✨🌱🍂✨️🌱🍂✨️🌱🍂✨️🌱🍂✨️🌱🍂✨️
‘’አዳም ከልጆቹ ጋር ያመሰግንሻል። በሱ የተፈረደ መርገመ ሥጋ ባንቺ ጠፍቷልና፡፡… ዕብራዊው ያዕቆብም ከልጁ ከይሁዳ ጋር ያመሰግንሻል። የርሱ በረከት በልጅሽ ተፈጽሟልና። እግዚአብሔር ይሁዳን ባረከው እንዲህ ሲል፡፡ ይሁዳ ሆይ ወንድሞችህ አንተን ያመሰግናሉ። እጅህ በጠላቶችህ ደንደስ ላይ ነው፡፡ የአባትህ ልጆች ይሰግዱልሃል፡፡…
ሙሴ ከእስራኤል ልጆች ሁሉ ጋር ያመሰግንሻል። እግዚአብሔር በሙሴ ኦሪት ስላንቺ እንዲህ ይላልና፡፡ ሰማይ አድምጥ እነግርህማለሁ ምድርም ያፌን ነገር ትስማ። ትምህርቴም እንደ ዝናብ ትፍሰስ ነገሬም እንደ ጠል እንደካፊያም በእርሻ ላይ ይውረድ። እንደ ጠፈጠፍም እንደ ነጠብጣብም ሣር ይሁን። እንግዲህ አንቺን እርሻ ብሎ ጠራሽ ልጅሽን ደግሞ ጠል አለው፡፡
ዳዊት ከመዘምራን ጋር ያመሰግንሻል። እንዲህ ሲል መሠረቶቿ በተቀደሱ ተራራዎች ናቸው። እግዚአብሔር ከያዕቆብ መኖርያዎች ይልቅ የጽንን ደጆች ይመርጣቸዋል። የእግዚአብሔር አገር ሆይ በአንቺ የተከበረ ነገር ይባላል፡፡
ማኅበረ መላእክት ሁሉ ያመሰግኑሻል። በንጽሕና ሥርዓት እርሳቸውን መስለሻልና፡፡
ማኅበረ ነቢያት ሁላቸው ያመሰግኑሻል። ትንቢታቸው ባንቺ ተፈጽሟልና፡፡
የሐዋርያት ማኅበር ያመሰግኑሻል። የተወደደ ልጅሽ ወንድም ሆኗቸዋልና። ለመንግሥቱም ወራሾች አድርጓቸዋልና፡፡
የበጎ ጎልማሶች ሰማዕታት ያመሰግኑሻል። የልጅሽን መከራ አንድነት በሥጋቸው ተቀብለዋልና፡፡
ደናግል መነኮሳት ያመሰግኑሻል። አኗኗራቸውን ለንጽሕናሽ አምሳል ብፅዓት አድርገዋልና፡፡
ሊቃነ ጳጳሳት ኤጲስቆጶሳት ያመሰግኑሻል። የልጅሽ አንደበት ሥልጣን በአንደበታቸው ተዋህዷልና።
ቀሳውስት ያመሰግቡሻል። ለክህነታቸው መዓርግ ልጅሽ አለቃ ሁኗልና፡፡
ስለ በጎ መልእክት የሚፋጠኑ ዲያቆናት ያመሰግኑሻል። በልጅሽ ገዥነት የምሥጢር አገልጋዮች መልእክተኞች ሆነዋልና፡፡
አናጉንስጢስ መዘምራን ያመሰግኑሻል። ለልጅሽ ምስጋና በቤተ መቅደስ ድምፃቸው እንደ ወርቅ ጸናጽል ይሰማልና፡፡
የክርስቲያን ማኅበር ሁሉ ያመሰግኑሻል፡፡ ከልጅሽ ከቀኙ ጎኑ የተገኘውን የጥምቀት ድርብ በፍታ ተጎናጽፈዋልና፡፡''
ከአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
አርጋኖን ዘሰኑይ ምዕ ፲፪ ፥ ፮ - ፴፭
@sebhwo_leamlakne✨🌱🍂✨️🌱🍂✨️🌱🍂✨️🌱🍂✨️🌱🍂✨️