በሚያንማር ከእገታ ነፃ ወጥተው የነበሩ ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገራቸው የሚመልሳቸው አካል በመጥፋቱ ወደ አስፈሪ ካምፖች ሊመለሱ መሆኑን ተናገሩ‼️
በሚያንማር በእገታ ተይዘው ከባድ ስራ ካለ ክፍያ ሲሰሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያን በአንድ የአካባቢው ጦር ሀይል ከሳምንታት በፊት ነፃ ቢወጡም ወደ ሀገራቸው የሚመልሳቸው አካል በመጥፋቱ ወደ አስፈሪ ካምፖች ሊመለሱ መሆኑን ተናግረዋል።
"ወደ ሀገራችን ለመውጣት ዛሬ ነገ እያልን ወደ አስፈሪው ካምፓኒ ተመለሱ ተባልን" ብለው ለመሠረት ሚድያ ቃላቸውን የሰጡት ኢትዮጵያውያኑ አብዛኞቹ ተዳክመው የሞት አፋፍ ጭምር ላይ ያሉ እንደሚገኙ ተናግረዋል።
"በሚያንማር ተገደን የማጭበርበር ስራ ላይ የነበርንና በሚሊተሪ ድጋፍ ነጻ የወጣን ከ730 በላይ የምንሆን ኢትዮጵያዊን በሁለት የሚሊተሪ ካምፖች ሆነን የሀገራችን ምላሽና የማጓጓዝ ስራ ከተጠባበቅን ሁለተኛ ወራችን እያገባደድን እንገኛለን" የሚሉት ዜጎች ይህም ከካምፓኒ ለመውጣት ሲጠየቁ ከነበረው 5 ሺህ ዶላር ነጻ ያደረጋቸው እና የኢትዮጵያ መንግስትም ፓርኮቹ ድረስ ገብቶ ዜጎቹን ለማውጣት ተፈጥሮበት የነበረውን ፈተና ያቀለለ ምቹ አጋጣሚ ነበር ይላሉ።
"እዚህ ካምፕ በቆየንበት የሁለት ወር ጊዜ ውስጥ በየጊዜው ከኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የወላጆች ኮሚቴ ሒደቱ እየተሰራበት እንደሆነ በሚደርሱን መረጃዎች እየተጽናናን ቆይተናል፡፡ በመካከላችንም የቀዶ ጥገና የተሰራላቸውና ማገገም ያልቻሉ፣ በተፈጥሮ አደጋው አደጋ የደረሰባቸውና የሚፈሳቸው ደም አሁን ድረስ ያላቆመ፣ በአንጀት እና አንገት ህመም ራሳቸውን ችለው መንቀሳቀስ ማይችሉ እና ሌሎችም ጽኑ ህሙማን እንዳሉ እና በቂ ህክምና ማግኘት ማይቻልበት ጠረፍ ላይ መሆናችን ሰው እንዳናጣ እየሰጋን መሆኑን ለሚዲያዎች እና ለመንግስት ተቋማት እያሳወቅን የቆየን መሆናችን ይታወቃል" ብለው አስረድተዋል።
አክለውም "ሚሊተሪው የተያዘውን ምግብ ቢያቀርብም ከሀይማኖታችንና ከሀገራችን የአመጋገብ ባህል ጋር ፈጽሞ የማይሔድ የእስያ ምግብ በመሆኑ በውድ ዋጋ በሽያጭ የሚያቀርቧቸውን ምግቦች እየገዛን እንጠቀም ነበር። አሁን ግን ሁላችንም እጃችን ላይ የነበረንን ገንዘብ ጨርሰን ምግብና መድኃኒት ምንገዛበት የሌለን በመሆኑ ለረሀብ እና ለጤና ችግር ተጋልጠናል፡፡ ይህንን ሁሉ ችግር ያልፋል ብለን በኢትዮጵያ መንግስት እና ኤምባሲዎቹ እየተሰሩ ያሉ እኛን የመመለስ ስራ በተስፋ እየጠበቅን ባለንበት ወቅት ሁላችንንም ያስደነገጠ እና ተስፋችን የቀማን ችግር ተከስቷል፡፡"
"ይህም ከአረመኔያዊ አያያዝ አውጥቶ ካምፕ ውስጥ ያስገባን ሚሊተሪ የእለት ምግብ የሚለውን እያቀረበ የሀገራችን ምላሽ እየተጠባበቀ የነበረ ቢሆንም ከኢትዮጵያ መንግስት እና በኤምባሲዎቻችን በኩል እየተሰራ ያለው እኛን ወደ ሀገር የመመለስ ስራ እጅጉን የተጓተተ በመሆኑ እና ከ29 ሀገራት እኛ ብቻ በመቅረታችን ሚሊተሪው በኢትዮጵያ መንግሥት ተስፋ ቆርጦ ወዷ ካምፓኒዎች እንዲንመለስ ሊጠይቀን ችሏል" በማለት በሀዘን ያሉበትን ሁኔታ ለመሠረት ሚድያ አስረድተዋል።
"ይህም በብዙዎቻችን ላይ ትልቅ ሽብርና መደናገጥ የፈጠረ አደገኛ ክስተት ሆኖ ለጭንቀት የዳረገን ጉዳይ ነው። በመሆኑም ሚዲያዎች፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ኤምባሲዎች ለዚህ አደገኛ ሒደት ፈጣን ግብረ መልስ በመስጠት ወደ ሀገራችን መመለስ ካልቻሉ መቀልበስ የማንችለው የ735 ወጣት ህይወት አደጋ ውስጥ እየገባ እንደሆነ ማሳወቅ እንፈልጋለን" ብለዋል።
"የኢትዮጵያ መንግስት እኛን የመመለስ አቅም የለውም ወይ? መልሱ አዎ ከሆነ ተመልሰን እዛ ካምፓኒ ከምንገባ እዚሁ እራሳችንን እናጠፋለን፣ የመጨረሻ አማራጭ እሱ ነዉ፣ የመጨረሻ ዛሬ ተስፋ ቆርጠናል፣ ጭንቀታችን በርትቷል ስለዚህ መልስ እንፈልጋለን" በማለት ተናግረዋል።
እስራኤል የተባለ አንድ ኢትዮጵያዊ "አሁን በምንገኝበት ቦታ ላይ ምግብ በቀን አንዴ እና አልፎ አልፎ ሁለቴ ይሰጣሉ፣ የሚጠጣ ውሃ ስለሌላ የመጸዳጃ ውሃ ነው የምንጠጣው። የምንተኛው መሬት ላይ ነው፣ በረሀብ እና በህክምና እጦት እያለቀን ነው፣ እኛ ያለንበትን አካባቢ የሚያስተዳድረው DKBA (Democratic Karna Buddhist Arm) ይባላል። አካባቢው ያልተረጋጋ እና ጦርነት ያለበት ነው ስለዚህ ለእኛ ትልቅ ስጋት ፈጥሮብናል፣ ሌሎች አገራት ወጥተው አለቁ፣ ዛሬ ራሱ ዩጋንዳ አውጥቷል። ኢትዮጵያውያን ብቻ ቀርተዋል። ሌሎች አገራትን ሊያወጡ ሲመጡ ስንጠይቃቸው የኢትዮጵያ መንግሥት መልስ አይሰጥም ይሉናል" ብሏል።
"የሌሎች ሀገራት 40 እና 30 ዜጎች እየወጡ ነው፣ ነገር ግን የኢትዮጵያ መንግሥት ከ250 በላይ ዜጎች እያሉ ዝምታን መርጧል፣ መንግስት ለምን እንደዚህ ይጨክንብናል? እኛ ኢትዮጵያዊን አይደለንም። የደቡብ አፍሪካ መንግስት እዚህ ያሉ 3ቱንም ዜጎቹን ከትናንት በስትያ ፍለጋ መጥቶ ወስዳል፣ እኛስ?" ብሎ ጠይቋል።
@Esat_tv1@Esat_tv1