ኢትዮጵ


Kanal geosi va tili: Efiopiya, Amharcha
Toifa: Bloglar



Kanal geosi va tili
Efiopiya, Amharcha
Toifa
Bloglar
Statistika
Postlar filtri




Watch "ጥቁር ሚድያ / Tikur Media" on YouTube
https://youtube.com/channel/UCocJLpAzn-e-deqcd3wfPgA


በክፍል ሁለት ጽሁፋችን የኢየሱሳዊያንን (jesuits) ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ተከትሎ ህዝቡ የቆየ ሃይማኖቱን በሮም ካቶሊክ እምነት ላለመቀየር ያደረገውን ተቃውሞ ተመልክተን ነበር። ኢየሱሳዊያኑም ቢሆኑ የራሳቻውን ሃይማኖት በአገሬው ህዝብ ላይ ለመጫን ያደርጉ የነበረውን ጥረት ያክል የህዝቡን ኑሮ ከመሰረቱ ለመቀየር የሚረዱ የፈጠራና የለውጥ ትምህርቶችን ለማስተማር ያደረጉት ጥረት እዚህ ግባ የሚባል አልነበረም። በፖርቱጋሎች የተጻፉት የታሪክ መዛግብት በግልጽ እንደሚያሳዩት ኢየሱሳዊያኑ ሚሲዮኖች ትልቁ ትኩረታቸው የነበሩት ሃይማኖታዊ ጉዳዮች ነበሩ። ቅዳሜና እሁድን እንደ ሰንበት ተቀብሎ ያከብር የነበረውን የረጅም ዘመን የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታይ እሁድን ብቻ ሰንበት እንዲያከብር፣ ካህናቱ ሳያገቡ በድንግልና እንዲኖሩ ከማስተማር ባሻገር ሰለ ተሻሻለ የግብርና ዘዴ፣ ስለዘመናዊ የከብት እርባታ፣ስለ ደን ጥበቃ ዘዴ እና ስለ ዘመናዊ ገበያና መገበያያ አገሬውን ለማስተማር ፍላጎት አልነበራቸውም።

የጣናዋ ጀልባ
አንድ ፖርቱጋላዊ ከእንጨት የተጠረበ ጀልባ ሰርቶ በጣና ሀይቅ ላይ ይቀዝፍ ነበር። ይሁንና ኋላቀር በሆነ መንገድ ጀልባዎችን ሰርተው ይጠቀሙ የነበሩ የዘመኑ ሰዎች ይህን ዓይነቱን የቴክኖሎጂ ሽግግር ተከትለው የተሻሻለ ጀልባ ሰርተው ሲጠቀሙ አናስተውልም።
በሌላውም ዘርፍ ያየን እንደሆነ ሚሲዮናዊያኑ የራሳቸውን መኖሪያ በዘመናዊ መልክ በግንብ ይገነቡ የነበረ ሲሆን ፣ የአገሬው ህዝብ ግን ኑሮው እዛችው የሳር ጎጆ ውስጥ ነበር። ኢትዮጵያ ውስጥ በዘመኑ የነበሩት ኋላ ቀር የእርሻ መሳሪያ፣ የዲንጋይ ወፍጮ፣ የእንጨት ትራስ ዛሬም ድረስ በአንዳንድ አከባቢ በጥቅም ላይ ሲውሉ ማየት አገሪቱን የኢትኖሎጂካል ሙዚየም ያስመስላታል።
ፖርቱጋሎች እና ፖርቱጋሎቹ ከህንድ ያስመጧቸው ባለሞያዎች ጥለው ያለፏቸው ጥቂት የቴክኖሎጂ አሻራዎች ግን አልታጡም። ከነዚህም መካከል በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው ግንባታ ነው። ፖርቱጋሎች የገነቧቸው ቤተ-መንግሥቶች ፣ ድልድዮችና ቤቶች ዛሬም ድረስ በአንዳንድ ቦታ አሻራቸው አልጠፋም።

ዘመነ ጎንደር
የጎንደር ከተማ በ1636 ዓ.ም. መቆርቆር የፈጠራና ለውጥ እንቅስቃሴን ያነቃቃ ክስተት ነበር። በዘመኑ የተገነቡት የፋሲለደስና የሌሎቹም ነገሥታት ቤተ-መንግሥት የአዲስ ዘመን ጅማሮ ምልክቶች ነበሩ። የታዋቂው ተጓዥ ጀምስ ብሩስ ዘገባ ይህንን ሀሳብ የሚያጠናክር ሆኖ እናገኘዋለን። እንደ ጀምስ ብሩስ ዘገባ አጼ ኢያሱ ዳግማዊ ቤተመንግሥቱን ለማስጌጥና ለማስዋብ የግሪኮቹን እውቀትና ጥበብ በሚገባ ከመጠቀሙም ባሻገር እራሱ አጼ ኢያሱ ዳግማዊ በራሱ እጅ የግሪኮቹን መሳሪያዎች ተጠቅሞ የተለያዩ ሙከራዎችን ያደርግ ነበር። ለዚህም እንደምሳሌ ለመጥቀስ ኮምፓስ በመጠቀም ልክ እንደ ግሪኮቹ ሁሉ የኮከብ ምልክትን መሳል ችሎ ነበር።

አጼ ኢያሱ ቀዳማዊም እንዲሁ ለፈጠራና ለውጥ ትልቅ ፍላጎት የነበረው ንጉሥ ነበር። በካይሮ የፈረንሳይ ቆንጽል የነበረው De Maillet እንደጻፈለን ኢያሱ ቀዳማዊ ከካይሮ የተለያዩ ባለሞያዎች (ግንበኞች፣አናጺዎች፣አርክቴክቶች፣ የህክምና ባለሞያዎች፣ወዘተ) እንዲመጡለት ደብዳቤ ይለዋወጥ ነበር። ሌላው ምስክር ፈረንሳዊው ተጓዥ Charles Poncet በጻፈው ማስታወሻ እንደገለጸው አጼ ኢያሱ ወደ ጎንደር የመጡላቸውን መድኃኒቶች ምንነትና አጠቃቀማቸውንም ጭምር እየጠየቁ በጽሁፍ እንዲቀመጥ ያደርጉ ነበር። ከዚህም ባሻገር ንጉሡ የመድኃኒት አዋቂ አውሮፓዊያንን መድኃኒት እንዲቀምሙ በማዘዝ በምስጢር ተሸሽጎ የመድኃኒቶቹን የቅመማ ሂደት ይከታተል ነበር።
በቀጣይ የ19ኛውን መቶ ክፍለ ዘመን መባቻ ታሪክ እናነሳለን ።
ቸር ቆዩን!


​​#ፈጠራና_ለዉጥ_በኢትዮጵያ_ከጥንት_ጀምሮ_እስከ_1930ዎቹ
ክፍል 2

በመካከለኛው ዘመን በንጽጽር ኢትዮጵያ ለሌሎች ዓለማት ሥልጣኔ እና እውቀት በሯን መዝጋቷ የአገሪቱን የፈጠራና የለውጥ ጉዞ ተንፏቃቂ አድርጎት ነበር። በዘመኑ ምቹ የነበረው የዓየር ጠባይ የሚሰጠው ምርት ከበቂ በላይ በመሆኑ ጊዜው የደስታና የፈንጠዚያ ነበር ማለት ይቻላል። አንዳንዴ የዓየር ሁኔታው ሲዛባና ህዝቡ ለድርቅ ብሎም ለረሃብ ሲጋለጥ ሁኔታው ከፈጣሪ እንደተላከ ቁጣ ነበር የሚታየው። ይህም ችግሩ የፈጠራና የለውጥ አስተሳሰብ አብዮት እንዳይነሳ እንቅፋት ሆኖ ቆይቷል። ከዚህም በተጨማሪ እንደ ዘርዓያዕቆብ ዓይነት የኦርቶዶክስ ክርስትና ጥብቅ አማኝ ነገሥታት ከፈጠራና ለውጥ እንቅስቃሴ ይልቅ ለሃይማኖታዊ ጉዳዮች ያደሉ ነበሩ።

በዘመኑ ከውጭ ዓለማት ጋር ግንኙነት ለማድረግ ከሞከሩት ነገሥታት መካከል አጼ ይስሐቅ ተጠቃሽ ነው። የአጼ ይስሐቅ የውጭ ግንኙነትም ቢሆን በዋነኝነት ትኩረቱን ያደረገው በጦር መሳሪያና በወታደራዊ ጉዳዮች ላይ ነበር። ይህ ንጉሥ የቱርኪሽ ማምሉኮችን በመቅጠር ለወታደሮቹ ሥልጠና እንዲሰጡለት፣የተለያዩ የጦር መሳሪያዎች እንዲሰሩለትና የግብር ስርዓቱን እንዲያደራጁለት አድርጎ ነበር። ከዚህም በተጨማሪ በ1428 ዓ.ም. በዛሬዋ ስፔን አከባቢ ለምትገኘው የአራጎን ንጉሥ አፎንሶ የእጅ ሥራ ጥበበኞችን(artisan) እንዲልክለት የሚጠይቅ ደብዳቤ ጽፎ ነበር።

አጼ ልብነ ድንግል ለፖርቱጋሉ ንጉሥ ማኑኤል ቀዳማዊ በጻፈው ደብዳቤ የወርቅና የብር እንዲሁም የነሃስ ማንጠር ችሎታ ያላቸውን እና በነዚህ ማዕድናት ቤተክርስቲያንን ማስዋብ የሚችሉ ባለሞያዎችን እንዲልክለት ጠይቋል። አክሎም እኝህን ባለሞያዎች ቢልክለት ተንከባክቦ እንደሚይዛቸው እና ወደ አገራቸው መመለስ በፈቀዱ ጊዜም ያለምንም ችግር መመለስ እንደሚችሉ በእግዜብሔር ስም ቃል ገብቶለታል።
-Send masters who can make figures of gold and silver, copper, iron, tin, and lead, and send me lead for the churches; and masters of gilding with gold leaf, and of making gold leaf; and this soon, and let them come to remain with me here and in my favor. And when they may wish to return at their desire, I will not detain them and this I swear by Jesus Christ, Son of the Living God.”
ከዚህም በተጨማሪ አጼ ልብነ ድንግል ለንጉሥ ማኑኤል ቀዳማዊ ልጅ Joao III ተመሳሳይ ደብዳቤ ጽፎ ነበር።
የኋላ ኋላ በአህመድ ግራኝ ወረራ ጊዜ በ1541 ዓ.ም Christovao da Gama የተመራ 400 ወታደሮችንና 130 ባሮችን ያቀፈ ቡድን ከፖርቱጋል መጥቶ በጦርነቱ ላይ ድጋፉን ሰጥቷል። ከጦርነቱም በኋላ አጼ ገላውዲዎስ እነኝህን የውጭ ዜጎች አገር ውስጥ ለማስቀረት ትልቅ ጥረት ማድረጉን ታሪክ ይነግረናል። በዚሁ ጊዜ አጼ ገላውዲዎስ የቀጠራቸው የአርመን፣የግብጽ እና የሶሪያ ዜጎች በቤተመንግሥት ግንባታ ሥራ ላይ ተሳትፈው ነበር።

ዘመነ ሰርጸ-ድንግል
ሌላው በመካከለኛው ዘመን ከነበሩ የኢትዮጵያ ነገሥታት መካከል የተለያዩ ባለሞያዎችን ከውጭ አገር ለማስመጣት ሙከራ ያደረገው አጼ ሰርጸ-ድንግል ነው። አጼ ሰርጸ-ድንግል በ1589 ዓ.ም. ለፖርቱጋሉ ንጉሥ ፍሊፔ ዳግማዊ በጻፈው ደብዳቤ ፣ የተለያዩ የጦር መሳሪያ ሥራ እውቀት ያላቸውን ባለሞያዎች እንዲልክለት ጠይቆ ነበር። ከዚህም በተጨማሪ ሰርጸ-ድንግል በጉዛራ ቤተመንግሥት እንዲገነቡለት Garneau እና Arnaud የተባሉ ፈረንሳዊያን ባለሞያዎችን ቀጥሮ እንደነበር ይነገራል። የሰርጸ-ድንግል ወንድም ዘ-ድንግልም እንዲሁ ለንጉሥ ፍሊፔ ሶስተኛ የብረት ሥራ ባለሞያዎችን እንዲልክለት በደብዳቤ መጠየቁን ታሪክ ያወሳል።

ምጽአተ ኢየሱሳዊያን (jesuits)
የ16ኛው እና የ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያና የአውሮፓዊያን ግንኙነት ወደ አዲስ ምዕራፍ የተሸጋገረው የኢየሱሳዊያንን በ1557ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ተከትሎ ነው። የኢየሱሳዊያንን መምጣት ተከትሎ የአውሮፓን ድጋፍ እጅጉን ይሹ የነበሩት ዘ-ድንግል እና ሱስኒዮስ የሮማን ካቶሊክ እምነት ተቀበሉ። ነገር ግን ኢየሱሳዊያኑ ተስፋ እንዳደረጉት ሰፊው ህዝብ የሮም ካቶሊክ እምነትን ለመቀበል ፍቃደኛ አልነበረም። በዚህም የተነሳ ብዙ ደም አፋሳሽ አመጾች ተከስተው ነበር።

ከ1541-1633 ዓ.ም. በነበረው ዘመን ከፖርቱጋሎች ጥቂት እንቅስቃሴዎች በተቀር ኢትዮጵያ ከውጭ አገራት ጋር የነበራት ግንኙነት በአገሪቱ ኢኮኖሚ እንዲሁም በፈጠራና ለውጥ ላይ ያስከተለው ለውጥ እምብዛም ነው። በዘመኑ የነበሩ የአገሪቱ ነገሥታትም ከጦር መሳሪያ በቀር በሌሎች ቴክኖሎጂዎች ላይ ትኩረት ሲያደርጉ አይታይም። በሌላም በኩል ከውጪ የመጡትን ባለሞያዎች እውቀት ወደ አገር ልጅ የሚያሸጋግር ተቋም አልነበረም። የሰውም ሞያውን የመልመድ ፍላጎት ነበር ለማለት የሚያስደፍር አልነበረም።

ይቀጥላል


#ፈጠራና_ለዉጥ_በኢትዮጵያ_ከጥንት_ጀምሮ_እስከ_1930ዎቹ

በኢትዮጵያ ከጥንት እስከዛሬ የተለያዩ የፈጠራ ሥራ ሙከራዎችና የሥልጣኔ አሻራዎች ታይተዋል። ታዋቂው ልበ-ኢትዮጵያዊ የታሪክ ተመራማሪ ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት እኝህን የለውጥና የሥልጣኔ ጮራዎች፣ በተለይም ከመካከለኛው ዘመን ጀምሮ እስከ 1930ዎቹ የታዩትን በታሪክ መዝገብ ሰንደው አኑረውልናል። እኛም ለናንተ ለተወደዳችሁ አንባቢዎቻችን በሚመች መልኩ እንዲህ ወደ አማርኛ ቋንቋ መልሰን አሰናድተናል። መልካም ንባብ!
የኢትዮጵያ ተፈጥሯዊ መልክዓ-ምድር እና በተራሮች የተከበበች አገር መሆኗ አውሮፓዊያን አፍሪካን በተቀራመቱበት ዘመን (scramble for Africa) ነጻነቷን ጠብቃ ለረዥም ዘመናት እንድትኖር ረድቷታል። የዚህች አገር በቅኝ ያለመገዛት ታሪክ እንቆቅልሽ የሆነበት Daniel Thwaite የተባለ ጸሀፊ The Seething African Pot: A Study of Black Nationalism, 1882-1935 በተሰኘ መጽሀፉ ስለኢትዮጵያ ክብር እንዲህ ይላል፤
Ethiopia’s prestige in Africa consequent upon her triumphant success in repelling invasion, and in having remained unconquered throughout the centuries, is practically unfathomable. To the Africans in general, not only to those who invoked her as a liberator, she stands as a granite monument, a living exponent and testimony of the innate puissance of the black race, the shrine enclosing the last sacred spark of African political freedom, the impregnable rock of black resistance against white invasion, a living symbol, an incarnation of African independence.”
ይች የአፍሪካ ትንሳኤ ተምሳሌት ፣ የጥቁር ትግል አይበገሬነት ህያው ማሳያ ሲል ይህ ደራሲ የገለጻት አገራችን ኢትዮጵያ በብዙ መልኩ የሄደችበት የታሪክ መንገድ ከሌሎች የአፍሪካ አገራት የተለየ ነው። ይህም መሆኑ አገሪቱ በታሪኳ ያለፈችበት የፈጠራና ለውጥ (innovation and change) ሂደት የራሱ የሆነ አሉታዊም አውንታዊም ገጽታ እንዲኖረው አድርጎታል።

#ጥንታዊ_አክሱም
ይህ ዘመን በኢትዮጵያ የፈጠራና ለውጥ ታሪክ ውስጥ ወርቃማው ዘመን ነበር ሊባል ይችላል። በስነ-ህንጻው ዘርፍ የአክሱም ሀውልት በዘመኑ ኢትዮጵያዊያን የነበሩበትን የስነ-ህንጻ ደረጃ ሲያመላክት፣ በዘመኑ የነበረው የጽሁፍና የቋንቋ እድገት፣ በገንዘብ የመገበያየት ሥልጣኔ፣ ወዘተ የዘመኑን የእድገት ደረጃ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው።

የአክሱም ዘመን ኢትዮጵያ ለውጭው ዓለም እውቀትና ጥበብ በሯን የዘጋች አልነበረችም። ለዚህ እንደማሳያ በክብረ ነገሥት ላይ የሰፈረውን የንግሥት ሳባንና የንጉሥ ሰለሞንን ታሪክ ማንሳት ይቻላል። በዚህ ታሪክ ውስጥ ንግሥተ ሳባ ስለ ሰለሞን ጥበብ ሰምታ ለጥበብ ካላት ታላቅ ፍላጎት የተነሳ እየሩሳሌም ድረስ ተጉዛ ከንጉሥ ሰለሞን መገናኘቷን እናያለን። ከዚህም በተጨማሪ እንደ ዞስካለስ ዓይነቱ የአክሱም ነገሥታት የግሪክን ስነ-ጽሁፍ ጠንቅቀው ያውቁ እንደነበር በታሪክ ድርሳናት ተጽፎ እናገኛለን። ከዚህም በተጨማሪ የግሪክ ፊደላት በአክሱማዊያን ሳንቲሞች ላይ ታትመው ይታዩ ነበር። በአክሱማዊያን ኪነ-ህንጻ ላይም የግሪክ አማልክት የሆኑት ዜዉስ፣አሬስ እና ፖሴይዶን ተቀርጸው ይታያሉ።

በሀይማኖቱ ረገድ በአክሱም ዘመነ መንግሥት የታዩትን ለውጦች ስንመለከት፣ የአክሱም ዘመን ኢትዮጵያዊያን በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በንጉሥ ኢዛና ዘመነ መንግሥት ክርስትናን መቀበላቸውን በኋላም ከአረቡ አለም ለተሰደዱ መስሊሞች አምባ መጠጊያ መሆናቸውን ታሪክ ይነግረናል። በዚህ ጊዜ የአክሱም ንጉሥ የነበረው ንጉሥ አርማህ፣ እሱን ተማምነው የመጡትን የነብዪ መሐመድ ተከታዮች ከሳሾቻቸው አሳልፎ እንዲሰጣቸው ሲጠይቁት…..” የወርቅ ተራራ ብትሰጡኝ እንኳን እንኚህን ሰዎች አሳልፌ አልሰጣችሁም”። ነበር ያላቸው።
ንጉሥ አርማህ …..”የወርቅ ተራራ ብትሰጡኝ እንኳን እንኚህን ሰዎች አሳልፌ አልሰጣችሁም”።

#የአክሱማዊያን_የንግድ_ግንኙነት
የአክሱም ዘመን ኢትዮጵያ በመካከለኛው ምስራቅ ተጽዕኖ ፈጣሪ ከነበሩ አገራት መካከል ግንባር ቀደም ነበረች። ለጊዜውም ቢሆን ደቡብ አረቢያን ተቆጣጥረው የነበሩት አክሱማዊያን በታላላቆቹ ኢምፓየሮች ዘንድ ትልቅ ተቀባይነትን እና የዲፕሎማሲ ግንኙነት ጥያቄዎችን ያስተናግዱ ነበር። በዚህም ምክንያት በንግዱ ዘርፍ ከግብጽ፣ኑቢያ፣አረቢያ፣ ፐርሺያና ህንድ ግንኙነት የነበራቸው አክሱማዊያን መርከቦቻቸው ቀይ ባህርን እና የህንድ ውቂያኖስን አቋርጠው ሩቅ ተጓዦች ነበሩ።

በቀጣይ ክፍል የመካከለኛውን ዘመን ኢትዮጵያ የፈጠራና የለውጥ ታሪክ እንቃኛለን።


ፈጠራና ለዉጥ በኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ እስከ 1930ዎቹ
:
:
#ከምሽቱ 1 ሰዐት ላይ ይጠብቁን
@ethyoop
@ethyoop


#የገንዘብ_ታሪክ_በኢትዮጵያ

በኢትዮጵያ ገንዘብ አስቀርጸው መገበያየትን የጀመሩት የአክሱም ነገሥታት መሆናቸውን ታሪክ ያስረዳናል። በላይ ግደይ በ1983 ዓ.ም. ታትሞ በወጣውና ገንዘብ ባንክና መድኀን በኢትዮጵያ በተሰኘ መጽሀፋቸው ላይ በግልጽ እንዳሰፈሩት ከጥንት አክሱማዊያን ነገሥታት መካከል ንጉሥ ኢንደቢስና ንጉሥ አፊላስ የራሳቸውን ህጋዊ ገንዘብ አሳትመው በውጭና በውስጥ በገንዘብ አማካኝነት ይገበያዩ ነበር። ይህም የአክሱማዊያን ስልጣኔ በዘመኑ ምን ደረጃ ላይ ደርሶ እንደነበር ከሚመሰክሩ ጉዳዮች አንደኛው ነው። አክሱም በጊዜው ከነበሩ አራት ታላላቅ ሥልጣኔዎች መካከል አንዷ እንደነበረች ባዕዳን ሳይቀር የመሰከሩት ሀቅ ነው። በዚህም ከፋርስ እስከ ቻይና ከአረቢያ እስከ ሮም የተዘረጋ የውጭ ግንኙነትን አክሱማዊያን መመስረት ችለው ነበር።
ከንጉስ ኢንደቢስና ከንጉሥ አፊላስ ውጪ ብዙ አክሱማዊያን ነገሥታት ገንዘብ አሳትመው እንደነበር ቢታወቅም በዚህ ረገድ ስሙ ጎልቶ የሚነሳውና የሐበሻ ቆስጠንጢኖስ እየተባለ የሚጠራው ገናናው ንጉሥ ኢዛና ነው። የንጉሥ ኢንደቢስና የንጉስ አፊላስ ገንዘቦች በአንደኛው ገጽ የራሳቸው ምስል በገብስና በስንዴ ዛላ ተከበው በሌላው ገጽ ደግሞ የጸሀይና የጨረቃ ምስልና አንዳንዴም አጭር ምሳሌያዊ ንግግር ተቀርጸውባቸው ይገኛሉ። እነኚህ ሳንቲሞች በጥቂቱ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም ይገኙ እንጂ አብዛኛዎቹ በውጪው ዓለም ተበትነዋል። በተለይም በኤደን (የመን) ብዙ የአክሱማዊያን ገንዘቦች ይገኛሉ። በላይ ግደይ በመጽሀፋቸው የዚህን ምክንያት ሲያስቀምጡ አክሱማዊያን በጊዜው የምንንም ይገዙ ስለነበር ለወታደር ደሞዝ ሊከፈል የሄደ ገንዘብ ሳይሆን አይቀርም ይላሉ። የንጉሥ ኢዛናን ገንዘብ ስንመለከት ሁለት አይነት ገንዘቦችን እናገኛለን። ንጉሡ ክርስትናን ከመቀበሉ በፊት ያሳተመው ገንዘብ የነበረው ሲሆን ክርስትናን ከተቀበለ በኋላ ደግሞ የመስቀል ምልክትን ያካተተ ገንዘብ አሳትሟል። በዚህም በዓለም የመስቀል ምልክትን በገንዘቡ ላይ ያሳተመ ቀደምት ንጉሥ ለመሆን በቅቷል።
የአክሱማዊያን ስልጣኔ ከጠፋ በኋላ ኢትዮጵያ ዓለምን ረስታ ዓለምም ኢትዮጵያን ረስቶ ዘመናት አልፈዋል። በዚህ መካከል ኢትዮጵያ ገንዘብ አሳትማ ከመገበያየት ስልጣኔ ወርዳ እቃን በእቃ በመለወጥ የግብይት ሂደት ውስጥ ረዥም ዘመናትን ካሳለፈች በኋላ በመካከሉ ማሪያ ትሬዛ ታለር የተባለው የመገበያያ ገንዘብ በጎረቤት ሀገሮች በኩል በነጋዴዎች አማካይነት ወደ ኢትዮጵያ ገብቶ ዋና የመገበያያ ገንዘብ ሊሆን ቻለ። ይህ ገንዘብ እ.አ.አ. በ1751 ዓ.ም ለኦስትሪያዋ ንግሥት መታሰቢያ የወጣ ገንዘብ ነበር። ይህ ታላቅ ተወዳጅነትን ያተረፈው ገንዘብ በአዋጅ በኢትዮጵያ ገንዘብ እስከተተካበት 1937 ዓ.ም. ድረስ በስፋት ለረዥም ጊዜ ሲያገለግል ቆይቷል።

አጼ ምንሊክ እና አጼ ኃ/ሥላሴ ያወጡት ገንዘብ

አጼ ምንሊክ በዘመናቸው ስላሳተሙት ገንዘብ ባላምባራስ መኅተመ ሥላሴ ወልደ መስቀል በዝክረ ነገር መጽሀፋቸው ይህን ብለዋል።

"ከ፲ ፱ ፻ ፩(1901) ፡ ዓ ፡ ም ፡ በፊት ፡ ምንም ፡ ቀደም ፡ ብሎ ፡ በነምሳዋ ፡ ንግ ሥት ፡ በማሪ፡ ቴሬዝ ፡ መልክ ፡ የታተመ ፡ የብር ፡ ገንዘብ ፡ በኢትዮጵያ ፡ ቢታወቅ ፤ አብዛኛው ፡ ሕዝብ ፡ ይሻሻጥና ፡ ይገዛዛ ፡ የነበረው ፡ በጥ ይትና ፡ ባሞሌ ፥ ሸቀጥ ፡ በመለዋወጥ ፡ ነበር ፤ ኋላ ፡ ግን ፡ ዐፄ ፡ ምኒልክ ፡ ባንድ ፡ ንጉሠ ፡ ነገሥት ፡ መንግሥት ፡ የሚኖር ፡ ሕዝብ ፡ በየጐጡ፡ እንደ ፡ ፈቀደውና ፡ እንደ ፡ ወደደው ፡ መተዳደር ፡ የያዘው ፤ መንግ ሥት ፡ አስቦ ፡ ተፈላጊ ፡ የሆነውን ፡ ባያደራጅለት ፡ ነው ፡ ብለው ፡ ለመ ላው ፡ ሕዝባቸው ፡ አንድነትን ፡ ሰጥቶ ፡ ያስተዳደሩንም ፡ ሥራ ፡ ምቹ ፡ ለማድረግ ፡ በመልካቸውና ፡ በስማቸው ፡ ገንዘብ ፡ አሳትመው ፡ በዚሁም ፡ ሕዝቡ ፡ እንዲገበያይበት ፡ ባ፲ ፱ ፻ ፩(1901) ፡ ዓ ፡ ም ፡ ቀጥሎ ፡ ያለውን ፡ ዐዋጅ ፡ ኣደረጉ ።
በኢትዮጵያ ፡ የመገበያያ ፡ ገንዘብ ፡ ብር ፡ እንዲሆን ፡ የተነገረ ፡
ዐዋጅ ።
ሞአ ፡ አንበሳ ፡ ዘእምነገደ ፡ ይሁዳ ። ምኒልክ ፡ ሥዩመ ፡ እግዚአብሔር ፡
ንጉሠ ፡ ነገሥት ፡ ዘኢትዮጵያ ። ከዚህ ፡ ቀደም ፡ ነጋዴም ፥ ወታደርም ፡ ባላገርም ፡ የሆንክ ፡ ሰው ፡ ሁለ ፡ በየገበያውና ፡ በየመንገዱ ፡ በስፍራውም ፡ ሁሉ ፡ በጥይት ፡ ስት ገበያይ ፡ ትኖር ፡ ነበር ፤ አሁን ፡ ግን ፡ በኔ ፡ መልክና ፡ ስም ፡ የተሠራ ፡ ብር ፣ አላድ ፣ ሩብ ፣ ትሙን ፤ መሓለቅ ፡ ኣድርጌልኻለሁና ፡ በዚህ ፡ ተገ በያይ ፡ እንጂ ፡ እንግዴህ ፡ በጥይት ፡ መገበያየት ፡ ይቅር ፡ ብያለሁ ፡ የሚሸጥም ፡ ጥይት ፡ ከቤቱ ፡ ያለው ፡ ሰው ፡ ሁሉ ፡ እጅምሩክ ፡ እየወሰደ ፡ ለጅምሩክ ፡ ሹም ፡ ይስጥ ፣ ጥይትም ፡ ለመግዛት ፡ የፈለገው ፡ ሰው ፡ እጅ ምሩክ ፡ እየሄደ ፡ ይግዛው ፤ ይኸንንም ፡ ዐዋጅ ፡ አፍርሶ ፡ ጥይት ፡ ርስ ፡ በራሱ ፡ ሲሻሻጥና ፡ ሲገዛዛ ፡ የተገኘ ፡ ሰው ፤ ገዥውም ፡ ሻጭውም ፡ ስለ ቅጣታቸው ፡ ባ፩(1) ፡ ጥይት ፡ ፩ ፡ ፩ ፡ ብር ፡ ይክፈሉ ፤ ይህነንም ፡ ዐዋጅ ፡ አፍርሶ ፡ ጥይት ፡ ሲሻሻጥ ፡ አግኝቶ ፡ ወደ ፡ ዳኛ ፡ ያመጣ ፡ ሰው ፡ በቅ ጣት ፡ ከሚከፍሉት ፡ ገንዘብ ፡ እኩሌታውን ፡ ሊያዥው ፡ መርቄለታለሁ።
(ኅዳር ፡ ፳ ፪ (22) ፡ ቀን ፡ ፲ ፱ ፻ ፩ (1901) ፡ ዓ፡ ም ፡ እንጦጦ ፡ ከተማ ፡ ተጻፈ ።)
አዲሱ ፡ ገንዘብ ፡ የተሠራው ፡ ከብር ፡ ስለ ፡ ሆነ ፤ በራሱ ፡ ዋጋ ፡ ያ ለው ፡ በመሆኑ፡ ጭምር ፡ በመላው ፡ ግዛታቸው ፡ በፍጥነት ፡ ያለችግር ፡ ታወቀ ። አንድ፡ ብር፡ ሁለት ፡ አላድ ፡ አራት ፡ ሩብ ፡ ስምንት ፡ ትሙን ፡ ዐሥራ ፡ ስድስት ፡ መሐለቅ ፡ ይመነዘራል ።ይኸም፡ ለማንኛቸውም፡ ጕዳይ ፡ በገበያ ፡ ላይ ፡ ለመገበያየት ፡ የተ መቸ ፡ በመሆኑና ፡ ቢያስቀምጡት ፡ ስለማይበላሽ ፥ በሕዝቡ ፡ ዘንድ ፡ በጣም፡ የተወደደና ፡ የተፈለገ ፡ ሆነ ።
ከዚያም ፡ ወዲህ ፡ በን ፡ ነ ፡ ዘውዲቱ ፡ ዘመን ፡ ለመንግሥትም ፡ ለድኻም ፡ የተመቸ ፡ እንዲሆን ፡ በማሰብ ፡ ቤሳ ፡ የተባለ ፡ ከመዳብ ፡ የተ ሠራ ፡ የብር ፡ ፴ ፪ኛ(32ኛ) ፡ ባፄ ፡ ምኒልክ ፡ መልክ ፡ ታተመ ። ቀጥሎም፣ በባንክ ፡ በኩል ፡ በሁለት፣ ባምስት ፤ባሥር፤ ባምሳ፣ባንድ፡ መቶ፤ ባምስ መቶና ፡ ባንድ ፡ ሺሕ፡ ብር ፡ ሒሳብ ፡ የታተመ ፡ ባንክ ፡ ኖት ፡ የተባለ - የገንዘብ ፡ ወረቀት፡ ወጣ ።
ግርማዊ ፡ ቀዳማዊ ፡ ኃይለ ፡ ሥላሴ ፡ የንጉሠ ፡ ነገሥት ፡ ዘውድ ፡ በጫኑ ፡ ዘመን ፡ ባ፲ ፱ ፻ ፳ ፫(1923) ፡ ዓ ፡ ም ፡ ግን ፡ በጣም ፡ ተሻሽሎ ፡ እንደ ፡ ዓለም ፡ ሕግ ፡ ሁሉ ፡ በሳንቲም ፡ የሚታሰቡ ፡
መቶ ፡ ሳንቲም ፡(አንድ ፡ ብር) ፡
አምሳ ፡ ሳንቲም ፡(አላድ)
ካያ፡አምስት፡ ሳንቲም ፡ (ሩብ)
ዐሥር ፡ ሳንቲም
አምስት ፡ ሳንቲም
አንድ ፡ሳንቲም ኒኬል፡ የሆኑ ፡ ገንዘቦች ፡ በግርማዊነታቸው፡መልክና፡ ስም፡ታትመው ፡ ጠላት፡በኢትዮጵያ፡እገባ፡ ድረስ፡ እስካ፱ ፻ ፳ ፰ ፡ ዓ ፡ ም ፡ ሕዝቡ፡ በደስታ፡ ተቀብሎ ፡ ሲገበያይባቸው : ቈይቷል ።"

ይቀጥላል


#የገንዘብ_ታሪክ_በኢትዮጵያ

:
:
:
:
:
:
°
°
°
#ዛሬ_ማታ


#ኢትዮጵ
ኢትዮጵያ በራሷ ቀመር ጊዜን የምትቆጥር አገር ናት። በዚህም መሰረት ከአስራ ሁለቱ ባለሰላሳ ቀናት ወራት በተጨማሪ አስራ ሶስተኛ ወርም አላት። ለዚህም ነው የአስራ ሶስት ወር ጸጋ ሀገር መባሏ። ይህች ወር ጷጉሜን ትባላለች። ይህቺ የዘመን ድልድይ የሆነች ወር አምስት፣ ሲሻት ስድስት፣ አልፎም ሰባት ቀናት የምትሆንበት ጊዜ አለ። ለመሆኑ ጳጉሜን ከዬት መጣች? ጥንተ መሰረቷስ ምንድነው? ለዚህ ጥያቄ መልስ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት የዳንኤል ክብረት እይታዎች በሚለው ጦማሩ ላይ “ጳጉሜን - አምስት፣ ስድስት፣ ሰባት” በሚል ርዕስ ያሰፈረው ጽሁፍ ይህን ይላል።
“ጳጉሜ ማለት በግሪክ ‹ጭማሪ› ማለት ሲሆን ዓመቱን በሠላሳ ቀናት ስንከፍለው የሚተርፉትን ዕለታት ሰብስበው የሰየሟት ተጨማሪ ወር ናት፡፡ ወይም በየዕለቱ በፀሐይና በጨረቃ አቆጣጠር መካከል የሚፈጠረውን ልዩነት ሰብስበው ያከማቹባት ወር ትባላለች፡፡ ዓመቱ በዐውደ ፀሐይ ሲለካ 365 ቀናት ከ15 ኬክሮስ 6 ካልዒት ሲሆን በጨረቃ ሲለካ ደግሞ 354 ቀናት ከ22 ኬክሮስ፣ 1 ካልዒት፣ 36 ሣልሲት፣ 52 ራብዒት፣ 48 ኀምሲት ነው፡፡ (60 ኬክሮስ አንድ ቀን ነው)በሁለቱ መካከል(በፀሐይና በጨረቃ) በዓመት ውስጥ ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ7 ኬክሮስ ይሆናል፡፡ [በነገራችን ላይ በዘመን አቆጣጠራችን ውስጥ ከዕለት በታች የምንቆጥርባቸው ስድስት መለኪያዎች አሉ፡፡ ኬክሮስ፣ ካልዒት፣ ሣልሲት፣ ራብዒት፣ ኀምሲትና ሳድሲት፡፡ 60 ሳድሲት አንድ ኀምሲት፣ 60 ኀምሲት አንድ ራብዒት፣ 60 ራብዒት አንድ ሣልሲት፣ 60 ሳልሲት አንድ ካልዒት፣ 60 ካልዒት ደግሞ 1 ኬክሮስ ይሆናል፡፡ 60 ኬክሮስ ደግሞ 1 ዕለት፡፡ 1 ኬክሮስ 24 ደቂቃ ነው]
ጳጉሜን ለማግኘት የሚጠቅመን የየዕለቱን ልዩነታቸውን መመልከቱ ነው፡፡ በየዕለቱ በጨረቃና በፀሐይ መካከል 1 ኬክሮስ 52 ካልዒት(60 ካልዒት አንድ ኬክሮስ ነው)፣ ከ 31 ሣልሲት(60 ሣልሲት አንድ ካልዒት ነው) ይሆናል፡፡[ይህም ማለት 5 ሰዓት ከ48 ደቂቃ ከ46 ካልዒት(ሴኮንድ?)] ይህ ልዩነት በአንድ ወር ምን እንደሚደርስ ለማወቅ በ30 እናባዛው፡፡ 30 ኬክሮስ፣ 1560 ካልዒት፣ ከ930 ሣልሲት ይሆናል፡፡ የዓመቱን ለማግኘት ደግሞ በ12 እናባዛው፡፡ 360 ኬክሮስ(፩)፣ 18720 ካልዒት(፪)፣ 11160 ሣልሲት(፫) ይመጣል፡፡
ቀደም ብለን 60 ኬክሮስ አንድ ዕለት ይሆናል ባልነው መሠረት 360 ኬክሮስ ለ60 ሲካፈል 6 ዕለታትን ይሰጠናል(፩)፡፡ 18720 ካልዒትን(፪) በስድሳ በማካፈል 312 ኬክሮስን እናገኛለን፡፡ ያም ማለት ትርፉን 12 ኬክሮስ ትተን 300ውን ኬክሮስ ለ60 በማካፈል 5 ዕለት እናገኛለን፡፡ ይኼም ማለት 5 ዕለት ከ12 ኬክሮስ(፬) ይሆናል፡፡ 11160 ሣልሲትን(፫)ለ60 ብናካፍለው 186 ካልዒት ወይም ደግሞ 3 ኬክሮስና 6 ካልዒት(፭) ይሆናል ማለት ነው፡፡
ከላይ ኬክሮስን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነው(፩) 6 ዕለት አለ፡፡ ይኼ ዕለት ሕጸጽ ይባላል፡፡ ፀሐይና ጨረቃን እኩል መስከረም አንድ ላይ ዓመቱን ብናስጀምራቸው ፀሐይ የወሯ መጠን ምንጊዜም ሠላሳ ሲሆን ጨረቃ ግን በአንደኛው ወር 29 በሌላኛው ወር ግን 30 ስለምትሆን ዓመቱ እኩል አያልቅም የጨረቃ ዓመት ነሐሴ 24 ቀን ያልቃል፡፡ ይህም ማለት ጨረቃ በሁለት ወር አንድ ጉድለት ታመጣለች፡፡ ያንን ነው ሊቃውንቱ ሕጸጽ(ጉድለት) ያሉት፡፡ በዚህም መሠረት ከላይ ኬክሮሱን(፩) በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነውን 6 ዕለት ለጨረቃ ሕጸጽ ስንሰጠው የመስከረም/ ጥቅምት (1)፣ የጥቅምት/ ኅዳር(2)፣ የጥር/ የካቲት(3)፣ የመጋቢት/ ሚያዝያ(4)፣ የግንቦት/ ሰኔ (5)፣ የሐምሌ ነሐሴ (6) ሆነው ተካፍለው ያልቃሉ፡፡
በሌላም በኩል ደግሞ በጨረቃና በፀሐይ ዑደት መካከል በዓመት ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) ይሆናል፡፡ ስድስቱን ዕለታት ጨረቃ ለምታጎልበት (ሕጸጽ) ብንሰጠው ቀሪ 5 ዕለት ይኖረናል፡፡ ጳጉሜ ማለት እነዚህ 5 ቀናት ናቸው፡፡ አሁን የአሥራ አንዱን ዕለታት ከፈጸምን ሽርፍራፊዎቹን (15 ኬክሮስና 6 ካልዒት) እንይ፡፡
ከላይ እንዳየነው በፀሐይና ጨረቃ ዓመታት መካከል የተፈጠሩትን 11 ቀናት ስድስቱ ለሕጸጽ ማሟያ ሲገቡ የቀሩት 5 ዕለታት ናቸው ጳጉሜ የምትባለውን ወር በመሠረታዊነት የፈጠሯት፡፡ በጎርጎርዮሳውያኑ አቆጣጠር እነዚህ 5 ተጨማሪ ዕለታት በጃንዋሪ፣ ማርች፣ ሜይ፣ ጁላይና ኦገስት ላይ ስለተጨመሩ እነዚህ ወራት 31 ለመሆን ተገድደዋል፡፡ (ይህንን የከፈለው በ46 ቅልክ የነበረው ዩልየስ ቄሣር ነው፡፡ ለአራቱ ወሮች 30 ቀን፣ ለአንዱ 28/29 (በየአራት ዓመቱ)፣ ለቀሩት ሰባት ወሮች ደግሞ 31 ሰጥቷቸዋል፤ ለአምስቱ ወሮች 31 ያደረጋቸው ከጳጉሜ ወስዶ ሲሆን ለሁለቱ ወሮች አንዳንድ ቀን የጨመረላቸው ከፌቡርዋሪ 2 ቀናት ወስዶና ወሩን 28 አድርጎ ነው)፡፡
ከእንግዲህ የሚቀሩን ከላይ የየዕለቱን ልዩነት ለዓመት ስናባዛ (ቁጥር ፪ና ፫ ተመልከት) የቀሩን 15 ኬክሮስና 6 ካልዒት ናቸው፡፡ ሁለቱን ከላይ ያየናቸውን (፬ና፭) ስንደምራቸው (12 ኬክሮስ + 3 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) 15 ኬክሮስ ከ 6 ካልዒት ይመጣሉ፡፡
ቀደም ብለን አንድ ዕለት 60 ኬክሮስ ነው ብለናል፡፡ ስለዚህም አንድ ዕለት (60 ኬክሮስ) ለማግኘት ከላይ ያገኘነውን 15 ኬክሮስ በ 4 ማባዛት አለብን፡፡ በአራት ዓመት አንዴ ጳጉሜ 6 የምትሆነው እነዚህ በየዓመቱ የተጠራቀሙት 15 ኬክሮሶች አንድ ላይ መጥተው በአራት ዓመት አንድ ጊዜ አንድ ዕለት ስለሚሆኑ ነው፡፡ እርሷም ሠግር(leap year) ትባላለች፡፡ ጎርጎርዮሳውያኑ ይህቺን ሠግር በፌቡርዋሪ ወር ላይ ጨምረው ወሩን በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ 29 ቀን ያደርጉታል፡፡
15ቱ ኬክሮስ በአራት ዓመት ተደምረው አንድ ዕለት መጡና በአራት ዓመት አንዴ ጳጉሜን ስድስት አደረጓት፡፡ የቀረችው 6 ካልዒትስ (ቁጥር ፭) የት ትግባ?
ካልዒት አንዲት ዕለት ትሆን ዘንድ 3600 ካልዒት ያስፈልጋሉ፡፡ ይህንን ያህል ካልዒት ለማግኘት 600 ዓመታት ያስፈልጉናል፡፡ ለዚህ ነው ጳጉሜ በየስድስት መቶ ዓመታት ሰባት የምትሆነው፡፡ እስካን የጠየቅኳቸው የባሕረ ሐሳብና የታሪክ ሊቃውንት በታሪካችን ውስጥ ጳጉሜን 7 የሆነችበትን ዘመን እንደማያውቁ ነግረውኛል፡፡ ሒሳቡ ሲሰላ በየ 600 ዓመቱ ሰባት ትሆናለች ቢባልም አስቦ በስድስት መቶኛው ዓመት ሰባት የሚያደርጋት እንደሌለ ይናገራሉ፡፡ በፈረንጆቹ ብሂል ‹ፌብሩዋሪ 30› ማለት የመሆን ዕድል ያለው ነገር ግን ሆኖሞ የማያውቅ ሊሆንም የማይችል(possible but never happen)› ተደርጎ እንደተወሰደው ሁሉ ምናልባት በኛም ጳጉሜን 7 ማለት እንደዚያው ይሆን ይሆናል፡፡


የጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት አጠቃላይ መረጃ

የጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ሁለት ዞኖችንና ስምንት ወረዳዎችን አካቷል፡፡

የስፍራው አቀማመጥ
ክልሉ በኢትዩጵያ ምእራባዊ ጫፍ አካባቢ የሚገኝ ሲሆን፣ በምእራብ ደቡብና ሰሜን ሱዳንን ሲያዋስን፣ በደቡብና በምስራቅ ደግሞ የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች ብሄራዊ ክልላዊ መንግስትን ያዋስናል፣ እንዲሁም የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በሰሜንና ምስራቅ ያዋስኑታል፡፡
ርእሰ ከተማ
የክልሉ ርእሰ ከተማ ጋምቤላ ነው፡፡

የቆዳ ስፋት
ክልሉን በቅርቡ የተቀላቀለውን ወረዳ ሳይጨምር የክልሉ የቆዳ ስፋት 25‚274 ኪ.ሜ ይደርሳል፡፡

ስነ-ህዝብ
በ1987 በተደረገው የህዝብ ቆጠራ መስረት፣ የህዝብ ብዛቷ 182.862 ሲሆን ከነዚህ ውስጥም 92‚090 የሚሆነው ወንዶች ሲሆን 88‚960 ደግሞ ሴቶች ናቸው፡፡
153‚438 /84.9%/ የሚሆነው ህዝብ በክልሉ በገጠራማ ቦታዎች ውስጥ የኖራል፡፡
ዋና ዋናዎቹ የክልሉ ብሄረሰቦች ኑዌር፣ አኙዋክ፣ መዘንገር፣ አፓና እና ኮሞ ይባላሉ፡፡ በተጨማሪም የኦሮሞ፣ አማራ፣ ከምባታ፣ ከፉ፣ ትግሬ እና ሌሎችም ብሄረሰቦች በክልሉ ይኖራሉ፡፡
ከጠቅላላው የህዘብ ስብጥር 46 ከመቶ ኑዌር፣ 27 ከመቶ አኙዋክ፣ 8 ከመቶ አማራ 6 ከመቶ ኦሮሞ፣ 5.8 ከመቶ መዠንገር፣ 4.1 ከመቶ ከፋ ፣ 2 ከመቶ ሞካ ፣ 1.6 ከመቶ ትግሬ እና 5.5 ከመቶ የሚሆነው ደግሞ ከደቡብ ህዝቦች ናቸው፡፡

አማርኛ የክልሉ የስራ ቋንቋ ነው፡፡
የተለያዩ እምነት ተከታዬች የሚኖሩበት ክልል ነው፡፡ 44 ከመቶ የኘሮቴስታንት፣ 24.1 ከመቶ የኦርቶዶክስ፣ 10.3 ከመቶ የባህላዊ ሀይማኖት ፣ 5.1 ከመቶ የእስልምና፣ 3.2 ከመቶ የካቶሊክ እና 12.7 ከመቶ የሌሎች ሀይማኖት ተከታዮች ይኖሩበታል፡፡

ዋነኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች
አብዛኛው የክልሉ ህዝብ አርብቶ አደር ነው፡፡ በአንዳንድ የክልሉ አካባቢዎች ሰሊጥና ሌሎች የቅባት ክህሎችን፣ ማንጐ፣ ሙዝና ወዘተ በማምረት ይተዳደራሉ፡፡
የመሬት አቀማመጥ እና የአየር ንብረት
ክልሉ በአብዛኛው ጠፍጣፋ የመሬት አቀማመጥ ሲኖረው፣ እርጥበት ያለው ሞቃት የአየር ንብረትን ይዟል፡፡
ለ17 አመት የተመዘገበው አመታዊ የአየር ንብረቱ 615.9 ሚ.ሜ ሲሆን፣ 21.12ocዝቅተኛ እና 35.9ocከፍተኛ የሙቀት መጠን በአማካኝ ተመዝግቦል፡፡

ወንዞችና ሀይቆች
ባሮ የተባለው፣ በኢትዮጵያ ሙስጥ ብቸኛው ለመጓጓዣ የሚያገለግለው ወንዝም በዚሁ ክልል ነው የሚገኘው፡፡ ወንዙ ክልሉን ከሱዳን ጋር ያገናኛል፡፡

ቱሪዝምና ቅርሶች
የጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ በክልሉ የሚገኝ የቱሪስት መሰህብ ነው፡፡ በተጨማሪም እንደ ዝሆን፣ ጐሽ፣ ዝንጀሮና በቀቀን የመሳሰሉ የዱር እንሰሳት ይገኙበታል፡፡




ኢትዮጵ
የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት አጠቃላይ መረጃ


የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በ10 አሰተዳደራዊ ዞኖች፣ በአንድ ልዩ ዞን፣ በ105 ወረዳዎች እና በ78 የከተማ ማዕከሎች የተዋቀረ ነው፡፡ አማርኛ የክልሉ የስራ ቋንቋ ነው፡፡

የስፍራው አቀማመጥ
የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በሰሜናዊ-ምዕራብ እና በመሀከለኛው ሰሜን የኢትዮጵያ ክፍል የሚገኝ ሲሆን ክልሉ በሰሜን ከትግራይ ክልል፣ በምስራቅ ከአፋር ክልል፣ በደቡብ ከኦሮሚያ ክልል፣ በደቡብ-ምዕራብ ከቤኒሻንጉል-ጉምዝ ክልል እንዲሁም በደቡብ ከሱዳን ሪፐብሊክ ጋር ይዋሰናል፡፡

የቆዳ ስፋት
የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት 170‚752 ስኩ.ኪ.ሜ የሚገመት የቆዳ ስፋት ይሸፍናል፡፡

ርእሰ ከተማ
ባህር ዳር የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ርእሰ ከተማ ነች፡፡

ስነ-ህዝብ
በ1994 በተገኘው የህዝብ ቆጠራ መሰረት የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት የህዝብ ብዛት 13,834,297 ሲሆን ከዚህም ውስጥ 6,947,546 ወንዶች እና 6,886,751 ሴቶች ናቸው፡፡ ይህ እንዳለ ሆኖ 1‚265‚315 በከተሞች ኗሪ ሲሆን 12‚568‚982 በገጠራማው የክልሉ ቦታዎች ይኖራል ይህም ከአጠቃላዩ የህዝብ መጠን 90 ከመቶ የሸፍናል፡፡
በሀይማኖት ረገድም 81.5% የኦርቶዶክስ ክርስትያን፣ 18.1% የእስልምና እና 014% የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ ነው፡፡
በብሄር ስብጥር አኳያም 91.2% የአማራ፣ 3% የኦሮሞ፣ 2.7% የአገው/አዊ፣ 1.2% የቅማንት እና 1% የአገው/ካምይር ብሄረሰቦች ይኖራሉ፡፡

ዋነኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች
በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስትከሚገኘው ህዝብ 85% የሚሆነው በግብርና ስራ ላይ የተሰማራ ነው፡፡ ክልሉ የጤፍ ምርትን በዋነኛነት ከሚያመርቱ ክልሎች አንዱ ነው፣ ከዚህም በተጨማሪ ገብስ፣ ስንዴ፣ የቅባት እህሎች፣ ማሽላ፣ ለውዝ፣ ሽንብራና ባቄላ በከፍተኛ ደረጃ የሚመረቱ ሰብሎች ናቸው፡፡
እንደ ጥጥ፣ ሰሊጥ፣ ሱፍ እና የሸንኮራ አገዳ የመሳሰሉት የአገዳ ሰብሎችም በሰፊውና በድንግሉ የክልሉ ቆላማ ለም መሬት ላይ ይመረታሉ፡፡
ከጣና ሀይቅና አባይ ወንዝን ከመሳሰሉ ትላልቅ ተፋሰሶች የሚገኘው የውሀ ሀብት ለክልሉ የመስኖ እርሻ ትልቅ አስተዋፅኦ ያበረክታሉ፡፡
ከክልሉ የመሬት ሀብት 450‚000 ሄክታር የሚሆነው ለእርሻና ለመስኖ ስራ በተለይም ለፍራፍሬና ለአበባ ምርት የተመቸ ነው፡፡
የመሬት አቀማመጥ እና የአየር ንብረት
የአማራ ክልል ከመሬት አቀማመጥ አንፃር ሲታይ በሁለት ዋናዋና ክፍሎች ይመደባል እነሱም የከፍተኛ ተራራማ አካባቢዎች እና የዝቅተኛ ቦታዎች ናቸው፡፡
የከፍተኛ ቦታዎቹ ከባህር ጠለል በላይ ከ1‚500 ሜትር በላይ ሲገኙ የክልሉን ሰሜናዊ እና ምስራቃዊ ቦታዎች ይሸፍናሉ፡፡ እነዚህ ከፍተኛ ቦታዎች በሰንሰላታማ ተራራዎች የተከበቡ ናቸው፡፡
በ4620 ሜትር ከፍታ ላይ የሚገኘው የራስ ደጀን ተራራ ኢትዮጵያ ውስጥ ትልቁ የተራራ ከፍታ ሲሆን፤ 4620 ሜትር ከፍታ ያለው የጉና ተራራ፣ 4184 ሜትር ከፍታ ያለው የጮቄ ተራራ እና 4190 ሜትር ከፍታ ያለው የአቡነ ዮሴፍ ተራራ በዚሁ የክልሉ አካባቢዎች የሚገኙ ናቸው፡፡
የዝቅተኛው የክልሉ ክፍል በዋነኛነት የምዕራባዊውንና የምስራቁን አካባቢ የሚሸፍን ሲሆን፤ ከ500 እስከ 1‚500 ሜትር ከባህር ጠለል በላይ ከፍታ አለው፡፡
በክልሉ የተለያዩ የአየር ንብረት ያላችው አካባቢዎች ሲገኙ 31% ቆላማ፣ 44% ወይና ደጋማ፣ 25% ደጋማ ቦታዎች ናቸው፡፡
በአብዛኛው የክልሉ ቦታዎች አመታዊ አማካኝ የሙቀት መጠን ከ15 c አስከ 21 c ይደርሳል፡፡
ክልሉ በሀገሪቱ እስከ 80% የሚደርሰውን የዝናብ መጠን ያስመዘግባል፡፡ ከፍተኛው የዝናብ መጠን በክረምት ወራት የሚመዘገበው ሲሆን፤ ይህም ወራት ከሰኔ አጋማሽ እስከ መስከረም መጀመሪያ ይዘልቃል፡፡

ወንዞችና ሀይቆች
የአማራ ብሄራዊ ክልል በ3 የወንዝ ተፋሰሶች የተከፈለ ነው እነሱም አባይ፣ ተከዜ እና አዋሽ ወንዞች ናቸው፡፡
ጥቁር አባይ ከሁሉም ረጅሙ ሲሆን 172‚254 ስኩዌር ኪ.ሜ የቆዳ ስፋት ይሸፍናል፡፡ ይሄው ወንዝ ካርቱም ከሚገኘው ነጭ አባይ ጋር እስኪገናኝ ድረስ ያለው ርዝመት 1‚450 ኪ.ሜትር ነው፡፡ ከዚህም ውስጥ 800 ኪ.ሜትሩ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚያደርገው ጉዞ ነው፡፡
የአባይ ወንዝ
የተከዜ ወንዝ ወደ 88‚000 ስኩዌር ኪ.ሜትር የቆዳ ስፋት ይሸፍናል፡፡
ከነዚህ ወንዞች በተጨማሪ አንገረብ፣ ሚሌ፣ ከሰም እና ጀማ የተባሉ ወንዞች በክልሉ የሚገኙ ተፋሰሶች ናቸው፡፡
በኢትዮጵያ ውስጥ በስፋቱ አንደኛ የሆነው የጣና ሀይቅ በዚሁ ክልል ይገኛል፡፡ ይህ ሀይቅ 3‚600 ስኩዌር ኪ.ሜትር ስፋት አለው፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን ሌሎች በእሳተ ጎመራ አማካኝነት የተፈጠሩ እንደ ዘንገና፣ ጉደና፣ አርዲቦ እና ሎግያ የተባሉ አነስተኛ ሀይቆችም በክልሉ ይገኛሉ፡፡
በክልሉ የሚገኙት ሀይቆችና ወንዞች ለሀይድሮ ኤለክትሪክ ሀይል ማመነጪያነት፣ ለመስኖ አገልግሎት እና ለአሳ ማጥመድ የሚሆን እምቅ ቸሎታ ያላቸው ናቸው፡፡

የቁም ከብት ሀብት
በክልሉ ወደ 9.1 ሚሊዮን የቀንድ ከብቶች፣ 8.4 ሚሊዮን በጎችና ፍየሎች፣ 1.6 ሚሊዮንየጋማ ከብቶች እንዲሁም 8.5 ሚሊዮን ዶሮዎች ይገኛሉ፡፡ ይህም ማለት በሀገሪቱ ከሚገኘው የቁም ከብት 40 ከመቶው በዚህ ክልለ የሚገኝ ነው፡፡ ይህ ትልቅ የቁም ከብት ሀብት ክልሉን ለስጋና ወተት ምርት፣ ለቆዳና ሌጦ ምርት ምቹ ያደርገዋል፡፡

የዱር እንስሳት
በሰሜን ተራሮች ብሄራዊ ፓርክ የሚገኙት እንደ ዋልያ አይቤክስ፣ የሰሜን ቀይ ቀበሮ፣ ጭላዳ ዝንጀሮ እና ሌሎች ብርቅዬ እንስሳት በክልሉ የገኛሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በክልሉ የተለያዩ የአእዋፍ አይነቶች ይኖራሉ፡፡

ማዕድን
በአማራ ክልል ውስጥ እንደ ከሰል/ኮል፣ ሼል፣ ላይምስቶን፣ ሊግናይት፣ የኖራ ድንጋይ፣ ሲሊካ፣ ድኝ እና ቤንቶኔት የተባሉ ማእድናት ይገኛሉ፡፡
ከዚህም በተጨማሪ የተለያዩ የፍልውሀ ምንጮችና የማእድን ውሀዎች በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ሀብቶች ናቸው፡፡

ቱሪዝም እና ቅርሶች
በ12ኛው ክፍለ ዘመን የተፈለፈለው የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስትያናት፣ የጎንደር ጥንታዊ ቤተመንግስቶች እና ሌሎችም ታሪካዊ መስህቦች በክልሉ ይገኛሉ፡፡
በጣና ሀይቅ ደሴቶች ላይ በሚገኙ ገዳማት ጥንታዊ የግድግዳ ላይ ስእሎች፣ ተጠብቀው የቆዩ የጥንት ነገስታት አፅሞችና ቅሪተ አካሎች እንዲሁም ልዩ ልዩ የእደ-ጥበብ ውጤቶች ይገኛሉ፡፡
ገዳማትን ከያዙት የጣና ሃይቅ ደሴቶች አንዱ የሆነው ፣ ደቅ ደሴት
የሰሜን ተራሮች ብሄራዊ ፓርክ በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኘውን ብርቅዬ እንስሳ ዋልያ አይቤክስን ለመጎብኘት እንዲሁም የተራራ መውጣት ስፖርት ለማካሄድ ከፍተኛ ቁጠር ያለው ቱሪስት የሚሄድበት የቱሪስት መዳረሻ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ለአለም አቀፍ ቅርስ ጥበቃ ካስመዘገበቻቸው 8 ቅርሶች ሶስቱ የሚገኙት በዚሁ ክልል ነው፡፡ ከእነዚህ ሁሉ ቅርሶች ባሻግር የጢስ አባይ ፏፏቴ፣ በሰሜን ሸዋ የሚገኙት ልዩ አፈጣጠር ያላቸው ዋሻዎችና አለቶች አንዲሁም የ"መርጡለ ማርያም" ቤተክርስትያን ሌሎች የቱሪስት መስህቦች ናቸው፡፡


​​ኢትዮጵ
የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት አጠቃላይ መረጃ

የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በ4 አሰተዳደራዊ ዞኖች ፣ በአንድ ልዩ ዞን ፣ በ35 ወረዳዎች እና በ74 ከተማዎች የተዋቀረ ነው። የክልሉ ምክር ቤት የከፍተኛ አስተዳደር አካል ሲሆን 152 የካቢኔ አባላትን የያዘ ነው። የህግ አስፈፃሚው አካል በ16 ተወካዮች የተዋቀረ ነው።
የስፍራው አቀማመጥ
የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በሰሜናዊው የኢትዮጵያ ጫፍ የሚገኝ ሲሆን ክልሉ በሰሜን ከኤርትራ፣ በምስራቅ ከአፋር ክልል፣ በደቡብ ከአማራ ክልል እንዲሁም በምእራብ ከሱዳን ሪፐብሊክ ጋር ይዋሰናል፡፡


ርእሰ ከተማ
መቀሌ የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ርእሰ ከተማ ነች፡፡
የቆዳ ስፋት
የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት 80000 ስኩ.ኪ.ሜ የሚገመት የቆዳ ስፋት ይሸፍናል፡፡

ስነ-ህዝብ
በ1994 በተገኘው የህዝብ ቆጠራ መሰረት የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የህዝብ ብዛት 3,136,267 ሲሆን ከዚህም ውስጥ 1,542,165 ወንዶች እና 2,667,789 ሴቶች ናቸው።
በሀይማኖት ረገድም 95.5% የኦርቶዶክስ ክርስትያን፣ 4.19% የእስልምና እና 0.4% የካቶሊክ እምነት ተከታይ ነው።
በብሄር ስብጥር ረገድም 94.98% የትግራዊ፣ 2.6% የአማራ፣ 0.7% የኢሮብ እና 0.05% የኩናማ ብሄረሰቦች ይኖራሉ፡፡ ትግርኛ የክልሉ የስራ ቋንቋ በመሆን ያገለግላል።

ዋነኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች
በትግራይ ብሔራዊ ክልል ከሚገኘው ህዝብ 83% የሚሆነው በግብርና ስራ ላይ የተሰማራ ነው፡፡
ጤፍ፣ ስንዴ እና ገብስ ዋነኛ የሰብል ምርቶች ሲሆኑ ባቄላ፤ የጥራጥሬ እህሎች፣ ሽንኩርት እና ድንች እንዲሁ በክልሉ ይመረታሉ፡፡
ተዳፋታማ የመሬት አቀማመጥ ባላቸው የክልሉ አካባቢዎች የመስኖ እና የእርከን መፍትሄዎችን በመጠቀም የእርሻ ስራ ይከናወንባቸዋል፡፡
የትግራይ ክልል የጥጥ፣ የእጣን፣ የሰሊጥ እና የተለያዩ ማእድናትን ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በማቅረብ ይታወቃል፡፡
ከክልሉም የመሬት ይዞታ 1.5 ሚሊዮን ሄክታር መልማት የሚችል ሲሆን ከዚህም ውስጥ 1 ሚሊዮን ሄክታሩ ለእርሻ አገልገሎት የዋለ ነው፤ የተቀረው 420,877 ሄክታር መሬት ደግሞ የእርከን ስራን በመጠቀም የለማ ነው፡፡
የተለያዩ የእደ-ጥበብ(እንደ ወርቅ ማንጠር፣ የስዕል እና የእንጨት ቅርፃ ቅርፅ) ስራዎች ሌላው በክልሉ በሚገኙ ታሪካዊ ቦታዎች ላይ የሚስተዋሉ የስራ አንቅስቃሴዎች ናቸው፡፡

የመሬት አቀማመጥ እና የአየር ንብረት
ምንም እንኳን ክልሉ ከ3,250 - 3,500 ሜትር ከፍታ ባላቸው የተራራ ሰንሰለቶች እና የተፈጥሮ መስህቦች የተከበበ ቢሆንም፤ ለዘመናት ሲፈራረቅበት የቆየ የመሬት መሸርሸር፣ የደን መጨፍጨፍ እና ከመጠን በላይ የሆነ የግጦሽ መሬት አጠቃቀም የክልሉን መሬት ለደረቅና ዛፍ-አልባ ሜዳዎች፣ኮረብታዎችና ተራራዎች አጋልጦታል፡፡
ይህ ክልል እጅግ በጣም የተለያዩ የከፍታ ልዩነቶችን ያስተናግዳል፡፡
የክልሉ የከፍታ መጠን ከባህር ጠለል በላይ ከ600 - 2,700 ሜትር ሲሆን
የተከዜ ሸለቆ ከባህር ጠለል በላይ 550 ሜትር ከፍታ ላይ ሲገኝ
"የክሳድ ጉዶ" የተራራ ጫፍ ደግሞ ከባህር ጠለል በላይ በ3,935 ሜትር ከፍታ ላይ ይገኛል፡፡ ይህም በመሀከላዊ ደጋማ አካባቢዎች ከሚገኙ የትግራይ ውብ የተፈጥሮ እይታዎች አንዱ ያደርገዋል፡፡
በክልሉ የተለያዩ የአየር ንብረት ያላችው አካባቢዎች ሲገኙ 39% ቆላማ፣ 49% ወይና ደጋማ፣ 12% ደጋማ ቦታዎች ናቸው፡፡ የክልሉ አመታዊ አማካኝ የዝናብ መጠን ከ450 – 980 ሚ.ሜ ይደርሳል፡፡

ወንዞችና ሀይቆች
ከአማራ ብሄራዊ ክልል የሚነሳው የተከዜ ወንዝ እንዲሁም ከኤርትራ የሚነሳው የመረብ ወንዝ የትግራይ ክልልን የሚያቋርጡ ድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ናቸው፡፡
እንደ ገባ፣ ወሪ፣ በርበር፣ አርቋ እና ጠጠር የተባሉ ለመስኖ ስራ ጠቃሚ የሆኑ አነስተኛ ወንዞችም በክልሉ ይፈሳሉ፡፡
የተከዜ ወንዝ የሀይድሮ ኤሌክትሪክ ሀይል ማመንጫነት እያገለገለ ይገኛል፡፡
የተከዜ ሃይድሮ ኤሌክትሪክ ኀይል ማመንጫ ግድብ
ሌላው በክልሉ የሚገኘው የአሸንጌ ሀይቅ ውብ የሆኑ አእዋፋትን ለመመልከት እና አሳ ለማጥመድ የተመቸ እና ቀልብን የሚስብ የተፈጥሮ መስዕብ ነው፡፡
ውብ አእዋፋት በአሸንጌ ሃይቅ

የቁም ከብት ሀብት
በክልሉ ወደ 11.51 ሚሊዮን የሚጠጋ የቤት እንስሳት ሲገኙ ከነዚህም ውስጥ 2.15 ሚሊዮን የቀንድ ከብቶች፣ 5.63 ሚሊዮን በጎችና ፍየሎች እንዲሁም 392,000 የጋማ ከብቶች ናቸው፡፡

የዱር እንስሳት
ዝሆን፣ ነብር፣ አጋዘንና የምኒሊክ ድኩላ በክልሉ የሚገኙ የዱር አራዊቶች ናቸው፡፡

ማዕድን
የትግራይ ክልል በኢትዮጵያ ውስጥ በማዕድን ሀብት ከበለፀጉ አካባቢዎች አንዱ ነው፡፡
በክልሉ ከተገኙ የብረት ማዕድናት ውስጥ ወርቅ፣ መዳብ፣ የብረት ኦር, ዚንክ, ሊድ እና ኒኬል ይገኙበታል፡፡
አስቤስቶስ, የሲሊከን አሸዋ, ካኦሊን, ግራፋይት, ላይም ስቶን, እብነ-በረድ, ግራናይት እና ዶሎማይት የተባሉ ብረት ያልሆኑ ማዕድናት በክልሉ ይገኛሉ፡፡

ቱሪዝም እና ቅርሶች
የትግራይ ክልል በተደጋጋሚ ከሚጠቀሱ የሰው ልጅ የስልጣኔ እና የባህል ዝርዝሮች ውስጥ የሚገኝ እና በአለም ላይ ከሚታወቁ ጥቂት ታሪካዊ ቦታዎች አንዱ ነው፡፡
ክልሉ በአህጉራችን ከሚገኙ እጅግ በጣም ወሳኝ የሆኑ የታሪክ ሀውልቶች የሚገኙበት ነው፡፡ ይህም ማለት ከቅድመ - ክርስትና በፊት የቆሙ ታላላቅ ሀውልቶች ይገኙበታል፡፡
ከክርሰቶስ ልደት በፊት በ2ኛው ክፍለ ዘመን የቆመው የአክሱም ሀውልት፣
ከክርሰቶስ ልደት በፊት በ5ኛው ክፍለ ዘመን እና ከቅድመ አክሱም ግዛት በፊት የተገነባው "የጨረቃ ቤተ-መቅደስ"፣
የንግስት ሳባ የመታጠቢያ ቤት እና ቤተ-መንግስት፣ የታቦተ ፅዮን ማደሪያ ይህ ሁሉ በክልሉ የሚገኙ ዋናዋና ቅርሶች ናቸው፡፡
የአክሱም ሃውልት
ታቦተ ጽዮንም ከእየሩሳሌም ቤተ-መቅደስ የመጣ እንደሆነ ይታመናል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ክልሉ በአለም ላይ ታላቅ የሆኑትን ሁለት ሀይማኖቶች እነሱም ክርስትናን በ4ኛው እንዲሁም እስልምናን በ6ኛው ክፍለ ዘመን ወደ ኢትዮጵያ ለማስገባት እንደ በር አገልግሏል፡፡
የነጃሺ መሰጊድም በክልሉ የሚገኝ ሌላው የታሪክ እና የሀይማኖት መስህብ ነው፡፡

በክልሉ ከ120 በላይ የሚሆኑ ለገዳም አገልግሎት የሚውሉ ፍልፍል አብያተ ክርስትያናት እና ዋሻዎች ሲገኙ በትግራይ በሚገኙ ተራራዎች ሁሉ ተሰራጭተው ይገኛሉ፡፡
እነዚሁ ገዳማትና ዋሻዎች በውስጣቸው የተለያዩ የብር መስቀሎችን፣ የሚያንፀባርቁ ዘውዶችን፣ ጥንታዊ የብራና ፅሁፎችን እና የሳባ ፊደላት የተቀረጸባቸውን ድንጋዮች ይዘዋል፡፡ እነዚህና ሌሎች መሰል የባህል ቅርሶች ተደማምረው ክልሉን በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኝ ተመን የለሽ አካባቢ ያደርገዋል፡፡


ውድ የኢትዮጵ ተከታታዮች ስለ ኢትዮጵያ አጠቃላይ መረጃ የጀመርነውን ጽሑፍ እንደወደዳችሁት ተስፋ አለን። በቀጣይ ደግሞ ሁሉንም ክልሎች ለመዳሰስ እንሞክራለን። ኢትዮጵያን ሙሉ አድርገን እንመለከት ዘንድ እንደሚረዳን ተስፋ አለን።

ኢትዮጵያ ሐገራችንና እና እኛ ኢትዮጵያውያን ታሪካችን እንደመልካችን ሁሉ ዥንጉርጉር ነው። ለአንዱ አያታችን የተመቸች ኢትዮጵያ ለአንዱ አያታችን ጎርባጣ ነበረች። አንዱን ያስተማረ፥ ለወግ ለማዕረግ ያበቃ ስርዓት ሌላውን በጥይት ቆልቷል፥ ከሀገር ባለቤትነት አግልሏል። ይህ ግን ማናቸውም የብዙ ዘመን ታሪክ ያለው አገር እና አበረው የኖሩ ህዝቦች ሊኖራቸው ከሚችል የተለየ እውነታ አይመስለኝም። ምናልባት እንዲህ ያለው የትርክት ብዝሃነት ዛሬ ላይ ለእኛ ታላቅ አደጋ የጋረጥብን ሁሉንም ትርክቶች እኩል የእኛው ታሪክ እንደሆኑ አለማመቻመች መቀበል ስላቃተን ይሆን? የአንዱ ጀግኖች ለሌላው ባይሆኑም አብረን ለቆምንባት አገር ያደረጉትን በጎም ሆነ ክፉ በግልፅ መወያየት መቻል አለብን። የእኔንም እንዲሁ። የእኔን አትንኩ የእናንተን አርክሱ አይነት ውይይት ግን ምናልባት ተጨማሪ ቁርሾ ይፈጥር እንደሆነ እንጂ ትርፍ አይኖረውም።"
መልእክታችን ነው።

እናመሠግናለን!!
ኢትዮጵ


ኢትዮጵ
•የኢትዮጵያ አጠቃላይ መረጃ

ጠቅላይ ሚንስቴር መለስ ዜናዊ ነሃሴ 14፣ 2004 ዓም ከዚህ አለምበሞት ሲለዩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴር የነበሩት ኃይለማርያም ደሳለኝ ጠቅላይ ሚኒስቴር ሆነው ተሾሙ።

•የመንግስት አወቃቀር

ኢትዮጵያ የፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግስት አወቃቀር ሲኖራት በ10 የብሔራዊ ክልላዊ መንግስታት እንዲሁም በሁለት የከተማ መስተዳድሮች የተዋቀረች ነች፡፡ አወቃቀራቸውም በሕገ መንግስቱ በተደነገገው መሰረት «በህዝብ አሰፋፈር ፣ ቋንቋ ፣ ማንነት እና ፈቃድ ላይ» ተመስርቶ ሲሆን ክልሎቹም የሚከተሉት ናቸው።

1. የትግራይ ክልል
2. የአፋር ክልል
3. የአማራ ክልል
4. የኦሮሚያ ክልል
5. የሶማሌ ክልል
6. የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል
7. የደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል
8. የጋምቤላ ክልል
9. የሀረሪ ክልል
10. የሲዳማ ክልል
11. በተጨማሪም የአዲስ አበባ እና የድሬዳዋ ከተማ መስተዳደሮች ይገኙበታል።

እነዚህ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስታት አንዲሁም ሁለቱ የከተማ መስተዳደሮች በ800 ወረዳዎቸና ወደ 15000 በሚጠጉ ቀበሌዎች(5000 የከተማና 10000 የገጠር) የተከፋፈሉ ናቸው።

•ህዝብ
በ1999 ዓ.ም በተደረገው የህዝብና ቤት ቆጠራ እና ትንበያ መሰረትም በአሁኑ ጊዜወደ 90 ሚሊዮን የሚጠጋ ህዝብ አላት፡፡ ከዚህም ውስጥ ወደ 84 ከመቶ የሚጠጋው በገጠሪቱ የኢትዮጵያ ክፍል ሲኖር የተቀረው በከተማና ከፊል ከተማ በሆኑ ቦታዎች ይኖራል፡፡

ኢትዮጵያ ከ80 በላይ የሚሆኑ ብሄር ብሄረሰቦች የሚገኙባት ሀገር ነች። የኦሮሞ፣ የአማራ፣ እና የትግራይ እንዲሁም የሶማሌ ብሄረሰቦች ከጠቅላላው የአገሪቱዋ ሕዝብ ቁጥር ክ3/4ኛ በላይ የሚሆነውን ይይዛሉ።
በሃይማኖት በኩልም ክርስትናና እስልምና በስፋት የሚስተዋልባት አገር ናት። እስልምና ከ 25-30% ፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ተከታዮች ከ 60-65% ፡ ፐሮቴስታንት ደግሞ 10% የሚሆነውን ድርሻ ይሸፍናል።
የወንድ አማካኝ እድሜ 53.42 ዓመት ሲሆን የሴት ደግሞ 55.42 ዓመት ነው።
የዕድሜ ስብጥር (በመቶኛ)
0-14 አመት - 42.8%
15-19 አመት - 10.5%
20-49 አመት - 37.4%
50-59 አመት - 4.9%
60ና ከዛ በላይ: 4.4%

•ቋንቋዎች

በኢትዮጵያ ውስጥ ከ80 በላይ ብሄር ብሄረሰቦች የሚኖሩ ሲሆን በቋንቋም በኩል ከ80 በላይ የሚሆኑ ቋንቋዎች የሚነገርባት ሀገር ናት፡፡
በአሁኑ ወቅት በእብዛኛው ኢትዮጵያውያን የሚነገሩት ቋንቋዎች አማርኛ እና ኦሮምኛ ሲሆኑ፤ አማርኛ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል ያሉ ነዋሪዎች የመማሪያ፤ የመገበያያ እንዲሁም የስራ ቋንቋ ሆኖ የቆየ በመሆኑ በአሁኑ ወቅት የብሄራዊ ቋንቋ ነው።
በኢትዮጵያ የሚነገሩት ቋንቋዎች ወደ አራት ዋና ዋና የቋንቋ ክፍሎች ሊካተቱ ይችላሉ። እነዚሁም:-

#ኩሻዊ: ወደ 19 ቋንቋዎችን የያዘ
#የአባይ-ሰሃራዊ: ወደ 20 ቋንቋዎችን የያዘ
#ኦሞአዊ: ወደ 23 ቋንቋዎችን የያዘና
#ሴማዊ: ወደ 12 ቋንቋዎችን የያዙ ናቸው።

ኩሻዊ ከሚባሉት ቋንቋዎች ዋና ዋናዎቹ ኦሮምኛ፣ ሶማልኛ፣ አፋርኛ፣ ሲዳምኛ፣ ሃዲያኛ እና ከምባትኛ ሲሆኑ ከአባይ-ሰሃራዊ የቋንቋ ምድብ የሚካተቱት በርታኛ፣ ኩናማኛ፣ ጉሙዝኛ፣ ሙርሲኛ እና የመሳሰሉት ናቸው። እንደ ወላይትኛ፣ ጋሞኛ፣ ከፋኛ፣ ሃመርኛ የመሳሰሉት የኦሞአዊ ቋንቋ ዘሮች ሲሆኑ አማርኛ፣ ትግርኛ፣ ጉራጊኛ፣ ስልጢኛ፣ ሀደሪኛ እና መሰል ቋንቋዎች ከሴማዊ ቋንቋዎች ይመደባሉ።
የሴሚቲክ ምንጭ ያላቸው እንደ አማርኛ ያሉት ቋንቋዎች የራሱ የሆነ የተለየ የፊደል ስርአት ያላቸው ሲሆን ይህም ኢትዮጵያን ከአፍሪካ ብቸኛዋ ባለ ጥንት ፊደል ሀገር ያደርጋታል። እነኚህ የሴሚቲክ ምንጭ ያላችው ቋንቋዎች ግዕዝ የተባለ በአሁኑ ወቅት ከቤተክርስትያን ውጭ ለእለት ተእለት ግልጋሎት ላይ የማይውል ግንድ ዘር አላቸው።

•ኢኮኖሚ

የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በዋነኛነት በግብርና ዘርፍ የተያዘ ነው ከዚህም ከሀገሪቱ ጠቅላላ የውስጥ ምርት 45 ከመቶውን ይሸፍናል፣ 10 ከመቶ የሚሆነው የኢንዱስትሪ ዘርፍ ሲሆን፣ 13.3 ከመቶው ደግሞ የማምረቻው ዘርፍ ይይዛል፡፡
የወጪ ንግድም የሚከናወን ሲሆን ከዚህም ውስጥ እስከ 60 ከመቶ የሚደርሰው የቡና መላክ ወጪ ንግድ ነው፡፡

•ግብርና

እርሻ የአገሪቱ የጀርባ አጥንት ሲሆን አገሪቱ ከዚሁ የኢኮኖሚ ዘርፍ ቡና፣ የቅባት እህሎች፣ አበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ ስኳር እና የከብት መኖ ወደ ውጭ ትልካለች፡፡
ከዚህም በተጨማሪ የከብት ሀብት ልማት በመኖሩ ከዚህ ዘርፍ የቁም ከብት፣ ቆዳና ሌጦ በመላክ የውጭ ምንዛሬ ታገኛለች፡፡
ኢትዮጵያ ካሏት አጠቃላይ ዘርፎች ውስጥ የግብርና ዘርፍ ቀዳሚውን ሲይዝ በ2006/07 ዓ.ም በተገኘ አመታዊ ስሌት መሰረት ግብርና 45.9 ከመቶ የሚሆነውን የሀገሪቱ የምርት ውጤት ይሸፍናል፡፡ ወደ 45 ከመቶ የሚሆነው የሀገሪቱ መሬት ለግብርና ስራ ምቹ ነው፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ወቅት ወደ 10‚556 ሄክታር መሬት ብቻ ለእርሻ አገልግሎት የዋለ ነው፡፡

•የአምራች ዘርፍ

በ2006/07 ዓ.ም 13.3 ከመቶ የሚሆነውን የሀገሪቱን ጠቅላላ ምርት ያስመዘገበው ይህ ዘርፍ ነው፡፡ ከዚህም ዘርፍ የምግብ፣ የለስላሳ መጠጦች፣ የጨርቃ ጨርቅና የቆዳና ሌጦ ውጤቶች ይገኙበታል፡፡
ዘርፉ በዋነኛነት ከግብርና የሚገኙ ምርቶችን ለማቀነባበር እና ለማምረት ይንቀሳቀሳል፡፡ በዚህም ለሀገር ውስጥ ገበያ የሚውሉ የሸማቾች እቃዎችን ያቀርባል፡፡ ወደ ውጭ ከሚላኩ ምርቶችም ጨርቃ ጨርቅ፣ የታሸገና የቀዘቀዘ ስጋ፣ በከፊል የተጨረሱ ቆዳና ሌጦ፣ ስኳርና ሞላሰስ፣ የእግር አልባሳት፣ ትንባሆ፣ ለስላሳ መጠጦች፣ ዘይት፣ ሰም ፣ ሌዘርና የሌዘር ውጤቶችን ያቀርባል፡፡

•አገልግሎት ሰጪ ዘርፍ
የአገልግሎት ሰጪ ዘርፍ 40.5 ከመቶ የሚሆነውን የሀገር ውስጥ ምርት ይሸፍናል፡፡ ይህ ዘርፍ በአሁኑ ወቅት ቀስ በቀስ በማደግ ላይ የሚገኝ ሲሆን በ1996/97 ዓ.ም ከነበረበት 36 ከመቶ በ2006/07 40.8 ከመቶ ሊደርስ ችሏል፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው በተፈጠረው የትምህርት፣ የሪል-እስቴት፣ የኪራይ እና የንግድ እንቅስቃሴዎች፣ በጅምላና ችርቻሮ ንግድ፣ እንዲሁም የሆቴልና ሬስቶራንት ንኡስ-ዘርፎች እድገት ምክንያት ነው፡፡

•የመገበያያ ገንዘብ:

የኢትዮጵያ የገንዘብ መለኪያ ብር ነው
1 ብር ከ100 ሳንቲሞች ጋር እኩል ነው
የብር ኖቶች
ባለ 1 ብር ኖት
ባለ 5 ብር ኖት
ባለ 10 ብር ኖት
ባለ 50 ብር ኖት
ባለ 100 ብር ኖት
የመዳብ ሳንቲሞች፡ 1፣5፣10፣25፣ እና 50 ሳንቲሞች
የውጭ ምንዛሬ አገልግሎት በአየር መንገዶች እና ፈቃድ ባለቸው ሆቴሎች ይገኛል፡፡

ምንጭ
የኢትዮጵያ መንግስት ፖርታል
ማእከላዊ ስታትስቲክስ እጀንሲ
የኢትዮጵያ ብሄራው ባንክ ድረ-ገፅ


ኢትዮጵ
የኢትዮጵያ አጠቃላይ መረጃ

•መልክዓምድር
ኢትዮጵያ በሰሜን ምስራቅ አፍሪካ ከ3-14 ዲግሪ ሰሜን እና ከ33-48 ዲግሪ ምሥራቅ የምትገኝ አገር ስትሆን የቆዳ ስፋቱዋም 1,127,127 ካሬ ኪ.ሜ. ነው።
በሰሜን ከኤርትራ፣ በምዕራብ ከሱዳን፣ በደቡብ ከኬኒያ፣ እንዲሁም በምሥራቅ ከጅቡቲ እና ከሶማሊያ ጋር ትዋሰናለች።

የኢትዮጵያ አብዛኛው ግዛት በተራሮችና በሀይቆች የተሞላ ሲሆን፣ ታላቁ የምሥራቅ አፍሪካ ስምጥ ሸለቆ እነዚህኑ ከፍተኛ ቦታዎች ከሰሜን ምሥራቅ ወደ ደቡብ ምዕራብ በመጋደም ለሁለት ይከፍላቸዋል። በስምጥ ሸለቆው ዙሪያም በረሃማ የሆኑ ዝቅተኛ ቦታዎች ይገኛሉ። ይኅን መሰሉ የመልክዓ-ምድር ልዩነት አገሪቷ የተለያዩ የአየር ንብረት፣ የአፈር፣ የዕፅዋት እና የሕዝብ አሰፋፈር ገጽታዎች እንዲኖራት አስችሏታል።
(ምስል 1•የኢትዮጵያ ካርታ 2•የኢትዮጵያ ስምጥ ሸለቆ)

በከፍታና በመልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ የተነሣ በኢትዮጵያ ውስጥ ሦስት ዐይነት የአየር-ንብረት ክልሎች ይገኛሉ።
እነሱም:-
➊ደጋ - ከፍታቸው ከባሕር ጠለል 2400 ሜትር የሚጀምር እና የሙቀት መጠናቸው ከ 16 ዲግረ ሴ.ግ የማይበልጥ፤
➋ወይናደጋ - ከፍታቸው ከባሕር ጠለል ከ1500 እስከ 2400 ሜትር፣ ሙቀታቸውም ከ16 ዲግረ ሴ.ግ እስከ 30 ዲግረ ሴ.ግ የሚደርስና፣
➌ቆላ - ከባህር ጠለል በታች ጀምሮ እስከ 1500 ሜትር ከፍታ ያላቸው፣ የሙቀት መጠናቸውም ከ30 ዲግረ ሴ.ግ እስከ 50 ዲግረ ሴ.ግ የሚደርስ አከባቢዎች ናቸው።

ዋናው የዝናብ ወቅት ከሰኔ አጋማሽ እስከ መስከረም አጋማሽ ሲሆን፣ ከሱ ቀደም ብሎ አልፎ አልፎ የሚጥል የበልግ ዝናብ በየካቲት እና በመጋቢት ይከሰታል። የተቀሩት ወራት በአብዛኛው ደረቅ ናቸው።
•የኢትዮጵያ ዋና ከተማ አዲስ አበባ ነው

•አጠቃላይ ታሪክ

ከጥንት ጀምሮ ከነበሩ አገሮች የምትመደብና በአፍሪካ ከሚገኙ አገሮች ከሁሉም የበለጠ ረጅም እድሜ ያስቆጠረች አገር ነች፡፡ አምስት ሚሊዮን አመት የሚሆነውና በጣም ረጅም እድሜ ያስቆጠረው የሰው ቅሪት የተገኘው በኢትዮጵያ አዋሽ ሸለቆ አካባቢ ሲሆን ይህም፣ 3.2 ሚሊዮን አመት የሆነውን እዛው አካባቢ የተገኘውን የሉሲን /ድንቅነሽን/ አጽም በእድሜ ይበልጣል፡፡

በአራተኛው ክፍለ ዘመን ከግብጽና ሶሪያ ሚሲዮኖች መጥተው ክርስትናን ለኢትዮጵያ አስተዋውቀው ነበር፡፡ ነገር ግን በሰባተኛው ክፍለ ዘመን በእስልምና መስፋፋት ምክንያት ኢትዮጵያ ከአውሮፖውያኑ ክርስትና ርቃ ቆይታለች፡፡ ከዛም በ1500 ዎቹ ፖርቱጋሎች በህንድ ውቅያኖስ ላይ የነበራቸውን ይዞታ ለማጠናከርና ኢትዮጵያ ውስጥ የሮማ ካቶሊክን ለማስፋፋት ሲሉ ከኢትዮጵያ ጋር የነበራቸውን ግንኙነት መልሰው ጀምረው ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት አንድ ክ/ዘመን ያህል የፈጀ የሀይማኖት ግጭት በ1630ዎቹ ተነስቶ ከውጪ የመጡትን ሚሲዮናዊያንን በሙሉ ከኢትዮጵያ ተባረው ሲወጡ ተፈጽሟል፡፡ ይህ የከፋ የግጭት ጊዜ ኢትዮጵያ የውጭ ክርስትያኖች ላይ እና አውሮፖውያኖች ላይ እስከ ሀያኛው ክፍለ ዘመን ድረስ ፊቷን እንድታዞር አስተዋጾ ከማድረጉም በተጨማሪ እስከ 19ኛው ክ/ዘመን አጋማሽ ድረስ ኢትዮጵያ ከመላው አለም ተገልላ እንድትቆይ አድርጓታል፡፡

ከ1700ዎቹ ጀምሮ 100 ለሚሆኑ አመታት ኢትዮጵያ ማዕከላዊ አገዛዝ ሳይኖሯት ቆይታለች፡፡ ይህም "የመሳፍንት ዘመነ መንግስት" የተለያዩ የኢትዮጵያን ክፍል ይገዙ በነበሩ ገዢዎች መሀል በነበረው ፉክክር የተነሳ በመጣው ብጥብጥ ሲታወቅ በ1869 ግን አፄ ቴዎድሮስ መሳፍንቶችን አንድ ላይ በማምጣት ዋነኛ አሰባሳቢ ሀይል ሆነዋል፡፡ ተከታያቸው አፄ ዮሀንስም አፄ ቴዎድሮስ የጀመሩትን ቀጥለው ኢትዮጵያን ለመውረር ሙከራ ያደረጉትን ደርቡሾችና ሱዳኖችን ረተው መልሰዋል፡፡

ከ1881 እስከ 1905 ዳግማዊ አፄ ሚኒሊክ በአፍሪካ ይዞታቸውን እያሰፉ የነበሩትን የአውሮፖ ሀይሎችን ጥቃት በመከላከል ኢትዮጵያን ገዝተዋል፡፡ በዛ ጊዜ ጣልያን ኤርትራን በከፊል ቅኝ ገዝታ የነበረችበትና በ1880ዎቹ አጋማሽ ላይ ደግሞ ሙሉ ለሙሉ ቅኝ ገዝታት የነበረችበት ጊዜ ስለነበር ከሌሎች አውሮፖ አገራት በበለጠ ለኢትዮጵያ አስጊ ነበረች፡፡ በ1880 ግን እስከዛሬ ድረስ ዝነኛ በሆነው የአድዋ ጦርነት ኢትዮጵያ ጣልያንን አሸንፋ በአፍሪካ የቀኝ ገዥ ሀይሎችን ያሸነፈች የመጀመሪያዋ ሀገር ሆናለች፡፡

በ1908 የክርስትና ሀይማኖት ሹማምንት ልጅ እያሱን ለእስላሙ ህብረተሰብ በመቆርቆራቸው ምክንያት ከስልጣን አውርደው የዳግማዊ ሚኒሊክ ልጅ የሆኑትን እቴጌ ዘውዲቱን ስልጣን ላይ አውጥተዋቸዋል፡፡ የሳቸው የቅርብ የስጋ ዘመድ የነበረውም ራስ ተፈሪ መኮንንም ሞግዚት አስተዳደርና ወራሽ ሆነው ተሹመዋል፡፡

እቴጌ ዘውዲቱ በ1922 ሲሞቱ ተተኪያቸው ስማቸውን ወደ ሀይለስላሴ በመቀየር ስልጣን ላይ ወጡ፡፡ ነገር ግን በ1928 ዓ.ም የጣልያን ሀይሎች ኢትዮጵያን ለአጭር ጊዜ ወረው ሲቆጣጠሩ ግዛታቸው ተቋርጦ ነበር፡፡ ይህን ጊዜም አፄ ሀይለስላሴ ለሊግ ኦፍ ኔሽንስ ይግባኝ ብለው ሰሚ ስላጡ ወደ እንግሊዝ ተሰደው ለሚቀጥሉት አምስት አመታት የኢትዮጵያ አርበኞች ከብሪታንያ ጋር በመተባበር ጣልያንን እስኪያሸንፉ ድረስ ወደ ስልጣናቸው አልተመለሱም ነበር፡፡

አፄ ሀይለ ስላሴ እስከ 1966 ድረስ ስልጣን ላይ ከቆዩ በኋላ በምትካቸው የጊዜአዊ ወታደራዊ ምክር ቤት /ደርግ - ኮሚቴ የሚል ትርጉም ሲኖረው/ ስልጣን ይዘው በስም ሶሻሊስት የሆነ በአቋም ግን ወታደራዊ አመራር ያለው መንግስት ተመሰረተ። ከዚህ ክስተት በኋላ ሻለቃ መንግስቱ ሀይለ ማሪያም እንደ ኘሬዝዳንትና እንደ ደርግ ሊቀ መንበር ስልጣን ያዙ፡፡

በ1980ዎቹ መጀመሪያ በኢትዮጵያ በተለይ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል በሚገኙት ትግራይና ኤርትራ መንግስታዊ ግልበጣ ተካሄደ፡፡ በ1981ዓ.ም የትግራይ ህዝቦች ነፃ አውጪ ግንባር /ትህነግ/ ከብሄረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ/ብአዴን/ እና ከኦሮሞ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት /ኦህዴድ/ ጋር አንድ ላይ በመሆን የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ን መሰረቱ በግንቦት 1983 ላይም የኢህአዲግ ሀይሎች ወደ አዲስ አበባ በመግባት ኮሎኔል መንግስቱ ወደ ዙንባቢዌ እንዲሰደድ ሆኗል፡፡
በ1983 ከኢህአዲግ እና ሌሎች የአገሪቷ የፖለቲካ ፓርቲዎች የተውጣጡ 87 የተወካዮች ምክር ቤትና በሽግግር ህገ መንግስት የኢትዮጵያ ሽግግር መንግስት ተቋቋመ፡፡
በዛው አመት በኢሳያስ አፈወርቂ መሪነት የኤርትራ ህዝቦች ነፃ አውጭ ግንባር /ኤህነግ/ ከ30 አመታት ትግል በኋላ ኤርትራን ተቆጣጥሮ ጊዜአዊ መንግስት መሰረተ፡፡ እስከ ግንቦት 1985 ዓ.ም ድረስም ኤርትራዊያኖች በተባበሩት መንግስታት ክትትል የጠየቁት የመገንጠል መብታቸውን እስኪያገኙ ድረስ የጊዜአዊው መንግስትም ስልጣን ላይ ቆየ፡፡
በኢትዮጵያም ኘሬዘዳንት መለስ ዜናዊና የሽግግር መንግስቱ አባላት በሰኔ በ1986 ዓ.ም 548 አባላት ባሉት ለህገ መንግስታዊ ምክር ቤቶች ምርጫ ተካሄደ፡፡ በ1987ዓ.ም መጀመሪያ ላይ የተመረጡት የምክር ቤቱ አባላት የኢፌዲሪን ህገ መንግስት ተቀበሉ፡፡ የፖርላማ ምርጫ ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደው በ1987 ዓ.ም ሲሆን በዛው አመት ነሀሴ ወር ላይ መንግስት ተቋቋመ፡፡ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ተመረጡ

☞ይቀጥላል☜


#ኢትዮጵ

#የኢትዮጵያ_አጠቃላይ_መረጃ

•መልክዓምድር

•አጠር ያለ ታሪክ

•የመንግስት አወቃቀር

•ቋንቋዎች እና ሌሎች መረጃዎችን





ነገ ማታ 1፡00 ይጠብቁን
ኢትዮጵ


#የ1906_የበልጂየም_እና_የእንግሊዝ_ስምምነት

ይህ ስምምነት ግንቦት 09 ቀን 1906 እ.ኤ.አ በበልጂየም(ኮንጎን በመወከል) እና በእንግሊዝ መካከል የተከናወነ ሆኖ በዚሁ ስምምነት በአንቀፅ 3 ላይ በግልፅ እንደተመለከተው የኮንጎ መንግስት ከሰምሊኪ ወይም ከልሳንጎ ወንዝ ወደ አልበርት ሀይቅ የሚወርደውን ውሀ ከሱዳን መንግስት ጋር አስቀድሞ ሳይስማማ የውሀውን ይዘት የሚቀንስ ስራ እንዳይሰራ ወይም ውሀውን የሚቀንስ ስራ ለመስራት ለማንም ፈቃድ እንዳይሰጥ በዚህ ውል አድርገዋል የሚል ነበር፡፡ ይህ ስምምነት የኮንጎ ህዝብ ከናይል ወንዝ ላይ የመጠቀም መብቱን የሚከለክል፤የሀገሪቱ ብሄራዊ ጥቅምን የሚጎዳ በበልጅየም ፍላጎት ብቻ የተፈረመ ሲሆን የታችኞች ተፋሰስ ሀገራትን ብቻ የሚጠቅም ኢ-ፍትሀዊ ስምምነት በመሆኑ ተቀባይነት ሊኖረው አይችልም፡፡

#የ1906_የእንግሊዝ_የጣልያንና_የፈረንሳይ_ስምምነት

ይህ ስምምነት በእንግሊዝ፣ ጣልያንና ፈረንሳይ መካከል በሎንደን የተከናወነ የሶስትዮሽ ስምምነት(Tripartite Agreement) ሲሆን በዚሁ ስምምነት አንቀፅ 4(a)ላይ እንደተመለከተው ፍፁም ግዛታዊ አንድነት ላይ በመመስረት የኢትዮጵያ መብትን ገታ በማድረግ በአንድ በኩል፤ጣልያን በሶማሊያና በኤርትራ ላይ ያላትን የቆየ ጥቅምን በማስጠበቅ በሌላ በኩል፤የእንግሊዝና የግብጽ ጥቅም በናይል ወንዝ ለማረጋገጥ ሶስቱም ሀገራት የተስማሙበት ነው፡፡ ይህ ስምምነት ኢትዮጵያ በልአላዊ ግዛቷ ላይ በሚገኝ የውሀ ኃብት እንዳትጠቀም ሙሉ ለሙሉ ያገለላት በመሆኑ በውሀዋ ላይ እንድትገለገል ሊያሰቆማት የሚችል የውጭ ሃይል እንደሌለና ስምምነቱንም በኢትዮጵያ ተቀባይነት እንደማይኖረው በግልፅ ለሀገራቱ አሳውቃለች፡፡

#የ1925_የእንግሊዝና_የጣልያን_ስምምነት
በ1919 እ.ኤ.አ እንግሊዝ በጣና ሀይቅ ላይ ግድብ እንድትሰራ የኢትዮጵያ ይሁንታ እንድታገኝ ጣልያን ድጋፏን የምትሰጥ መሆኗን የሚገልፅ የስምምነት ማእቀፍ በእንግሊዝና በጣልያን መካከል ተከናወነ፡፡ ይህን ስምምነትን ተከትሎ በ1925 እ.ኤ.አ.ግብፅና ሱዳን በነጭና ሰማያዊ ናይል (ጥቁር አባይ) እንዲሁም በሌሎች የናይል ገባሪ ወንዞች ላይ የውሀ ስራዎችን ለመስራት ቅድሚያ መብት እንዳላቸውና ሌሎች ሀገራት የወንዙን የውሀ ይዘት የሚቀንስ ማንኛውም አይነት ስራ እንደማይሰሩ በመግለፅ ጣልያንና እንግሊዝ የማስታወሻ ልውውጥ አደረጉ፡፡ ይህ የደብዳቤ ልውውጥን ኢትዮጵያ እንደማትቀበለው ተቋውሟን ገልፃለች፤ቅሬታዋን በወቅቱ ለነበረው የአለም መንግስታት ድርጅት (League of Nations) አስታውቃለች፡፡

#የ1929_የእንግሊዝ_እና_የግብፅ_ስምምነት

ይህ ስምምነት ሱዳንን እና ሌሎች በእንግሊዝ ስር የነበሩ ቅኝ ተገዢዎችን(ኡጋንዳ፣ ኬንያና ታንዛንያን)በመወከል በእንግሊዝ እና በግብፅ መካከል የተከናወነ ሆኖ የናይል ወንዝ ተፋሰስ ሀገራትን ሊጎናፀፉት የሚገባቸውን ተፈጥሮአዊና ፍትሀዊ የውኃ ኃብት ተጠቃሚነትን እውቅና የማይሰጥ ፍፁም የሁለትዮሽ ስምምነት ነበር፡፡ ይህ ስምምነት ሱዳንን የተወሰነ ድርሻ ብቻ እንዲሰጣት በማድረግ ግብጽና እንግሊዝ ብቻቸውን የናይል ወንዝ ተጠቃሚ እንደሆኑ በተለይም ግብፅ በናይል ወንዝ ላይ በብቸኝነት የመወሰንና ድምፅን በድምፅ የመሻር ስልጣን(Veto Power)እንደላትና ይህ መብትም ካለምንም ጣልቃ ገብነት የሚቀጥል መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ የግብፅ ፈቃድ ሳይታከልበት በናይልን ሆነ ናይልን በሚገብሩ ወንዞች ላይ ምንም አይነት የመስኖ ሆነ የኤሌክትሪክ ሃይል አገልግሎት ለመስጠት የሚችል ግንባታ በሌሎች ተፋሰስ ሀገራት መከናወን እንደሌለበት ማእቀብ የሚጥል ነበር፡፡
የ1952 የእንግሊዝና የግብፅ ስምምነት(The Owen Falls Agreement)
የኡጋንዳ ቅኝ ገዥ በነበረችው በእንግሊዝና በግብፅ መካከል የተከናወነ ሆኖ የስምምነቱ ይዘትም በአንድ በኩል ኡጋንዳ ለኤሌክትሪክ ሃይል አመንጪነት የሚውል ግድብ ለመገንባት የሚያስችል ህጋዊ መእቀፍ ለማግኘት፤በሌላ በኩል ደግሞ ግብፅ በናይል ላይ የነበራትን የተቆጣጣሪነትና የአለቃነት ስልጣን አስጠብቆ ለማስቀጠል በማለም የተፈፀመ ነበር፡፡ ይኸውም ግብፅ ካልፈቀደች ምንም አይነት ስራ መስራት እንደማይቻል እውቅና ለመስጠት በማሰብ የተከናወነ ይመስላል፡፡

#የ1959_የግብጽና_የሱዳን_ስምምነት
ይህ ስምምነት በዩናይትድ አራብ ሪፓብሊክ ግብጽና በሱዳን ሪፓብሊክ መካከል የተከናወነ ሲሆን የ1929 ስምምነት ተቀጥያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ምክንያቱም ከፍተኛው የናይል ውኃ የግብጽ እንደሆነ እውቅና የሚሰጥ ስምምነት ነበር፡፡ በዚሁ ስምምነት አንቀጽ 4 ላይ በግልጽ እንደተመለከተው 55.5 ቢሊዮን ኩቢክ ሜትር ለግብጽ፣ 18.5 ቢሊዮን ኩቢክ ሜትር ለሱዳን በመስጠት ቀሪው 10 ቢሊዮን ኩቢክ ሜትር ደግሞ የአከባቢው የኢኮሎጂካዊ ሚዛን ለመጠበቅ ወደ ሰሃራ ምድረ በዳ እንዲተን በመስማማት ኢትዮጵያ በብርጭቆ እንኳን ውኃ የምትቀዳበት መብት ያላገኘችበት አስገራሚ ውል ነበር፡፡ ይህ ስምምነት ሌሎች ተፋሰስ ሀገራትን ያገለለና ፍፁም የሁለትዮሽ ውል ስለነበር በኢትዮጵያ ተቀባይነት እንደሌለው ተደጋግሞ ተገልጿል፡፡

📣📣 ጽንሰ ኢትዮጵያ ሐዳስ 📣📣
🇪🇹🇪🇹🇪🇹

#ለማንኛውም ሐሳብ እና አስተያየት
👉👉 @Yottor_bot 👈👈
ላይ ያድርሱን።


#ኢትዮጵ


#በናይል_ላይ_የተፈፀሙ_ስምምነቶች
በናይል ዙርያ ላይ የተከናወኑ ውሎችና ስምምነቶች በዋነኛነት በቅኝ ገዢዎች የተከናወኑ ሲሆን ግብጽን ማእከል ያደረጉና ሌሎች ተፋሰስ ሀገራትን የሚያገሉ ብሎም ጉዳት የሚያስከትሉ ናቸው፡፡ የናይል ወንዝ የቅኝ ገዢዎች ቀልብና ፍላጎት መሳብ የጀመረው ከ19ኛ መክዘ ጀምሮ ነው፡፡ በሚያስገርም ሁኔታ እንግሊዝ የናይል ወንዝን አጠቃቀምና አጠባበቅን በማስመልከት ስምንት ስምምነቶችን ተፈራርማለች፡፡ እንግሊዝ ለምን ይህን ያህል ስምምነት በናይል ወንዝ ላይ መዋዋል አስፈለጋት የሚለውን ጥያቄ ስናይ እንግሊዝ የግብፅ ቅኝ ገዥ ስለነበረች በአንድም በሌላ መንገድም የራሷን ጥቅም እያሰከበረች ነበር፡፡ ሌሎች የቅኝ ገዥ ሀገራትም በናይል ወንዝ ዙርያ ሲያከናውኑዋቸው የነበሩት ስምምነቶች የራሳቸውን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማጎልበት እንደነበር ግልጽ ነው፡፡ ይሁንና የእነዚህ ስምምነቶች ትሩፋቶች የግብፅ ብሄራዊ ጥቅም ብቻ የሚያስከብሩና የሌሎች ተፋሰስ ሀገራት ጥቅም ታሳቢ ያላደረጉ ነበር፡፡ እ.ኤ.አ ከ1891 እስከ 1959 ድረስ በናይል ወንዝና ገባሪዎቹ ላይ የተከናወኑ ስምምነቶች እንደሚከተለው እንያቸው፡፡

#የ1891_የጣልያንና_የእንግሊዝ_ስምምነት

ይህ ስምምነት የግብፅን ጥቅም ላለመንካት ሲባል ጣልያን በአትባራ ወይም ተከዜ ወንዝ ላይ ግድብ እንደማትሰራ ከእንግሊዝ ጋር የተዋዋለችበት ነው፡፡ በውሉ አንቀፅ 3 ላይ እንደሰፈረው ጣልያን የናይል ገባር ወንዝ የሆነውና ከአዲስቷ የቅኝ ተገዥ ኤርትራ ግዛት ላይ የሚነሳውን አትባራ ወንዝ ላይ የመስኖ ወይም የውኃውን ፍሰት የሚቀንስ ማንኛውም አይነት ስራ እንደማትሰራ ከእንግሊዝ ጋር ውል ማድረጓን ያሳያል፡፡ ጣልያን ከሃፀይ ዮውሀንስ መስዋእትነት በኃላ እ.ኤ.አ. ከ1890-1941 የኤርትራ ቅኝ ገዥ እንደነበረች የሚታወስ ሲሆን ይህ ውል ፍፁም ኢ-ፍትሀዊና በምን አገባኝ ስሜት የተፈፀመ መሆኑን መገመት የሚከብድ አይደለም፡፡

#የ1901_የእንግሊዝና_የጣልያን_ስምምነት

ይህ ስምምነት ከደቡባዊ አስመራ ተነስቶ አትባራ ወንዝን የሚገብርና በመጨረሻም ወደ ናይል የሚቀላቀል ጋሽ/መረብ ወንዝን በማስመልከት በእንግሊዝና በጣልያን መካከል የተከናወነ ሲሆን ይዘቱም ኤርትራ በመልካም የጉርብትና መርህ ላይ ተመስርታ በወንዙ ላይ የመጠቀም መብት እንዳላት እውቅና የሚሰጥ በመሆኑ ከሌሎች የቅኝ ገዢዎች ስምምነቶች በተሻለ ሁኔታ ፍትሀዊና የአሁኗ ኤርትራን መብት የማይጎዳ ነው ይባላል፡፡

#የ1902_የእንግሊዝና_የኢትዮጵያ_ስምምነት

ይህ ስምምነት ግንቦት 15 ቀን 1902 እ.ኤ.አ የሱዳን ቅኝ ገዥ በነበረችው በእንግሊዝ እና በኢትዮጵያ መካከል የተከናወነ የአዲስ አበባ የድንበር ስምምነት ነበር፡፡ ይሁንና በዚሁ ስምምነት አንቀጽ 3 ላይ መነሻቸው ከኢትዮጵያ ያደረጉ የናይል ገባሪ ወንዞችን የሚመለከት የውኃ ስምምነት ይዘትም ተካትቶበታል፡፡ በስምምነቱ መሰረት ንጉስ ሚኒሊክ በግዛቱ በኢትዮጵያ ውስጥ የእንግሊዝና የሱዳን መንግስታት ፈቃድ ሳያገኝ የአባይን ወንዝ ፍሰትን ማስቆም የሚችል ማንኛውም አይነት ስራ እንዲሰራ የማይፈቅድ መሆኑን የተስማማበት ውል ነበር፡፡ ይህ ውል የኢትዮጵያ መንግስት ሳይገደድና በራሱ ፍላጎት ስምምነቱን የፈረመበት በመሆኑ ኢትዮጵያ የምትገደድበት ውል ነው የሚል በግብፅ በኩል ክርክር ይነሳል፡፡
የስምምነቱ አንቀፅ 3 የእንግሊዝኛና የአማርኛ ቅጂዎች በተከታታይ እንደሚከተለው እንያቸው፡፡

“His Majesty the Emperor Menelik II, King of kings of Ethiopia, engages himself towards the Government of His Britannic Majesty not to construct or allow to be constructed, any works across the Blue Nile, Lake Tana or the Sobat, which would arrest the flow of their waters into the Nile except in agreement with his Britannic Majesty�s Government and the Government of the Sudan�.
ጃንሆይ ዳግማዊ ምንይልክ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ከጥቁር አባይና ከባህረ ፃና ከሰባት ወንዝ ወደ ነጭ ዐባይ የሚወርደውን ውሀ ከእንግሊዝ ጋር አስቀድመው ሳያስማሙ ወንዝ ተዳር እዳር የሚደፍን ስራ እንዳይሰሩ ወይም ወንዝ የሚደፍን ስራ ለመስራት ለማንም ፈቃድ እንዳይሰጡ በዚህ ውል አድርገዋል፡፡"

ይህ ውል የኢትዮጵያ ሉአላዊነትን የሚነካ አወዛጋቢ ይዘት ያለው ቢመስልም አሁንም ግን ህጋዊነቱን ውድቅ ለማድረግ የሚጠቅሙ ክፍተቶች ያሉበት መሆኑንም በብዙ የውሀ ሕግ ልሂቃኖች የሚታመንበት ነው፡፡ ለምሳሌ አንደኛ ውሉ በእንግሊዝም ሆነ በኢትዮጵያ አልፀደቀም ወይም Ratify አልተደረገም፡፡ ይሁንና ከዚህ ጋር ተያይዞ በወቅቱ የሁለትዮሽ ሆነ የባለብዙ ወገን ስምምነቶችን ማጽደቅ የሚችል የተለየ ተቋም ባልነበረበት ሁኔታ ስለ ውሎችን መፈረም እንጂ ስለማፅደቅ የሕግ ክርክር ሆኖ መነሳት የለበትም የሚል የመልሶ ማጥቃት ክርክርም ይነሳል፤ምክንያቱም እንደአሁኑ ዘመን የስልጣን ክፍፍል የሚደግፍ ህጋዊ መርህ ባልነበረበት በተለይም ደግሞ ሕግ አውጪ፣ ሕግ አጽዳቂና ሕግ ትርጓሚ ራሱ ንጉሱ በሆነበት ሁኔታ የሁለትዮሽ ስምምነት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ካልፀደቀ ተቀባይነት የለውም የሚለውን ክርክር ውሀ የሚያነሳ አይደለም በማለት ይከራከራሉ፡፡

ሁለተኛ በእንግሊዘኛውና በአማርኛው መካከል የቃላት አለመጣጣምና የትርጉም መጣረስ አለበት፤በአማርኛው ቅጂ የኢትዮጵያ መንግስት የማሳወቅ ግዴታ የገባው እንግሊዝን ብቻ ሲሆን በእንግሊዘኛው ቅጂ ላይ ግን ሱዳንም ተጨምራለች፡፡ ይህ የአማርኛ ቅጂ የኢትዮጵያ መንግስት ፍላጎት መገለጫ ነው ተብሎ የሚታሰበው እንግሊዝ ሱዳንን ትታ እስክትሄድ ድረስ የሚቆይ ጊዚያዊ ግዴታ መግባቱን ነው፤ለዚሁ ማሳያም በውሉ አንቀፅ 4 ላይ “ለቅቆ እስኪሄዱ” የሚል የአማርኛ ቃልና “Removed” የሚል የእንግሊዘኛ ቃል እናገኛለን፡፡ በሌላ በኩል ውኃውን Arrest ወይም Block ማድረግን ወይም ሙሉ በሙሉ ማስቆምን እንጂ ማንኛውም አይነት ተጠቃሚነትን የሚከለክል ውል አይደለም፡፡ ዞሮ ዞሮ የውሉ የአማርኛ ቅጂ ከእንግሊዘኛው በተሻለ ሁኔታ የኢትዮጵያን ጥቅም የሚያስከብር ቢሆንም የውሉ የእንግሊዘኛው ቅጂም ኢትዮጵያ ወንዟን ከመጠቀም የማይከለክላትና እንግሊዝ ሱዳንን ለቃ ከሄደች በኃላም የውሉ ተፈፃሚነትን የሚያበቃ በመሆኑ ኢትዮጵያ በአሁን ጊዜ ይህን ውል የምትቀበልበት የሕግ ምክንያት የለም፡፡ ግብፅም የውሉ 3ኛ ወገን እንጂ ፈራሚ ባለመሆኗ ይህን ውል በማንሳት መከራከር አትችልም፡፡

📣📣 ጽንሰ ኢትዮጵያ ሐዳስ 📣📣
🇪🇹🇪🇹🇪🇹

#ለማንኛውም ሐሳብ እና አስተያየት
👉👉 @Yottor_bot 👈👈
ላይ ያድርሱን።


#ኢትዮጵ
#በአባይ_ላይ_የተደረጉ_ውሎች

ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ፀጋ የተከበበች ውብ ሀገር ብትሆንም በድህነት አዘቅት ውስጥ ተዘፍቃ የምትኖር፤ባደጉ ሀገራት ተረፈ ምርትና የአየር ብክለት ገፈት ቀማሽነት፤በሚጠጣ ንጹህ ውኃ እጥረት ተጠቂነት የምትነሳ ሀገር ነች፡፡ ኢትዮጵያ በመአድን፣ በለም መሬት፣ በእንስሳት፣ በውኃ ኃብት እንዲሁም በሌሎች አላቂና አላቂ ያልሆኑ የተፈጥሮ ሀብቶች ባለፀጋ መሆኗን የሚካድ ባይሆንም በተፈጥሮ የታደለችውን ኃብት ጥቅም ላይ ከማዋል ረገድ ግን እምብዛም አይደለችም፡፡ ሜዳዋንና ተራሯን የሚሸፍን የተፈጥሮ ዝናብ እየተቀበለች ይህ ዝናብ አፈሯንና ወርቋን ጠራርጎ በመውሰድ ለጎረቤት ሀገራት ነፃ ስጦታና ችሮታ እንዲሆን ከመፍቀድ ውጪ የልማት መንገዱን አልተገለጠላትም፡፡ ወንዞች በደራሽ ውኃ ተጥለቅልቀው የገበሬ ማሳ የጎርፍ ሲሳይ ሲያደርጉ ማየት ክረምት በመጣ ቁጥር የምንገነዘበው መራራ እውነት ነው፡፡ አባይን የሚያክል ግዙፍ የውሀ ኃብት ከጉሮሮዋ እየፈለቀቁ የራሳቸው ከርሰ ምድር ሲሞሉ ኢትዮጵያ የበይ ተመልካች ሆና መኖሯን ግርምት ይፈጥራል፡፡

ናይል የሚባለው የአለም ረዥሙ ወንዝ ላይ ያለው ውኃ 85%ቱ የኢትዮጵያ ነው፡፡ ይሁንና ከ50% በላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ኑሮውን በኩራዝ መብራት ይመራል፡፡ ይህ ክስተት ወገብን ይቆርጣል፡፡ ”ከሞኝ ደጃፍ ሞፈር ይቆረጣል” እንዲሉ ግብፅ በናይል ወንዝ ላይ 5% እንኳን አስተዋፅኦ ሳታደርግ በምስራቅም በምእራብም የዚሁ ወንዝ ብቸኛ አለቃ ነኝ በማለት በሌሎች የናይል ተፋሰስ ሀገራት ላይ የምትሰነዝረው ዛቻና ማስፈራርያ የሚያስገርም ነው፡፡ የናይል ወንዝ ብቸኛ ባለቤት እንደሆነች በመግለፅ አሁናዊ ተጠቃሚነቷን የሚነካ ማንኛውም አይነት እንቅስቃሴ የደም መስዋእትነት ለመክፈል ዝግጁ እንደሆነች በተለያዩ አጋጣሚዎች ስትገልፅ መስማት የተለመደ ሆኗል፡፡ ሆኖም ኢትዮጵያ የግብፅ ሽለላና ቀረርቶ ጆሮ ዳባ ልበስ በማለት በግዛታዊ ክልሏ ውስጥ በሚገኝ በጥቁር አባይ ላይ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ ጀምራ ከ70% በላይ ማድረሷን ይታወቃል፡፡ በሌላ በኩል ይህ ግድብ ለግብፅ ራስ ምታት እንደሆነባት፤ኢትዮጵያ የያዘቸውን የልማት መንገድ ለማደናቀፍም ያልፈነቀለችው ድንጋይ እንደሌለ፤በቀጣይም የማትቆፍረው ጉድጓድ እንደማይኖር ኢትዮጵያውያን የምንገነዘበው እውነት ነው፡፡ የናይል ወንዝ በግብፅና በኢትዮጵያ መካከል የፈጠረውን ውጥረት በተለያዩ ወቅቶች የውጭና የሀገር ውስጥ ሚድያዎች ርእሰ ዜና በመሆን የአለም አቀፉ ማህበረሰብ ቀልብ መሳብ የቻለ፤አሁንም ውጥረቱ በስምምነት ያልተቋጨ ክስተት ሆኖ ቀጥሏል፡፡

#የናይል_ወንዝ_የማን_ነው

ናይል የአለም ረዥሙ ድንበር ተሻጋሪ ወንዝ ሆኖ 11 ተፋሰስ ሀገራትን የሚያቋርጥ ነው፡፡ የወንዙ ላዕላይ ተፋሰስ ሀገራት የሚባሉት ኢትዮጵያ፣ ታንዛንያ፣ ኡጋንዳና ኬንያ፤የመሀል ተፋሰስ ሀገራት ደቡብ ሱዳን፣ ኤርትራ፣ ሩዋንዳና ብሩንዲ፤የታሕታይ ተፋሰስ ሀገራት ደግሞ ሱዳን እና ግብጽ ናቸው፡፡ የናይል ገባር ወንዞች ነጭ ናይል፣ ሰማያዊ ናይል(አባይ) እና አትባራ ወንዞች ናቸው፡፡ ነጭ አባይ ከታንዛንያ፣ ኡጋንዳና ኬንያ ድንበሮች አካባቢ ከሚገኘው ከቪክቶርያ ሀይቅ ተነስቶ ወደ ናይል ወንዝ የሚቀላቀል ሆኖ 15% አስተዋፅኦ ያደርጋል፡፡ ሰማያዊ ናይል(አባይ) ደግሞ ከጣና ሀይቅ የሚነሳና 70% አካባቢ አስተዋጽኦ የሚያደርግ ሲሆን አትባራ የተባለው ወንዝ ደግሞ በተከዘና በሰቲት ወንዝ ገባሪነት ከኤርትራ እና ከኢትዮጵያ ተነስቶ በሱዳን በኩል አድርጎ ናይልን የሚቀላቀልና 15% አስተዋጽኦ የሚያደርግ ነው፡፡ ሰማያዊ ናይል(ጥቁር አባይና አትባራ)ከኢትዮጵያ ሉአላዊ ግዛት ተነስተው ኴርቱምን አቋርጠው ግብፅ የሚገቡና 85% የናይል የውሀ ይዘት የሚሽፍኑ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ሰማያዊና ነጭ ናይል በደቡባዊ የሱዳን ክፍል በሚገኘው ኳርቱም አካባቢ ይገናኙና ተያይዘው ወደ ግብፅ ሲና በረሀ በመክነፍ ሜዲትራንያን ባህርን ይቀላቀላሉ፡፡

(( ይቀጥላል))
📣📣 ጽንሰ ኢትዮጵያ ሐዳስ 📣📣
🇪🇹🇪🇹🇪🇹

#ለማንኛውም ሐሳብ እና አስተያየት
👉👉 @Yottor_bot 👈👈
ላይ ያድርሱን።

20 ta oxirgi post ko‘rsatilgan.

2 369

obunachilar
Kanal statistikasi