ዓላማን ሳይለቁ ውጣ ውረዶችን የማስተናገድ ሰፊነት“በእያንዳንዱ ነገር በነገርም ሁሉ መጥገብንና መራብንም መብዛትንና መጉደልን ተምሬአለሁ። ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ” (ፊል 4፡12-13)፡፡
አንዳንድ ጊዜ አንድን ነገር ጀምረን ገና አንድ እርምጃ ሳንራመድ ውጣውረዶች በሕይወታችን ብቅ ማለት ይጀምራሉ፡፡ ይህ በሚሆንበት ጊዜ ሰፊነታችን ወሳኝ ነው፡፡
በሚመጡት ውጣውረዶች በመጨናነቅ እነሱ እስከሚወገዱ ዓላማችን ይገታል ወይስ ውስጣችንን ሰፋ አድርገንና ጌታችንን አምነን በዙሪያችን ምንም አይነት ማዕበል ቢነሳ ወደፊት እንገሰግሳለን? ሊመለስ የሚገባው ጥያቄ፡፡
ሐዋርያው ጳውሎስ ምንም እንኳን ሙታንን እስከማስነሳት የደረሰ የምነት ሰው ቢሆንም በተለያዩ ውጣ ውረዶች ማለፍ ነበረበት፡፡ ለእርሱ እምነት ማለት ካለምንም ችግር መኖር ሳይሆን በምንም ነገር ውስጥ ለማለፍ የሚያስችል ኃይል ሊሰጠው የሚችለውን ጌታ ማመን ማለት ነበር፡፡
ልበ ሰፊዎች ከሌሎቹ የሚለዩት በጊዜአዊ ደስታም ሆነ ኃዘን ከጨበጡት ዓላማቸው የአለመነቃነቃቸው ዝንባሌ ነው፡፡ ይህንን ሰፊነት ለመለማመድ ደግሞ ልክ እንደነሱ ልንገነዘባቸው የሚገቡን እውነታዎች ይኖራሉ፡፡
1. የተዛባውን አመለካከት ማስተካከል“በእኔ ሰላም እንዲኖራችሁ፣ ይህን ነግሬአችኋለሁ። በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ”” ዮሐ. 16፡33
ክርስቶስ እዚህ ጋር ሊያሳስበን የፈለገው እውነታ፣ ሰላማችን ከሚነጥቁ ሁኔታዎች አንዱ በአለም ሳለን ምንም መከራ እንደሌለብን ስንቆትርና መከራው ሲደርስ የሚገጥመን የመናወጥ ሁኔታ ነው፡፡ ለዚህ ነው ሰላም እንዲኖራችሁ በማለት በአለም ያለውን እውነታ የሚነግረን፡፡ ስለዚህም በምንም አይነት ውጣ ውረድ ውስጥ ብናልፍም እንኳን ሳንናወጥ ለመኖር በክርስቶስ እስካለሁ ድረስ ምንም አይደርስብንም የሚለውን የተዛባ አመለካከት ማስተካከል የግድ ነው፡፡
2. የሁኔታዎችን ጊዜያዊነት መገንዘብ“በክርስቶስ ወደ ዘላለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ሁሉ አምላክ፣ ለጥቂት ጊዜ መከራ ከተቀበላችሁ በኋላ እርሱ ራሱ መልሶ ያበረታችኋል፤አጽንቶም ያቆማችኋል” (1ጴጥ. 5:10)፡፡
እውነቱ አጭርና ግልጽ ነው! መከራ ለጥቂት ጊዜ ነው፡፡ መከራው ካለፈ በኋላ ግን መልሶ የሚበረታና እስከመጨረሻው የሚያጸና ጸጋ ይሰጠናል፡፡ በዚህ መለኮታዊ አሰራር ደግሞ ደስ ልንሰኝ ይገባናል፡፡ “ምክንያቱም ቀላልና ጊዜያዊ የሆነው መከራችን ወደር የማይገኝለት ዘላለማዊ ክብር ያስገኝልናል” (2ቆሮ. 4:17)፡፡
3. የችግርን ጥቅም መገንዘብ“በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ምክንያቱም ፈተናን ሲቋቋም እግዚአብሔር ለሚወዱት የሰጠውን ተስፋ፣ የሕይወትን አክሊል ያገኛል” (ያዕ. 1:12)፡፡
በምንም አይነት ፈተና ውስጥ ብናልፍ ያንን ለመቋቋም ስንወስን ሽልማትን ከጌታ እንቀበላለን፡፡ ይህ ሽልማት ቀደም ብለን በተመለከትናቸው ትቅሶች መሰረት ምድራዊ ገጽታ ሲኖረው በያእቆብ መልእክት መሰረት ደግሞ ዘላለማዊ ክብርና አክሊል የሚሰጥ ሽልማት ነው፡፡ ይህንን መገንዘብ ይህ ነው የማይባል ሰፊነትን ይሰጠናል፡፡
የሚቀጥለው ትምህርት፡ “መርህን ሳይለቁ በዓለም የመሰማራት ሰፊነት” @revealjesus