መንግስት በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች እየተፈጸሙ ላሉት የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች በቂ ትኩረት አልሰጠም!
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ ) የተሰጠ መግለጫ;
መስከረም 17/2016 ዓ.ም
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ) በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች በመንግስት የጸጥታ አካላትና በታጠቁ ሀይሎች የሚፈጸሙ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች ዘርፈ ብዙ የሆነ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችን እያስከተሉ በመሆናቸው መፍትሔ እንዲያገኙ በተከታታይ ጋዜጣዊ መግለጫዎችን በማውጣት
የሚመለከታቸው አካላት መፍትሄ እንዲሰጡት ሲያሳስብ ቢቆይም ችግሩ ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ ዜጎች ከፍተኛ ለሆነ የሰው ህይወት መጥፋት፣ የአካል ጉዳት፣የንብረት ዝርፊያና መውደም ፤ ለእገታና መፈናቀል እየተዳረጉ ይገኛሉ፡፡
በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን ጊዳ ወረዳ ኤጀሬ ቀበሌ በቀን 02/01/16ዓ.ም በታጣቂዎች በተፈጸመ
ጥቃት የአንድ ቤተሰብ አባል የሆኑ 4 ሰዎች መገደላቸውን እና በኪራሙ ወረዳ በቀን 02/01/16 የአንድ ሰው
ህይወት ሲያልፍ አንድ ሰው መቁሰሉን እንዲሁም በቀን 04/01/16 ወደ ጊዳ ከተማ ይጓዙ የነበሩተሳፋሪዎችን የታጠቁ ኃይሎች መንገድ ላይ አዉርደው ወንዶችን በመለየት "ጋራ ዲቾ"(ዲቾ ዳገት) በሚባል
ቦታ በርካታ ሰዎች መግደላቸውንና ማቁሰላቸውን በተመሳሳይ በቄለም ወለጋ ዞን አንፍሎ ወረዳ ሱዲ
ቀበሌ በቀን 27/12/15ዓ.ም በመንግስት የጸጥታ አካላት በተፈጸመ ጥቃት የሰው ህይወት ማለፉን እና
የአካል ጉዳት መድረሱን ኢሰመጉ ከአካባቢው ባገኘው መረጃ ለማወቅ የቻለ ሲሆን ኢሰመጉ ስለጉዳዩ መረጃ
እንዲሰጠው የምስራቅ ወለጋ ዞን ፖሊስ መምሪያ፣ የአስተዳደርና ጸጥታ እና የሚሊሻ ዘርፍ በቀን
11/1/2016ዓ.ም በደብዳቤ ቁጥር GMNIDL 01-348/14 የጠየቀ ሲሆን የምሰራቅ ወለጋ ዞን ኃላፊ የሰውህይወት መጥፋቱንና የአካል ጉዳት መድረሱን ትክክለኛነት በቃል ያረጋገጡ ቢሆንም መረጃውን ግን
በደብዳቤ መስጠት እንደማይችሉ ገልጸዋል፡፡
ተያያዥ የህግ ግዴታዎች፡
ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች መግለጫ (UDHR) አንቀጽ 3፣ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ዓለም አቀፍ
ቃል-ኪዳንም (ICCPR) በአንቀጽ 6(1) እና 9(1) ላይ እያንዳንዱ ሰው በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህንነቱ
የመጠበቅ መብት እንዳለው ያረጋግጣል።
ይህንኑ መብት በማረጋገጥ፣ መንግሥታት በቃል-ኪዳኑ (ICPR) የተረጋገጡትን መብቶች በግዛታቸው የማክበር፣ የማስከበርና የማሟላት ግዴታ እንዳለባቸውም በአንቀጽ
2(1) እና 2(2) ይደነግጋል።
የአፍሪካ ቻርተር በሰዎች እና ህዝቦች መብቶች (ACHPR) አንቀጽ 4 ማንኛውም ግለሰብ በሕይወት የመኖር መብቱና የአካሉ ደህንነት መብቱ ሊከበርለትና ሊጠበቅለት እንደሚገባና እነዚህን መብቶቹን በዘፈቀደ ሊነፈግ እንደማይችል ተመላክቷል።
የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 14 “ማንኛውም
ሰው ሰብዓዊ በመሆኑ የማይደፈርና የማይገሰስ በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህንነትና የነጻነት መብት አለው”
ሲል ይደነግጋል።
በተመሳሳይ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ-መንግስት አንቀፅ 15 ማንኛውም ሰው በሕይወት የመኖር
መብት እንዳለውና በሕግ ከተደነገገው ውጪ ሕይወቱን ሊያጣ እንደማይችል በግልፅ ደንግጓል፡፡
በተመሳሳይ
የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ-መንግስት በአንቀጽ 16 ላይ ማንም ሰው በአካሉ ላይ ጉዳት እንዳይደርስበት የመጠበቅ
መብት አለው ሲል ያስቀምጣል፡፡
የኢሰመጉ ጥሪ፡
የኦሮሚያ ክልል መንግስት በኦሮሚያ የተለያዩ አካባቢዎች በመንግስት የጸጥታ አካላትና በታጠቁ
ኃይሎች በንጹሃን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ዘርፈ ብዙ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች በአስቸኳይ
እንዲያስቆም፣
መንግስት የዜጎቹን የሰብዓዊ መብቶች የማስከበር ሀላፊነቱን በአግባቡ እንዲወጣ፣
የፌደራል እና የኦሮምያ ክልል መንግስታት በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች የሚኖሩ ማህበረሰቦች በነጻነት ተንቀሳቅሰው የእለት ተግባራቸውን እንዲፈጽሙ እና በሰላም ወጥተው እንዲገቡ ዜጎችን የመጠበቅ ሀላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ፣
በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በተደጋጋሚ በመንግስት የጸጥታ አካላት እና የታጠቁ ኃይሎች በሚፈጸሙ ጥቃቶች ውስጥ እጃቸው ያለበትን አካላት መንግስት በህግ አግባብ ተጠያቂ እንዲያደርግ ኢሰመጉ ጥሪውን ያቀርባል፡፡
@Addis_Reporter@Addis_Reporter