አዲሱ የገቢ ግብር አዋጅ‼️
ከሃምሌ ወር 2017 ዓ.ም ጀምሮ በስራ ላይ ይውላል ተብሎ የሚጠበቀው አዲሱ የገቢ ግብር አዋጅ ረቂቅ ከላይ ተያይዟል።
የገቢ ግብር ማሻሽያ ረቂቅ አዋጁ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎች ያለባቸውን የግብር ጫና መቀነስ አንዱ አላማው ቢሆንም፤ በውስጡ የያዛቸው ድንጋጌዎች ግን እሱን አንደማያመለክቱ እንደራሴዎች ተናግረዋል፡፡
ረቂቅ አዋጁ በአለም ባንክ መስፈርት መሰረት የድሃ ድሃን የገቢ ግብር የሚያስከፍል ነው በሚል ተተችቷል፡፡
አንድ ሰው ከ30,000 ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ ማንኛውንም ነገር ከተገበያየ መቶ በመቶ እጥፍ ቅጣት እንዲከፍል የገቢ ግብር ማሻሽያ ረቂቅ አዋጅ ያስገድዳል፤ ይህም በፓርላማ ጥያቄ አስነስቷል፡፡
እንደራሴዎቹ በረቂቅ አዋጁ ላይ ትችት እና ቅሬታ ያቀረቡት ትናንት ከሰዓት በኋላ በህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀት እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በገቢ ግብር ረቂቅ አዋጅ ላይ ውይይት ባካሄዱበት ወቅት ነው፡፡
በረቂቅ አዋጁ ላይ ሀሳባቸውን የሰጡት አንድ የምክር ቤት አባል በማሻሻያው ላይ የቀረበው፤ ሰራተኛ ከሚያገኘው ወርሃዊ ደመወዝ ላይ ተቆራጭ የሚደረግበት መነሻ የግብር ምጣኔ ምንን መሰረት ተደርጎ እንደተወሰነ ለእኔ ግልጽ አልሆነልኝም ብለዋል፡፡
ቢያንስ በደመወዝ ማሻሻያው በተደረሰበት ዝቅተኛ የደመወዝ መጠን 4570 ብር ያለውን ለምን ከታክስ ነጻ መደረግ እንዳልተቻለ የጠየቁት የምክር ቤት አባሉ ለምን ከ2000 በላይ የሚያገኙ ተቀጣሪ ሰራተኞች የገቢ ግብር እዲከፍሉ ተደረገ? ሲሉ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
ዝቅተኛ ገቢ ለሚያገኘው ሰራተኛ እኛ እና የገንዘብ ሚኒስቴር ነን እንጂ የምናስብለት ሌላ አካል ያለ አይመስለኝም ያሉት ተወካዩ ለምን የግብር መነሻ ከገንዝብ የመግዛት አቅም ጋር የሚመጣጠን አልሆነም? ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
ገቢ እንዳይቀርብን እንፈልጋለን ያሉት እንደራሴው ግን ገቢውን ማሳደግ ያለብን በዚህ መንገድ መሆን የለበትም ብለዋል፡፡
አስተዳደራዊ ክፍሉን በአግባቡ ከያዝን ማካካስ አይቻልም ወይ ሲሉ የጠየቁት የምክር ቤት አባሉ ይሄ ነገር ቅሬታ ያስነሳብናል ይሄን እንዴት አይታችሁታል? ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
መሆን የሚገባውን ነው ማድረግ ያልብን ያሉት የምክር ቤት አባሉ እኔ እያልኩ ያለሁት ዝቅተኛውም ሰው አይጎዳብን፣ የመንግስት ገቢም መቅረት የለበትም ነው ብለዋል፡፡
አቶ ወንደሰን አድማሴ የተባሉ ሌላ የምክር ቤት አባል በበኩላቸው ግብር መክፈል ያለበት ማነው? የሚል ጥያቄ ከጠየቁ በኋላ የድሃ ድሃ ወይም ( #Absolute_Poverty ) ውስጥ ያለ ሰው ግብር መክፈል አለበት ወይ? ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ2022 በአለም ባንክ በተሰራ ጥናት አንድ ሰው በቀን ከ2.15 ዶላር በታች የሚያገኝ ከሆነ ድሃ እንደሆነ ያሳያል ያሉት አቶ ወንደሰን፤ የኢትዮጵያውን ግን አሁን ባለው የምንዛሪ ተመን ከዚያ ከፍ ያለ ስለ ሆነ absolute poverty ውስጥ ያለ ሰው ግብር መገበር አለበት ወይ ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
ሌላው የምክር ቤት አባሉ እና ቋሚ ኮሚቴው የጠየቀው ጥያቄ በጥሬ ገንዘብ ግብይት ላይ የተጣለውን ገደብ የተመለከተ ነው፡፡
በማሻሽያ ረቂቅ አዋጅ መሰረት ከ30,000 ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ የሚደረግ ግብይትን የሚከለክል ሲሆን ሲገበያይ የተገኘ ሰው ደግሞ የከፈለውን ገንዘብ በእጥፍ እንዲከፍል ያስገድዳል፡፡
Via :- Sheger fm
@Addis_Reporter@Addis_Reporter