" ተቋሙ የተገኘበትን የኦዲት ግኝት ማስተካከያ ለማድረግ ዝግጁነት የለውም " - የፌዴራል ዋና ኦዲተር🚨 " ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ የበጀት ጉድለት ተገኝቶበታል !! " " የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አላግባብ የህዝብና የመንግሥት ሀብት እንዲባክን አድርጓል " ሲል በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሰታወቀ።
ቋሚ ኮሚቴው ይህን ያለው የሚኒስቴሩን የፕሮጀክት ውልና የሰው ሀብት አስተዳደር አፈፃፀም የክዋኔ ሪፖርትን በገመገመበት ወቅት ነው።
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የሺመቤት ደምሴ (ዶ/ር) ፤ " ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የሚያከናውናቸው ፕሮጀክቶች ወደ ትግበራ ከመግባታቸው በፊት የቅድመ አዋጭነት ጥናት ግምገማ ተደርጎላቸው እንዲከናወኑ አልተደረገም " ብለዋል።
" በመንግሥት በጀትና በዓለም አቀፍ ድጋፍና ብድር የሚከናወኑ ፕሮጀክቶች የትግበራ ቅደም ተከተል ተሰጥቷቸው ለምክረ ሀሳብ ለሚመለከታቸው አካለት አለማቅረቡ ተገቢነት የሌለው ነው " ሲሉ ገልፀዋል።
በተያዘላቸው ጊዜ ያላለቁ ፕሮጀክቶች ወቅታዊ ሁኔታ የማይታወቅ ሲሆን፣ የፋይናንስና የፊዚካል አፈፃፀማቸው የተስማሚነት ችግር እንዳለበት አሳውቀዋል።
በተጨማሪም ፕሮጀክቶች ሳይጠናቀቁ አቋርጦ በጀቱን ወደ ሌላ ፕሮጀክት የማዘዋወር ሂደት ረገድ የህግ፣ የመመሪያ፣ የአሰራር ጥሰት የታየበት በመሆኑ ሊታረም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
" ለትራንስፖርት ኪራይ፣ ለዳታ ማዕከል ግንባታ፣ ለሳይንስ ካፌና ለሰራተኛ ደሞዝ ያለአግባብ የወጣውን ወጪ ኦዲት በማድረግ በ15 ቀናት ውስጥ ለቋሚ ኮሚቴው ሪፖርት እንዲያደርግ " ሲሉም አሳስበዋል።
ከሰው ሀብት ጋር ተያይዞም መስሪያ ቤቱ ሰራተኞችን #በሪኮመንዴሽን_የሚቀጥርበት ሁኔታ ህግና ስርዓት ያልተከተለ በመሆኑ ሰራተኞችን አወዳድሮ ሊቀጥርና አሰራሩ ሊታረም እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
ከንብረት ማስመለስ ጋር በተያያዘም ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የለቀቁና ጡረታ የወጡ ሰራተኞች ያልመለሷቸውን በጥቅል ከፍተኛ ዋጋ ያላቸውን የመንግስትና የህዝብ ሀብት በአግባቡ የማስመለስ ስራ መስራት አለበት ብለዋል፡፡
በተጨማሪም ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ የበጀት ጉድለት እንደተገኘበት በማመልከት የአሰራር ሂደቶችን በማረምና ለጉድለቱ መንስኤ የሆኑ ግለሰቦችን የህግ ተጠያቂ በማድረግ ለምክር ቤቱ እንዲያሳውቅ ቋሚ ኮሚቴው አሳስቧል።
የፌዴራል ዋና ኦዲተር ወይዘሮ መሰረት ደምጤ ፤ " ተቋሙ የተገኘበትን የኦዲት ግኝት ማስተካከያ ለማድረግ ዝግጁነት የለውም " ሲሉ ተናግረዋል።
" ተጀምሮ ላልተጠናቀቀ ፕሮጀክት ገንዘብ ወጪ ተደርጓል " ብለዋል።
" የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የሰው ሀብትና የንብረት አስተዳደር ሂደቱ ደካማ ነው " ብለው " ከህግ አግባብ ውጪ የተከፈሉ ክፍያዎች ላይ በፍጥነት የእርምት እርምጃ መውሰድ ይጠበቅበታል " ሲሉ ተናግረዋል።
በኦዲት ክፍተቶች ላይ የፌዴራል ፀረ ሙስና ኮሚሽን ክትትል በማድረግ የህግ ተጠያቂነት ማስፈን እንደሚጠበቅበት ተመላክቷታ።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ምን መለሱ ?
በለጠ (ዶ/ር) ፤ " ተቋሙ የሚሰራቸው ሥራዎች ዘርፈ ብዙ በመሆናቸው በአንዳንድ ዘርፎች የኦዲት ጉድለት ተከስቷል " ሲሉ ተደምጠዋል።
" ችግሮቹን ለመፍታት የድርጊት መርሐግብር በማዘጋጀት የተወሰዱ እርምጃዎችን ለቋሚ ኮሚቴው እናቀርባለን " ብለዋል።
" ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025ን ተግባራዊ ለማድረግ ከዓለም ባንክና ከአጋር አካለት ጋር የሚሰሩ ሥራዎች በአይነትና በቁጥር በርካታ ናቸው " ያሉት ሚኒስትሩ " የተስተዋሉ የኦዲት ክፍተቶችን ለማረም ዝግጁ ነን " ብለዋል። #EPA #HoPR
@tikvahethiopia