ፍልስፍና ለላቀ አስተሳሰብ Philosophy


Kanal geosi va tili: Efiopiya, Amharcha
Toifa: ko‘rsatilmagan


ፍልስፍና  እውነትን በመፈለግ- ልማዳዊ እምነቶችን በመሞገት እና ጭፍን አመለካከቶችን በጥበብ በመመርመር ወደ ላቀ አሰተሳሰብ ያሻግራል።
በዚህ ቻናል አለም ላይ ያሉ ፍልስፍናዎች ፤ ርዕዮት አለሞች ፤  ሀይማኖቶች እና አስተሳሰቦች በነፃነት ይዳሰሳሉ።

Связанные каналы  |  Похожие каналы

Kanal geosi va tili
Efiopiya, Amharcha
Toifa
ko‘rsatilmagan
Statistika
Postlar filtri


ኤግዚስቴንሻሊዝም እና ኒሂሊዝም

ኤግዚስቴንሻሊዝም በፍልስፍና ውስጥ ብዙ ከተሠራባቻው ፍልስፍናዊ ንድፈ-ሐሳቦች አንዱ ነው፤ በአንዳንድ ምልከታዎቹ ከኒሂሊዝም ጋር የሚጋራቸው ነጥቦች ስለሚኖሩ ሁለቱን ንድፈ-ሐሳቦች ቁልጭ አድርጎ ማሳየት ባይቻል እንኳ ተዛምዶና ተባዕዷቸውን ለማሳየት መሞከር ተገቢ ነው። ኤግዚስቴንሻሊዝም “አሁን” እና “እዚህ” በሚሉ ነጥቦች ያምናል። “ኒሂሊዝም” ግን በምንም አያምንም፤ ካመነም በምንም ነው።

ኒሂሊዝም የትኛውንም ዓይነት ዓለማዊ ሀቅ አይቀበልም፤ በ19ኛው ክፍለ ዘመን በሩስያ ሥነ-ጽሑፎች ውስጥ እንዳበበ ወይም እንደተመሠረተ ይታሰባል። በዚያም በሩስያ በነበሩ ተቋማዋዊ መዋቅሮች አመጽ ከመነሳት አልፎ የትኛውም መንግስታዊ፣ ሃይማኖታዊ እና ማኅበራዊ መዋቅርንም መቃወም ችሏል።

“ኤግዚስቴንሻሊዝም” በየትኛውም የሕይወት ትርጓሜ የማይስማማ ነገር ግን እያንዳንዱ ግለሰብ የራሱን ዓለም መሥራት እንደሚችል የሚያስረዳ ወይም በእዚህ እውነት የሚያምን ነው። በጠቅላላው ሁለቱም እሳቤዎች ናቸው። መነጽራቸው የሚለያየው ግባቸው ላይ ነው።

ኒሂሊዝም በምንም ከማመን ይልቅ ምንምን የሚያመልክ ነው። በምንምነት ማመን በክብ ውስጥ ላለ ነገር ሁሉ ዕውቅና መስጠት ነው። “ኤፕሲቲሞሎጅካል” ፍልስፍናቸውም “ራሽናሊዝም” እና “ማቴሪያሊዝም” ነው፡ የግለሰብ ነጻነት ደግሞ የመጨረሻ ግባቸው። አይዲያሊዝም ወይም እምነታዊነት ለእነርሱ ዋጋ የለውም።

ኒሂሊስት ሰዎች “እግዚአብሔር የለም” ብለው የሚያምኑ ሰዎች አይደሉም፤ ይልቁንም የእግዚአብሔርን መኖር ማረጋገጥ እስካልተቻለ ድረስ በእግዚአብሔር መኖር እርግጠኞች አይደሉም። በሌላ ምሳሌ ደግሞ ለማየት አንዲት ሚስት በባሏ ላይ ብትቀላውጥ “ባል ግድ የለም አይጎዳኝም” ብሎ ያልፋል ማለት አይደለም፤ ነገር ግን ጉዳዩ የሚሆነው ሚስት በሕይወት ውስጥ ትቀላውጥ እንደሆነ ማስረጃዎች በመኖራቸውና ባለመኖራቸው ላይ ነው። ይህም ሆኖ ሚስት መቀላወጧ በማስረጃ የተረጋገጠም ቢሆን ባል የሆነ ጊዜ በእርሷ ላይ ስላለመቀላጡ ማስረጃው ምንድን ነው? ስለዚህም እርግጠኛ የምንሆንበት ሕይወት የለንምና ሚስት ቀላውጣ ብትገኝ የሚደንቅ ሊሆን አይችልም ይላሉ።

ይሄንን ነገራቸውን ሊገለጥ የሚችል ሁለት ገላጭ ምሳሌዎቻቸውን ማየት እንችላለን። “What he wished to believe, that is what each man believes” “ሊያምን የሚመኘው ማንም የሚያምነውን ነው” እና “The life of mortals is so mean a thing as to be virtually un-life” “የሟች መኖር ማለት አለመኖር ነው” ወይም “ሟች ሕይወቱ አለመኖር ነው”። (ሁለቱም አባባሎች በሃይዲገር የተጠቀሱ ናቸው)

ኒሂሊስቶች ለእዚህ እሳቤአቸው አስረጂ የሚያደርጉት የሰው ልጅ ምኞትን እና ቅዠትን ከሕይወቱ ካስወጣ ምንም መሆኑን ይገነዘባል” የሚል ነው። ለመሆኑ የኒሂሊስቶች መጨረሻ ምን ሊሆን ይችላል? እነርሱስ በምን ሊገለጡ ይችላሉ? ሕይወት ትርጉም የላትም፣ ይች ዓለምም ምንም ናት ብለው ያመኑ ኒሂሊስቶች ከእነዚህ በአንደኛው ጥላ ላይ ያርፋሉ።

ፍልስፍናዊ ሞት ፡

እጅ ይሰጣሉ፤ “ሕይወት ትርጉም አልባ ናት ስለዚህም መፈላሰፌ ዋጋ የለውም” ከሚል መነሻ ራሳቸውን በሃይማኖት ጥላ ሥር ይደብቃሉ፤ ወይም በአንድም በሌላ መንፈሳዊ ዋሻ ውስጥ ራሳቸውን ያስቀምጣሉ።

አካላዊ ሞት :

ትርጉም አልባ በሆነ ዓለም ውስጥ በሕይወት መኖር አሰልቺና የስቃይ ምንጭ ስለሚሆንባቸው ራሳቸውን ያጠፋሉ።

መቀበል :

ሕይወት እውነተኛ እና የመጨረሻ ትርጉም እንደሌላት እያወቁ መኖር።

ለመደምደም ሦስት ተመሳሳይ የሚመስሉ ነገር ግን የተለያዩ ፅንሰ ሐሳቦችን እንይ

ኤግዚስቴንሻሊዝም

"በግለሰባዊ ግንዛቤ፣ ግለሰባዊ መልካም ፈቃድና ግለሰባዊ ኃላፊነት ውህድ ኑረት አንድ ሰው በዓለም ውስጥ የራሱን የሕይወት ትርጓሜ መስጠት ይችላል ወይም ይገባዋል” ብሎ የሚያምን ነው።

ኒሂሊዝም

“ዓለም ትርጉም አልባ ነው ብሎ ማመን ብቻ ሳይሆን ለዚህ ዓለም እና ሕይወት ትርጉም ለመስጠት መሞከር በራሱ ምንምነት ነው” ብሎ የሚያምን ነው።

አብዘርዲዝም :

ደግሞ ለሕይወት ትርጉም ለማግኘት የሚደረገው ትግል ሁሉ ከተፈጥሮ የተነሣ ሁሌም ከትርጉም አልባነት ጋር የሚደረግ ግብ ግብ ነው፣ ነገር ግን ሕይወት ማለት ሁሌም ቢሆን ይህንን ተቀብሎ ሕይወት ልትሰጥ የምትችለውን አዎንታዊነት ሁሉ ለማግኘት መፍጨርጨር ነው።

በስተመጨረሻ ሥራ ላይ ያለውን የፍልስፍና ትርጓሜ ማየቱ መልካም ይሆናል። እስካሁን ያየናቸው የፍልስፍና ትርጓሜዎች በቅን ልቦና ያየ ሰው ፍልስፍናን እንዲህ ሊበይነው ይችላል። ወይም ይገባል።

“ፍልስፍና ማለት ጥብቅ በሆነ ምክንያታዊነት ላይ በመመሥረት በጣም ጠቃሚ የሆኑ ጥያቄዎችን ለመመለስ መሞከር ማለት ነው”

በዚህ ብያኔ ውስጥ ያለው መሠረታዊ ጭብጥ “ጥብቅ እና ምክንያታዊ" የሚለው ነው። ነገር ግን “ስለምን?” –እዚህ ጋ ልዩነቶች ሊኖሩ ይችላሉ። በማውጠንጠን፣ በመተንተን ወይም በኀልዮአዊነት መንገዶችም ቢሆን እያንዳንዳቸው በሚያተኩሩባቸው ጉዳዮች ላይ በቂ አስረጂ ያለውን ጥብቅ ምክንያታዊነት ማቅረብ ነው። እንዳየነውም በተለያየ መደብ ያሉት ፈላስፎች በራሳቸው ጠቃሚ ያሏቸውን ጥያቄዎች ለመመለስ ይሠራሉ። እነዚያም ጥያቄዎች ለእነርሱ መሠረታዊ ናቸው።

ደሳለኝ ስዩም
📚የፍልስፍና መግቢያ
@Zephilosophy
@Zephilosophy


ሐይማኖተኛ እንጂ መንፈሳዊያን አይደለንም

~
አምልኮታችን ውስጥ ስሜት እንጂ ስክነት የለም... ቶሎ ነው ቱግ የምንለው... አንዳንዴ ለእግዜሩ/ አላህ 'ጠበቃ' የሆንን ሁሉ ይመስለናል... ስሜት ደግሞ የተቀባበለ ጠብመንጃ ማለት ነው... በየትኛውም ሰዓት ቃታው ሊሳብ ይችላል... አያድርስ ነው ያኔ...
------
ይህ ለምን ሆነ?…
----
ስሜት ሐይማኖተኛ ብቻ ከመሆን ሲወለድ ስክነት መንፈሳዊነትን ከመደረብ ይመዘዛል… እኛ ደግሞ ሐይማኖተኛ እንጂ መንፈሳዊያን አይደለንም… ስለምን ቢሉ “መምህራኑ” የሐይማኖት እውቀትን ከስሜት ጋር ሰጡን እንጂ መንፈሳዊነትን ከስክነት ጋር አላሳዩንም…
-----
ሌላም አለ… ‘በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ’… እንዲሉ…

•  ባለፉት አስርት ዓመታት ከዘመን ጋር የነወሩ፣ በንዋይ መገዛት እንጂ ራስን መግዛት የማያውቁ ተኩላዎች ከስማቸው ፊት በሚያስቀምጡት ‘የስያሜ’ ለምድ በግ መስለው ተቋማቱን አጨናንቀዋል…

•  ከደዌ ያልተላቀቀው ፖለቲካችን በሃሳብ ልዕልና ከመቆም ይልቅ በማናቆር ብልጠት ስለሚጓዝ እነዚህን ተቋማት እጀታ አድርጎ ግቡን ያስፈጽማል…

•  መጠየቅ፣ መመርመር፣ ለምን እንዴት ማለት የተነጠቀው ትውልድ ደግሞ በምንም ጉዳይ የእውር ድንብር ግርርርር ማለት መደበኛ ግብሩ ሆኗል… ግርግር  ለማን ይመቻል? - ለሌባ!!
___
እንደ ሙስሊምነትህ አክብሮት የምትሰጠውን ነገር ፕሮቴስታንቱ 'አልባሌ' ሲያደርገው መቆጨትህ ባይገርምም ነገሩን በመግባባት ማሳለፍህ ነው አማኝ የሚያስብልህ... ኦርቶዶክስ ሆነህ ሙስሊሙ ውድህን 'ሲያንቋሽሸው' የሚፈጠርብህ ጉዳት ይሁን ቢባል እንኳ እልሁን በፍቅር ለማብረድ ያለህ ብርታት ብቻ ነው ክርስቲያን 'ሚያደርግህ...
___
በማቃለል 'የከበረ' ክርስቲያን ሊኖር አይችልም... የተዋረደ ካልሆነ በቀር... አልባሌ በማድረግ የጸደቀ ፕሮቴስታንትም ፈልገን አናገኝም... በሞራል የዘቀጠ እንደሆን እንጂ… በእኔ እምነት ቅድስና የራስን ከመጠበቅ ጥንቃቄ በላይ የሌላውን ከማክበር ልዕልና ለመወለድ ቅርብ ነው... ያም ሆኖ ችግሩ ሲፈጠርስ?... ሰይፍ እንምዘዝ?... ደም እንቃባ?... ቤተ አምልኮ እናፍርስ?... በጭራሽ... ሰው በክፋቱ ልክ ቢከፉበት እጥፉን ይከፋል... በፍቅር ካረቁት ግን ለሁልጊዜ ይድናል...
___
አፍጋኖች እንዲህ ይላሉ...

"Don't use your teeth when you can untie the knot with your fingers"
___
ሐይማኖታዊ ጉዳዮችን የሚያስተናግደው መስተጋብራችን በብዙ እንከኖች የተሞላ ነው... ከትናንት ብዙ ብንርቅም አዘጋገማችን ግን መዳረሻን የሚያርቅ ይመስላል... እንደ ቤተ-አምልኳችን አስተምሮ እኛ መታረቅ እየተገባን በፖለቲከኞች እንታረቃለን… በመንፈሳዊ ስክነት በርደን እንድንታይ ሲጠበቅ በአፈሙዝ እንቀዘቅዛለን… ታዲያ ምኑ ላይ ነው የሐይማኖት ፋይዳው?... ሐይማኖተኛን እምነቱ ከመግደል ካላስቆመው ሌላውማ ስለምን ይፈረድበታል?... ሐይማኖተኝነት ሐይማኖቱን ሳይኖሩት ይሆኑታል እንዴ?...
----
“True religion is real living; living with all one's soul, with all one's goodness and righteousness.” - Albert Einstein
___
ለማንኛውም...
• ሁኔታዎችን በእኛ ላይ የመጣ፣ ሆን ተብሎ የተደረገ፣ ከጥላቻ የመነጨ ከሚል ፍረጃ ማላቀቅ ውብ ነገር ነው...

• አንዳንድ ሁኔታዎችን በመንጋ ቁርቁስ ከማጦዝ ይልቅ ተቋማዊ አልያም ጓዳዊ በሆኑ መንገዶች ለመፍታት መሞከር የማይሻገር ቁስል እንዳይፈጠር ያደርጋል...

• አንድና ሁለት ግለሰቦች የፈጸሙትን ጥፋት ግለሰቦቹ የተገኙበት ሐይማኖት /ተቋም/ ጉዳይ አድርጎ አለማሰብም በጎ ነገር ነው...
___

“When I meet a new person, I don't see race or religion. I look deeper. We must learn to satisfy our conflicts peacefully and to respect one another.” - Muhammad Ali
-----
መልካም ጊዜ

ደምስ ሰይፉ

@bridgethoughts

4.6k 0 42 28 105

"I reject any religious doctrine that does not appeal to reason and is in conflict with morality." 
— Mahatma Gandhi

@zephilosophy


የነቃ ሲመክር

ውዶቼ!
ተነሱ! ተነሱ! ተነሱ!
በጠያቂ አቅም ነው የሚሰራው መልሱ፡፡

ከኮከቦች ርቀት፣
ከባህሮች ስፋት፣
ከአውሎ ንፋስ ጉልበት
የተጠነሰሰ፤
የመገለጥ ወይን ከልቤ ፈሰሰ።
ከከፍታዎቼ፣ ከአደባባዮቼ ወስዶ ላይመልሰኝ፤
ከነፍሴ ተማክሮ ክንፌ ቀሰቀሰኝ።

ሰረገላው አይቆም፣ ነጂውም አይተኛ፤
ጥያቄም፣ ይቅርታም፣
ፀፀትም፣ ትዝብትም - ይልካል ወደእኛ፤ “ተጓዦቼን ሁሉ ምንድን አስተኛቸው?
እኔ መቆም አላውቅ -
             ወይኔ ረበሽኳቸው!” ይላል።

ዕረፍት የማያውቀው - ፈጣን ሰረገላ፣
መንቃት በማያውቁ- ተጓዦች ሲሞላ፤
የመገለጥ ወይን በአፍጢሙ ተደፋ፤
“ወራጅ አለ!” የሚል ተሳፋሪ ጠፋ።


ውዶቼ!
ተነሱ! ተነሱ! ተነሱ!
ግለጡ፣ ኀስሱ፣
ከጥያቄ ጅረት በጥራት ፍሰሱ፤
ሰፊ ጊዜ ስጡ ክንፍ ከነፍስያ እንዲወሳወሱ።
ጎዳናው፣ ሸለቆው፣
ጋራው፣ ሸንተረሩ - አዲስ ፊት እንዲያዩ፤
“ወራጅ አለ!” በሉ በየአደባባዩ።

ምንጭ -የመንፈስ ከፍታ
ደራሲ-ሩሚ
በረከት በላይነህ እንደተረጎመው!!

@Zephilosophy
@Zephilosophy


የጠየቁ ተሻግረው አሻገሩን

ስንቱ ይሁን የፖሟ ፍሬ ስትወድቅ እየተመለከተ “ለምን? እና እንዴት? ሳይል ያለፈ! አንድ ሰው ግን ጠየቀ፤ አይዛክ ኒውተን፡፡ ኒውተን አእምሮቸውን በተገቢው ተጠቅመው ማለትም ማወቅን ሽተው፣ ያወቁትንም ለወግ አብቅተውና ለማዕረግ አድርሰው ከራሳቸው አልፎ ለሌሎች ከተረፉት መካከል በምሳሌነት ሊነሳ የሚችል ግለሰብ ነው። ይህ ሳይንቲስት “በምን ምክንያት?፣ ከምን የተነሳ?' ብሎ፤ በመጠየቅ መንገድ ተጉዞ ምላሾችን ፈለገና ስለ መሬት ስበት እንዲገባን አደረገን። የፍጥነት እና የኃይል ምጥነት እንዲሁም የአድራጊ እና ተደራጊ እኩልነት ሕጎችን አጥንቶ ሚስጥራትን ገለጠልን። ይህን ማድረግ የቻለው አእምሮን በሚገባ ለመጠቀም ከሚያስችሉ መንገዶች መካከል የብልህ ምርጫ የሆነውን መጠየቅን በመምረጡ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡

ይህን መንገድ በመምረጥ ብልህነታቸውን ካስመስከሩ መሃከል በምሳሌነት ኒውተንን ብጠቅስም በተመሳሳይ በመጠየቅ መንገድ ተራምደው መዳረሻቸውን ተሻጋሪ እና አሻጋሪ ያደረጉ ሌሎችም አሉ። ኾኖም አሳዛኙ ነገር ለተፈጠረባቸው ጥያቄ መልስ ለማግኝት ዳክረው እውቀትን ያገኙ ሳይንቲስቶች፣ ተመራማሪዎች፣ ፈላስፎች በርካታ አሊያም በቂ የሚባል አለመሆናቸው ነው። ግና ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት እኚህ በቁጥር ውስን የሆኑ ብልሆች ለምን እንዴት የት ብለው በመጠየቃቸው እና ጥቂት የማይባል ምላሾችን ፈልገው በማግኝታቸው ብሎ ዓለመ ሰማያትን፣ ምድራችንን እና ማንነታችንን እንድናውቅ ረድተናል፤ እየሩዱንም ይገኛሉ፡፡ ከተፈጥሮ ጋር ተስማምተን እንዴት ዘላቂ መሆን እንደምንችል በምርምር ውጤታቸው አስተምረውናል። ታመን እንድንድን እና እድሜያችንን እንዲዘልቅ መንገድ ጠርገውልናል። ኑሯችን በኋላቀርነት ገመድ ተተብትቦ እንዳይቀር፣ አኗኗራችን ምቹ እንዲሆን፣ እመርታችን እንዲጎለብት እና ዕይታችን እንዲሰፋ አድርገዋል።

አሁንም ቢኾን የመጠየቅ ጉዞን መከተል እንዳለበት ተረድቶ የወሰነ እንዲሁም ወስኖ መራመድ የጀመረ ሰው መዳረሻው ከላይ በምሳሌነት ካየነው የኒውተን ታሪክ የተለየ አይሆንም። እንግዲህ ይህን ያወቀ ተጓዥ በጨለማ ውስጥ ብርሃን ማግኝት እንደሚችል ያምናል፤ ያውቃልም። ይህ መንገደኛ ማምለጫ የለሽ በሚመስል ወጥመድ ውስጥ ቢገኝ እንኳን መውጫ እና ማምለጫ ዘዴን ያበጃል እንጂ በፍጹም ተስፋ አይቆርጥም፡፡ እንዲህ ዓይነት ተራማጅ ሰው መሬት ላይ የማያወርደው ህልም እንደሌለው ከእውነቶቹ አንዱ ነው፡፡ ወደ ኋላ ሊጎቱት የሚችሉ እልፍ አእላፍ ነገሮች እንደሚገጥሙት ቀድሞዎንም ያውቃል። ነገር ግን መሮጥ ቢያቅተው ተራምዶ፣ መራመድ ቢሳነው ተንፏቆ፣ መንፏቀቅ ቢያቅተው ወደ ፊት ወድቆ ካለመበት ይደርሳል፤ አሸናፊም ይሆናል። አሸናፊም ሲሆን ከራሱ አልፎ ለብዙዎች በነገሮቹ ኹሉ ይተርፋል።

✍️ፍሬው ማሩፍ
📚ጥያቄዎቹ

@zephilosophy


ከከፍታ ምሳሌነት ወደ የኋላቀርነት ማሳያነት ለምን ተሸጋገርን?

ታሪክን ከእኛ ጋር አያይዤ ሳስብ ያለፉ ኹነቶቹን ምርኩዝ አድርገን ኢትዮጵያኖች "ትልቅ የነበረን ሕዝቦች ነን" የሚል ጥቅስ በየልባችን ሰንቀን፣ ጀርባችን ላይ በሚሰማን ሙቀት አማካኝነት ያለንበትን ኹኔታ እየለካን “ደህና ነን " እያልን የምንኖር መሆናችን አንዱ ነው፡፡ በሌላ በኩል ለዛሬ ጉድለታችን፣ ለአሁን ክፍተቶቻችን፣ ለስንፍናችን ሰበብ ፍለጋ ከአጽም ጋር ትግል ላይ መክረማችንም ይደንቀኛል፡፡

ቀዳሚ እንጂ ተከታይ ተሸናፊ ሳይሆን አሸናፊ እንደነበረን የቀደምት ስልጣኔዎቻችንን ምስክር ናቸው፡፡ ታዲያ ከቀዳሚነት ወደ ተከታይነት ፤ከክብር ወደ ውርደት፤ ከከፍታ ምሳሌነት ወደ የኋላቀርነት ማሳያ መቼ?፣ ለምን? እና እንዴት? ተሻጋገርን የሚለውን ለማወቅ  ታሪካችንን መመርመር ያስፈልጋል። ሌላው ቢቀር ታሪክን በመፈተሸ ለውጥ በማስተናገድ ሂደት ላይ የሚፈጠሩ መሰናክሎችን መቀነስ ይችላል፡፡

ዛሬ ሙሉ ሰውነታችን በድህንነት፣ በአስተሳሰብ ልልነት፣ የሚበጀንን ስልጣኔ በማጣት ቆሻሻ ታወሯል። ይህን ቆሻሻ የአመክንዮ እንዶድ በመቀንጠስ፣ ከሳይንስና ከጥበብ ወንዝ መመራመርንና መጠየቅን በመጭለፍ እንደመጽዳት ፋንታ በተቃራኒው እኛ እያደረግን ያለነው በአንድ እጃችን የድህንነት እከካችንን እያከክን፣ በሌላኛው ደግሞ ላለንበት ኹኔታ ምክንያት ናቸው ወደ ምንላቸው እየጠቆምን ጊዜያችንን በመንቀፍ እና በመተቻቸት መፍጀት ነው።

አሁን ላይ ላለንበት ኹኔታ ሰበብ ፍለጋ ከቅርጫታችን ውጪ በሚገኙ አካላት ላይ ጣት የመቀሰር አባዜ ማብቃት አለበት፡፡ ማውገዝ አለብንም ከተባለና ስራቸውን በአግባቡ ያልተወጡ ገዢዎችን፣ ለሆዳቸው ያደሩትን የማኅበረሰብ ወኪሎቻችን እና የሃይማኖት መሪዎችን ነው (ኹሉም ባይሆኑም ውሉ)፡፡ በየትውልዱ ብቅ ለማለት ድፍረት ያገኙትን እና ሊያነቁን የሞከሩቱን ሲያሳድዱ፣ ሲያስሩ እና ሲገድሉ እንደነበር ስለ ታሪካችን የሚናገሩትን መጽሐፍት ይነግሩናል። ኾኖም እነሱንም ቢሆኑ የሰሩት ስህተት ዳግም እንዳይከሰት ለመማሪያነት ካልተገለገልንበት በስተቀር ስማቸውን እየጠራን መቆዘሙና የጥፋተኝነት ካባ እያከናነቡ መሰንበቱ ምኑም አይጠቀመንም! መወጋገዝን ካመጣን አይቀር ራሳችንንም እናውግዝ፤ የማይጠቅሙ ባህሎችን መርምሮ ጥቅም ጉዳቱን ሊነግረን ላይ ታች የሚል አንቂዎቻችንን ያልሆነ ስም ሰጥተናልና፤ ልፋታቸውን መና ማድረግን የጀግንነት መስፍርት አድርገን አስቀመጠናልና!

ኢትዮጵያውያን አሁን ላለንበት ማኅበረሰባዊ፣ ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ዋነኛ ምክንያቶች ምን ይሆኑ ብዬ ብጠየቅ "ባይመችን እንኳን ተቀመጡ ባሉን ቦታ ላይ ቦታ ከመቀየር ይልቅ መቀመጫችንን እያታከክን ለመኖር በመመርጣችን ነው" ብዬ አስቀድሜ እመልሳለሁ፡፡ ዛሬም ድረስ የተቀመጥንበት ቦታ እንደቆረቆረን ብንገኝም ማን እንዳስቀመጠን እና ለምን እንደተቀመጥን አልጠየቅንም፡፡ ባይሆን መቀመጫችንን ከቦታው ጋር ለማለማመድ ጊዜና ጉልበታችንን እናባክናለን። ግና አሁንም ቢኾን አረፈደምና እንጠይቅ። ካልሆነ ግን ከድጡ ወደ ማጡ መንሸራተታችን አይቀርልንም(መንሸራተቱንማ ከጀመረን ቆይተናል፡፡)

ሌላኛው ምክንያት ብዬ የማስቀምጠው 'የሀገራችን ልክ ያልሆነና ወደ ኋላ ጎታች የሆነ ማኅበረሰባዊና ፓለቲካዊ ሥርዓት ጠልቆና ጠንክሮ በሀገራችን በመገንባቱ ነው' የሚል ነው፡፡ ይህ ሥርዓት  የሕዝብን ጊዜያዊ ስሜት በመኰርኰር የተካኑ ብልጣ-ብልጥ አላዋቂ ብሔርተኞችንና ጥቅመኞችን ንጉስ አድርጎ የሚያሾም ፤ በየዘመኑ ያሉብንን ችግሮች በመለየት ያሳዩንን፣ወደ ኋሊት እየተጓዝን መሆኑን በማስመልከት ሊያነቁን የሞከሩትን  አገርና ሕዝብ ወዳዶችን ደግሞ የበዪ ተመልካች የሚያደረግ ነው።

ትልቁ ችግራችን በርካታ ነገሮችን ሳንመረምር፣ ሳንፈትሽ እና ሳንጠይቅ እንደተነገረን የምንቀበል መሆናችን ነው።ብዙዎቻችን ስለ አንድ ነገር የሚኖረን ድምዳሜ አሊያም “እውነታው' ተብሎ የሚነገረንን ሐሳብ ለመፈተሽና ለመፈተን ጥረቱና ድፍረቱ የለንም።፡ በቸልተኝነት አውሎ ንፋስ የተወሰድን፣ ከፍርሃት ጥላ ገለል ማለት የተሳነን ሆነናል። አጎንብስ ስንባል እሺ፣ ተቀመጥ የሚል ቃል ስንሰማ ዝፍዝፍ፣ ሩጥ የሚል ድምጽ ስንሰማ ፈርጣጭ ሆነናል።

መፅሀፍ - ጥያቄዎቹ
ደራሲ- ፍሬው ማሩፍ

@zephilosophy
@zephilosophy

9.2k 1 22 15 33

እግዚአብሔር ለማይወደው ህዝብ የምጨነቀው ለምንድነው?
(ተስፋኣብ ተሾመ)
* * *

ዎልፍ ጋንግ ገፀባህርይ ነው። ደራሲ ቤተማሪያም ተሾመ 3ኛ ቤተ-መቅደስ በሚለው መፅሐፉ ላይ የፈጠረው ምናባዊ ገፀባህርይ

ዎልፍ ጋንግ በ77 ረሃብ ወቅት ሐገራችንን ለመርዳት ከጀርመን ወደ ኢትዮጵያ መጣ። የአንድ ግብረሰናይ ድርጅት አባል በመሆን በትጋራይ ያሉ ዜጎችን ሲረዳ ቆይቶ ከህብረተሰቡ ጋር ተላመደ። ትግረኛ ለመደ፥ ጠላ እና ዶሮ ወጥ ወደደ።
ትርሃስ የተባሉ እናት ደግሞ ጀርመናዊውን እንደ ቤተሰብ አቀረቡት።

ከእለታት በአንዱ፥ የደርግ አየር ሀይል ጥቃት ሲሰነዝር ብዙሃኑ ወደ ሞት ተነዱ። የእርስ በእርስ ጦርነት ወለድ ጥቃቱ በመደዳ ብዙዎችን ገደለ። እናት ትርሃስ ከሟቾች መካከል ነበረች።
ዎልፍ እየተሯሯጠ ቁስለኞችን ሲያግዝ የትርሃስን በድን አገኘ። የ እማማ ትርሃሰ በድን ከህፃን ልጃቸው አስክሬን ጋር ተቃቅፎ ተጋድሟል።

ድጋፍ ለማድረግ የመጣው ዎልፍ ጋንግ ሀዘን መታው። በሀዘን ውስጥ ሆኖ "እግዚአብሔር ያላዘነለትን ህዝብ እኔ ምን አባቴ ልፈጥለት ነው?" አለ።

ይህ ታሪክ በቤተማሪያም የልብወለድ መፅሐፍ ውስጥ ያለ ነው። ታሪኩ ምናብ ወለድ ቢሆንም ወደ እውነት የሚንጠራራ ነው።

በታሪክ አጋጣሚ እንደ ህዝብ ብዙ መከራ ተፈራርቆብናል። ከአንድ ችግር ወደ ሌላ ችግር እንሸጋገራለን። የሰላም ፋታ ሳናገኝ ወደ ጦርነት እንገባለን።
አያቶቻችን ላይ የወረደው የመከራ ዝናብ በእኛም ላይ ወርዷል። አባቶቻችንን የነረተ የችጋር ቡጢ እኛንም ነርቶናል። ከሰቆቃ ወደ ሌላ ሰቆቃ ስንሸጋገር ኖረናል።

የሆነብን ሁሉ እግዘብሔርን ሊራራልን ስላልወደደ እስኪመስል ድረስ መራር ነው። ዛሬም የትላንቱን በሚመስል ጭንቅ ውስጥ ነን።

እስከአሁን ከመለኮት አለም መፍትሄ ስንፈልግ ኖረናል። ፖለቲካ ወለድ ችግራችንን እግዚአብሔር እንዲፈታልን ስንሻ ነበርን። ምናልባት መፍትሄ የምናገኘው የመፍትሔ ፍለጋ መንገዳችንን በመቀየር ቢሆንስ?

ያ እስኪሆን ድረስ ግን ዎልፍ ጋንግ እንዳለው 'እግዚአብሔር ያላዘነለት ህዝብ' እንመስላለን።


@Tfanos

5.1k 0 16 22 61

"የማህበረሰብ ኮንትራት"
ሆብስ

ራስህን በዋሻ የሚኖር የጥንት ስው አድርገህ አስበው፡፡ በየለቱ ሚዳቋ በማደንህም ፊትህ በደስታ ተሞልቶ ወደ ልጆችህ እና ወደ ሚስትህ ትመለሳለህ፡፡ ሕይወትህን በእንዲህ አይነት ሁኔታ እየመራህ ሳለ፤ አንድ ቀን በመንገድህ ላይ ካንተ የገዘፈ ሰው ያጋጥምሃል፡፡

"ርቦኛል ካደንካት ሚዳቋ ጥቂት አምጣ" ይልሃል... ትደነግጣለህ፤ ፍዳህን አይተህ ነው ይህቺን ሚዳቋ ያደንካት።
"ለምን?" አልከው፡፡

"አንተን እና ቤተሰቦችህን ከሌላ ጉልበተኞች እጠብቃለሁ አንተም ምግብ ትሰጠኛለህ"

ሆብስ ይህን "#የማህበረሰብ_ኮንትራት" ሲል ይጠራዋል፡፡ አሁን ላይም መንግስት ብለን የምንጠራው ተቋም የተወለደው በዚህ መንገድ ነው፡፡

መንግስታት ከመመስረቱ በፊት ያለው የሰው ልጆች ሕይወት እጅግ አስፈሪ እና አዳጋች ነበር፡፡ ሰውም ከመጥፎነት የሚጋርደው ኃይል ከሌለው እና ያሻውን እንዲያደርግ ከተለቀቀ፣ ለፍቶ ከመብላት መስረቅን ያስቀድማል፡፡

ደህንነቱ ባልተጠበቀ ቦታ ላይ መኖር አስቸጋሪ ነውና፣ ሰዎች እንደ ማህበር የሚጠብቃቸውን እና ከግለሰቦች በላይ ኃይል ያለውን አካል ከመሃላቸው ይሾማሉ፡፡ አዎን መንግስት ካለ፣ ልክ እንደ ሌሎች እንስሳዎች ሁሉ ደስ እንዳለን የመስረቅም ሆነ የመገዳደል ነጻነት አይኖረንም፤ ሆኖም ንብረታችን እና ደህንነታችን እንዲጠበቅ ያደርግልናል። ሆብስ ይህ ነጻነት እና ምቾትን ይሰጠናል ይለናል ለምሳሌ ስራ መስራት ስንፈልግ ቤታችንን ዘግተን መውጣት እንችላለን፤ ለሰራነው ስራም በእርግጠኝነት ደሞዝ እንደምንቀበል እናምናለን፡፡ ይህም እንድናድግ ይረዳናል፡፡

“የማህበረሰብ ኮንትራት” በማህበሩ አካል በሆኑ ሰዎች መሃል የሚፈረም ስምምነት ነው፡፡ በፊርማችንም ከነጻነታችን እንደምንሰጥ ቃል እንገባለን፤ በሰጠነውም ነጻነት ልክ ደህንነትን እና ምቾትን እናገኛለን፡፡ የብዙሃን ድምጽም ከግለሰቦች ድምጽ በላይ ይሰማል።

የመንግስት የህዝብን ደህንነት ማስጠበቅ ከልማት፣ከዲሞክራሲ እና ከሁሉም ጥያቄዎች ቅድሚያ የሚሰጠው መሰረታዊ ጉዳይ ነው።

ሆብስ መንግስት ቢያስከፋንም ትዕዛዙን አልቀበልም ብለን ማመጽ አንችልም ይለናል፡፡ ምክንያቱም ለእኛ ባይመቸን እንኳ ለብዙዎች ልክ ነውና፤ ይህንን ኮንትራት መቅደድ የለብንም፡፡ በአንጻሩ ጆን ሎክ እና ዣን ዣክ ሩሶ ይህን የማህበረሰብ ኮንትራት ቀድሞውኑ መንግስት ካፈረሰው  ህዝቦች አመጻን ማስነሳት አለባቸው ይሉናል፡፡

አንተ እና መንግስትህ ስለምን ነገሮች ተፈራርማችኋል? መቼ ነው መንግስትህ ቃሉን የሚያፈርሰው? መቼስ ነው ማመጽ ያለብህ?

✍️ፍሉይ አለም

@zephilosophy


እኛ ግን ለመላው ጥቁር ሕዝብ ትርክት ቀማሪነት የታጨን ሆነን ሳለን የራሳችን የቤት ሥራ እንኳን ሰርተን ያልጨረስን መሳቂያ የመሆናችን ነገር ያሳዝናል፡፡

ታሪካችንን አላወቅነውም፡፡ መናናቂያ አድርግነዋል፡፡ በታሪክ አጋጣሚ ያገኘነውን በሰው ዘርን ሁሉ ፊት በግርማ ሊያስጠራን የሚችል ዕድል እንደዘበት አምልጦናል፡፡ እናስ ያቆሙን መሰረቶች ምን ያህል ጽኑዓን ነበሩ? እንደ ኅብረተሰብ የአቋራጭ ልክፍተኞች ሆነን ለመገኘታችን ምክንያቱ ምንድን ነው? የምንዋቀሰው፣ የምንናናቀው በድንቁርናችን ልክ አይደለምን? ለፍጥረት ሁሉ ከሚተርፍ በረከት፣ ኅሊና እና ርህራሄ ጋር ተፈጥረን ሳለን ዘመኑን ስላለመዋጀታችን ምክንያቱ ምንድነው?

በሰንደቅ ዓላማ ለሚያስለምን ችጋር ራሳችንን አላጨንምን?
በአለም ላይ ከየትኛው ሀገር ህዝብ በላይ ረሀብ ፣ስድት፣ መፈናቀል፤ የእርስ በርስ ጦርነት አላስተናገድምን?

ደሞስ የሚያስተባብረን አንድ የሆነ ዓይነት ቁጭት ለማግኘት ከነበረን የጥቁር ሕዝብ አለኝታነት ማማ ከመፈጥፈጥ፣ በሰንደቅዓላማ ከመለመን በላይ ሌላ ምን ውርደት ያስፈልገናል?

ያዕቆብ ብርሀኑ

@zephilosophy


አድዋ፦ ሶስተኛው ፍልስፍናዊ  አብዮት !!!!!
**
#Repost


"መሪ አስመሳይና አታላይ መሆን አለበት"
ማኪያቬሊ

ወደ ላይ መውጣት ከፈለግክ የግድ የበታቾችህን መጨፍለቅ ይኖርብሃልን? ስኬት የሚመጣው ሰዎችን በማታለል እና በክፋት ውስጥ ብቻ ነውን? ስለምንድን ነው በአብዛኛው ዘርፍ ላይ ከላይ የሚሆኑ ባለ ስልጣናት ወይም ፖለቲከኞች የእብደት ጠባይ ያላቸው?

የዲፕሎማቱ እና ፈላስፋው ማኪያቬሊ መጽሐፍ የሆነው The Prince ለዚህ መልስ አለው፡፡ ይህ አጭር መጽሐፍ እንዴት አንድ መሪ የራሱን የስልጣን ዘመን ማራዘም እንደሚችል ያሳያል።ምርጥ መሪ ማለት መልካም መሪ የሚል ቀጥተኛ ትርጓሜ የለውም፡፡ ምርጥ መሪ በምንም አይነት መንገድ ስልጣኑን የሚያስጠብቅ መሪ ነው ይለናል። ይህ መሪ ስልጣኑን ለማስጠበቅ ያጭበረብራል፣ ይሰርቃል፣ ህዝቡን ያታልላል።

በመፅሀፍ ውስጥ እነዚህ ሀሳቦች ይንፀባረቃሉ።

1.መሪ ሥነ - ምግባርን አሽቀንጥሮ መጣል
አለበት፡፡

ህዝቡ በከፋበት ዘመን ከመሪ መልካምነት ሊጠበቅ አይገባም ይላል ማኪያቬሊ ።መሪው በባህሪው መጥፎነት ኖሮበት ሣይሆን መጥፎ ህዝብ መጥፎ መሪን ስለሚያመጣ ነው፡፡ ህዝቡ ሥነ ምግባር የጉደለውና ሥርዓት የሚያውቅ ከሆነ በዚህ ሁኔታ አንድ መሪ የራሱን ደህንነት መጠበቅ ግዴታ ውስጥ ይገባል፡፡ ለዚህ ያለው ብቸኛ አማራጭ ኃይልን በመጠቀም ጨካኝነቱን ማሳየት ነው፡፡ ህዝቡ ገልበጥባጣ በመሆኑ መሪ ህዝቡን ማመን የለበትም፤ ህዝቡን ከማመን ይልቅ የራሱን ማንነት እንደሁኔታው እየቀያየረ መኖር ያስፈልገዋል፡፡ በዚህ ሁኔታ ማካቬሌ ፖለቲካን ከሥነ - ምግባር የሚነጥል ፍልስፍናን አቀረበ፡፡

2.መሪ የሐይማኖተኛና የቅድስና ህይወት ሊኖር አይገባም፡፡

ማኪያቬሊ ሲናገር ሐይማኖትን ህዝብ ይከተለው እንጅ መሪ ሊከተለውና ሊኖርበት አይገባም፡፡ መሪ ሐይማኖተኛ ከሆነ ትሑት ይሆናል፤ ትህትና ደግሞ ደካማ ያደርጋል፡፡ መሪ ደካማ ከሆነ በዙሪያው ያሉት ጠላቶቹ ሰለባ ይሆናል::

3. መሪ ለስልጣኑ ሕጋዊነት መጨነቅ የለበትም፡፡

ለማኪያቪሊ ህጋዊ መንግስት የሚያስፈልገው መረጋጋት ባለበት ሀገር ውስጥ ነው፡፡ መረጋጋት ከሌለ ህግም ቢኖር ተግባራዊ አይሆንም፤ ህግ አልባነትንም በህግ መመለስ አይቻልም፡፡ ህግ በጠፋበት ዘመን ህጋዊ ሥርዓት መፍጠር የሚቻለው ጸጥ - ለጥ አድርጐ በጉልበት መግዛት ሲቻል ነው፡፡ “መልካም ህግ ያለመልካም ክንድ ሊኖር ስለማይችል ከህግ ይልቅ የበረታች ክንድን እመርጣለሁ” ይላል ማኪያቬሊ፡፡

"Since there can not be good laws with out good arms, I will not consider laws but speak of arms.”

መጥፎ ህዝብ የመንግስት ቅጣት ስለሚፈራ ሣይወድ በግድ ሥርዓት ይይዛል፤ ስለዚህ መሪ ለመወደድ ከመጣር ይልቅ ለመፈራት ቢጥር የተሻለ ነው፡፡መሪ ይላል ማኪያቬሊ የመንግስትን ሥልጣን ለመያዝ ህጋዊ መንገድ ከመጠበቅ ይልቅ በራሱ ኃይል መተማመን ይገባዋል፡፡
ማኪያቬሊ በዚህ አመለካከቱ የመንግስት ሥልጣንና ህጋዊ ሥርዓት የተሳሰሩበትን ገመድ በጥሶ ጣለው፡፡

4.መሪ አስመሳይና አታላይ መሆን አለበት

ያልተረጋጋን የፖለቲካ ሁኔታ ማለፍ የሚችሉት ተንኮለኛ ሰዎች ናቸው ብሎ ማኪያቬሊ ያምናል፡፡ ተንኮለኛነቱ ለደህንነቱ በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ተንኮለኛነቱ የሚገለፀው ደግሞ ህዝቡን ለማሳሳት አስመሳይ ሁኖ ስለሚቀርብ ነው፡፡ መሪ ጥሩ ሰው ሳይሆን ነገር ግን ጥሩ ሰው መስሎ ህዝቡን መቅረብ አለበት፡፡ በዚህ ጊዜ አስመሳይነቱን ህዝቡ እንዳያውቅበት መጠንቀቅ አለበት፤ ለህዝቡ ሐቀኛ መስሎ ነው መታየት ያለበት፡፡ የህዝቡን ድጋፍ ለማግኘት ደግ መስሎ መታየት፤ ለፍትህ፣ ለእኩልነት፣ ለሰባዊነት የቆመ መስሎ መታየት አለበት፡፡ ነገር ግን በተግባር ከእነዚህ እሴቶች በተቃራኒ ሁኖ መኖር አለበት፡፡ ተቀናቃኞቹንና ደጋፊ መስለው በዙሪያው እየኖሩ ደባ የሚሠሩበትን ምቹ ሁኔታ ባገኘ ቁጥር ያለምንም ርህራሄ ማጥፋት አለበት፡፡ መሪ እንደ ተኩላ የራሱን እኩይነት በማይነቃ መልኩ ሸፍኖ መያዝ አለበት፡፡ ሊያጠቃቸው የሚፈልጋቸውንም የዋህ፣ ደካማና በእነርሱ ላይ ክፋት የማያስብ መስሎ በመታየት ሊያዘናጋቸውና ባላሰቡት ጊዜ ሊያጠቃቸው ይገባል ይለናል፡፡

___
መሪዎቻችን ይህን የማኪያቬሊን ፍልስፍና አብዝተው የሚጠቀሙት ይመስላል የሚያዋጣቸው ይመስላችኋልን?
ተወያዩቡት💬

@zephilosophy

10.5k 0 87 19 111

... ✍ ካለፈው የቀጠለ

የጆን ሎክ የማህበራዊ ውል ስምምነት ቀመር ንድፈ ሀሳብ በዘመናችን ውስጥ የዳበረ ዲሞክራሲያዊ ስርዓትን እያራመዱ ለሚገኙት እንደ አሜሪካና ምእራብ አውሮፓ ላሉ ሀገራት ፈር ቀዳጅ ሆኖ የሚጠቀስ ፍልስፍና እንደሆነና የዘመናዊ ሊበራል ዲሞክራሲ ርዕዮተ ዓለም ጠንሳሽ እንደሆነም ተንታኞች ይናገራሉ፡፡

እንደ ታዋቂ የፖለቲካ ተንታኝ ሀሮልድ ላስኪ (Harold Laski) አገላለጽ ‹‹የጆን ሎክ ንድፈ ሀሳብ በእንግሊዝ የፖለቲካ ታሪክ ሙስጥ ቋሚ አሻራ ትቶ ያለፈ በዚህ ላይ ደግሞ በአሜሪካ ፓለቲካ ስርዓት ጠንሳሾች ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ ከማሳደሩም በላይ የአሜሪካ ህገ መንግስት የተወሰኑ አንቀጾች ቃል በቃል ከእርሱ ስራዎች የተገለበጡ ናቸው›› በማለት ይናገራል፡፡

ቀጥለን የምናየው ከ1712-1778 ድረስ የኖረውን ፈረንሳዊ ፈሳስፋ ጂን ጃኩስ ሩሶ (Jean Jacques Rousseau) ን ሲሆን ይህም ፈስስፋ ከቶማስ ሆብስና ጆን ሎክ ቀጥሎ ከመንግስት ስርዓት ጋር በተያያዘ ለሚነሱ ፍልስፍናዊ የመከራከሪያ ሀሳቦች ከፍተኛ ተጽእኖ ያሳደረ እንደነበርም ይነገርለታል፡፡ ታዲያ ይህ ፈላስፋ በስራዎቹ ታሪክ የማይረሳቸውን የ1789ኙን የፈረንሳይ አብዮት በማነሳሳትና የህዝባዊ ሉአላዊነት ንድፈ ሀሳብ (the theory of popular soveneity ) በማመንጨት ጉልህ ሚና የተጫወተ ሰው ነው፡፡

ጂን ጃኩየስ ሩሶ እንደ ሎክ 'የሰው ልጅ በተፈጥርው ቅንና ሩህሩህ መሆኑን› ቢያምንም ነገር ግን እነዚህ መልካም ባህሪያት በግል ሀብት መፈጠርና በህዝብ ቁጥር መጨመር ምክንያት ሰውን ራስ ወዳድ እንዲሆንና በሌሎች ዘንድም ገዝፎ ለመታየት አንዲጥር ያደርገዋል፡፡ ይህ ደግሞ አላስፈላጊ ወደ ሆነ የርስ በርስ ፉክክር ውስጥ ተገብቶ ሰላም እንዲደፈርስና መሰረቱም አንዲናጋ ጉልህ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ እናም የማህበረሰቡን ሰላምና መረጋጋት ለማስከበር ሰዎች በስምምነት ማህበራዊ ውል ስምምነት ቀመር ኖሯቸው አንድ የፖለቲካ ተቋም መመስረት
እንደሚገባቸው ይገልጻል፡፡

የሩሶ የማህበራዊ ውል ስምምነት ንድፈ ሀሳብ ከቶማስ ሆብስ ጋር ተመሳሳይ የሚያደርገው ሰዎች ለሚያቋቁሙት የበላይ አካል ነጻነታቸውን አሳልፈው መስጠት እንደሚገባቸው ማመኑ ሲሆን በአንጻሩ ‹‹ከፍተኛ ስልጣን የሚይዘው ህብረተሰቡ ነው›› የሚለው ሀሳቡ ከጆን ሎክ ጋር ቁርኝት እንዲኖረው ያደርገዋል፡፡ .

አንዳንዶች የሩሶ የበላይ ተቋም (higher institution) አወቃቀርና አደረጃጀት ወጥነት የጎደለውና ብዥታን የሚፈጥር (para- doxical) ነው ሲሱ ይተቹታል፡፡ ስአብነት ያህል እስቲ the general will የሚለውን ሀሳብ ለመረዳት እንሞክር፡፡

እንደ ሩሶ እምነት በማንኛውም ህብረተሰብ ዘንድ ሁለት ፍላጎቶች ይንጸባረቃሉ፡፡ ከነዚህም አንደኛው በህብረተሰቡ ያለ ልዩነት በጋራ የሚስማሙባቸውና የሚፈቅዱአቸው ፍላጎቶች (the will of all ) ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ከጋራ ፍላጎቶች ጋር የማይስማሙ የእያንዳንዱ ሰው ግላዊ ፈቃድ ድምር (the general will) የሚባለው ነው፡፡ ታዲያ የአንድ ህብረተሰብ የጋራ ደህንነት (common good) ሊረጋገጥ የሚችለው የእያንዳንዱን ልዩነት በማጥበብ ለጋራ አላማ የሚል ስራ በመስራትና ለውጥ ለማምጣት በመታገል መሆን እንዳለበት ያስገነዝባል፡፡ ይህም የሚሆነው የሚመሰረተው ተቋም በግለሰቦች ልዩነት ድምር ላይ የተገነባ ስራ ሲሰራ ይሆናል፡፡

የሩሶ የማህበራዊ ውል ስምምነት ቀመር ሁለት አበይት አደረጃጀት ሲኖረው አንደኛው ሰዎች ነጻነታቸውን ሙሉ ለሙሉ አሳልፈው በመስጠት የሚያቋቁሙት ማህበራዊ ተቋም (community based institution) ሲሆን ሁለተኛ ለዚህ ማህበራዊ ተቋም ተጠሪ ሆኖ የሚያገለግለው አካል መንግስት (government) ይሆናል፡፡ በነዚህ አደረጃጀቶች ውስጥ የህዝብ ስልጣን ከፍተኛና ፍጹም ስለሆነ በማንኛውም መልኩ ሊነጣጠስ ሊከፋፈል፣ ሊገረሰስ እንዲሁም ሊወድቅ አይችልም፡፡

የሩሶ የማህበረሰብ ስልጣን ልክ እንደ ሆብስ ምሉዕ በመሆኑ ለግለሰብ ቅሬታዎችና ፍላጎቶች ቦታ የማይሰጥ ነው፡፡ ምክንያቱም እንደ ሩሶ ግንዛቤ ይህ አካል ህብረተሰቡ በጋራ የተስማማበትና የመምራት ነፃነቱንም ሙሉ ለሙሉ የሰው አካል በመሆኑ የሁሉንም ሰው ፍላጎት የማንጸባረቅ ውስጣዊ (በውስጠ ታዋቂነት) ስምምነት እንዳለው ስለሚቆጠር ነው፡፡ የዚህ ማህበረሰባዊ ስልጣን ከፍተኛው አካል ህግ አውጪ (legislative body) ሲሆን እያንዳንዱ የመንግስት ተግባራትና ክንውኖች በህግ የተገደቡ በመሆናቸው ለህዝቡ ሰላምና መረጋጋት በመፍጠር በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ፡፡ ... ይላል ሩሶ

ታዲያ የጆን ሎክ ፖለቲካዊ ፍልስፍና በአሜሪካ ህገ መንግስት (American Constitution) ተጨባጭ መነሻ እንደሆነ ሁሉ የሩሶም ማህበራዊ ዉል ስምምነት ቀመር ደግሞ ለፈረንሳይ ህገ መንግስት መሰረት ከመሆኑም ከላይ ከሩሶ ፍልስፍናዊ እሳቤዎች በቀጥታ የተወሰዱ አንቀጾችም ይገኙበታል፡፡

እኛም መንግስታችን የቱ ይሁን? ብለን እንጠይቅ....

ምላሹን በልባችን እናሳድር!!

@zephilosophy
@zephilosophy


የሰው ልጅ በተፈጥሮው ስግብግብና ራስ ወዳድ በመሆኑ ቆፍጠን ያለ መሪ ያስፈልገዋል

ምንጭ ፦ ፍልስፍናና ዘላለማዊ ጥያቄዎቹ
ፀሀፊ፦ ቤተልሔም ለገሰ

ፍልስፍና ከሚያነሳቸው አበይት ጉዳዮች አንዱ ፖለቲካ ነው፡፡ ፖለቲካን ስናነሳ ደግሞ አስቀድመን ከምንጠይቃቸው ጥያቄዎች መካከል ‹‹አንድ ሀገር ብሎም መንግስት እንዴት ተመሰረተ? መንግስት ከመኖሩ በፊት ሰዎች እንዴት ይኖሩ ነበር? አኗኗራቸውስ ፍትሀዊ ነበርን? የመንግስት መቋቋም ለማህበረሰቡ ምን ፋይዳ አስው? የሚሉና የመሳሰሉት ይገኙበታሉ፡፡ እኛም የአንደ ሀገር መገለጫ ከሆኑት ውስጥ ዋነኛ ሚና ስለሚጫወተው መንግስት (goverment) የዚህንም ተቋም ምንነትና ስለ አጀማመሩ የተሰነዘሩ ፍልስፍናዊ መከራከሪያ ሀሳቦችን እያየን እንዘልቃለን ...

አንዲት ሀገር በመንግስት እንድትተዳደር መነሻ ሀሳብ የሆነው የማህበራዊ ውል ስምምነት ቀመር (social contract theory) ሲሆን ይህም ውል 'መንግስት ከመፈጠሩ በፊት ሰዎች ይኖሩበት የነበረው የተፈጥሮ ስርዓት አስተማማኝና ዘላቂ የሆነ ሰላምና መረጋጋትን ማረጋገጥ ስለማይቻል የበላይ አካል መፈጠር አለበት› ከሚል ሀሳብ የመነጨ እንደሆነ ተንታኞች ይናገራሉ፡፡ ታዲያ በዚህ ዙሪያ የተለያዩ ፍልስፍናዊ መከራከሪያ ሀሳቦች ሲያቀርቡ ከነበሩት መካከል ዋነኞቹ ቶማስ ሆብስ (Thomas Hobbes) ጆን ሎክ (john locke) እና ሩሶ (Rousseau) ይገኙበታል። እስኪ የነዚህን ፈላስፎች ሀሳብ በዝርዝር እንመልከት. ..

ቶማስ ሆብስ እ.አ.አ ከ1599-1679 ይኖር የነበረ እንግሊዛዊ ፈላስፋ ሲሆን በእርሱ ዘመን ተከስቶ የነበረው የእንግሊዝ እርስ በርስ ጦርነት በስራዎቹ ላይ ተጽእኖ እንዳሳደረ ይታመናል፡፡ እናም ይህ ጦርነት የቱን ያህል ስጋት ላይ እንደጣለው ለመግለጽ በአንድ ወቅት ‹‹እኔና ፍርሀት መንታ ሆነን ተፈጠርን›› ( I and fear were born twins) ሲል ተናግሯል፡፡

ሆብስ የማህበራዊ ውል ስምምነት ቀመር እንዲፈጠር አስተዋጽኦ ያደረገው 'የሰው ተፈጥሮዊ ባህሪይ' እንደሆነ ይናገራል፡፡ እንደሱ አባባል ‹‹አብዛኛው ሰው የሚመራው ነገሮችን እያሰበና እያገናዘበ ሳይሆን ይልቁንም በስሜትና በራስ ወዳድነት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ሰዎችን በፍርሀትና በጦርነት ስጋት ውስጥ እንዲዘፈቁ ያደርጋል፡፡ ስለዚህም ሰዎች አንድ ወጥ የሆነ የማህበራዊ ውል ስምምነት ኖሯቸው ጠንካራ መንግስት ካላቋቋሙ በስተቀር የአበዛኛው ሰው ቅጥ የለሽ ስግብግብ ባህሪይና ዝና ወዳድነት የለት ተዕለት ኑሮውን በአስተማማኝ ሁኔታ መምራት እንዳይችልና ህይወቱም ፍጹም አስቀያሚና ጭካኔ የተሞላ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡››

‹‹መንግስት›› የሚባለው ተቋም የመኖሩ አስፈላጊነትና ፋይዳ ይህ ከሆነ ዘንድ፣ የዚህ መንግስት የሚባል ተቋም ስልጣኑ አስከምን ድረስ ነው? ለሚለው ጥያቄ ሆብስ፤ ሰዎች ለሚመሰርቱት መንግስታዊ ተቋም ተፈጥሮአዊ መብቶቻቸውን ሙሉ በሙሱ አሳልፈው መስጠት እንደሚገባቸውና ይህ የመረጡት አካል ከሁሉም በላይ ፈላጭ ቆራጭ ሆኖ ማዘዝ እንደሚገባው ብሎም ስልጣኑ ገደብ የለሽ መሆን እንዳለበት ያስረዳል፡፡ በዚህም እ.አ.አ በ1651 ለህትመት ያበቃውና በባህር እንስሳት ገዢ የተሰየመው 'ዘ ሴቪያታን› የተሰኘው መጽሀፍ ሆብስ ስሰው ልጅ ያለውን ጨለምተኛ አስተሳሰብ ያሳበቀበትና በብዙ ፖለቲካ ተንታኞች ዘንድም ፍጹማዊ ፈላጭ ቆራጭ አገዛዝ ስርዓት አቀንቃኝ' ተብሎ እንዲታማም አድርጎታል፡፡

በአንጻሩ እ.አ.አ ከ1632-1704 የኖረውና ለዘመናዊ የፖለቲካ ስርዓት መፈጠር ፈር ቀዳጅ እንደሆነ የሚነገርለት አንግሊዛዊ ፈላስፋ ጆን ሎክ እንደ ሆብስ ለሰው ልጅ ያለው አመለካከት ጨለምተኛ ሳይሆን የሰው ልጅ በተፈጥሮው ደግና ሩህሩህ እንዲሁም በጎና ቅን አሳቢ እንደሆነ ያምናል፡ ፡ እንደሱም አባባል ሰዎች መንግስት ባልነበረበትና በተፈጥሮ ስርዓተ ህግ ስር በሚተዳደሩበት ወቅት በነጻነትና በራሳቸው ፍላጎት የመመራት መብት ስለ ነበራቸው የሌላውን ሰው ህይወትም ሆነ ንብረት አደጋ ላይ የሚጥል ድርጊት ፈጽሞ አያደርጉም፡፡ ‹‹ነገር ግን . . ›› ይላል ሎክ ‹‹ . ነገር ግን ማንም አብዛኛው ሰው ነገሮችን በማመዛዘን የሚኖር ፍጡር ቢሆንም አልፎ አልፎ የሚከሰቱ ሁኔታዎች ሰውን ወደ ጸብ አጫሪነት ሊያመሩት ይችላሉ፡፡ ስለሆነም የሰው ልጅ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላሙን ለማረጋገጥ እንዲያስችለው ተፈጥሮ የቸረችውን ነጻነቱን በመስጠት ማህበራዊ ውል ስምምነት እንዲፈጽም ማህበራዊ ተቋም (social institution) እንዲመሰርቱ ይመክራል፡፡

ሎክ ሀሳቡን ሲቀጥልም ‹‹በማህበራዊ ውል ስምምነት የሚመሰረተው ማህበራዊ ተቋም (መንግስት) ውስን የሆነ ስልጣን አንዳለውና ይህም ተቋም በህግ የበላይነት ስር የሚተዳደር እንደሆነ በዜጎች መሰረታዊ መብቶች ውስጥም ጣልቃ መግባት እንደሌለበት ... የዜጎችን መብት የሚሸራርፍ ድርጊቶችን ቢፈጽም ህዝቡ የሰጠውን ስልጣን የመገፈፍ መብት እንዳለው ይናገራል፡፡ ታዲያ የዚህ ታላቅ ስልጣን ባለቤት ሊሆን የሚችለው በህዝቡ ይሁንታ የተመረጡ ሰዎች የሚያቋቁሙት የህገ አዉጪ አካል ሲሆን ተጠሪነቱም በቀጥታ ለህዝቡ እንደሆነ አፅንዖት ሰጥቶ ይናገራል፡፡

✍ ይቀጥላል✍

@zephilosophy
@zephilosophy


የሜታፊዚክስ ፍልስፍና ሙግቶች
.....የቀጠለ
4.esse est percibi -በርክሌይ

በርክሌ esse est percipi የሚል ፍልስፍናዊ ሀረግ አለው ሃረጉ የተፈጠረው ከላቲን ቃላት ሲሆን፣ ትርጓሜውም “መሆን ማለት ማስተዋል" ነው፡፡ ወንበር በውኑ ዓለም ላይ ያለ ነገር ለመሆን የግድ የሚያስተውለው አካል ያስፈልገዋል፡፡ የሚዳስሰው አልያም የሚመለከተው ሰው ከሌለ ወንበሩ አንችልም፡፡ በጫካ ውስጥ የወደቀው ዛፍ ሰሚ ከሌለው ድምጽ አያሰማም፣ ጓደኛህም አንተ ካላየኸው ወይም ካልነካኸው በውኑ ዓለም አለ ማለት  አንችልም።

የእውኑ ዓለምም የሚፈልቀው ከአንተ አእምሮ በመነሳት ነው፡፡ ህንጻዎችን  ስትመለከት፣ የአበባ መዓዛን ስትምግ፣ ትኩስ ቡና ምላስህን ሲያቃጥለው እነዚህ ሁሉ በአእምሮህ ያሉ የውኑ ዓለም መገለጫዎች ናቸው፡፡ የውኑ ዓለምም የሚያየው (የሚያስተውለው) አካል ሳይኖር ሲቀር መኖሩ ያበቃለታል፡፡

ሆኖም ግን ሰው (ወይም ሌላ አስተዋይ) በማይደርስበት በረሃ ላይም እኮ ዛፎች፣ ተራሮች፣ ድንጋዮች አሉ ይህ ስለምን ሆነ? ለምንስ እነርሱም አልተሰወሩም፡፡
የባርክሌ ምላሽ ቀላል እና አጭር ነው፤

“እግዚአብሔር አለ!” ተመልካች በሌለበት ሁሉ፣ በአጽናፈ አለሙ በሙሉ እግዚአብሔር ተመልካች ነው፡፡  ለዛም ነው የተከልናት አበባ ወደ ቤታችን እስክንመለስ ድረስ ሳትሰወር የምትጠብቀን፤ ለዚህም ነው በጥቅጥቅ ደን መሃል የወደቀ ዛፍ ድምጽ የሚያሰማው፡፡

5.ቅዱሱ አባትችን -ፍሮይድ

እድሜያችን ምንም ያህል ቢሆን እንኳን በውስጣችን ልጅነት አለ፡፡ ሁሌም ቢሆን እንፈራለን፤ ሁሌም ቢሆን ከችግር የሚያወጣን አልያም እጃችንን ይዞ ጨለማውን የሚያሻግረን አባት እንፈልጋለን፡፡ ህግ አልባ በመሰለችን ዓለም ላይ ነጋችን ምን እንደሚሆን አናውቅምና “አይዞህ አትፍራ እኔ አለሁ” የሚለን አባት ከጎናችን እንዲኖር እንፈልጋለን፡፡

በአለማችን ላይ ስሙ የገነነው  ኦስትሪያዊው ኒሮሎጂስት ሲግመንድ ፍሮይድ- ይህ ነው ሰዎች የማይታይ፣ የማይጨበጥ አባት እንዲፈጥሩ ያስገደዳቸው ይለናል፡፡ ሁሉን ቻይ፣ ሁሉን አድራጊ፣ ደስ ባለን ጊዜ የምንጨቀጭቀው ልክ እንደ አባታችን የሆነ አምላክ - እግዚአብሔር።
ፍሮይድ ሁላችንም በህጻንነታችን ደካማ እና እርዳታ ፈላጊ ነበርን ይለናል፡፡ እርዳታም ባስፈለገን ቁጥር ወደ ወላጅ አባታችን እንሄዳለን፤ ሆኖም እያደግን ስንመጣ አባታችን እንደኛ ከፍጹምነት የጎደለ ፍጡር እንደሆነ እና ሁሉንም ፍላጎቶቻችንን ሊያሟላልን እንደማይችል
እንረዳለን፡፡ ነገር ግን ሁሌም ቢሆን ከአደጋ የሚጠብቀን አካል እንዲኖር እንፈልጋለን፡፡

የሰው ልጅ ተፈጥሮ ሲከፋበት፤ ልክ አባቱን እርዳኝ እንደሚለው ሁሉ ፈጣሪውን ይማጸናል፡፡ ልክ በመኪና መንገድ ላይ እጃችንን ይዞ መንገድ እንደሚያሻግረን ወላጅ አባታችን ሁሉ፣ ይህ ፈጣሪ በጨለማ ጊዜያቶቻችን ላይ እጃችንን ይዞ ያሻግረናል፤ ፈጣሪ ለመልካምነታችንም ከረሜላ (ገነትን) ይሸልመናል፤ ስናጠፋም በቀበቶው ይገርፈናል (ወደ ሲኦል ይዶለናል)

ኃይማኖት ከጥንት ጀምሮ የሰዎችን ምኞት ሲያሳካ ቆይቷል። ደካማነታችን ከምንም፣ ከማንም በላይ ሃያል የሆነ አባትን እንድንፈጥር አደረገን፡፡' ኃይማኖት ለሰው ልጆች የሞት ፍርሃትን አስወገደላቸው፤ ነገውን ለማያውቅ ሰውም ሁሉ ነገሩን በአምላኩ ላይ እንዲጥል አስቻለው፤ መልካም በማድረጉም ይሸለማልና መልካምነትን ወደደ፤ ቢያጠፋም  በዘላለም እሳት ይቃጠላልና ከእኩይነት ሸሸ፡፡ ለራሱም፤ ሁሉም ነገር ጥሩ ይሆናል... በታላቁ አባትህ እጅ ነህና! "አለው::

6.Abductive reasoning
ፔሊ

በአስራ ስምንተኛው ክፍለ ዘመን የነበረ ዊልያም ፔሊ የሚባል አንድ ቄስ የእግዚአብሔርን መኖር ወይም ሃልወተ እግዚአብሔርን ሊያረጋግጥልን የሚችል ሙግት አነሳ፡፡ ሙግቱም teleological argument ይሰኛል። በእርሱ ሙግትም በጫካ ውስጥ ሲጓዝ ሰዓት ወድቆ ያገኘ ሰው በእርግጠኛነት ሰዓቱ ሰሪ እንዳለው ያውቃል። ሰዓቱም እንዲሁ በዘፈቀደ ንፋስ በሰበሰባቸው ብረቶች አልተሰራም፡፡ እናስ ለዚህ ተራ ሰዓት እንኳ ፈጣሪ ካለው፣ እንዴት ውስብስብ ተደርጎ የተሰራን ሁለንተና (ዩኒቨርስ) ፈጣሪ የለውም እንላለን?

የስው ልጅ ልብ ሳያቋርጥ በደቂቃ ደም እየመጠነ ይረጫል፤ ሳንባው ለሰከንድ እንኳ ሳያቋርጥ አየር ያስገባል አየር ያስወጣል፤ አይኖቹ በዓለም ላይ ካሉ ካሜራዎች ሁሉ በብዙ እጥፍ ምስልን ይቀርጻሉ እናስ ይህ ከእጅ ሰዓት በላይ የተወሳሰበን ፍጡር የአጋጣሚ ሂደት ፈጠረውን?

ከሰው ጀምረን እስከ ሁለንተና ድረስ ተፈጥሮን እየተነተንናት ብንጓዝ ልክ ገዢ እንዳላት ሁሉ፣ በህግ እና በስርዓት ስትመራ እንመለከታታለን፡፡ ተፈጥሮ ከቅንጣት ጀምሮ እስከ ግዙፍ ከዋክብት ድረስ ያሉ ውስብስብ ሰዓቶችን ይዛለች።

እናም የፔሊ ጥያቄም ይህ ነው - ሰዓትን ለመፍጠር ሰዓት ሰሪ ካስፈለገ፣ ስለምን ተፈጥሮስ ንድፍ አውጪ የላትም?

ይህ የቴሎሎጂካል ሙግት abductive reasoning ወይም ጠላፊ የምክንያት ሂደት ይባላል፡፡ ይህም የነገሩን መጨረሻ በማየት ብቻ መጀመሪያውን ለመገመት ያስችለናል፡፡ ለምሳሌ በግማሽ ነዶ ያለቀ ሲጋራ በመንገድ ላይ ቢያጋጥመን፣ ሲጋራውን ሲያጨሰው የነበረ ሰው እንዳለ መገመት እንችላለን፡፡

በተመሳሳይ ሂደትም የቴሎሎጂካል ሙግትም- የምናየውን የተወሳሰበ ዓለም የፈጠረ እና ዓለም ሁሉ በህገ ተፈጥሮ እንዲመራ ያደረገ አካል አለ፤ እርሱም እግዚአብሔር ነው ይለናል።

@zephilosophy


የሜታፊዚክስ ፍልስፍና ሙግቶች

የሰው ልጅ ለዘመናት መልስ አልባ እንቆቅልሾችን ለመመለስ ሞክሯል። ገደብ አልባ ስለሆነው ሁለንተና ገደብ ባለው አእምሮ አሰላስሏል። ከጥያቄዎቹም አንዱ የሆነው ማን ፈጠረን? የሚለው ነው፡፡ ይህ ሁሉ ዓለም ከምን ጀምሮ እዚህ ደረሰ? በተለያየ ዘመን ከተለያየ ቦታ የተነሱ የስድስት ፈላስፎች ሙግት እናያለን
ሶስቱ የአምለክን መኖር በአመክንዮ አስረግጠው ሲያስረዱ
ሶስቱ ደግሞ የሰው ልጅ ስነ ልቦናዊ ወይም ፓለቲካዊ በሆነ ምክንያት አምላኩን ፈጠረ ብለው ይሞግታሉ እስቲ አንድ በአንድ እንያቸው።

1.Cosmological argument - አል ኬንዲ

ሁሉም ነገር በሆነ ጊዜ ላይ የሆነ ቦታ ይጀምራል፡፡ ሁሉም ነገሮችም ለመከሰታቸው መንስኤ የሆነ አካል አላቸው፡፡ የምትንከባለል ኳስን በማየት ብቻ መጀመሪያውኑ ከቆመችበት እንድትንቀሳቀስ ያደረጋት እና የጠለዛት ሰው እንዳለ ማወቅ እንችላለን፡፡
ይህ ቀላል የሆነ ለነገሮች ያለን እይታ፣ የእግዚአብሔርን ሃለዎት ወይም የፈጣሪ መኖርን ለማስረዳት ከሚቀርቡ ሃሳቦች አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ የሙግቱ ስያሜም Cosmological argument ይሰኛል፡፡ የሙግቱ መነሻ ጥንታዊቷ ግሪክ ብትሆንም፣ የአስራ ዘጠነኛው ክፍለ ዘመን ኢስላማዊ ፈላስፋ የሆነው አል ኬንዲ በቀላል ቋንቋ አስቀምጦልናል፡፡ አመክንዮው ቀላል ነው።
A.ነገር ሁሉ ለመከሰት የግድ መነሻ አለው
B.ሁለተንተና ተከስቷል

2.ሰው በአምሳሉ አምላኩን ፈጠረ-ፎየር ባክ

ሰዎች ይታመማሉ፣ ይፈራሉ፣ ይወድቃሉ፣ ይሞታሉ... እናም ከዚህ ሁሉ መከራ የሚያስጥላቸውን መሸሸጊያ ፈጠሩ፡፡ የዓለምን ስቃይ በራሳቸው አቅም ማምለጥ አይችሉምና ከስቃይ የሚያተርፋቸውን ፍጹማዊ አምላክ በአምሳላቸው ሰሩ፡፡ ይህንን አምላክ ልክ እንደ ራሳቸው አካል ይቆጥሩታል፤ ልክ እጃቸው እንደሆነ ሁሉ ያጎርሰናል ብለው ያስባሉ፤ ልክ እግራቸው እንደሆነ ሁሉ ያሻግረናል ይላሉ።
_
“በሞት ጥላ መካከል እንኳ ብሄድ አንተ ከእኔ ጋር ነህና ክፉን አልፈራም፤ በትርህና በትርህና ምርኵዝህ እነርሱ ያጽናኑኛል” እንዳለው  መዝሙረኛው ዳዊት፣ አምላክ የሰዎችን ጉድለት ሊሞላ ተፈጠረ  ይለናል ፎየርባክ፡፡

3.የህዝቦች ማደንዘዣ- ማርክስ

ማርክስ ኃይማኖት በገዢዎች (ቡርዥዋ) የተፈጠረ እና ሰራተኛው በእነርሱ ላይ እንዳያምጽ ማድረጊያ መሳሪያ ነው ይለናል፡፡

ኃይማኖት ይህን የሚያደርገው በሁለት አይነት መንገዶች ነው። አንደኛው ለምስኪን፣ ደሃዎች ወይም መልካም ለሆኑ ሰዎች እንደ ሽልማት ዘላለማዊ ገነትን በማቅረብ ሲሆን፣ በአንጻሩ ከህግ ወጥተው ለሚያምጹ እና መጥፎ ለሚያደርጉ ደግሞ ዘላለማዊ ቅጣት ይጠብቃቸዋል።

ሁለተኛው ፤ኃይማኖት እንደ እጽ ማደንዘዣ ነው ይለናል ማርክስ ፤ ልክ እንደ ኦፒየም አብዛኛውን የማህበረሰብ ክፍል ያደነዝዘዋል። በችግር ውስጥ እንኳ ቢሆን ደስተኛ እንደሆነ ያስባል፤ ህመሙም አይሰማውም... ደንዝዟልና፡፡ ከልባቸው መዝሙርን ይዘምራሉ፣ በደስታ ውስጥ ሆነው ይጸልያሉ... ይህም ጥያቄ ማንሻ ጊዜ እንዳይኖራቸው ያደርጋል፡፡ የዓለምን ኢ-ፍትሃዊነትንም የአምላካቸው እቅድ አካል አድርገው በደስታ ይቀበሉታል፡፡ ዓለም ምን ብትከፋቸው፣ ፍርዱን ለፈጣሪ ይተዋሉ እንጂ በገዢዎች ላይ አያምጹም፡፡

@zephilosophy


ሃልወተ እግዚአብሔር & The problem of evil

አምላክ እንደ ሆንክ አስብ፡፡ አለማትን ሁሉ ፈጠርክ። እናም ፈጥረህ ስትጨርስ የእጅህን አቧራ አራግፈህ ገሸሽ አልክ፤ ሁሉንም ፍትህን ለመመልከት በሚያስችልህም ሰባተኛ ሰማይ ላይ መኖሪያህን አዘጋጀህ። የፈጠርከው ዓለም ውብ ነው፤ እልፍ አእላፍ ከዋክብቶችንም በውስጡ ይዟል፤ ከፈጠርካቸው አለማትም በአንዷ ላይ፣ ላባ እና መንቁር አልባ የሆነ በሁለት እግር የሚጓዝ ፍጡር አለባት... ነገር ሁሉ መልካም እንደሆነም አየህ፡፡

ጎንህን ለማሳረፍም ጭልጥ ያለ እንቅልፍ ውስጥ ገባህ። ሆኖም በመሃል የፈጠርካቸው ፍጡራን በጫጫታቸው ቀሰቀሱህ። አስታወስክ እነዚያ በሁለት እግር ሂያጅ ፍጡራን... እርስ በእርስ እየተገዳደሉ ነው፤ ከፊሎቹም ምግብ እያሉ ወዳንተ ያለቅሳሉ፤ ሌሎች በህመም ይሰቃያሉ...

አሁን ላይ አንተ ምን ታደርግላቸዋለህ? ማንስ ነው ለዚህ ሁሉ መከራ ተጠያቂ የሚሆነው?

ይህ ጥያቄ “problem of evil” ተብሎ ይጠራል፡፡ በዓለም ሁሉ ስለምን መጥፎ ነገሮች ኖሩ?
ስኮትላንዳዊው ፈላስፋ ዴቪድ ሂዩም
  በአምላኩ ላይ ጥያቄን ያነሳል ፦

አምላክ ሁሉን ቻይ (omnipotent)፣
ሁሉን አዋቂ (omniscient) እና
ፍጹም መልካም(omnibenevolent) ነውን?

ስለምንስ መከራችንን ሳያይ ቀረ፣ ይህ ሁሉ ስቃይስ በእኛ ላይ ሲሆን እርሱ የት ነበር? ሲል ይጠይቃል።

ፍጹም መልካም፣ ሁሉን ወዳጅ የሆነ አምላክ እንዴት አይሁዶች በእሳት እንዲጠበሱ ፈቀደ? ስለምን ህጻናት በርሃብ እንዲሞቱ ሆኑ? ደካማው ሚዳቋ ስለምን ለበረታው አንበሳ ምግብ እንዲሆን ተፈረደበት?

ምናልባት ሁሉን ቻይ ሳይሆን ቀርቶ ይሆን? መርዳት እየፈለገ ሆኖም አቅሙ ስለሌለው ነው እጁን ያልዘረጋው?

ምናልባትም አላወቀም ይሆናል? ሁሉን አዋቂ ካልሆነ ልንፈርድበት አይገባም፡፡
ሆኖም ግን ይህን አምላክ ፍጹም መልካም፣ ሁሉን ቻይ እና ፍጹም አዋቂ ነው ብለን ማለት አንችልም፡፡
በተመሳሳይ ጊዜ ሶስቱንም መሆን አይችልም፡፡ ከሶስቱ ባህርያቱ ቢያንስ አንዱን ልንቀማው ይገባል፡፡

በመከራችን አልረዳንምና ለመከራችን ተጠያቂውም እርሱ ይሆናል። የሚጠብቀን አንቀላፍቶ ይሆን?

ሁለት አይነት ክፋቶች በዓለም ላይ አሉ - ምድራዊ እና ተፈጥሯዊ (ለምሳሌ፤ የመሬት መንቀጥቀጥ፣ ድርቅ፣ ወረርሽኝ እና ወዘተ) እና ሰዋዊ  (መገዳደል፣ ውሸት፣ መስረቅ እና ወዘተ)
ሁለቱም ክፋቶች ጥያቄን ያስነሳሉ፡፡

የመጀመሪያው ማን ነው ዓለምን ከነችግሮቿ የፈጠራት የሚል ጥያቄን ያስነሳል። ሁለተኛው ሰዎች ክፋት እንዲያደርጉ የፈቀደላቸው ማን ነው? የሚል ጥያቄን ያስነሳል፡፡

ለዚህ ጥያቄ መልስ ለመስጠት አስቸጋሪ የሚያደርገው በኃይማኖተኞች ዘንድ የተሳለው አምላክ ሃያል መሆኑ ነው። አምላክ የፈለገውን እንደፈለገው ቢፈጽም የሚጠይቀው አካል መኖር የለበትም ምክንያቱም እርሱ ሃያል ነው።

በኃይማኖተኞች ዘንድ ለ “problem of evil” የተሰጡ ምላሾች አሉ። ምላሾቹም ቲዮዲሲ ተብለው ይጠራሉ።
ሶስት አይነት መልሶችንም ያቀርቡልናል፡፡

⭐️የመጀመሪያው የሰው ልጅ ክፋትን እንዲሰራ ነጻ ፍቃድ አለው የሚል ይሆናል። ሰው እሳት እና ፍትፍት ከፊቱ ቀርቦለታል፤ መልካሙን ወይም መጥፎውን የመምረጥ ድርሻውም የእርሱ ነው ይሉናል፡፡

⭐️ሁለተኛው፤ እኛ ማን ነን ይህ ክፉ ነው፣ ይህ ደግሞ መጥፎ ነው ብለን የምንሰይመው? ለምሳሌ እሳተ ገሞራ በተፈጥሮው መጥፎ ይመስላል፤ የብዙ አራዊቶችንም ሕይወት ሊቀጥፍ ይችላል፤ ሆኖም እሳተ ገሞራ በመኖሩ ምክንያት ነው ተራራዎች የተፈጠሩት ተራሮችም ለደኖች፣ ወንዞች እና ሌሎችም መፈጠር ምክንያት ናቸው፡፡ እናም መልካም እና መጥፎ የሆነውን የሚለይልን አምላካችን እንጂ እኛ አይደለንም፡፡

⭐️ሶስተኛው ሁሉም ነገር የፈጣሪ እቅድ አካል ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ህጻን በርሃብ ሲሞት ምናልባትም ወደ ዘላለማዊ ማር እና ወተት ወደሚፈስባት ዓለም እየተጓዘ ይሆናል። የእርሱንም እቅድ መጨረሻ አናውቅምና ይህ መልካም ነው፣ ይህ መጥፎ ነው ማለት አንችልም፡ በሕይወትህ መጥፎ አጋጣሚዎች ተከስተውብህ የሆኑት ለበጎ ነው እንኳንም ሆኑ ብለህ አታውቅም? ምናልባትም ይህም የእርሱ
እቅድ አካል ይሆናል፡፡

ምንጭ -ፍልስፍና ከዘርዓ ያዕቆብ-ሶቅራጠስ
ፁሁፍ -ፍሉይ አለም

በኃይማኖተኞች ዘንድ ለ “problem of evil” የተሰጡ ምላሾች በቂ ናቸው ብላችሁ ታስባለችሁ ?ከነዚህ ውጪስ ሌሎች ምላሾች የሉም ይሁን?
ግሩፕ ላይ ተወያዩበት
👇👇👇
https://t.me/+XgPfefgVVvRhZjk0


«አብዛኛው የሰው ልጅ የሚከተላቸው እምነቶችና በእምነቱ ውስጥ የሚፈፅማቸው ድርጊቶች መነሻቸው  ልማድ ነው። እምነት በዕውቀት መገለጥን ካልያዘ የሚጠይቀውም ሆነ ምላሽ የሚያገኝለት ጥያቄ ስለማይኖር ሌሎች ስለሚያደርጉት ብቻ የሚደረግ ከንቱ ተግባር ሆኖ ይቀራል።»
ዜኖች

@zephilosophy

9.9k 0 24 44 67

ሐይማኖት- ፍቅር
--
“I belong to no religion. My religion is Love. Every heart is my temple.” ~ Rumi

የእውነትን መንገድ ሊያሳዩን በመሃከላችን በስጋ የተመላለሱ ምርጦች እልፍ ናቸው… ሁሉም ለሁሉ የሚሆን ቅን መልዕክት ትተውልናል… ‘ለእነ እከሌ ብለን መጣን’ ባይሉም “ለእኛ መጡ” ብለን ግን ከፋፍለናቸዋል… ጭራሽ በስማቸው አጥር አበጅተናል - ሐይማኖት!!… እናም ዛሬ ቡድሃ፣ ኢየሱስ፣ መሐመድ፣ ኮንፊሺየስ፣ ክሪሽናና ሌሎች ምርጦች ከአጥሩ ውጭ ላሉ ሰዎች እንዳይደርሱ ማዕቀብ ተጥሎባቸዋል… የሁሉም መልዕክት አንድና ተመሳሳይ ቢሆንም ተከታይ ነን ባዮቹ ውሎ እያደር በፈጠሩት ግንብ ምክንያት መተያየት አልተቻለም… ቢያንስ ከአጥሩ ጫፍ ሰይፍና ጦር እንጂ የፍቅር ቃል አይወረወርም…
እኒያ ምርጦች ግን ምን ነበር ያሉት?...
ኢየሱስ – In everything, do to others as you would have them do to you; for this is the law and the prophets. (Jesus – Matthew 7:12)
ነቢዩ መሐመድ – Not one of you truly believers until you wish for others what you wish for yourself. (The Prophet Mohamed, Hadith)
ቡድሐ - Treat not others in ways that you yourself would find hurtful. (Udana – Varga 5:18)
ሌላውንም እንዲሁ ዘርዝሩ… ይሁዲዎች እንደሚሉት “What is hateful to you, do not do to your neighbor. This is the whole Torah.” - “በአንተ ሊደረግ የማትፈልገውን ነገር በሌላው አታድርግ” ከሚል የፍቅር ቃል ውጭ ምንም አታገኙም… ቢገኝም “… “All the rest is commentary!!!” - (Hillel, Talmud, and Shabbat 31a)
***

@Bridgethoughts
@Zephilosophy


"ብዙሀኑን የሚያታልል ጌታቸው ይሆናል ፤ ከዓይናቸው ላይ ቅዠትን ለማጥራት የሚሞክረው መቀጣጫ ይሆናል!።"
ኒቼ
   


ቡድናዊነት በድናዊነት?
ብርሀን ደርበው

የምንከተለው ፋሽን፣ የሚያስቁን ቀልዶች የምንወዳቸው ሙዚቃዎች ወዘተ ወዘተ... እውን የወደድነው የምንወደውን ነው? የምናደርገው ሁሉ በራሳችን ውሳኔ እና ፍላጎት የተደረገ ወይስ ቀልብያችን የሚለን ሌላ ሆኖ አንዳች ኃይል አስገድዶን?

አንዳንዴ እራሴን እንዲህ ብዬ ጠይቃለሁ የምትከተለው ፋሽን የሚያስቁህ ቀልዶች የምትወዳቸው ሙዚቃዎች ወዘተ ወዘተ... ያንተ ምርጫ ወይስ አንዳች ኃይል አስገድዶህ ምትመርጠው? እውን የወደድከው ሁሉ የምትወደውን ነው? የምታደርጋቸው ውሳኔዎች ባንተ ፍላጎት በቀልብያህ ፍቃድ ወይስ ሌሎች ስለወደዱት ላለመነጠል በዓለም ውስጥ
መናኒ ላለመሆን?

Solomon Asch የተባለ ሳይኮሎጂስት Confirmity Line Experiment የምትባል የሰውን ልጅ ውሳኔ አሰጣጥ የምትገመግም አንዲት የምትገርም ጥናት አለችው። እነሆ ጥናቱ A,B,C ሲል የሰየማቸውን ሦስት የተለያየ ቁመት ያላቸው መስመሮች አዘጋጀ።

ተሳታፊዎች በተዘጋጀላቸው ክፍል ውስጥ ሁሉም በየተራ የትኛው መስመር ረዥም እንደሆነ ጮክ ብለው ይናገራሉ። ታድያ ይሄ ሁሉ ሲሆን ክፍሉ ውስጥ በየዙሩ ከሚገኙት ተሳታፊዎች ከአንዱ ወይ ከሁለቱ በቀር ሁሉም ተዋናያን(ሆን ብለው ስህተት የሆነውን እንዲመርጡ) ይሆኑና በመጨረሻ የተቀረው መልሱን እንዲመልስ ይደረጋል።

ታድያ ውጤቱም ከቅጥረኛ ተዋናያን ጋር ከነበሩት ውስጥ በአማካይ 75% ተሳታፊዎች ቢያንስ አንዴ ስህተት የሆነ መልስ ሰጥተዋል። በአንጻሩ ያላንዳች ተጽእኖ ለብቻቸውን (control group) የመለሱ ተሳታፊዎች ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ ትክክለኛውን መልስ መልሰዋል።

በጥቅሉ የጥናቱ ውጤት እንደሚያሳየው እውነታው ግልጽ እና እርግጥ ሆኖ ሳለ ከሌሎች ላለመነጠል ሲል እያወቀው አልያም ብዙ ሰው ካለውማ ልክ ነው (ሞት ከአገር ጋር እንቅልፍ ነው እንዲሉ አበው) በማለት ካለው እውነት የብዙኃኑን ስህተት ይቀላቀላል።

ግላዊነት በሚንቆለጳጰስበት በዚህ በዘመነ ሉላዊነት ምንበላውን ምግብ ፣የት መብላት እንዳለብን፣ ምንለብሰውን ልብስ፣ ማንን መጥላት፣ ማንን መደገፍ እንዳለብን ሁሉ ባንድም ይሁን በሌላ መንገድ የሚወስንልን ማህበራዊ ሚድያው ሆኗል። ፍቅራችን አድናቆታችን ጥላቻችን የኛ አይደለም። ከየትኛውም ጊዜ በላቀ የመንጋነት ስነልቡና በዓለም ላይ ተንሰራፍቷል። ሌሎችን ቀድሞ መከተል ሌሎችን እንደመምራት የሚቆጠርበት ዘመን ላይ ነን።

ቡድናዊ አስተሳሰብ የተለየ ሃሳብ ማመንጨትን ፣ በተለየ መንገድ ነገሮችን ተረድቶ የተለየ
መፍትሔ መስጠትን ፣ አዲስ እይታን፣ ልዩ ምልከታን በጥቅሉ በራስ መቆምን የሚገድል
ከቡድን ውጭ ያለን ሁሉ በድን የሚል ምልከታ ነው።

Hannah Arendt የተባለች ፖለቲካል ፊሎሶፊስት Adolf Eichman ስለሚባል የናዚ መኮነን የፍርድ ሂደት ላይ በጻፈችው Eichman in Jerusalem በተባለ መጽሐፏ እንዲህ ትለናለች ‘’The sad truth is that most evil is done by people who had never made up their minds to be good or evil. ‘’

የሚያሳዝነው ብዙ ክፋቶችና ጥፋቶች የተሠሩት ክፉና ደጉን ለይተው ክፋትን በሚፈጽሙ ክፉ ሰዎች እና አረመኔዎች ሳይሆን ኢየሱስ “የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው።” እንዳለው የሚያደርጉትን ሁሉ አስበውበት ሳይሆን አሳስበዋቸው በፈጸሙ ፤ ስማ በለው በሚመራቸው ጆሯቸው የአእምሮዋቸውን ቦታ በተካባቸው ብኩኖች ነው።

ከሶቅራጥስ ግድያ እስከ ክርስቶስ ስቅላት፣ከጆርዳኖ ቡሩኖ ቃጠሎ እስከ ስልሣዎቹ መረሸን፤ ከናዚ የዘር ፍጅት እስከ አገራችን ፍጅት በፍራቻ በጥላቻ ና በስጋት
ቡድኖች በባህል በፖለቲካ እና በሃይማኖት ስም የመንጋ ውሳኔዎችን በማስተላለፍ ታላቅ ጥፋት


ብዙኃንን መከተል ለምን?

የሰው ልጅ ተፈጥሮ(Human natures need to belong) Aristotile(አርስጣጣሊስ) Man is by nature a social animal ሰው በተፈጥሮው ማህበራዊ እንስሣ ነው ይለናል።

በሰው ልጅ ዝግመተ ለውጥ ውስጥ ለአደን ለመሄድም ሆነ ከአራዊት ጥቃት እራስን ለማዳን የሰው ልጅ ሕይወቱን ለማስቀጠል የሄደበት መንገድ በቡድን መሆንን ነው። ታድያ በስነ ተረክ እና በባህል ተጠቅሞ ኃይልን ለማንበር ፣ ሰላምን ለማስፈን እና ነውጥን ለመግራት የሚያደርገው ትግል በ DNAያችን እና በ ንቃት ህሊናችን ውስጥ ስለሚታተም ከመንጋው መነጠል ወደ ሞት መጓዝ ነው ብሎ እንዲያስብ እና እንዲደምድም ያደርዋል።

ታድያ እርግጠኛ ባለመሆን ፤ተቀባይነትን ለማግኘት፤ መጣልን/መገለልን ፍራቻ በጥቅሉ ክብርን ለማግዘፍና ህላዌን ለማስቀጠል ሲል ብዙኃኑን ይከተላል።
የማህበራዊ ሚዲያን መስፋፋት ተከትሎ የዲጂታል መንጋነትም ለመቆጣጠር በማያስችል ሁኔታ እየተስፋፋ ነው። ጭብጨባችን እንኳ የራሳችን አይደለም። የገደል ማሚቶዎች ሆነናል ፤ በቀቀናዊ ማንነትን ተላብሰናል። ነገሩን ተረዱትም አልተረዱትም ሃሳብን በሃሳብ ከመሞገት ይልቅ በስድብ፣በዛቻ እና በማስፈራራት የሚመልሱ ከልቡናቸው/በጣታቸው በኩልም ይሁን በአፋቸው/ ከጸያፍ ነገር በቀር የሌለ የሚመስል ባለማእረግ ተራጋሚዎችን እያፈራን ነው።

ዲጂታል መንጋዎች ተከታዮቻቸው እንዲነኩባቸው አስተያየት እንዲሰጥባቸው አንዳች ትችት እንዲደርስባቸው አይፈልጉም። የሚከተሉትን ሰዎች ከፈጣሪያችው እኩል አንዳንዴም በላይ እንከን የለሽ አድርገው ስለሳሏቸው እነሱን ለነካባቸው እንጦሮንጦስ ድረስ ወርደው በቀል የመሰላቸውን ነገር ለማድረግ ሁሌም ዝግጁ ናቸው።

ኒቼ Beyond Good and Evil መጽሐፉ ላይ እንዲህ ይላል “Insanity in individuals is something rare - but in groups, parties, nations and epochs, it is the rule.” ቡድኖች እብደታቸውን ሕግ ያደርጉታል።

በማህበር ሲታበድ፤ በጎራ ሲወፈፍ፣ በወል ሲነሆለል፤ ስሜት ይነግሣል ምክንያት ቦታ ያጣል። መቃወም ያስወግራል ፣ መለየት ያስቀጣል ፣መሞገት ያሠድዳል፣ መመርመር ያስቀስፋል ። ከኛ ወዲያ ክንደብርቱ ከኛ ወድያ ኃያል ርቱዕ ከኛ ወድያ ጎራሽ... ፣ ከኛ ወዲያ ላሳር ከኛ ወድያ... ። የሁሉ ነገር መለኪያ ፣ የሁሉ ነገር መተኪያ፣ እና ሁሉ ነገር በራሱ እኛ ነን የሚል የተደፈነ አስተሳሰብን ያጸናል።

እኛ ደሞ(የመተርጎም ነጻነቱን ላንባቢው ትተን) መኖርን የሚያክል ጥናት የለምና ኖረን ካየነው እንዲህ እንላለን Even a pacifist in a mob could become a warmonger.
ቡድናዊነት/የመንጋ እሳቤ በግለሰቦች ውስጥ ያለን እውነት፣ ለውጥ ፣ሂደትና ፈጠራ ወደ በድንነት በመለወጥ በራስ መቆምን የሚያሽመደምድ ነው። መንጋነት ሲነግሥ ሰውነት ይረክሳል፣ ፍትሕ ትንጋደዳለች፣ ስልጣኔ አፈር ይበላዋል።

የወል እሳቤ ማጤን መመርመርን በጥቅሉ ሰው መሆንን የሚገድል ነቀርሳ ነው።በጅምላ
ማሰብ፤ የሰው ልጅ የመጀመርያው ሞቱ ነው። ቆም ብለህ አስብ።ከእሳቱ ከልለው ከጨለማው
የዶሉህን ትተህ የራስህን ሻማ ለኩሰህ ብርሃንህን አብራ።ሰው ሆነህ ሳለህ እራስህን ስለምን ታሳንሳለህ? ራስህን ችለህ አስብ! በራስህ ተጠራ! ሰው ሁን!

ብዙኃን በመንጋ ፣በቡድን፣ በጎራ ሲያስቡና ሲወስኑ ብቻቸውን መቆም የቻሉ ምንኛ የታደሉ ናቸው። የሰውነት ምልአት የመሻገር ከፍታ እነርሱ ጋር ናትና።

ቸር ያቆየን!

Credit to ባይራ ዲጂታል መፅሄት

@Bayradigital
@Zephilosophy

13k 1 58 4 85
20 ta oxirgi post ko‘rsatilgan.