“ብዙ ከእኛ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ነገሮች ይኖራሉ። ነገር ግን ሁሉም ነገር በትክክል ከተካሄደ ሊበቃን ይችላል” - ምክትል ኮሚሽነር ሒሩት ኃ/ስላሴከቀናት በፊት አንድ አመት ተጨማሪ የሥራ ጊዜ በፓርላማ የተሰጠው የ3 አመታት የሥራ ዘመኑን ነገ ይጠናቅቅ የነበረው የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የ3 አመታት ክንውንና የቀጣይ አቅጣጫውን በተመለከተ ዛሬ በስካይ ላይት ሆቴል መግለጫ ሰጥቷል።
በዚህም ኮሚሽኑ የተሰጠው ተጨማሪ ጊዜ በቂ ነው? አጠቃላይ ሥራውስ መቼ ይጠናቀቃል? በሚል ከጋዜጠኞች ለቀረላቸው ጥያቄ ምክትል ዋና ኮሚሽነር ሂሩት ገብረ ስላሴ፣ “ብዙ ከእኛ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ነገሮች ይኖራሉ። ነገር ግን ሁሉም ነገር በትክክል ከተካሄደ ሊበቃን ይችላል” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።
"ከእኛ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ነገሮች አሉ” ያሉት፣ ምክትል ዋና ኮሚሽነሯ ይህን ይበሉ እንጂ ከቁጥጥር ውጪ ስለሆኑ ነገሮችን በዝርዝር አልገለጹም።
11 ኮሚሽነሮች እንዳሉና ሥራውን ተባብሮ ለመስራት እንደሚቻል ገልጸው፣ "ተጨማሪ አንዳንድ ሥራዎችን የሚያቃልሉ ነገሮች በመንግስትም ሆነ በሌሎች ከተፈጠሩልን ስራችንን ያጣድፋል" ብለዋል።
“ምክክር በዚህ ሰዓት ውስጥ ተመካክራችሁ በዚህ ጊዜ ውስጥ ውሳኔ ስጡ የሚባልበት አይደለም። ህዝቦች ቁጭ ብለው ጊዜ ውስደው ተመካክረው የሚወሰኑት ሂደት ስለሆነ በቀላሉ የሚወሰኑ አጀንዳዎች ይኖራሉ። ጊዜ የሚፈጁም ሊኖሩ ይችላሉ” ሲሉም አስረድተዋል።
አክለው፣ “በዚህ ምክንያት በትክክል በዚህ ጊዜ ውስጥ ያልቃል ለማለት ያስቸግራል” ብለው፣ ሆኖም ግን ኮሚሽኑ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሥራውን ለመጨረስ ጥረት እንደሚያደርግ ገልጸዋል።
የተወሰኑ ፓርቲዎች ባልተሳተፉበት የምክክሩ ሂደቱ ሙሉ ይሆናል? በሚል ለቀረበው ጥያቄም፣ ፓርቲዎች በምክክሩ እንዲሳተፉ ጥረት መደረጉን ገልጸው፣ “ዳተኛ ሆነው” ያልገቡት እንዲገቡ ደግሞ ንግግር እንደተደረገ፣ አሁንም ጥረቱ እንደሚቀጥል አስረድተዋል።
ዋና ኮሚሽነር መስፍን ዓርዓያ (ፕ/ር) በበኩላቸው፣ በመግለጫው ባደረጉት ንግግር በሕጋዊ ከተመዘገቡ ወደ 70 ፓርቲዎች 57 የሚሆኑት ከኮሚሽኑ ጋር እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።
ከታጣቂዎች ጋር ንግግር ተደርጎ እንደሆን ከጋዜጠኞች ጥያቄ ቀርቦላቸው በሰጡት ማብራሪያ ዋና ኮሚሽነሩ፣ የፋኖ ታጣቂዎችን እንዳነጋገሩ፣ “ሊከፋፍለን ነው” በሚል ስማቸው እንደሚነሳ አስታውሰው ተከታዩን ብለዋል።
ምን አሉ?
“ሀገራዊ ምክክሩ ማንንም መከፋፈል አይመኝም። የሚመኘው፣ መደረግ አለበት ብሎ የሚያምነውም ሁሉም ተሳታፊ እንዲሆን ነው።
እኔ ፋኖ መሆናቸውን አላውቅም አንድ ታጣቂ ቡድን ራሳቸው ደውለውልኝ ‘የምክክር ኮሚሽኑን ሥራ ተገንዝበናል። ‘በዚህ መሠረት ወደ ትግሉ የገባንበትን አጀንዳ ወደ እናንተ አምጥተን ወደ ውይይት የሚቀርብ ከሆነ መሳሪያችንን ለማስቀመጥ ዝግጁ ነን’ የሚል በቀጥታ በግሌ አቅርበውልኛል። ይሄን ሰው በተደጋጋሚ አግኝተዋለሁ።
እዛ ላሉትም የደኅንነት፣ አካላት በስልክ አግኝቼ እነዚህ ሰዎች በአግባቡ መሠረት ሰላማዊ ጥበቃ ተደርጎላቸው አጀንዳቸውን የሚያመጡበት መንገድ እንዲመቻች ይሄን አስተላልፌያለሁ።
ይህን ሳደርግ ለሀገራዊ ምክክር ጉባዔ በማሳወቅ ነው። እንጂ የፋኖ ናቸው ብዬ የተናገርኩት አንድም የለም” ብለዋል።
በሌላ በኩል በዛሬው መግለጫ የኮሚሽኑ የ3 አመታት ክንውኖች በኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር መስፍን ዓርዓያ (ፕ/ር) በዝርዝር የቀረቡ ሲሆን፣ ይህንኑ ሪፓርት ከቀናት በፊት አድርሰናችሁ ነበር።
(ተጨማሪ ዘገባ በቀጣይ የምናቀርብ ይህናል)
#TikvahEthiopiaFamilyAA
@tikvahethiopia