የቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንፆኪያ እሳቤ በኬልቄዶናውያን ምስጢራት ላይ፡ ለአሁናዊ የቤተክርስቲያን አንድነት ያለው አበርክቶ
ከጉባኤ ኬልቄዶን በኋላ በኢ-ኬልቄዶናውያን መካከል ተገንጣዊነትን እና አዲስ መዋቅር ፈጣሪ የኾኑ (Separatist) በጆፓ ጳጳስ በቴዎዶጦስ የሚመሩ፣በንጉሥ ዜይኑን (Emperor Zeno) ሄኖቲኮን የሚመሩ ሄኖቲካውያን (Henotist) እንዲሁም እንደ ቅዱስ ሳዊሮስ ሁለቱንም የሚያወግዙ በሚል የተፈጠረ ክርክር ነበር፣ቅዱስ ሳዊሮስ ተገንጣዊነትን (Separatism) ደጋፊ አልነበረም ይህ ማለት ግን ኬልቄዶንን ተቀብሏል ማለት አይደለም፣ንጉሥ ዜይኑን ያወጣው ሄኖቲኮን በአንዳንድ ኬልቄዶናውያን ኾነ በኢ-ኬልቄዶናውያን ዘንድ ተቀባይነት አግኝቶ ሄኖቲካውያን ጳጳሳት በሁለቱም ዘንድ ፈጥሯል። ለምሳሌ እነ ጴጥሮስ ሞንጎስ(የእስክንድርያ ፓትርያሪክ) ዘንድ ተቀባይነት አግኝቷል። በማዮማ-ጋዛ ጳጳስ በቅዱስ ጴጥሮስ ሮሀዊ¹ እና በተማሪው በቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንፆኪያ ያሉ የተዋሕዶ አርበኛ ግን በምልአት አልተቀበሉትም ነበር ምክንያቱም የንጉሥ ዜይኑን ሄኖቲኮን እውነት ነው "ሁለት ባህርይ"(In Two Natures) የሚል ነገረ-ክርስቶስን ቢያወግዝም እና የኬልቄዶንን ጉባኤ ውሳኔ ቅቡልነት ቢቃወምም በግልጽ(Explicitly) በሆነ መንገድ ጉባኤውን አላወገዘም። በዚህ ምክንያት ቅዱስ ሳዊሮስ ከአባቶቹ ከእነ ቅዱስ ጴጥሮስ ሮሀዊ ጎን ቆሞ እነ ጴጥሮስ ሞንጎስን ተቃውሟል።
በዚያው ልክ ግን በኢ-ኬልቄዶናውያን ዘንድ ተገንጣዎች እና ወግ አጥባቂ የሆኑ፣ለአንድነት የማይቀኑ ሰዎች እንደ የጆፓ ጳጳስ ቴዎዶጦስ፣ዮልያኖስ ፈረሳዊ እና ተከታዮቹ እንዲሁም የቴላ ጳጳስ ዮሐንስ፣ኢሳይያስ አርመንያዊ እና ጎርጎርዮስ ዘጳንጦስ ያሉ ሰዎችም ነበሩ። ቅዱስ ሳዊሮስ ሁለቱንም አካላት ተቃውሟል እነ ጴጥሮስ ሞንጎስንም ሆነ ኬልቄዶናውያንን ዳግም ጥምቀት አጥምቀው ከኅብረት የሚጨምሩትንም ሆነ በዳግም-ቅብአተ ሜሮን (Re-Anointing) የሚቀበሉ ኢ-ኬልቄዶናውያንን ተቃውሟል። እነርሱን በሚቃወመው ደብዳቤውም² በቅዱስ ሜሮን ኬልቄዶናውያንን ወደ ኅብረት ማግባትን ኬልቄዶኖውያንን በዚህ መልኩ መቀበል ከመንፈስቅዱስ ፀጋ የተነጠሉ እና ፀጋ መንፈስቅዱስ ያልተቀበሉ ስለሚያስብላቸው፣ የምንከተለው የቀደሙን አበው ባስቀመጡት ነው ይላል፤ይህም ማለት በቀደሙት አበው ዘንድ በቅዱስ ቆጵርያኖስ እና በሮሙ ፖፕ እስጢፋኖስ መካከል የተነሳውን ክርክር ያነሳዋል፣በቅዱስ ቆጵርያኖስ እና በአፍሪካውያን ጉባኤያት የተቀነነው "ከማንኛውም ምንፍቅና የሚመጣ ሰው ምንም አይነት ጥምቀት ካልተጠመቀ፣ በቤተክርስቲያን ጥምቀት ፍጽምናን ማግኘት አለበት" የሚል ቢሆንም የማንኛውም አይነት መናፍቃን እንደሆኑ አለዩም ነገርግን ሁሉንም በአንድ አይነት ተቀጽላ አመጡት እንጂ³ ይህን አቋም የያዙት ግን ለእግዚአብሔር ከመቅናት እና ለእርሱ ካላቸው ፍቅር ነው ይለናል ቅዱስ ሳዊሮስ⁴ ነገርግን በወቅቱ የነበረ ታላቁ ቅዱስ ዲዮናስዮስ ዘእስክንድርያ የምንፍቅናዎቹን አይነት እና ቀመረ-ጥምቀቱን (Formula of baptism) ይለያያል ማለትም ጥምቀቱ በስመ-ሥላሴ ከሆነ እና ጥምቀቱ የተፈጸመው በመናፍቃን ቢኾንም እንኳ የሦሥቱን የሥላሴ አካላቶችን የሚያምኑ ከሆነ ድጋሜ አይጠመቁም የሚል መካከለኛ አቋም የቤተክርስቲያን ነው ይለናል ቅዱሱ⁵ የአፍሪካውያን እና የቅዱስ ቆጵርያኖስ አቋም መናፍቃንን በአንድ መገለጫ ቢጠቅሱም በዘመነኛቸው በቅዱስ ዲዮናስዮስ ግን ተለያይቷል ይህን አስመልክቶ ቅዱስ ሳዊሮስ ሲያጠቃልለው እንዲህ ይለናል፦
"በሥጋዊ ሕመም ጊዜ እያንዳንዱ ደካማነት በጥቅሉ በሽታ ተብሎ እንደሚጠራና ይህ አጠቃላይ ስምም እንደ ትኩሳት፣ የሆድ እብጠት እና የዝሆኔ በሽታ (Elephantiasis) ያሉ ብዙ የተለያዩ በሽታዎችን እንደሚያጠቃልል ሁሉ፤ በእምነት ድክመት ረገድም ከጤናማው ቃል (ከቀጥተኛው እምነት) ዘወር ማለት ሁሉ በጥቅሉ ምንፍቅና⁶ ይባላል። ነገር ግን በዚህ ጥቅል ስም ስር የሚካተቱት እያንዳንዱ መንፈሳዊ በሽታዎች ተመሳሳይ ባህርይ የላቸውም፤ በክፋታቸውም (በክህደት ደረጃቸው) እኩል አይደሉም። ነገር ግን፣ አንድ የተዋጣለት ሐኪም ትኩሳት ያለበትን ሰው በአንድ መንገድ፣ ብርድ ብርድ የሚለውን ወይም የሆድ እብጠት ያለበትን ወይም የጣፊያ ክፍል ያበጠበትን ሰው ደግሞ በሌላ መንገድ እንደሚያክም ሁሉ፤ በተመሳሳይ መልኩ አብያተ ክርስቲያናትን ከተራ መንፈሳዊነትና ማስተዋል በላይ በሆነ ጥበብ የመገቡና የፈወሱ አባቶችም የእያንዳንዱን ክህደት ባህርይ መለየት ትክክል እንደሆነ ፈረዱ። በብናጥስ⁷ እና በፎጢኖስ⁸ በሽታ የተያዙትን ሰዎች ለማከም የሚሆን ፈውስ፣ በጳውሎስ ሳምሳጢ⁹ የክህደት ዝቅጠትና ረግረግ ከቆሸሹት ሰዎች ጋር እኩል መሆን የለበትም ብለው አሰቡ። የሦስት መቶ አሥራ ስምንቱ (የኒቂያ) አባቶች አሥራ ዘጠነኛው ቀኖና ከጳውሎስ ሳምሳጢ ወገን የሚመጡት እንደገና እንዲጠመቁ (Re-Baptized) ያዝዛል፤ ነገር ግን ከፎጢኖስና ከብናጥስ ወገን ወደ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ለሚመለሱት ደግሞ በፍርግያ ሎዶቅያ በተሰበሰበው ሲኖዶስ የተደነገገው መቶ አሥረኛው ቀኖና በቅብአ ሜሮን
(Chrism) ብቻ ፍጹማን እንዲሆኑ ወሰነ፤ ምንም እንኳን የሳምሳጢው ጳውሎስንና የፎጢኖስን አሳዛኝ ክህደት የወለደቻቸው በአብዛኛው ያችው አንዲት ስንፍና ብትሆንም፣ እርስ በርሳቸውም የሚለያዩት በጥቂቱ ብቻ ቢሆንም።"¹⁰
ስለዚህ በቅዱስ ሳዊሮስ ዓይን የኬልቄዶናውያን ሚስጥራት እንዴት መታየት አለባቸው? በንስጥሮሳውያን ላይም ቢኾን በቤተክርስቲያን ዘንድ አንዳንዶች በዳግም-ጥምቀት አንዳንዶች በቅብአ ሜሮን እንደሚቀበሏቸው፣በኋላ ላይ ግን ንስጥሮሳውያን ወደ ቤተክርስቲያን ኅብረት ሲመጡ ንስጥሮሳዊነትን በመካድ (By confession) ብቻ እንዲሆን ተወስኗል ስለሆነም የኬልቄዶናውያን ጉዳይም ከዚህ የተለየ አይሆንም።የቅዱስ ሳዊሮስን ሀሳብ እንዲህ መረዳት እንችላለን፦
1.ንስጥሮሳውያን ሆኑ ኬልቄዶናውያን በተዋሕዶ ካለው ልዩነት በቀር በክርስቶስ ዘልዓለማዊነት፣ከአብ ጋር ዕሩይ እና የተካከለ መኾኑን ያምናሉ። ይህ ማለት ልክ እንደ ፎጢኖስ ኾነ እንደ ጳውሎስ ሳምሳጢ ሊታዩ አይገቡም ይህም ማለት የንስጥሮሳውያን ክህደት በተዋሕዶው ነበር የጳውሎስ ሳምሳጢ እና የፎጢኖስ ክህደት ግን ከክርስቶስ መለኮታዊ ባህርይ ጋር የሚገናኝ ምንፍቅና በመናገራቸው፣የንሰጥሮሳውያን ግን ከዚህ በተለየ በመኾኑ ነው ቅዱስ ሳዊሮስ ሁለቱን ያወዳደረው።
2.ቀመረ-ጥምቀታቸው(Baptism Formula) በሥላሴ ስም የተከወነ መኾኑ እና በሥላሴ ላይ ያላቸው እምነት ልከኛ መኾኑ።
3.በቀደሙት አበው ዘንድ ይህ እንደ መተዳደሪያ ያገለገለ እና እንደ ቅዱስ ጢሞቴዎስ ዘእስክንድርያ እና ቅዱስ ጴጥሮስ ዘሮሀ ያሉ ኬልቄዶንን የተቃወሙ የተዋሕዶ አርበኞች የቴዎዶጦስ ዘጆፓን ሀሳብ ሳይሆን የቅዱስ ሳዊሮስን ሀሳብ መቀበላቸው ሲኾን ይህንን ትምህርታዊ ቅብብሎሽ ቅዱስ ሳዊሮስን ያጠናው Iain R.Torrance እንዲህ ይገልጠዋል፦
"እርሱ የዳግም ቅብአትን(Re-Anointing) ሥርዓት በግልጽ አውግዟል። በዚህም ምክንያት፣ ከቄርሎስ ተነሥቶ፣ በጢሞቴዎስ በኩል አልፎ፣ እስከ ሳዊሮስ ድረስ የዘለቀውን የማይለወጥና ወጥ የሆነ የአሠራር ሥርዓት በግልጽ ማየት እንችላለን።"¹¹
@pan_oriental_orthodox6