማምረቻ ሼድ ግንባታ ተከናውኗል እንዲሁም የሸማ ስራ ሙያ እንዲሰለጥኑ በማድረግ ወደ ስራ እንዲገቡ ተደርጓል፣ ለስራው የሚያስፈልጉ መሳሪያዎች እና የጥሬ እቃ ግብዓቶችም ተሟልተዋል።
❖ የሻማ እና የጧፍ መስሪያ ማሽን ግዢ ተከናውኗል።
❖ አካባቢው በተደጋጋሚ በድርቅ የሚጠቃ በመሆኑ ለገዳማዊያኑ የተሻለ ለማድረግ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ።
❖ ወደ ገዳሙ የሚያደርስ 8 (ስምንት) ኪሎ ሜትር ደረጃ አንድ የጠጠር መንገድ ሥራ ተሰርቷል።
❖ የእናቶች የመጸዳጃ ቤቶች ግንባታ ተከናውኗል
❖ ለግንባታ አገልግሎት የሚውል ሲሚንቶ ማቡኪያ ማሽን፣ የብረታ ብረትና የእንጨት መስሪያ ማሽነሪ ግዥ ተፈጽሟል
❖ የገዳሙ ይዞታ ህጋዊ የይዞታ ማረጋገጫ ያልነበረው በመሆኑ የገዳሙ ህጋዊ ይዞታ እንዲረጋገጥ ተደርጓል።
❖ ገዳማዊያኑ ቀጣይነት ያለው ገቢ እንዲያመነጩ በማሰብ በሃሙሲት ከተማ የሸቀጣ ሸቀጥ እና የንዋያት ቅዱሳት መሸጫ ሱቅ ተከፍቶ ወደ ስራ ተገብቷል።
❖ ለግንባታ የሚውል በሃሙሲት ከተማ 30ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ከመንግስት በሊዝ በመውሰድ የአብነት ት/ቤት፣ አለማዊ ት/ቤት እንዲሁም የመጀመሪያ ደረጃ ጤና ጣቢያ በተጨማሪም ሌሎችም ገዳማዊያን አስፈላጊ የሆኑ የልማት ስራዎች የሚሰሩበት ይሆናል።
ከሚዲያው አካባቢ በተለይም ቲክቶክ አንዳንድ ቲክቶክሮች የገዳሙ አባቶችን ሆነ የቤተክርስቲያን መዋቅር ምንም አይነት መረጃ ሳይጠይቁና ያለ ምንም ተጨባጭ ማስረጃ በይመስለኛል ብቻ፣ የገዳሙንም የተከታዮቻቸውንም ክብር በማይመጥን መልኩ ተገቢና ትክክለኛ ያልሆኑ መረጃዎችን ማሰራጨት ተገቢ አይደለም ተብሏል።
በቀጣይ ለሚሰሩት የልማት ሥራዎች ማከናወኛ የሚሆን ድጋፍን ለማሰባሰብ በቀጣይም የተለያዩ መርህ-ግብሮች የሚከናወኑ ይሆናል።
ለአብነትም፡-
❖ ከመጋቢት 25 እስከ ሚያዝያ 2 ቀን 2017 ዓ.ም ምዕመኑ ከገዳሙ በረከት እንዲያገኙ እንዲሁም ገዳሙን እንዲጎበኙ የጉዞ መርሃግብር ተዘጋጅቷል።
❖ የድጋፍ ማሰባሰቢያ የቀጥታ ስርጭት መርሃ ግብር በተለያዩ የሚዲያ ተቋማት የሚከናወን ይሆናል።
❖ ጥቅምት 16 ቀን 2018 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ ብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት እና ሊቃውንት ቤተክርስቲያን በተገኙበት ታላቅ የገቢ ማሰባሰቢያ ጉባኤ ይኖረናል፤
❖ የሚዲያ ንቅናቄ ዘመቻውም እንደተጠበቀ ሆኖ በተለይም ከቤተ ክርስቲያን የሚዲያ አካላት ጋር በመነጋገርም ዶክሜንተሪዎችን እንዲሰሩና ምዕመኑ ገዳማዊያኑ ያሉባቸውን ችግሮች በመረዳት ድጋፍ እንዲያደርጉ ለማስቻል ስራዎች የሚሰሩ ይሆናል፡፡
@sheger_press@sheger_press