Posts filter


በርታ በል!
፨፨////፨፨
መድሃኒት ቀማሚው ለመድሃኒትነት የሚያገለግሉትን ግብዓቶች ፍለጋ ወደ ጫካ ይገባል፤ አትክልቶችንም ያስሳል። አሰሳው መድሃኒት ለመቀመምና ታካሚውን ከህመሙ ለማዳን እንዲሁም ለማሳረፍ ነው። ጥረቱ ግን አልጋ በአልጋ አልነበረም፤ የሚያገኛቸው ቅጠሎች ሁሉ ለፈለገው መድሃኒት የሚሆኑ አልነበሩም ነገር ግን ትከክለኛውን ቅጠልና ሌሎች ግብዓቶችን ፍለጋ ማሰሱን አላቆመም። ጥረቱም መና እንዳይቀር፣ ታካሚውም እንዲፈወስ የሚጠበቅበትን ሁሉ ለማድረግ እራሱን በይበልጥ አዘጋጅቶ ጥረቱን ቀጥሏል። በእርሱ ድካም ታካሚው ቢያመልጠው ቁጪትና ፀፀቱ የህይወት ዘመን ቁስሉ ነው። ነገር ግን ስለበረታ የታካሚውን ህይወት መታደግ ቻለ። አንተም ሁሌም ደስተኛ ላትሆን ትችላለህ፣ ህይወት ፊቷን ልታዞርብህ እድልም ጀርባ ልትሰጥህ ትችላለች፣ ቀኑ ሰጨልምብህ ተስፋ ለመቁረጥ ልታቀርብህም ትችላለች። ነገር ግን ካደረካቸው በላይ ባላደረካቸው እየተቆጨህና እየታመምክ ከምትኖር አሁን በርታ በል። የምታየው ሁሉ የሚያነቃህ፣ የምትሰማው ሁሉ የሚያበረታታህ፣ የምትሰራው ሁሉ ለውጤት የሚያበቃህ ላይሆን ይችላል። አንተ በፈለከው ጉጉት ልክ ብዙዎች አይሳኩም፤ መንገድህ አይቀናም፤  ሃሳብህ አይሞላም። ካልጠነከርክ ግን ሁሉም ያበቃል።

አዎ! ጀግናዬ..! በርታ በል! በመኖርህ የምታዝን ሳትሆን ስላለህ ብቻ፣ አምላክህ ፊት በመቆምህ ብቻ ህያዊት ነፍስህን በተስፋ የምትሞላ ሁን። ጠንካራ ነህና ቀላል ነገር አይሰብርህም፤ ብርቱ ነህና በጥቃቅን ክፍተት ተስፋ አትቆርጥም። ከባዱ ሊሰብርህ ቢመጣም እንዳትበገር፤ እጅህን ለመስጠት አትፋጠን። ተስፋህ ውስጥ ገና ያልኖርከው፣ ያላጣጣምከው፣ ያልተነካ ሙሉ ህይወት አለ። በእራሰህ አዝነህ ተስፋ ስላጣህ ከምንም የከፋውን ምንም ሳታገኝ ምንም ታጣለህ፤ እራስህን ትጥላለህ፤ በእራስህ ትከፋለህ፤ መልካሟን የህይወት ገፅም ወደ ክፉ፣ አስደሳቿንም ወደ አሳዛኝ ትቀይራታለህ። ያለፈው ጊዜ ቢያሳምምህ፣ ቢያሰቃይህ፣ ቢያቆስልህም ከበረታህ ከአሁን ጀምሮ ያለው ጊዜ ግን ይጠግንሃል፤ ያክምሃል፤ ያሳርፍሃል።

አዎ! ደጋግመህ በእራስህ ከማዘን ተቆጠብ፤ በእራስህ ከመጨከን ተመለስ። የማይደክም፣ የማይዝል፣ የማይታመም ሰው የለም። ሲስቅ የምታየው ሁሉ የሚያለቅስበት ጊዜ ነበር፤ ሲደሰት የተመለከትከው ሁሉ በህይወት አጋጣሚ ለአሳዛኝ ክስተት የሚጋለጥበት ጊዜ ይኖረዋል። ኑሮ ስለከበደህ ህይወትህን እንደ እርግማን አትቁጠራት፤ ችግር ስለተደራረበብህ በብሶት አንገትህን አትድፋ። የጨለመችው ጀንበር ጎህ ለምትቀደው ብረሃን ቦታ የምትለቅበት ጊዜ ይመጣል፤ መቼም ጨልሞ አይቀርም። የምታምነው አምላክ ሁሌም ከጎንህ ነውና መቼም ብቻህን እንደሆንክ አይሰማህ። ከተሰባሪው ሰው በላይ በማይበገረው ፅኑ ድጋፍህ በሆነው በፈጣሪህ ተማመን። በምክንያት የሆኑት ሁሉ በምክንያት ያልፋሉ፤ ያስደመመህን ለውጥ በሰዎች ላይ እንዳየሀው አትቀርም፤ ከበረታህ፣ በተስፋ ከተሞላህ፣ ካመንክ፣ በእምነትህ ልክ ከጣርክ ያለጥርጥር ያንን ለውጥ በአንተም ህይወት ሲከሰት ትመለከተዋለህ።


ቀላሉን እርሱት!
፨፨፨//////፨፨፨
ስለ ቀላሉ ገንዘብ መስሪያ መንገድ ብዙ ሲባል ሰምታችኋል፣ ስለ ቀላሉ ስራ ብዙ ተብላችኋል፣ ስለ አቋራጩ ሃብት ማከማቻ መንገድ፣ ስለ ተለመደው የቁማር ጫወታ ከብዙም ብዙ ሰምታችኋል፣ ከመስማትም በላይ ደጋግማችሁ ሞክራችሁታል። ነገር ግን ምን አገኛችሁ? እድሜን ከማባከን፣ ስሜትን ከመረበሽና እንቅልፍን ከማጣት በቀር ምን አተረፋችሁ? ምንም። ሁሌም የሰነፎች መገለጫ አቋራጭ መንገድ ነው፤ ሌቦች አምታተው ማትረፍ የሚፈልጉ ናቸው። ለማንም ያልሰራውን መስጠት እንደማትፈልጉ ሁሉ ባልሰራችሁትም ለመሸለም አትሯሯጡ። ቀላሉን መምረጥ ቀላል እንደሚያደርጋችሁ አስታውሱ፣ አቋራጩን መምረጥ ብኩን እንደሚያደርጋችሁ ተረዱ። ለሰነፎች ቦታ የማትሰጥ፣ በቀላሉ የማታበለፅግ፣ በአጭሩም ትርፋማ የማታደርግ ዓለም ላይ እንደምትኖሩ እወቁ።

አዎ! ቀላሉን እርሱት፣ አቋራጩን አቁሙ፣ ማምታታቱ ይቅርባችሁ፣ እራሳችሁም አትወናበዱ። ሰው ያደረገውን ማድረግ ትችላላችሁና ለከባዱ ፈተና እራሳችሁን አዘጋጁ፣ ውስብስቡን ለማለፍ፣ ከባዱን ለመጋፈጥ፣ ፍረሃታችሁን ለማሸነፍ፣ የወደፊት ህይወታችሁን ለማስተካከል፣ ልባችሁን ለማሳረፍ፣ እራሳችሁን ከድህነት ወለል ነፃ ለማውጣት መንፈሳችሁን አጠንክሩ፣ ስሜታችሁን አድሱ፣ ወኔያችሁን አነሳሱ። ከማንም ሳታንሱ ከማንም ያነሰ ህይወት ለመኖር አትንደርደሩ። ማንም ብትሆኑ ያለማቋረጥ የምትሰሩት ስራ የማይከፍላችሁ መንገድ አይኖርም። ተፈጥሮ የምትመራው በአንድ ህግ ብቻ ነው። "ከባዱ ምርጫ ከባድ ባለድል ያደርጋል፣ ቀላሉምርጫ ልፍስፍስ ደካማ ያደርጋል።" ከህጉ ዝንፍ ማለት ለህይወት ዘመን ከባድ ፀፀት ይዳርጋል።

አዎ! ጀግናዬ..! ቀላሉን ማሳደድ አቁመ እራስህን ፈትነው፣ እያወክ ዋጋ አስከፍለው፣ አቀርቅሮ አሰንዲሰራ አድርገው፣ ሳያቋርጥ እንዲተጋ አድርገው። ሰው የሚጠቁምህን ቀላል ስራ ሁሉ አትመን፣ የተባልከውን ሁሉ በመጀመር ጊዜ አታጥፋ። ዋጋህ የሚጨምረው ልክ እንደብረቱ በእሳት ስትፈተን እንደሆነ አስታውስ። አጭሯን እድሜ በልፍስፍሶች መንገድ እየተጓዝክ ይበልጥ አታሳጥራት፣ ውዷን ህይወትህን ትርጉም በማይሰጡ ጥቃቅን ተግባራት እርባና ቢስ አታድርጋት። ጨከን በል፣ ፈተና ያለውን ምርጫ በልበሙሉነት ምረጥ፣ ላሰኘህ ሳይሆን ለሚጠቅምህ፣ ለቀለለህ ሳይሆን ከብዶ ለሚያከብድህ እራስህን አሳልፈህ ስጥ። ጠንክረህ ተፋለም፣ እስከመጨረሻው ታገል፣ መቼም ተስፋህን አትጣ፣ ለከባዱ የህይወት ምርጫም የሚመጥን ማንነትን ገንባ።


ጨለማው አብቅቷል!
፨፨፨፨/////////፨፨፨፨
አዎ! ጠለማው አብቅቷል እናም ድጋሜ አይመለስም፣ አሳፋሪው ወቅት፣ አስፈሪው ጊዜ አልፏል እናም ድጋሜ አትመለከተውም። ከልክ በላይ ማሰብ፣ ለሚሆነውም ለማይሆነውም መጨነቅ፣ በየትኛውም ስፍራ አቀርቅሮ መጓዝ፣ ለከባዱ የህይወት አጋጣሚ አስቀድሞ መንበርከክ፣ ሰዎች ባስቀመጡት ክብ ደጋግሞ መመላለስ፣ በራስ አለመተማመን፣ በራስ ማፈር፣ እራስን ማሸማቀቅና ማጎሳቆል ሁሉ አብቅቷል። ለእራስህ የምትኖርበት ጊዜ መጥቷል፣ እራስህን የምታኮራበት፣ ከጨለማው አስተሳሰብ፣ ከውድቀት አቋም እራስህን ነፃ የምታወጣበት ጊዜ አሁን ነው። ብዙዎች ስለወደፊት ያወራሉ፣ ብዙዎች በትናንትናቸው ታስረዋል አንተ ግን ዛሬ አሁን የውሳኔ ሰው ሆነህ ተገኝ፣ ዛሬውኑ ህይወትህን ወደመቀየር ተሸጋገር። ለራስህ የገባሃቸው መሰረተ ቢስ ቃላቶች፣ የሚገባህን ህይወት መኖር ያልቻልክበት ጊዜ እንዲያበቃ አድርግ።

አዎ! ጀግናዬ..! ጨለማው አብቅቷል፣ የብረሃን መንገድ ተጀምሯል፤ የኋሊቱ ጉዞ ቆሟል ወደፊት መራመድ ጀምረሃል፤ በራስ ማዘን አብቅቷል በማንነት መኩራት ተጀምሯል። ማስመሳል፣ እራስን ማታለል፣ ለታይታ መኖር ለእይታ መመላለስ፣ እራስን በየአቅጣጫው ማድከም፣ ህይወትን ማክበድ ቀርቷል። ብዙዎች እውነታን መጋፈጥ ይፈራሉ፣ ብዙዎች ሪስክ መውሰድ ይፈራሉ፣ ብዙዎች በስንፍና ታስረዋል፣ በእምነት ማጣት በጥርጣሬያቸው እየተበዘበዙ ነው፣ ብዙዎች ከተግባር በራቀ ሃሳብ፣ እርምጃ ባልተወሰደበት ህልም፣ ከዛሬ ነገ ተንከባሎ በመጣ እቅድ በጭንቀት ይኖራሉ። ከብዙዎቹ አንዱ እንደሆንክ ከተሰማህ እርምጃ የምትወስደው እንደለመድከው በሃሳብ ወይም በእቅድ ወይም በወሬ ሳይሆን በተግባር እንደሆነ አስታውስ።

አዎ! ህይወት ለማን ቀላል ሆና ታውቃለች? ኑሮ ለማን አልጋባልጋ ሆኖ ያውቃል? ለማንም። ማንም ህይወቱን ወዶ ተመችቶት ለመኖር የግድ ማድረግ ያለበት ነገር ይኖራል። በተመሳሳይ የለውጥ አመለካከት፣ በተለመደው የህይወት መረዳት፣ በአንዳይነት የግል አቋም አንዳች የሚፈጠር ነገር የለም። የጨለማው ዘመን ያበቃ ዘንድ ህልምህን መሞከር ይኖርብሃል፣ ከቀደመው ችግር ለመውጣት አዲስ አደጋን መጋፈጥ የግድ ነው፣ ትናንትህን ለማደስ ዛሬ እንቅስቃሴ መጀመር ይጠበቅብሃል። ያለ ተግባር የሚገፈፍ ጨለማ፣ ያለጥረትም የሚመጣ ለውጥ የለም። የምርም ህይወትህን ከወደድከው ይበልጥ ትደሰትበት ዘንድ በምትፈልገው መንገድ መቀየር ይኖርብሃል። ቀስበቀስ ነገር ግን በእርግጥም ነገሮችን ትቀይራለህ፣ በሂደት ነገር ግን የምርም የምትመኘውን ህይወት መኖር ትጀምራለህ። በተስፋህ ተማመን በከባዱ መንገድም ህይወትህን አሻሽል።


ከዓለም ተላቀቅ!
፨፨፨////////፨፨፨
መለየት ደስ ይላል፣ በታሪክ ውስጥ ማለፍ፣ የእራስን አሻራ ማሳረፍ፣ ሆነም ቀረም የሚያኮራን ተግባር መፈፀም የተለየ ስሜትን ይፈጥራል። ዓለም ሁሌም ስጋን መማረክ ትፈልጋለች፣ ምድር በየቀኑ የጥፋትን በር ከፍታ ትጠባበቃለች። ትኩረት በየሔድንበት ሁሉ በሚታደንበት ዓለም እየኖርን ትኩረትን ሰብስቦ፣ እራስን ገዝቶ፣ ምግባርን አስቀድሞ፣ በአምላክ እየተመሩ መኖር እጅግ ከባድ ነው። ህያዊት ነፍስ የተጠማችው መንፈሳዊውን ስራ እንጂ ምድራዊውን ፌሽታ አይደለም። ለነፍሳችሁ ስትታዘዙ የዓለም አብረቅራቂ ጊጣጌጥ ሁሉ የማይረባ ኮተት እንደሆነ ይገባችኋል። ነፍስ ምንምእንኳን በስጋ ብትጨቆንም የዘወትር ፍላጎቷና አምሮቷ ግን ለአምላኳ መገዛትና በህግጋቱ መመራት ብቻ ነው።

አዎ! ጀግናዬ..! ከዓለም ተላቀቅ፣ ገደብ ከሌለው ስጋዊ ፍቃድ እራስህን ጠብቅ፣ ሰዶ ማሳደድ ውስጥ አትግባ፣ ከዓለም ለማትረፍ አትሽቀዳደም፣ ክብርን ለማግኘት በጥፋት መንገድ አትጓዝ። የዓለም መድሃኒት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን አለ፦ "ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል፤ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም።" ለገንዘብ የሚገዛ እግዚአብሔርን ሊያከብር አይችልም፤ እግዚአብሔር አምላኩንም ያከበረ እንዲሁ በምድራዊ ንብረትና ዝና አይሰናከልም፣ ለእርሱም ብሎ እራሱን አያጣም፣ ነፍሱንም አያረክስም። የዓለምን ሃብት በሙሉ በእጅ ብታስገባና የእግዚአብሔርን ፍቅር ብታጣ ትርፍህ ምንድነው?

አዎ! ትርፍ ለሌለው ድካም እራስህን አታጋልጥ፣ ለማታርፍበት፣ ውስጥህን ለማታረጋጋበት፣ ሰላምህን ለማታረጋግጥበት ነገር ዋጋ ከመክፈል ተቆጠብ። እራስን መግዛት ተለማመድ ከዛም በላይ እራስህን ለእግዚአብሔር ለማስገዛት የምትፋጠን ሁን። በአምላኩ የሚታመን፣ ለፈጣሪው እራሱን የሰጠ፣ መንፈሱን ለጌታው ያስገዛ ሰው ሁሌም ህይወቱ የተረጋጋችና በሃሴት የተሞላች ነች። በዓላትን አስታኮ ስጋን ብቻ ለማስደሰት መሽቀዳደም፣ መንፈሳዊነትን ረስቶ በዓለም ዳንኪራ ለመሳተፍ መፋጠን፣ እድሜን ጨምሮ፣ ጤናን ሰጥቶ፣ ባርኮና ጠብቆ ለዚ ያደረሰን ፈጣሪ ዘንግቶ የስጋን ፍቃድ ብቻ ለመፈፀም መቻኮል አግባብ አይደለም። በደስታህም ሆነ በሃዘንህ ወቅት የፈጣሪህን አብሮነት አስብ። በደስታህ አመስግነው በሃዘንህም ተማፀነው። በምንም ሁኔታ ውስጥ ብትሆንም በቻልከው መጠን ለነፍስህ የሚበጃትን የአምላክህን ፍቃድ መጠበቅህን አንዳትዘናጋ።


ብርቱዎች ብቻ ይበረታሉ!
፨፨፨፨፨//////////፨፨፨፨፨
ጥሩ በሚባሉት ጊዜያት ማንኛውም ሰው ጥሩ ነው፤ በመልካሙ ጊዜ ብዙ ሰው ሰዎችን ለመርዳት አይቸገርም፣ እንዲሁም ጎበዝ ነው፤ ጠንካራ ነው፣ ማድረግ የሚፈልገውን ያደርጋል፣  በፈለገው ቦታ ይገኛል፣ የተመኘውን ያገኛል፣ የሃሳቡን ይሞላል፣ ውጥኑን ያሳካል፣ መርዳት ያለበትን ይረዳል። ነገር ግን ጊዜያትና ሁኔታዎች ሁሌም በጥሩነታቸው ላይቀጥሉ ይችላሉ። በእኛም ይሁን በሌሎች ምክንያት፣ መልካም የተባሉት ሁነቶች ወደ አስከፊና ወደማይመቹ አጋጣሚዎች ይቀየራሉ። ይህም ሁኔታ በሰዎች መሃል ትልቁን የህይወትና የማንነት ልዩነት ይፈጥራል። ወንፊት ስንዴውን ከእንክርዳዱ እንደሚለየው ሁሉ ይህም ወቅት ጠንካሮችንና ደካሞችን፣ ብርቱዎችንና ሰነፎችን የሚለይ ሁነኛ ወቀት ነው።

አዎ! ጀግናዬ..! ብርቱዎች ብቻ ይበረታሉ! መጥፎ በሚባሉት ጊዜያት ጠንካሮች ብቻ ይጎብዛሉ፤ አስከፊ በተባለ ጊዜ ብርቱዎች ብቻ ይበረታሉ፤ ጀግኖች ብቻ ይጀግናሉ፣ ይጋፈጣሉ፤ ይታገለሉ። ለጋሶች ብቻ ይለግሳሉ፤ መልካሞች ብቻ በጎ ያደርጋሉ፤ ቅኖች ብቻ ቀና ይሆናሉ። የእያንዳንዱ ሰው ጥንካሬ በማይቹ ሁነቶች ውስጥ የተመቻቸ ስፍራን በመፍጠር ይለካል። ፅናትህን የሚፈትን ትንሽ ነገር ሲገጥምህ ከተሰበርክ ምንም ከሌላው የሚለይህ ነገር የለም። እንደማንኛውም ሰው ፈተናዎች ሲመጡ ታቆማለህ፣ ወደ ኋላ ትመለሳለህ፤ እጅህን ትሰጣለህ፣ ትሰበራለህ፤ ትሸነፋለህ። ነገር ግን ከሽንፈትህ ማግስት ለአሸናፊነት እራስህን አዘጋጅ።

አዎ! ጥላቻህ ለብክነት ያጋልጥሃልና፤ ማድረግ ከምትችለው ይከለክልሃልና፤ አምኖ ከመቀበል ዘወትር በምሬት እንድትኖር ያደርግሃልና ደጋግ ጊዜያትን እንደምትወደው ሁሉ ክፉና መጥፎ ጊዜያትንም አምርረህ አትጥላ። በተመቻቸ ጊዜ ስታደርገው የነበረው ባልተመቸህ ሰዓት ለማድረግ ቀላል አለመሆኑ ግልፅ ነው። በብዙ የምትፈተነውም በዛን ሰዓት ነው።
ይብዛም ይነስም በሰውነቱ የችግርን ገፈት ያልቀመሰ፣ በፈተና ውስጥ ያላለፈ ሰው አይኖርም። አንተም የእኔ በምትለው መንገድ የሚመጥንህ ፈተናና ችግር ይገጥምሃልና እራስህን ይበልጥ አጠንክር፤ ሁሌም ነገሮችን እንዳመጣጣቸው ለመመለስ ተዘጋጅ። አንተን ብሎ መምጣቱ ስለሚያስፈልግህ ነውና "ለምን እኔን?" ለማለት አትቸኩል።


አዲሱን መንገድ ውደደው!

ከዚህ በፊት ያልተጓዝክበትን፣ ያልሄድክበትን፣ ያልመረጥከውን መንገድ ውደደው፤ ከአዲሱ ተሞክሮህ ጋር ትስስር ፍጠር። ያላደረካቸውን ነገር ግን ያመንክባቸውን የተለዩ ድርጊቶች ከልብህ ውደዳቸው፣ ፈልጋቸው፣ ተዳፈራቸው፣ ተላመዳቸው። አዲስ መንገድ የአዲስ ግኚት ቁልፍ ነው፤ የአዲስ ግኚት መጨረሻም የተሻለና ከፍ ያለ ውጤት ማስገኛ ነው። ከዚህ በፊት ያልተደረጉ፣ በህይወታችን ፈፅመናቸው የማናውቃቸው፣ ኬት አንስተው የት ሊያደርሱን እንደሚችሉ የማናውቃቸው አዳዲስ ተግባሮች የምርጫችን ውጤት፣ የፍላጎታችን መነሻ ከሆኑ የተሻለ ነገር የማስገኘት እድላቸው ከፍተኛ ነው። ፍቅር ውስጥ ጥርጣሬ የለም፤ መውደድና ፍረሃት አብረው አይሄዱም፤ ህልምና ስጋት አይጣጣሙም። አዲስ ነገር እስኪጀመር ሊያስፈራ ይችላል፣ ካልተጀመረ ግን ሁሉም ነገር በነበረበት መቀጠሉ አይቀርም። ፍረሃትህን የሚደመስስ፣ ስጋትህን የሚያስወግድ መውደድ ያስፈልግሃል።

አዎ! ጀግናዬ..! አዲሱን መንገድ ውደደው! ፍረሃትህን በፍቅሩ አሸንፈው፣ ስጋትህን በመውደድህ ርታው፤ በሩን በድፍረት ክፈተው። በነገሮች ላይ ያለህ አረዳድ ሲቀየር፣ እይታዎችህ ሲለወጡ፣ በአዳዲስ እርምጃዎችህ ማመን ስትጀምር፣ ውስጥህ በድፍረት ሲሞላ፣ የወደድከው ላይ ስታተኩር የተዘጉ መንገዶች ይከፈቱልሃል፤ የተለየው እይታህ ለተለየ ውጤት፣ የተለየው ተግባርም ለተሻለ ድል ያበቃሃል። ሁሌም አዲስ ተግባር ውስጥ አዲስ ልምድ፣ አዲስ ውጤት፣ አዲስ ተሞክሮ ይገኛል። ከባቢህን የምትቀይረው የተሻለ ነገር ፍለጋ ነው፤ አዲስ ሰዎች የምትተዋወቀው፣ አዲስ ወዳጅነት የምትመሰርተው፣ አዲሱን መንገድ የመረጥከው ማንነትህን ለማሻሻል፣ እራስህን ለማብቃትና ለመቀየር ነው። የዘመናት ጥረትህ ተጨባጭ ውጤት ካላመጣልህ በተለየ አቅጣጫ መንቀሳቀሱ ያንተ ድርሻ ነው።

አዎ! የወደድከው ነገር አሸናፊ ያደርግልሃል፤ ምርጫህ ለውጤታማነት ያበቃሃል፤ እምነትህ ወደፊት ያራምድሃል። ስንቶች ለማይወዱት ስራ ስንት መሱዓትነት እየከፈሉ ባሉበት ሰዓት አንተ ለወደድከው፣ ለመረጥከው፣ ላመንክበት አዲስ መንገድ መሱዓትነት መክፈል አያቅትህም። ፍቅርህ ብቻ ብርታት ይሆንሃል፤ ፍረላጎትህ ብቻ እምቅ አቅምህን ያወጣዋል፤ መውደድህ ብቻ ህይወትና ተግባርህን ያስተሳስራል። ለእራስህ ብርታት መሆን ከፈለክ፣ ድሎችህን ማክበር፣ በጥንካሬዎችህ መደነቅ፣ ለተሻለ ነገር መብቃት ከፈለክ በአዲስ ወኔ፣ በአዲስ ፍቅር፣ በተለየ መንገድ ማሸነፍ ጀምር። ትናንት በነበርክበት መንገድ ምንም አይነት ስሜት ሰጪ አዲስ ግኚት ካልተገኘ በድፍረት የወደድከውን መምረጥ ያንተ ሃላፊነት ነው። ከልበህ የወደድከውን፣ ከመንፈስህ ጋር የተዋሃደውን፣ ስሜት የሚሰጥህን፣ ትልቅ ትርጉም እንዳለው የተማመንከውን ተግባር ከጀመርክ የምታቆምበት ምክንያት አይኖርህም። መውደድህን ሃይልህ፣ ፍቅርህን ብርታትህ አድርገው፤ ለወደድከው እስከ ጥግ መጋፈጥንም ከማንነትህ ጋር አዋህደው።


አይንህን ግለጥ!

ወደኋላ ዞረህ እራስህን ስትመለከት ምን ይታይሃል? ብዙ ርቀት ወደፊት ተጉዘሃል ወይስ እዛው አካባቢ በቅርብ ርቀት ነህ? ሃሳቦችህን በሚገባ አሳክተሃል ወይስ ከነጭራሹ ትተሃቸዋል? አምስት አመታትን ወደኋላ ስትቆጥር የነበሩ ችግሮችህ ዛሬም አሉ ይሆን? ያኔ ሲያስጨንቁህ የነበሩ ጉዳዮችስ ከምን ደረሱ? በጊዜ ፍጥነት ነገሮች በቶሉ ይቀያየራሉ። የሆነ ጊዜ እራስን ማወቅ፤ እራስ ላይ መስራት፣ እራስን ማዳን፤ ከእራስ በላይ ለሰዎች መኖር የሚባለውን ነገር አናውቀውም ነበር። ዛሬ ግን ህይወት በእራሷ በተግባር እያስተማረችን ነው። ዝም ብሎ በዘፈቀድ መኖር፣ ያለምንም እቅድና አላማ ምድር ላይ መመላለስ ህይወትን የባሰ ከባድና ውስብስብ እንደሚያደረግው እራሷ ህይወት በሚገባ አስረድታናለች።

አዎ! ጀግናዬ..! አይንህን ግለጥ፤ በአፅንዖት መመልከት ጀምር፤ እራስህን በሚገባ መርምር። ከአመታት በፊት የነበርክበት ስፍራ ነህ ወይስ እየተጓዝክ ነው? ዛሬም ባለፉት አመታት ችግሮችህ ተከበሃል ወይስ ከእንቅስቃሴህ ጋር ከተቀየሩ አዳዲስ ችግሮችህ ጋር ነህ? የት ነበርክ? የትስ አለህ? ምን ይዘሃል? ከምንስ ደርሰሃል? እድሜ እስከጨመረ ድረስ የፊት ገፅታ፣ የሰውነት አቋምና ድምፅ መቀየሩ አይቀርም። ዋናው ቁብነገር ግን እርሱ አይደለም። በግል ስብዕና፣ በአመለካከት፣ በአስተሳሰብ ልኬት፣ በማስተዋል ችሎታ እራስህ ላይ የተመለከትከው ለውጥና እድገት ምንድነው? ምናልባት በቻልከው መጠን ትጥር ይሆናል፤ ብዙ ስራ እየሰራህ፣ ብዙ ወዳጆችህን አፍርተህም ይሆናል። ሂደቱ ካልሰራህ ግን እራስህ ቆም ብለህ ማሰብ ይጠበቅብሃል።

አዎ! ምንም ቢሆን አንተን የማይቀይር፣ እሴት የማይጨምርብህ፣ ዋጋህን ከፍ የማያደርግ፣ ካለህበት ቦታ ፈቀቅ የማያደርግህ ጥረት ምንም ትርጉም የለውም። ከፍጥነቷ የተነሳ ህይወትን ትናንት ብለን ዛሬ ለማለት ጊዜ ልናጣ እንችላለን፤ ያለምንም ቁብነገርና አለማ የሚደረግ ሩጫ ደግሞ ጠዓም እያሳጣት በብዙ እጥፍ ያሳጥራታል። የመኖርህን ትርጉም ለመረዳት ጊዜ አታጥፋ፤ አይንህን በቶሎ ግለጥ፤ እርሱን ለማወቅ ማድረግ የሚጠበቅብህን ሁሉ አድርግ። በዚህ ጉዳይ ቀጠሮ ሰጠህ ማለት ህይወትህን ሙሉ፣ ትርፋማ፣ አስደሳችና በእግዚአብሔር የተወደደ ለማድረግ እያቅማማህ እንደሆነ እወቅ። ህይወትህን መቀየር እንደምትችል፣ የተሻለ ስፍራ ማድረስ እንደምትችል ማወቅህ ብቻ በቂ አይደለምና ውስጥህ የሚመላለሰውን ግሩም ሃሳብ በመተግበር በመግለፅ እውቀትህን ተግባራዊ አድርገው።


ራሳችሁን አትግለፁ!

ብዙዎች ምን ያስባሉ? ራሳቸውን ከልክ በላይ ስለገለፁ ሰዎች የሚረዷቸው ይመስላቸዋል፣ ደጋግመው ስለራሳቸው ስላወሩ ሰው የሚቀበላቸው ይመስላቸዋል፣ የራሳቸውን ችግር ሳይፈቱ የሌሎችን መፍታት እንደሚችሉ ያስባሉ። ነገር ግን ያለው እውነት ከዚህ የተለየ ነው። የሰው ልጅ የሚረዳችሁ ብዙ ስላወራችሁ ወይም ብዙ ስለ ለፋችሁ ሳይሆን ሊረዳችሁ ሲፈልግ ብቻ ነው፤ የሰው ልጅ ከጎናችሁ የሚቆመው ስላሳዘናችሁት ወይም ስር ስሩ ስላላችሁ ሳይሆን በአስፈላጊነቱ ሲያምን ብቻ ነው። ከሰው ጋር ባላችሁ ግልፅ ያልሆነ ግንኙነት ምክንያት ራሳችሁን ስቃይ ውስጥ አትክተቱ፣ ከልክ በላይ ብዙ ነገር ከሰው እየጠበቃችሁ ራሳችሁን አታስጨንቁ። የትኛውም ገደብ የሌለው ግንኙነት መጨረሻው መጎዳዳት እንደሆነ አስተውሉ። ማንንም ለመቆጣጠር አትሞክሩ፣ ማንም እንዲቆጣጠራችሁም አትፍቀዱ። ግንኙነት ሊኖራችሁ የሚችለው ከምታውቁት ሰው ጋር ብቻ እንዳልሆነ እወቁ። በየትኛውም ማህበራዊ ሚድያ የምታውቁትን ሰው ከልክ በላይ እየተከተላችሁና በእርሱ ሃሳብ እየተመራችሁ ከሆነ መጨረሻችሁ እንደማያምር አትጠራጠሩ። መቼም ቢሆን የእኔ የምትሉት አመለካከትና አቋም ሊኖራችሁ አይችልም፣ እንዴትም ቢሆን የምትኮሩበት ደረጃ ላይ ልትገኙ አትችሉም።

አዎ! ራሳችሁን አትግለፁ፤ የምታውቁት ሰው ሁሉ እንዲያውቃችሁ አታድርጉ። ፍላጎታችሁን የሚያውቅ፣ ውስጣችሁን የተረዳ፣ የሚያስደስታችሁን ነገር የሚያውቅ ሰው እናንተን ለመቆጣጠር ትልቅ ነገር ማድረግ አይጠበቅበትም። የምትፈልጉትን ያቀርብላችኋል እናንተም የራሳችሁን ህይወት መኖር ትታችሁ እርሱን መከተል ትጀምራላችሁ፣ ትኩረታችሁን ከራሳችሁ ላይ አንስታችሁ አርሱ ላይ ታደርጋላችሁ፣ ሁን ተብሎ ለሚሰጣችሁ ጊዜያዊ ደስታ ብላችሁ የወደፊት ህይወታችሁን መሱዓት ታደርጋላችሁ። ሳታውቁት ትኩረታችሁን እየሸጣችሁት ነው፣ ሳይገባችሁ የሆነ አካል ባሪያ እየሆናችሁ ነው፣ እንዲሁ በደፈናው ወደማታውቁት የህይወት መስመር እየገባችሁ ነው። ማንነታችሁ በታወቀ ቁጥር ለብዙ ሀሳቦች እየተጋለጣችሁ ትመጣላችሁ፣ ፍላጎታችሁን ባሳያችሁ መጠን ተከታይ ብቻ የመሆን እድላችሁ እየሰፋ ይመጣል። በምንም መንገድ ሊያነቁዋችሁና ለተሻለ ስፍራ ሊያበቋችሁ የማይችሉትን ከዛም በላይ የማይመለከቷችሁን ሰዎች ሌትከቀን ትከታተላላችሁ ቦሃላ ግን ራሳችሁን ትወቅሳላችሁ።

አዎ! ጀግናዬ..! አሰየታደንክ ነው፣ እየተፈለክ ነው። "እንዴት? ለምን?" ካልክ ምክንያቱም ሲበዛ ግልፅ ነህ፣ አዕምሮህን አደባባይ አስጥተሀዋል፣ የውስጥ ገመናህን ለማንም አሳይተሃል። የምትታደነውም ለሚሰጥህ ነገር ምንም የማትከፍል ከሆነ የምትሸጠው አንተ ስለሆንክ ነው። ግልፅ መሆን አለብኝ ካልክ የሚጠቅምህን አቋም ብቻ ግለፅ፣ ማንነቴ ሊታወቅ ይገባል ካልክ የሚጥልህን ማንነት አደባባይ አታውጣ። አደጋ ላይ ነህ ራስህን ጠብቅ፣ ህይወትህ በሰው ቁጥጥር ስር እየገባ ነው ፈጥነህ ራስህን አድን። አሁን የፈለከውን ነገር ሁሉ እያደረክ ያለህ ሊመስልህ ይችላል፣ ምናልባትም ዛሬ በምርጫህ እየኖርክ እንደሆነ ሊሰማህ ይችላል ነገር ግን አሁንም እውነታው ካልገባህ ቀስበቀስ ህይወትህ ካንተ ቁጥጥር ስር እየወጣ እንደሆነ አስተውል። ጊዜ አታጥፋ ከእያንዳንዱ ነገር ተማር። ከሰው ተማር፣ ከተፈጥሮ ተማር፣ ከህይወት ተማር፣ አንተን ማዕከል አድርገው ከሚሰሩ ፕሮግራሞች ተማር፣ ዘመንህን ሙሉ በመዝናናትና በጫወታ ጊዜህን አታባክን። ከመጣብህ አደጋ ራስህን አድን፣ በዙሪያህም ላሉት ከለላ ሁናቸው።


በእድልህ አትተማመን!

መዳረሻህ በእድልህ አይወሰንም፤ ስኬትህ በአጋጣሚ አይመጣም፤ ልዕልና እንዲሁ ከአየር ላይ የሚታፈስ አይደለም።  በውሳኔህ ልክ ህይወት የምትሰጥህ ስጦታ አለ፤ በምርጫህ አኳሃን የምትደርስበት ስፍራ ይኖራል። በእድል የሚያምን ስኬት የተባለውን አስደሳችና ትርጉም ሰጪ ህይወት ሊያገኝ አይችልም። በአጋጣሚ ነገሮች ሊመቻቹልህ ይችላሉ፤ እንደ እድል ከቤተሰብህ ባገኘሀው ንብረት ልትከብር ትችላለህ፤ ሎተሪም ሊደርስህ ይችላል። ነገር ግን ያ ሁሉ በአጋጣሚ የመጣው ነገር በአጋጣሚ ቢጠፋ ዳግም የምታገኝበት እድልህ እጅጉን ያነሰ ነው። መርጠህ የመጣህበት ስትመለስ ሊጠፋብህ አይችልም። በአጋጣሚ የገባህበት ስፍራ ግን መውጫውም አዳጋች ነው። ምርጫህ ውጤት እስኪያመጣ ድረስ ከባዱ መንገድ ነው፤ እድል ግን ከውጤቱ ቦሃላም ሆነ በፊት ከባድ ሁኔታ መፍጠሩ አይቀርም።

አዎ! ጀግናዬ..! በእድልህ አትተማመን፤ አጋጣሚ ላይ አትደገፍ። በምትኩ ለምርጫህ ትኩረት ስጥ፤ በውሳኔህ ተማመን፤ ለፍላጎትህ የምትከፍለውን መሱዓትነት በሚገባ ጠንቅቀህ እወቀው።  ለፍተው፣ ደክመው፣ ጥረው ግረው በተቀየሩ ሰዎች አትቅና። ከቻልክ የእነርሱን መንገድ ምረጥ፤ ካልሆነ ግን ስለ እድለኝነታቸው ደጋግመህ አታውራ። ታሪክ የሚፃፈው በእድልህ ሳይሆን በመረጥከው ምርጫ ነው። እድል ላይቀናህ ይችላል፣ የሚልቀው ምርጫህ ግን ሁሌም በእጅህ፣ ሁሌም በቅርብህ ነው። የያዝከውን ይዞ መቀመጥ ምርጫ ነው፤ ገና ለገና የሚመጣውን መጠባበቅ የአጋጣሚ ምርኮኛ፣ የእድል ተጧሪ መሆን ነው። ገና ለገና እንደሚፈጠር በሚታሰብ መላምት ህይወትህ ወደፊት ሊራመድ አይችልም። ምርጫህን በጊዜ ካልተጠቀምክ ኪሳራህ በየጊዜው እየጨመረ ይሔዳል።

አዎ! ገበሬ አምኖ ዘሩን ይዘራል፣ ፍሬውንም ያጭዳል። ያለመዝራትና መንግስት እንደሚረዳው የመጠበቅ ምርጫ ግን ነበረው። ይህ ግን የሚሆነው እድለኛ ከሆነ ብቻ ነው፤ ካልሆነ ግን እድሉን እያማረረ ለመኖር እራሱ ላይ መፍረዱ የግድ ነው። "እድሌ ጠማማ ነው፤ እኔ የነካውት ነገር አይበረክትም፤ እድለኛ አይደለሁም።" እያልክ እጅህን አጣጥፈህ የመቀመጥ ሙሉ ምርጫ አለህ፤ በዛው ልክ ጠማማውን እድልህን ለማቃናትም በድፍረት ወደ ተግባር የመግባት ምርጫ አለህ። እድልህን እርሳውና በምርጫህ ላይ ህይወትህን ገንባ፤ አጋጣሚዎችን መጠባበቅ አቁምና በውሳኔዎችህ አጋጣሚዎችን መፍጠር ጀምር። አብዝተህ ስለጠበከው የሚመጣው አጋጣሚ ሳይሆን ያንተ ብክነት እንደሆነ ተረዳ። በምጫህ ማንነትህን አስከብር፤ በውሳኔህ የወሳኝ አጋጣሚዎች ባለቤት ሁን።


በቀላችሁን መልሱ!

ብትፈልጉም ባትፈልጉም ማንም ቆሞ አይጠብቃችሁም፣ ተመኛችሁም አልተመኛችሁም ምንም ነገር በነበር አይቀጥልም። ያለፈው አልፏል፣ የሆነው ሆኗል፣ የሚሆነውም ወደፊት ይሆናል። በእናንተ ምርጫ ሳይሆን መሆን ስላለበት ይሆናል። በገዛ ፍቃዳችሁ ዓለም እንድትገፋችሁ፣ በምርጫችሁ ምድር ፊቷን እንድታዞርባችሁ፣ ሰዎችም እንዲርቋችሁ አታድርጉ። ህይወትን እንድ ህይወት ኑሯት፣ የግል ዓለማችሁን ሰፋ አድርጋችሁ ተመልከቷት፣ ያመለጣችሁን የተሻለ ኑሮ የመኖር እድል አሁን መበቀል ጀምሩ። ነገሮችን ሁሉ ግላዊ እያደረጋችሁ ራሳችሁን አታሰቃዩ። ከዚህ ቀደም የማትፈልጉትን ህይወት ስትኖሩ የነበራችሁት እናንተ ብቻ አይደላችሁም። ከዛ ህይወት ግን እናንተ ብቻ መውጣት ትችላላችሁ፣ ያንን ህይወት ግን እናንተ ብቻ ልትቋጩት ትችላላችሁ። በእርግጥ የሰው ህይወት አይመለከታችሁም ነገር ግን ውድቀትና ችግራችሁን ግላዊ ካደረጋችሁ በደምብ ይመለከታችኋል። በምንም ጉዳይ ከልክ በላይ ማዘን፣ መሳቀቅ፣ መጨነቅ አያስፈልግም። ከእናንተ አቅም በላይ የሆነን ነገር አምናችሁ ተቀበሉት፣ የእናንተ ጉዳይ ያልሆነን ነገር ተውት። ብዙ ጥላችሁ ልታልፉት የሚገቡ የህይወት ፈተናዎች እያሉባችሁ ከሰው ጋር ተጨማሪ ግግብግብ ውስጥ አትግቡ።

አዎ! የሰው ሳይሆን በሙላት የመኖር በቀላችሁን መልሱ፣ የክህደት ወይም የመገፋት ሳይሆን ከፍ ብሎ የመኖር በቀላችሁን፣ በስኬት መንገድ የመመላለስ አምሮታችሁን፣ ተርፎ ተትረፍርፎ የመኖር ምኞታችሁን መልሱ። ሰው መጣ ሰው ሄደ፣ አንዱ ጠቀማችሁ አንዱ ጎዳችሁ፣ በአንዱ አተረፋችሁ በአንዱ ከሰራችሁ፣ አንዱ አስደሰታችሁ አንዱ አሳዘናችሁ። ህይወት ግን በዚህ ነገር አትቆምም። ፈጣሪ የፈቀደው መሆኑ ላይቀር የሰውን በደልና ክፋት እየቆጠራችሁ ልባችሁን አታስጨንቁት፣ ከሆነላችሁ መልካም ነገር በላይ የሆነባችሁን መጥፎ ነገር አትቁጠሩ። ሰው እያሳደዳችሁ ህይወታችሁን በሚገባ ሳትኖሩ እንዳታልፉ፣ እድሜ ልካችሁን ስለሰው ጉዳይ እየተጨነቃችሁ የራሳችሁን ህይወት ባዶ አታድርጉት። መበቀል ካለባችሁ ሰውን ሳይሆን ራሳችሁን ተበቀሉ፣ መናደድ ካለባችሁ በሰው ሳይሆን በራሳችሁ ጥፋት ተናደዱ። ሰው ላይ ጣት መጠቆም እናንተን ጠንካራ ወይም ፃድቅ አያደርጋችሁም፣ የሆነ አካል መርጣችሁ መውቀስ ለእናንተ የሚያመጣላችሁ የተለየ ነገር የለም። ትርፍ ያለው ህይወት መኖር ከፈለጋችሁ፣ ትርጉም በሚሰጣችሁ መንገድ መመላለስ ካሰባችሁ እለት እለት ራሳችሁን ውቀሱ፣ ከባዶ ወቀሳም በላይ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ራሳችሁን አስጨንቃችሁ ፍሬ አፍሩ።

አዎ! ጀግናዬ..! ፍፁም ነፃ አውጪው በቀል በሰው ላይ የምትወጣው በቀል ሳይሆን ራስህ ላይ የምትወጣው በቀል ነው። ማንኛውንም የጎዳህን ሰው ዳግም ብትጎዳው በሰውዬው ጉዳት የምታገኘው አንዳች ትርፍ የለም። ይልቅ የራስህን የቀደመ ጥፋትና በደል ሽረህ ራስህን በተሻለ መንገድ ብትበቀል ከአንተ በላይ የሚጠቀም አካል የለም። በቀል ሁሌም አሉታዊ ተግባር አይደለም፣ በቀል ሁሌም ጥፋት አይደለም። ራስህን ተበቀልክ ማለት ያመለጡህን ጥሩ የህይወት አጋጣሚዎች ተበቀልክ ማለት ነው። ባለፈ ጊዜ ላይ ቆመህ መጪውን ጊዜ ማስተካከል አትችልም። የትኛውም ስህተትም ሆነ ጥፋት የሚታረመው ከአሁን ጀምሮ ባለው መጪ ጊዜ ነው። ፊት ኋላህን አስተውል፣ ግራ ቀኝህን ተመልከት፣ መጣል መነሳት ያሉባቸውን ነገሮች ለይ፣ ቀና ብለህም አዋጩን ትክክለኛ መንገድ ተከተል። በተበዳይነት እሳቤ ራስህን እየወቀስክ አትኑር። ለራስህ ክብርና ዋጋ ስትል በፍፁም የጎዱህ ፊት ዝቅ አትበል፣ ከእነርሱ በላይ ራሳን ከፍ የማድረግ ትልቅ አጀንዳ እንዳለህ በተግባር አሳይ።


ጉዞ ላይ ናችሁ!

ያላችሁበት ሁኔታና ቦታ የማይመች፣ አሰልቺ፣ ለእናንተ የማይመጥንና “ራሴን እዚህ ቦታ አገኘዋለሁ ብዬ አላስብም ነበር” የሚያሰኝ ቢሆንም፣ “እንኳን በዚያ ሁኔታ አለፍኩ” የምትሉበትን ሁኔታ መፍጠር ትችላላችሁ፡፡ ያንን ለመፍጠር ግን በጉዞ ላይ መሆን አለባችሁ፡፡

1.  ትምህርት፡- ካላችሁበት ሁኔታና ቦታ የምታገኙትን ሁሉ ትምህርት ውሰዱ፡፡ አንዳንድ የሕይወት ትምህርቶች በሁኔታው ካላለፋችሁ በስተቀር በፍጹም አትማሯቸውም፡፡ አንድ ልምምድ ጎጂን የባከነ የሚሆነው ትምህርት ካልተገኘበት ብቻ ነው፡፡

2.  ውሳኔ፡- ካላችሁበት ሁኔታና ቦታ ለመውጣት ተገቢውን ውሳኔ አድርጉ፡፡ ዋናው ነገር የላችሁበት ሁኔታ ሳይሆን በዚያ ላለመቆየት ያላችሁ ምርጫና ውሳኔ ጉዳይ ነው፡፡

3.  እቅድ፡- ካላችሁበት ሁኔታና ቦታ የምትወጡበትን ተገቢውን እቅድ አቅዱ፡፡ ካላችሁበት ሁኔታ ለመውጣት መወሰን ለብቻው በቂ አይደለም፡፡ በሚገባ የታሰበበትና ተግባራዊ ሊሆን የሚችልን እቅድ ከጊዜ ገደብ ጋር ማስቀመጥ የግድ ነው፡፡

4.  እንቅስቃሴ፡- ካላችሁበት ሁኔታና ቦታ ለመውጣ ተገቢውን እቅስቃሴ አድርጉ፡፡ ከትምህርቱ፣ ከውሳኔውና ከእቅዱ በኋላ፣ ባቀዳችሁት መሰረት ወቅቱን ጠብቃችሁ መንቀሳቀስ ከቻላችሁ የላቀ ማንነት ይዛችሁ መውጣታችሁ አይቀርም፡፡

ከላይ የተጠቀሱትን ተግባራዊ እውነታዎች ከተለማመዳችሁ ያላችሁበት ቦታ በእርግጥም የምትማሩበት፣ የምታድጉበትና ለነጋችሁ  በስላች የምትወጡበት ትክክለኛ ሁኔታና ቦታ ይሆንላችኋል፡፡


ውብ ነሽ!

ከሰዎች ጠብቀሽ ላታገኚው ትችያለሽ፣ በወዳጆችሽ መባል ፈልገሽ አልተባልሽም ይሆናል፣ የተለየ ቦታ በሰጠሻቸው ሰዎች እንዲሁ የተለየ ስፍራ አልተሰጠሽም ይሆናል። ነገር ግን አንድ ነገር አስታውሺ የትም ሳትሔጂ፣ ማንንም ሳትመስዪ፣ ከማንም ሳትወዳጂ፣ ማንም ሳይኖርሽ፣ ምንም ሳትጨምሪ እንዲሁ ውብ ነሽ። ውበትሽም የግድ በሰዎች ሊነገርና ሊደነቅ አይገባም። ዛሬ ውብ እንደሆንሽ የነገረሽ ሰው ነገም ውብ ስለመሆንሽ እንደሚመሰክር እርግጠኛ መሆን አትችይም። አዳማቂ የማይፈልገው ውበትሽ ከትምህርት ደረጃሽ የመጣ አይደለም፣ ከስራሽ የመጣ አይደለም፣ ከቤተሰቦችሽ የመጣ አይደለም፣ ከጓደኞችሽ የመጣ አይደለም። የውበትሽ ምንጭ የአምላክሽ ልጅ መሆንሽ ነው፤ የውበትሽ መነሻ ሴትነትሽ፣ አንቺነትሽና ጥልቁ ማንነትሽ ነው።

አዎ! ጀግኒት..! ውብ ነሽ! እስካከበርሽው ድረስ ሴት በመሆንሽ ብቻ ቆንጆ ነሽ፤ አሁን ያለሽበት ስፍራ በመገኘትሽ ብቻ ብርቱ ነሽ፣ እንዳቅምሽ ስለተንቀሳቀስሽ ብቻ ጠንካራ ሴት ነሽ። አለም የሚያደንቅልሽን ሳይሆን በአምላክሽ መንፈስ የተቃኘውን ውስጣዊ ውበትን የሚያዩ፣ የስብዕናሽን ጥልቀት የሚመረምሩ፣ እንዲሁ አይተው የሚማረኩብሽ ሰዎች እስኪከቡሽ ድረስ ውበትሽን ለእራስ ተናገሪ፣ ጥንካሬሽን ደጋግመሽ ለእራስሽ መስክሪ። የሚረዱሽን መምረጥ፣ የማይረዱሽንም የመተው ምርጫ አለሽ። ማንም እንዲያምንብሽ ዝቅ ብሎ የመለመን ግዴታ የለብሽም። አንደኛው ውበትሽ ክብርሽ እንደሆነ አስታውሺ። ለእራስሽ ብርታትና ሃይል መሆን ትችያለሽ፤ ለእራስሽ የሰጠሽውን ቦታ በመቀየር ብቻ አካባቢሽንና የተሰጠሽን ቦታ መቀየር ትችያለሽ።

አዎ! ጀግናዬ..! ወንድነት በእራሱ ለፈተና የሚያዘጋጅህ ቢሆንም በጥንካሬህ ግን አትጠራጠር። በህይወት እስካለህ ቀላል ነገር አገኛለሁ ብለህ እንዳታስብ። ከምድር በላይ አንተ ዋጋህን ጨምረህ፣ ይበልጥ ጠንክረህና ተሻሽለህ እስካተገኘህ ድረስ ሁሉም ነገር ከባድ ነው። እራስህን ለመስራት አትስነፍ፣ አቅምህን ከማጎልበት ወደኋላ አትበል፣ ምንም ድጋፍ ባታገኝ ድጋፍህ ወንድነትህና ፈጣሪ እንደሆነ አስታውስ። ወንድነት በእራሱ የሃላፊነት መለኪያ ነው። አሁንም ሃላፊነት አለብህ፣ ወደፊትም እንዲሁ ሃላፊነትህ ይጨምራል። ምንም ባይኖርህ፣ ማንም ባይጠጋህ እግዚአብሔር አምላክህን ብቻ ስለያዝክና ወንድ ስለሆንክ ጠንካራ ነህ፣ ብርቱ ነህ። ለእራስህ አይደለም ለምትወዳቸውና ለሚወዱህ ሁሉ ዋጋ ከፍለህ ህይወታቸውን የመቀየር አቅሙ አለህ። እራስህን ጠበቅ፣ እራስህን ተንከባከብ፣ የወንድነትህን ልክ ለእራስህም አሳየው።


በልብ ግዘፉ!

ሳታስቡት ቀን ይጥላችኋል፣ እንዲሁ ከመቅፅበት ነገሮች ይበላሹባችኋል፣ በአጋጣሚ በሰውም ሆነ በሁኔታዎች ተጎጂ ትሆናላችሁ፣ ብቻችሁን ፊትለፊት መጋፈጥ ላለባችሁ ችግር ትጋለጣላችሁ። አውቃችሁ አልገባችሁበትም ነገር ግን ከዚህ አጣብቂኝ የመውጣት ግዴታ ይኖርባችኋል፣ ፈልጋችሁ አልተፈተናችሁም ነገር ግን ፈተናውን የማለፍ ግዴታ አለባችሁ። ሁሉን ነገር እንደ አመጣጡ የሚመልስ ማንነት በአንዴ አይገነባም፣ ከሁኔታዎች በላይ የሆነ ስብዕና በትንሽ ጊዜ አይመጣም። ልባችሁ ትንሽ ሲሆን በትንሹም በትልቁም ነገር ላይ ለመፍረድ ትቸኩላላችሁ፣ የማስተዋል አቅማችሁ አናሳ ሲሆን ከራሳችሁ በላይ የሰውን ጉድፍና ድክመት መመልከት ትጀምራላችሁ፣ ያልተሰራ ማንነት ሲኖራችሁ ዝቅ ማለትን ትጠየፋላችሁ፣ ንቀትና እብሪት ይነግስባችኋል፣ በሰው ላይ የበላይነታችሁን ለማሳየት ትደክማላችሁ፣ ሁሉም ሰው እንዲወዳችሁና እንዲቀበላችሁ ትጠብቃላችሁ፣ ክፋትን በላቀ ክፋት፣ መጎዳትንም በሌላ ጉዳት ለመመለስና ለመሻር ትሞክራላችሁ። ስታድጉ ሁሉም ነገር ድካም እንደሆነ ይገባችኋል፣ ትንሽ መብሰል ስትጀምሩ ጥሩ ስለሆናችሁ ብቻ የሚወሰድባችሁ ነገር እንደሌለ ትረዳላችሁ።

አዎ! በልብ ግዘፉ፣ በሃሳብ እደጉ፣ ራሳችሁን በማስተዋል አንፁ፣ በትምህርት ከፍ በሉ፣ ለጥበብ ልቦናችሁን ክፈቱ፣ ብስለትን በጊዜ ተለማመዱ። እውቀት ስም ያስጠራል፣ ተፈላጊና ተወዳጅ ያደርጋል፣ ጥበብ ግን ያነግሳል፣ ጥበብ ችግር ፈቺና እንቁ ሰው ያደርጋል። ልባችሁን ለጥበብ ክፈቱ፣ ውስጣችሁን ተነግሮ በማያልቅ መንፈሳዊ እውቀት ሙሉት፣ ሁሉም ሰው የሚመኘውን ፅኑ ማንነት ገንቡ። ማድረግ እየቻላችሁ እናንተን የሚጠቅም ቢሆን አንኳን ሰውን የሚጎዳ ስለሆነ ብቻ የማታደርጉት ነገር ይኑር። ከማንኛውም ሰው ጋር የምትወዳደሩት በሚታየው ስኬት፣ ንብረት ወይም ገንዘብ ሳይሆን፣ በማይታየውና በመልካም ምግባሮች በሚገለጠው ትልቁ ልባችሁ ይሁን። ልባቸው ትልቅ የሆኑ ሰዎች ቅንኖች ናቸው፣ ራሳቸውን የሚያውቁ፣ የሚፈልጉትን የሚያውቁ፣ ህይወትን በተለየ መንገድ የተረዱና እንዴት ክብራቸውን ሳያጡ ከሰው ጋር መኖር እንደሚችሁ የተረዱ ሰዎች ናቸው። ልባችሁን ዘግታችሁ ራሳችሁን አታስጨንቁ፣ ቀለል ብላችሁ ቀላል ህይወት ኑሩ።

አዎ! ጀግናዬ..! በማይሆን መንገድ አዕምሮህን አትወጥረው፣ በአጉል ልክ አልባ የክፋት ሃሳብ ልህን አታስጨንቃት። ትልቅ ሆነህ ትንሽ ስራ አትስራ፣ እያወቅክ በሚያጠፋህ መጥፎ ምግባር አትወጠር። አንተ አሳልፈህ ካልሰጠሀው ያንተን ሰላም የሚቀማህ ሰው የለም፣ አንተ ካልፈቀድክ ማንም ከታላቅነት ማማህ ላይ ሊያወርድህ አይችልም። ለሰው ብዙ አድርገህ ምላሽ የጠበቅበትን ጊዜ አስታውስ፣ አንተ መልካም ሆነ በክፉ ሰዎች የተጎዳህበትን ወቅት አስታውስ፣ ብዙ ሰጥተህ ባዶ እጅህን የቀረበትን ሰዓት አስታውስ። ትልቅ ሰው የሚሰጠው ተቀባዩን ለመጥቀም ሳይሆን ራሱን ለመጥቀም ነው። ካንተ የሆነው ነገር በቅንነት ከሆነ ትልቁ ስጦታህና ሽልማት ውስጣዊ ሃሴት ነው። ልብህ ብሩህ ሆኖ ሳለ የጨለማን ሃሳብ አታስብ፣ ተስፋ እያለህ የተስፋ ቢስ ሰው ተግባርን አትፈፅም። ለሰው ለመድረስ ከመድከምህ በፊት አስቀድመህ ራስህን ከመጥፎ ትርክቶችና ኩናኔዎች አድን። ለራስህ መሆን ሰትችል ለሁሉ መድረስ ትችላለህ፣ ራስህን ሰትጠቅም የምትፈልገውን ሰው መጥቀም ትችላለህ። ያንተ እያረረ የሰው በማማሰል አትጠመድ። ምንምያህል ደግና መልካም ሰው ብትሆን ራስን ከማዳን የሚቀድም ሌላ በጎ ስራ እንደሌለህ አስታውስ።


እርሱን ታምኜ እወጣለሁ!

ከራስ ጋር ንግግር፦ " አዎ! እርሱን ታምኜ፣ እርሱን አምኜ፣ በእርሱ ተደግፌ አወጣለሁ እገባለሁ፣ አምላኬን ይዤ ባህሩን እሻገራለሁ፣ አውሎ ንፋሱን አልፈዋለሁ፣ ፈተናዬን እፈትነዋለሁ፣ ችግሬን አስቸግረዋለሁ። እንደማንኛውም የሰው ልጅ ትልቅ ራሃብ አለብኝ፣ እንደ ማንኛውም ሰው ይጠማኛል። መንፈሴ ይራባል፣ ነፍሴ ትጠማለች። መንፈሴም የሚጠግበው፣ ነፍሴም የምትረካው አምላኳን ያገኘች እለት ነው፣ በእርሱ ጥላ ስር የተከለለች እለት ነው፣ ከስጋዋ በላይ ሆና ለእርሱ የተገዛች እለት ነው። ትናንተ ስታገል ነበር፣ ዛሬም እየታገልኩ ነው፣ ነገም እንዲሁ ትግሌ ይቀጥላል። ሲሆን ሲሆን ግን ያለፈው ትግሌ በዓለም ለመድመቅ፣ ስጋዬን ለማድመቅ፣ ክብሬንም ለመጨመር ቢሆንም ከአሁን ቦሃላ ግን ድካሜ ሁሉን ነፍሴን ለማጉላት፣ መንፈሴን ለማርካት፣ አምላኬንም ለማስደሰት እንዲሆን እፈልጋለሁ። ባልናገረውም ነፍሴ ግን እሱን ታምናለች፣ እንዲህ በቃላት ባልዘረዝረው ውስጤ ግን በእርሱ ፍቅር ተማርኳል። እርሱን አምኜ ወጥቼ አፍሬ አላውቅም፣ እርሱን ተማምኜ ወጥቼ አንገት ደፍቼ አላውቅም። እርሱን ሳስብ ልቤ ትልቅ ነው፣ ፍቅሩን ለመለካት ስሞክር መለኪያ አላገኝለትም።

አዎ! እርሱን ታምኜ እወጣለሁ፣ አምላኬን ታምኜ እገባለሁ። መውጫና መግቢያዬን የሚጠብቅልኝ ድንቅ መካር ሃያል ጌታ አለኝ። ብዙ ክፉ ነገር ሲናገር ያላፈረው አንደበቴ የአምላኩን ድንቅ ስራ መናገር ክብሩ እንጂ እፍረቱ አይደለም። ኬት አንስቶ የት እንዳደረሰኝ፣ ከምንአይነት ማንነት እንደቀየረኝ፣ እንዴት አድርጎ ዳግም እንዳበጃጀኝ እኔና እርሱ ብቻ እናውቃለን። ለዘመናት ያደረገልኝን ሳልመሰክር ቆይቼያለሁ፣ ለዓመታት የሚሰጠኝን ሁሉ እንደ ግዴታ ስቆጥርበት ሰንብቼያለሁ። ከረፈደም ቢሆን አሁን ፍቅሩ ገብቶኛል፣ ጊዜው ከሔደም ቢሆን ማዳኑን ተመልክቼያለሁ። በስኬቴ ውስጥ ፍቅሩ አብሮኝ ነበር፣ በውድቀቴ ውስጥም እንዲሁ ፍቅሩ ነበር። "አሁን ተሳክቶለታል፣ ነገሮች ሁሉ ሆኖለታል የእኔ እርዳታ አያስፈልገውም በራሱ መንገድ ይሒድ" ብሎ ትቶኝ አያውቅም። "አሁን ወድቆል፣ የዲያብሎስ መጫወቻ ሆኗል፣ ኀጢአት ሰልጥኖበታል፣ አይነ ልቦናው በፍቅረ ነዋይ ታውሯል፣ ራሱን ለዓል ሰጥቷል" ብሎ በእኔ ተስፋ ቆርጦ ረስቶኝ አያውቅም። የዘላለም አባቴ ነውና እርሱ እንደ አባት ይጠብቀኛል፣ እኔም ልጁ ነኝና እንደ ልጁ እታዘዝለትና በሚመራኝ መንገድ እጓዝ ዘንድ እንደሚያበረታኝ አምናለሁ፣ አምኜም በእርሱ ፊት እመላለሳለሁ።"

አዎ! ጀግናዬ..! አንድ ሁለቴ ሳይሆን በጣም ብዙ ጊዜ እምነትህ ይፈተናል፣ አንድ ሁለቴ ሳይሆን በጣም ብዙ ጊዜ ለአምላክህ ያለህ ፍቅር ይፈተናል። ነገር ግን ፈተና ሁሉ ሊጥልህ እንደማይመጣ አስተውል። አብዛኛው ፈተናህ ለቀጣይ ጉዞህ መንገድ ከፋች ነው። እምነትና ፍቅር የሚፀኑት በከባባድ ፈተናዎች ወቅት ነው። ፅናት የሌለው እምነት እምነት አይደለም፣ በትዕግስት የማይመራ ፍቅር ፍቅር አይደለም። የአምላክን አሰራር ብዙ ለመመርመር አትሞክር። ዝም ብለህ ራስህን እየተመለከትክ እመን፣ እንዲሁ ላንተ ያደረገልህን እያስታወስክ አመስግነው። "ከመንፈስህ ወዴት እሄዳለሁ? ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ? ወደ ሰማይ ብወጣ አንተ በዚያ ነህ ወደ ሲኦልም ብወርድ በዚያ አለህ።" እንዳለ ቅዱስ ዳዊት አምላክህን አትሽሽ፣ ከእርሱም ተሰውረህ ለማጥፋት አትሞክር። የትም ሒድ እርሱ እዛ አብሮህ አለ፣ ምን አድርግ እርሱ እያንዳንዱን ድርጊትህን ያያል። ከማታመልጠው አባትህ ስር ለማምለጥ አትሩጥ፣ ይልቅ በእርሱ አምነህ ውጣ፣ በእርሱ ተማምነህ ግባ፣ የዓለምህም ገዢ፣ የምድራዊ መርከብህም ካፒቴን ሁን።


❤️አ😍ፈ😍ቅ😍ር😍ሻ😍ለ😍 ሁ❤️

አ🥰= አንድ ነገር ቀረኝ ከጥፋት መታቀብ
ፈ🥰= ፈልጌው አደለም አላበዛም ሰበብ
ቅ🥰= ቅንነትሽ ደስታ ስሜትን ይስባል
ር🥰= ርሀብን ያስታግሳል ጥምንም ያስቆማል
ሻ🥰= ሻማ ሁነሽኛል በጨለመው ጎኔ
ለ🥰= ለማንም አልፈቅድም እንዲለዩሽ ከ
#እኔ👈
ሁ🥰  = ሁሌም ወድሻለሁ ትናፍቂኛለሽ እስከማይሽ በ
#አይኔ😢


ብትወድቁ ትነሳላችሁ!

ትምክህት አያሰናክላችሁ፣ ትዕቢት መንገድ አያስታችሁ፣ አጉል ድፍረት ችግር ውስጥ አይክተታችሁ። ለሌላ ለማንም ሳይሆን ለራሳችሁ ጠንቃቃ ሁኑ፣ ሌላ ማንንም ለመጥቀም ሳይሆን ራሳችሁን ለመጥቀም ራሳችሁን ገስፁ። ስህተትና ውድቀት ብርቅ ባልሆነበት ዓለም ላይ እየኖራችሁ አንዴ ስለተሳሳታችሁ ወይም አንዴ ስለወደቃችሁ ሰማይ የተደፋባችሁ ምድር የዋጠቻችሁ አታስመስሉ። እደጉ ስትባሉ ስህተት ወደ ህይወታችሁ ይመጣል፣ መቀየር ካለባችሁ ውድቀት ደጋግሞ ይጎበኛችኋል። "በፍፁም እንዳትሳሳቱ፣ በፍፁም እንዳትወድቁ።" የሚል አስተምህሮ የለም። የስህተት ጥቅም የገባቸው ለመሳሳት ይደፍራሉ፣ የውድቀትን ትርፍ ያገኙ ደጋግመው ለመውደቅ ይዘጋጃሉ። ህይወት እስርቤት ሳትሆን ነፃ ሜዳ ነች። አስሬ ብትሳሳቱ በሰውኛ የሚፈርድባችሁ ሰው ቢኖርም ተጨማሪ እድል የሚሰጣችሁ ፈጠሪ ግን አለ። እድሉ የሚሰጣችሁም እንደገና እንድትሳሳቱና እንድትበድሉ ሳይሆን ከስህተታችሁ ታርማችሁ በትክክለኛው መንገድ እንድትጓዙ ነው። ጥሩ ተማሪ ስህተቱን አይደግምም፣ ብልህ ሰውም ዳግም በወደቀበት መንገድ አይጓዝም።

አዎ! የዓለም ፍፃሜ አታስመስሉት፣ ብትወድቁ ትነሳላችሁ፣ ብትሳሳቱ ትታረማላችሁ፣ ብትጠፉም ትመለሳላችሁ። ባለፈ መጥፎ ትዝታ ራሳችሁን አትሰሩ፣ በቀደመ ጥፋት ራሳችሁን እየወቀሳችሁ አትኑሩ። አዋቂ ሁኑ፣ አንዱን ስህተታችሁን ከቀጣዩ ስህተት መጠበቂያ አድርጉት፣ የአሁን ውድቀታችሁን ለቀጣይ ጉዟችሁ መጀመሪያ አድርጉት። በራሱ የሚያዝንን ሰው ማንም ሊያፅናናው አይችልም፣ ራሱ ላይ የሚጨክንን ሰው ማንም ሊረዳው አይችልም። እርግጥ ነው ፍረሃታችሁ መሳሳት ወይም መውደቁ ሳይሆን በስህታችሁ ወይም በውድቀታችሁ  ምክንያት የሚደርስባችሁ ሰው ትቺትና ፍርጃ ነው። ይሔን አስታውሱ፦ "ብዙ ሰው አዋቂ ሳይሆን ፈራጅ ነው፣ ብዙ ሰው አራሚ ሳይሆን ተቺ ነው።" በሳታችሁ ሰዓት ፈጣሪያችሁን አስቡ፣ ስትወድቁ አምላካችሁን ተመልከቱ። ሁሌም በስህተት መንገድ እንድትመላለሱ የሚፈልግ ፈጣሪ የላችሁም፣ እዛው በወደቃችሁበት ስፍራ እንድትቀሩ የሚፈልግ አምላክ የለም። መነሳታችሁን የሚፈልግ አባት አላችሁና እርሱን ተደግፋችሁ ዳግም ተነሱ፣ የእናንተን በትክክለኛው መንገድ መጓዝ የሚናፍቅ አምላክ አላችሁና መንገዱን እንዲመራችሁ ፍቀዱ።

አዎ! ጀግናዬ..! ከዋጋህ በታች አትኑር፣ በሚያጠፋህ መንገድ አትመላለስ፣ አስኮኙ ምግባር ላይ አትሰየም። አውቀህ አውቀህ ለድህነት ትቀርብ ይሆናል ፍፁም ነፃ የሚያወጣህና የሚያድንህ ግን እምነትህ ነው። አንድም ከስህተት የመውጣት እመነት፣ ሌላም ፈጣሪ ከስህተት እንደሚያወጣህ ማመን። ተስፋህን ቸል አትበለው፣ እምነትህን አትፈትነው፣ ዳግም የመነሳት ሃሳህን አትገዳደረው። አንድ ቀን ከተሳሳተው መንገድ ትወጣለህ፣ አንድ ቀን ካቀረቀርክበት ቀና ትላለህ፣ አንድ ቀን ውድቀትህን ትሽረዋለህ፣ በአምላክህ ፍቃድ ነፃ ሆነህ በሰው ፊት በነፃነት ትራመዳለህ። ሁሉም ሰው የራሱ የውድቀት ታሪክ አለው፣ ማንኛውም ሰው ደግሞ ማንሳት የማይፈልገው የህይወት ከስተት አለው። የተለየውና ልብ ሰባሪው ታሪክ ያንተ ብቻ አይደለም። ታሪክህ ምንም ይሁን እንዲያልፍ ፍቀድለት፣ ትዝታህ ምንም ይሁን እንዲያስርህ አትፍቀድለት። አሁን የትም በምንም ውስጥ ሁን፣ ያለህበት ስፍራ የተሳሳተ እንደሆነ ከተሰማህ ግን ጊዜ ሳታጠፋ ጥለሀው ውጣ፣ ከዳግም ውድቀትም ራስህን አድን።


ከምንም አትጣበቅ!

ለብቻ መሆን፣ እራስን በብዙ ዘርፍ መቻል፣ ለግል አቋም ታማኝና ቆራጥ መሆን፣ ከማንም ምንም ብታጣ እንኳን ከተፅዕኖ ነፃ መሆን መቻል ቀላል አይደለም። ቢሆን ኖሮ ብዙዎች ባደረጉትና ከሰዎች ሲለያዩ እራሳቸውን ባላጡ ነበር። ከአንድ ሰው ወይም ከቁስ ጋር ባለህ ግንኙነት ዘወትር ፈላጊው አንተ፣ ሙሉ ትኩረትህ እርሱ ላይ፣ ደስታና ሰላምህንም ከእርሱ እያገኘህ ከሆነ የአደጋህ ቀይ መብራት በትልቁ እንደበራ አስተውል። የዛፍ ቅርንጫፎች የዛፉ ስር ሲቆረጥ አብረው ይወድቃሉ፣ አንተም እንዲሁ የተደገፍከው፣ የተጣበከው፣ ከልብህ የተማመንክበት ነገር ካጋደለ ያንተም ህይወት ከማጋደልና ከመውደቅ አያመልጥም። እንደ ቀልድ የጀመርከው የትኛውም ግንኙነት ገዢህና መሪህ እንዲሆን አትፍቀድ። ምንም ዘላለማዊ ነገር የለም። ያለን ነገር ሁሉ ጅማሬና ፍፃሜ አለው።

አዎ! ጀግናዬ..! ከፈጣሪህ፣ ከአምላክህ በቀር ከአንዳች ምድራዊ ነገር ለመነጠል እስከሚያስቸግርህ ድረስ አትዋሃደው፤ ከምንም አትጣበቅ፤ ለማንም እራስህን፣ ክብርህን፣ ማንነትህንና ህልውናህን አሳልፈህ አትስጥ። ላንተም ሆነ ለአምላክህ ካንተ በላይ ዋጋ ያለው ነገር የለም። የሚመጡ ሁሉ የጊዜ ጉዳይ እንጂ የሆነ ጊዜ ጥለውህ ይሔዳሉ፤ የማይሔዱም ቢሆን ሊገዙህና እንደፈለጉ ሊነዱህ ስልጣን የላቸውም። የብዙዎች ስብራት፣ የብዙዎች ህመም፣ የብዙዎች ቁስል ዋናው ምክንያት ከልክ ያለፈ መዋሃድ፣ ገደብ የሌለው መጣበቅ ወይም Over Obsession, Over Attachment ነው። ፍቅርና Attachment, ግንኙነትና ጥገኝነት የተለያዩ ጉዳዮች ናቸው። ነፃነትን የሚነሳ ፍቅር ፍቅር ሳይሆን ጥገኝነት ነው፤ "ያለእርሱ መኖር አልችልም፤ ያለእርሷ ህይወት ለእኔ ባዶ ነው" የሚያስብል ግንኙነት ጤነኛ ግንኙነት አይደለም።

አዎ! ምንም አይነት ግንኙነት ውስጥ ብትሆን ትልቁና ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ አንተ ከእራስህ ጋር ያለህ ግንኙነትና አብራህ ያለችው ወዳጅህ ከእራሷ ጋር ያላት ግንኙነት ነው። ግንኙነት ውስጥ ያሉ ሁለት ሰዎች ከእራሳቸው ጋር ሰላም ከሆኑ፣ ምንም አይነት የጥገኝነት ባህሪና ሙጭጭ የማለት ፀባይ ከሌለባቸው ግንኙነት ሰላማዊ፣ የተረጋጋና አስደሳች የመሆን እንድሉ እጅግ በጣም ሰፊ ነው። ሰውን ተደግፈህ ሰው ቢጥልህ ካለሰውየው ድጋፍ ለመነሳት ልትቸገር ትችላለህ፤ ፈጣሪህንና እራስህን ተደግፈህ ብትወድቅ ግን በፈጣሪህ ድጋፍ ባንተ ብርታት ድጋሜ ትነሳለህ። እራስን ማክበር እራስን ከልብ የመውደድ አይነተኛ ማሳያ ነው። መገፋትህ እንዳያሳምምህ፣ በመገለልህ እንዳትሰበር፣ ሁሉም ቦታ በመገኘት ዋጋህን እንዳታጣ፣ ጥገኛ በመሆን ስሜትህ እንዳይጎዳ ከምንም በላይ ለእራስህ ቦታ ስጥ፣ ከማንም በተሻለ ከእግዚአብሔር አምላክህና ከእራስህ ጋር የጠበቀ ግንኙነት ይኑርህ። መጪው ቀድሞ ያልነበረ ስላለመሔዱም እርግጠኛ የማትሆንበት ነውና እራስህን በመውደድህ፣ ለእራስህም ቅድሚያ ባለመስጠትህ ምንም ሃፍረት አይሰማህ።


ያልተሰጠህን ለእራስህ ስጥ!

ብቻህን ትጓዛለህ ቢሆንም አትፈራም፤ ብቻህን ትለፋለህ ቢሆንም አትጨነቅም፤ ብቻህን ትኖራለህ ቢሆንም በእራስህ መቆም አይከብድህም፤ በችግሮችህ መዋል ማለፍ ትችላለህ፤ ብዙዎች ባያምኑብህ በእራስህ ትተማመናለህ፤ ማንም ባይደግፍህ እራስህን ትደግፋለህ፤ ማንም የተሻለ ቦታ ባይሰጥህ ለእራስህ ግሩም ቦታ ትሰጣለህ። ያጣሀውን ለእራስህ አድርግ፤ ያልተሰጠህን ለእራስህ ስጥ። ብቻህን ነበርክ ዛሬም ዳግም ብቻህን መቅረትህ ሊደንቅህ አይገባም። ሰዎች ይመጣሉ በፊት እንደነበርከውም ብቻህን ጥለውህ ይሔዳሉ። ብቸኝነትን ተለማመድ፤ ከሌሎች ስታገኘው የነበረውን ነገር ከእራስህ ለማግኘት ሞክር። በእርግጥ ሰው የሚሰጥህን በሙሉ ከእራስህ ላታገኝ ትችላለህ ከልቡ አምኖበት፣ ፈልጎና ወዶ የሚሰጥህ እስኪመጣ ግን ለእራስህ በፍፁም አንሰህ እንዳትገኝ። ለእራሱ፣ በእራሱ ደስተኛ፣ ጠንካራ ብርቱ የሆነ ሰው ከውድቀቱ እንዴት ማገገም እንዳለበት፣ በምንያክል ፍጥነት ዳግም መነሳት እንዳለበት፣ እንዴት እራሱን ዳግም ማግኘት እንደሚችል ጠንቅቆ ያውቃል።

አዎ! ጀግናዬ..! ያልተሰጠህን ለእራስህ ስጥ! ከሌሎች ጠብቀህ ያጣሀውን፣ ስትናፍቀው ያስቀሩብህን፣ እያስፈለገህ የተነፈከውን ነገር ለእራስህ በእራስህ ለመስጠት ቆርጠህ ተነስ። በሰዎች ችግር ምክንያት፣ በሰዎች ፍላጎት ማጣት፣ በሰዎች ፊታቸውን ማዞር ማላዘንህን አቁም፤ እራስህን መውቀስ አቁም፤ እራስህን ተጠያቂ ማድረግ አቁም። ይህ ጊዜ ብቸኝነትህን በሚገባ የምታከብርበት፣ ማየት ለሚገባቸው፣ ማየት ለሚፈልጉ ትክክለኛውን ማንነትህን የምታሳይበት ጊዜ እንደሆነ እወቅ። ብቻውን የፈለገውን ነገር ማድረግ የሚችልን ሰው የትኛውም ጫና ሊያስቆመው አይችልም፤ የትኛውም አይነት በደል ወደኋላ ሊያስቀረው አይችልም። ብቻህን ስትሆን ፍፁም የተለየህ ሰው ትሆናለህ፤ ፍፁም ከዚህ በፊት የማትታወቅ ላንተም ለሌላውም አዲስ ሰው ትሆናለህ።

አዎ! ድጋፍ ማጣትህ ያጠነክርሃል፤ የሚያምንብህ አለመኖሩ በእራስህ እንድታምን ያነሳሳሃል፤ በሰዎች መገፋትህ እግዚአብሔር አምላክህን እንድትጠጋ ያደርግሃል፤ ተቀባይነት ማጣትህ እራስህን ከነድክመቱ እንድትቀበለው ይጠቁምሃል። ብቻህን ስትጓዝ አብሮህ ያለው አምላክህ ነውና መከዳት የለም፤ መገፋት አይኖርም፤ ድራማ የለም፤ በሰዎች ስሜት ምክንያት ዋጋ መክፈል አይኖርም። ብቻህን እራስህ ላይ ትሰራለህ፤ ብቻህን እራስህን ታጠነክራለህ፤ ብቻህን ማን እንደሆንክ፣ ምን ማድረግ እንደምትችል ታሳያለህ። በስተመጨረሻም የእውቁ ደራሲ የዋይኒ ዳየርን ንግግር አስታውስ፡ "ብቻህን ስትሆን አብረሀው የምትሆነውን ሰው ከወደድከው በፍፁም ብቸኛ ልትሆን አትችልም።" ያንን ሰውም አንተ ሁን፤ በህይወትህ በጣም የምትፈልገውን ሰው እራስህ ሁን፤ እራስህ ላይ በመስራትህ የሚያኮራህን አይነት ሰው ሆነህ ተገኝ።


ከሃሳብ እለፉ!

ከሀሳብ እለፉ፣ ከተደጋጋሚ እቅድ ከፍ በሉ፣ ወደ ተግባር ተጠጉ፣ ሩጫውን ተቀላቀሉ፣ የረጅሙን ጉዞ ምዕራፍ ጀምሩ። ከእያንዳንዱ አስባችሁ ካልጀመራችሁት ነገር ጀርባ ከፍተኛ ፀፀት እንደሚጠብቃችሁ አስታውሱ። በሀሳብ ልክ ለመኖር፣ ፍላጎትን ለማሟላት፣ ወደ ላቀው ከፍታ ለመድረስ ጅማሮ አማራጭ የሌለው አማራጭ ነው። እስከ ዛሬ ለነገ የቀጠራቿቸውን ጉዳዮች አስታውሱ፣ ነገ ባላችሁት ቀን ስለማድረጋችሁ መርምሩ፣ በማወላወል ያጠፋቿቸውን ጊዜያት አስታውሱ። ሁሌም እያቀዳችሁ መኖር አትችሉም፣ ሁሌም በሀሳብ ውቂያኖስ ውስጥ ተዘፍቃችሁ አትቀሩም፣ ሁሌም በማወላወልና በማንገራገር እየተጨነቃችሁ አትኖሩም። እፎይታችሁ ያለው ከጅማሬያችሁ ቦሃላ ነው፣ ልባዊ መረጋጋትን የምታገኙት ወደምታስቡት አቅጣጫ መራመድ የጀመራችሁ እለት ብቻ ነው። ነገሮችን ሰፋ አድርጋችሁ ለመመልከት ሞክሩ፣ ከዛሬ ሁኔታችሁ በላይ ማሰብ ጀምሩ። ሀሰሳባችሁን አጠንክሩ፣ አግዝፉት፣ መቋጫውን ተግባር አድርጉት።

አዎ! ቆሞ ቀር አትሁኑ፣ የሀሳባችሁ ባሪያ፣ የጊዜያዊ ስሜታችሁ ተገዢ አትሁኑ። ከሃሳብ እለፉ፣ እቅዳችሁን ፈፅሙት፣ ፍላጎታችሁን ጨብጡት። እናንተ ቆማችሁ እየተጓዙ ካሉ ሰዎች ጋር አትፎካከሩ፣ እናንተ እያሰባችሁ ሀሳባችውን የሚፈፅሙ ሰዎችን አትገዳደሩ። ሰውን ማለፍ ላይ ሳይሆን እቅዳችሁን መፈፀም ጀምራችሁ ብቁ መሆን ላይ አተኩሩ፣ የተሻለ ነገር እንዲከናወንላችሁ ከማሰብ በላይ እንዲከናወንላችሁ የምትፈልጉትን ነገር በራሳችሁ ለማከናወን ሞክሩ። ከሰው ሲጠብቁ የነበሩ ሰዎች ዛሬም እዛው የጥበቃቸው ስፍራ ናቸው፤ በሰው ላይ እምነት የጣሉ ሰዎች ዛሬም ሰውን እየተጠባበቁ ነው፤ የሁኔታዎችን መገጣጠም ሲጠባበቁ የነበሩ ሰዎች አሁንም የማያባራ ሀሳብ ውስጥ ናቸው። የተቻላችሁን ያህል በትልቁ አስቡ ነገር ግን ሀሳባችሁን በትንሹ ጀምሩት፣ እንደ አቅማችሁ እቅድ አውጡ፣ ግብ አስቀምጡ፣ እቅዳችሁንም መፈፀም ጀምሩ፣ ወደ ግባችሁ ጉዞ ጀምሩ። አስተውሉ፣ ዙሪያችሁን ተመልከቱ፣ መርምሩ፣ አካባቢያችሁ ላይ ያለውን ለውጥ አጢኑ፣ ሀሳባችሁን አዳምጡ በራሳችሁ ያመጣችሁትን ለውጥም እንዲሁ መርምሩ።

አዎ! ጀግናዬ..! ትልቁ ሀሳብህ አብሮህ እስጊያረጅ አትጠብቅ፣ ፍላጎትህ ትርጉም አልባ ቅዠት እስኪሆን አትጠብቅ። እንደማንኛውም የሚያስብ ሰው ሳይሆን የሚያስበውን እንደሚኖር ጥቂት ሰው ለመኖር ሞክር። የሀሳብህ ትልቅነት፣ የፍላጎትህ ግዝፈት አንቅቶህ ወደ ተግባር እንዲያስገባህ አድርግ። የሀሳብህ እንቅፋቶች ምንድናቸው? በትንሹ እንዳትጀምር ያደረጉህ ነገሮች ምንድናቸው? የተግባር ሰው እንዳትሆን አስረው የያዙህ ነገሮች ምንድናቸው? እንቅፋቶችህን እወቅ፣ መሰናክሎችህን መርምር። አሁን መጀመር ባትችልም መሰናክል የሆኑህን ነገሮች መቀነስ ጀምር፣ የእውቀት ደረጃህን ከፍ አድርግ፣ የምትፈልገውን ነገር ግልፅ አድርግ። ማድረግ የምትፈልገውን ትልቅ ነገር ለማድረግም ሆነ ለመጀመር ስለሁሉም ነገር ማወቅ እንደሌለብህ እወቅ። ህልምህ ህልም ብቻ ሆኖ እንዳይቀር፣ ሀሳብህም ሀሳብ ብቻ ሆኖ እንዳይቀር ራስህን አደፋፍር፣ ፍላጎትህን አጥራ፣ ፍረሃትህን አስታግስ፣ በሀሳብህ እውንነት እመን፣ ወደ ተግባርም ግባ።


ከእራስህ ተነስ!

"የመውደድ አቅም ካለህ አስቀድመህ እራስህን ውደድ።" - Charles Bukowski

ማንንም ለመውደድ ጅማሬያችን እራሳችንን መውደዳችን ነው፤ ማንንም ለማክበራችን መሰረታችን እራሳችንን ማክበራችን ነው፤ ማንንም አስደሳች ለማድረግ ቀዳሚው እራሳችንን ማስደሰት መቻላችን ነው፤ በማንም ዘንድ ተቀባይነት ለማግኘታችን ዋስትናው እራሳችንን መቀበላችን ነው። ውጪውን ለማስተካከል ከመሔድህ በፊት አንተ ጋር ምንም መስተካከል የሚገባው፣ መታነፅ ያለበትና መሻሻል የሚኖርበት ነገር እንደሌለ እርግጠኛ ሁን። አመለካከትህ፣ አረዳድህ፣ የእምነት ደረጃህ፣ እውቀትህ፣ የማስተዋል አቅምህ፣ የመረዳት ችሎታህ ሁሉ እንከን አለባ እንደሆነ እርግጠኛ ሁን። ውጪው ላይ ጣትን ከመቀሰር በተሻለ እራስን መመልከት እራስን መረዳትና ለእራስ እምነት ታምኖ መገኘት ይቀድማል። እድሎች ቢያመልጡህ ተጎጂው አንተ ነህ፤ ከእራስህ ማግኘት የምትችለውንም ከሰዎች እየፈለክ፣ እየጠበክና በየቦታው እያሳደድክ ብትቆይ የምትጎዳው እራስህ ነው።

አዎ! ጀግናዬ..! ከእራስህ ተነስ! ከእራስህ ጀምር፣ መውደዱን ከእራስህ ጀምር፣ ማክበሩን ከእራስህ ጀምር፣ ጊዜ መስጠቱን፣ ማዳመጡን፣ መንከባከቡን፣ መደገፉን፣ ማነቃቃቱን ከእራስህ ጀምር። ለእራስህ የማትሰጠውን ፍቅርና ክብር ለማንም መስጠት እንደማትችል እወቅ። በእራስህ ደስተኛ ሳትሆን ሌላውን ደስተኛ አደርጋለሁ ብለህ አታስብ፤ እራስህን ሳትመራ፣ ፍላጎቶችህን ሳትቆጣጠር፣ ስሜትህ ላይ ሳትሰለጥን ሰዎችን እመራለሁ፣ ድርጅትን አስተዳድራለሁ፣ ሀገርን እረከባለሁ፣ ትውልድንም አንፃለሁ ብለህ አታስብ። ማንም ሰው የሌለውን ነገር ሊሰጥ አይችልም። ትርጉም ሰጪው፣ አትራፊውና ውጤታማው ህይወት የሚመጣው ሌላ ከማንም ሳይሆን ከእራሱ ከባለቤቱ ነው። ክፍተትህን እንዲሞሉልህ የምትጠብቃቸው ሰዎች እራሳቸው የእራሳቸው ክፍተትና ድክመት ይኖርባቸዋል። ጫማህ ቢጠብህ እግርህን እንደማታስተካክለው ሁሉ ነገሮች እንዳሰብከው ካለሆኑ ከነገሮቹ በላይ ለነገሮቹ ያለህን አመለካከት መርምረህ አስተካክል።

አዎ! ጊዜያዊ የአመለካከት ስህተትህ የእድሜህን እኩሌታ በጥበቃና በወቀሳ እንዲጨርሰው አታድርግ። ለእራስህ መታመን እየተቸገርክ፣ የግል አቋም መገንባት ላይ እየተንገጫገጭክ፣ ወደፊት የሚመሩህን መርሆችን ወደኋላ እየጣልክ፣ እራስህን የበታች መጪዎቹን የበላይ፣ እራስህን ደካማ ገና ወደህይወትህ የሚገቡ ሰዎችን ጠንካሮች አድርገህ ማሰብ እስካላቆምክ ድረስ የምትጠብቀውን ውጤት በፍፁም ልታገኝ እንደማትችል እወቅ። እራስህን ተቀበል፣ ክፍተቶችህን ሙላ፣ ድክመትህን አርም፣ ወደህይወትህ እንዲገቡ የምትጠብቃቸው ሰዎች ሊያደርጉልህ የሚችሉትን ነገር በጥቂቱም ቢሆን ለእራስህ አድርግ። መውደድ፣ ማፍቀር፣ ማክበር፣ መንከባከብ እችላለሁ ብለህ የምታስብ ከሆነ በቅድሚያ ለእራስህ ከማድረግ ተነስ። 

20 last posts shown.