🔊 #የሠራተኞችድምጽ
🟢
"ቅሬታችን በአስቸኳይ ምላሽ የማያገኝ ከሆነ ከየካቲት 15/2017 ዓ.ም ጀምሮ ሥራ እናቆማለን"- የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ሰራተኞች
🟢 "ለክልሉ መንግስት ቅሬታውን አቅርበናል። ነገር ግን ለቀረበለት ጥያቄ ምላሽ መስጠት አልቻለም " - የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ የሰው ኃብት አስተዳደር የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ሰራተኞች በሀገር አቀፍ ደረጃ ጥቅምት አንድ ተግባራዊ የተደረገው አዲሱ የደመወዝ ማሻሻያ ጭማሪ እስካሁን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ተግባራዊ ባለማድረጉ ለከፋ ችግር ተጋልጠናል ሲሉ ቅሬታቸውን አቅርበዋል።
በተጨማሪም የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሸን ለሁሉም ሲቪል ሰርቫንት የኑሮ ውድነት መደጎሚያ ያደረገውን ጭማሪ እስካሁን አልተጨመረንም ብለዋል።ሰራተኞቹ የተለያዩ ጥያቄዎችን ለክልሉ ገቢዎች ቢሮ ማቅረባቸውን የገለፁ ሲሆን ጥያቄያችን በቀጠሮ የታጀበ የአመታት ችግር ሆኖ ቀጥሏል ብለዋል።
"የክልሉ መንግስት የተቋሙን ሰራተኞች ድካም እና መስዋዕትነት የተረዳው አይመስለንም " ። እኛ " ተስፋ ቆርጠናል ፣ የሚሰማን አካል የለም ፣ እየታገትን እና እየተገደልን ነው ፣ከማህበራዊ ሂወት ተገለናል ብለዋል።
አክለውም "እንደሰው መቆጠር ናፍቆናል ፣ ችግሮቻችን በዝተዋል ፣ ችግሮችን የሚፈታልን የለም ፣ እባካችሁ የሚሰማን አካል ካለ የሁለት አመት ቅሬታችን ይሰማ " ሲሉ የነበሩበትን የችግር ግዝፈት ተናግረዋል።
አያይዘውም ሰራተኞቹ መጋቢት 5 / 2015 ዓ.ም ይወክሉናል ያሏቸውን ተወካይዮች በመምረጥ ለክልሉ ገቢዎች ቢሮ ፣ ለበጀትና ፋይናንስ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እና ለብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት አመራር እንዲሁም ለርዕሰ መስተዳድሩ ልዩ አማካሪ ቅሬታቸውን እንዳቀረቡ ገልፀዋል።
ሰራተኞቹም በሰዓቱ ለአመራሮቹ ያቀረቧቸው ጥያቄዎች በርካታ መሆናቸውን የገልፁ ሲሆን ከጥያቄዎቻቸው መካከል የገቢ ተቋሙ ሰራተኛ በልዩ ሁኔታ በጥናት ላይ የተመሰረተ ልዩ ጥቅማጥቅም ይደረግልን፣ የእርከን ጭማሪ በአደረጃጃትና በመመሪያ ደረጃ የወረደ ቢሆንም በአፈጻጸም ተግባራዊ ይደረግ እና የሰራተኛውን ጥቅም የሚመለከት ጥናት ሲጠና እስከ ታችኛዉ መዋቅር ያለ ባለሙያ ተሳታፊ ይደረግ የሚሉ እና መሰል ጥያቄዎች መሆናቸውን ጠቁመዋል።
በመሆኑም በሰዓቱ አመራሮቹ በምላሻቸው ጥያቄው ተገቢነት ያለው የባለሙያውን ሮሮና ብሶት ያዘለ ስለሆነ በቀጣይ የተሻለ ገቢ ለመሰብሰብ ይህንን አካል የግድ ማትጋትና ማበረታታት አስፈላጊ ስለሆነ ጥያቄውን እንፈታለን ብለውን ነበር ብለዋል።
ይሁን እንጂ ቅሬታችንን ሰምቶ የፈታልን አካል የለም ያሉ ሲሆን አሁንም ለከፋ ችግር ተጋልጠን እንገኛለን ሲሉ አክለዋል።
በሌላ በኩል ደግሞ ሰራተኞቹ የክልሉን የገቢዎች ቢሮ የሰው ሀብት አስተዳደር ቅሬታችንን ፍቱልን ብለን ጠይቀን ነበር ያሉ ሲሆን ሀላፊውም በምላሻቸው " ቅሬታችሁ ከአቅማችን በላይ ነው። በአስቸኳይ ምላሽ ይሰጣቸው ስንል ለክልሉ መንግስት ጥያቄ አቅርበናል እስካሁን ግን መልስ የለም " የሚል ምላሽ እንደተሰጣቸው ተናግረዋል።
አክለውም እንደተቋም በቀን እስከ 200 ሚሊየን ገቢ የሚሰበስብ ሰራተኛ አንድ ቀን ስራ ቢያቆም እንኳ ምን ሊፈጠር እንደሚችል መገመት ቀላል መሆኑን ጠቁመዋል።
ቅሬታ አቅራቢዎቹ በዝርዝር ምን አሉ?
ከደሴ ኮምቦልቻ የደወለልን ባለሙያ " ስራችን ከማህበረሰቡ ሂወት ነጥሎናል፣ ከነጋዴዎች አራርቆናል፣ ደመወዝ ሲያልቅብን እንኳ ከነጋዴዎች መበደር አንችልም፣ ቤት ለመከራየት ስንጠይቅ ገቢዎች ቢሮ ከሆነ የምትሰሩት አናከራይም እያሉን ነው፣ አሁን ላይ ችግሮችን መቋቋም አቅቶናል " ሲል ተናግሯል።ስሙን መጥቀስ ያልፈለገው የደባርቅ ከተማ ገቢዎች ቢሮ ሰራተኛ ደግሞ " የደረጃ እርከን እየተሰራልን አይደለም " 2012 ዓ.ም የደመወዝ ጭማሪ እንደተደረገ እስካሁን አልተጨመረንም " በስራ አጋጣሚ ሂወታቸውን የገበሩ ጓዶች አሉ " የክልሉን መንግስት ታግሰናል" አሁን ላይ ግን ኑሮ ከብዶናል " ሲል ገልጿል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያም የሰራተኞቹን ቅሬታ በመቀበል ለአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ የሰው ሃብት አስተዳደር ሀላፊ ለአቶ ሽመልስ አዱኛ ቅሬታቸውን ያቀረበ ሲሆን እርሳቸውም በምላሻቸው እንድህ ብለዋል።
" የሰራተኞቹ ቅሬታ ተገቢ ነው። በኛ በኩል ቅሬታውን እናውቃለን ። ለክልሉ መንግስት ቅሬታውን አቅርበናል። ነገር ግን ለቀረበለት ጥያቄ ምላሽ መስጠት አልቻለም "በዚህ ጉዳይ የተለየ መረጃ ልሰጥ አልችልም " ብለዋል።
ቲክቫህ የባለሙያዎችን ቅሬታ በተመለከተ የክልሉን መንግስት እና የኮሚኒኬሽን ባለሙያ እንዲሁም የክልሉን ገቢዎች ቢሮ ሃላፊ በስልክ አግኝቶ ምላሻቸውን ለማካተት ያደረገው ጥረት ባለመሳካቱ ምላሻቸውን ማካተት አልተቻለም።
በመጨረሻም ሰራተኞቹ ቅሬታችን በአስቸኳይ ምላሽ የማያገኝ ከሆነ ከየካቲት 15/2017 ዓ.ም ጀምሮ ስራ የምናቆም መሆኑን እንገልፃለን ብለዋል።
( ቲክቫህ ጉዳዩን እስከመጨረሻው ተከታትሎ መረጃውን የሚያደርሳችሁ ይሆናል )
#TikvahEthiopia
@tikvahethmagazine