ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካፒታል ማሳደጊያ የሚውል የ550 ሚሊዮን ዶላር ብድር በፓርላማ ጸደቀ ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካፒታል ማሳደጊያ የሚውል 550 ሚሊዮን ዶላርን ያካተተ የብድር ስምምነት፤ ዛሬ ሰኞ ጥር 19፤ 2017 በፓርላማ ጸደቀ። የካፒታል ማሳደጊያው፤ ባንኩን “የተሻለ ተወዳዳሪ” እና በቀጠናው መስራት የሚችል “ጠንካራ ባንክ እንዲሆን የሚያስችለው” ነው ተብሏል።
ለመንግስታዊው ባንክ ካፒታል ማሳደጊያ የሚውለው ገንዘብ፤ ዓለም አቀፉ የልማት ማህበር ለኢትዮጵያ መንግስት የሰጠው 700 ሚሊየን ዶላር ብድር አካል ነው።
በዓለም ባንክ ስር የሚገኘው ዓለም አቀፉ የልማት ማህበር ብድሩን የሰጠው፤ የኢትዮጵያን የፋይናንስ ስርዓትን ለማጠናከር በማሰብ ነው።
ይህንኑ በተመለከተ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት አጭር መግለጫ ያቀረቡት በፓርላማ ረዳት የመንግስት ተጠሪ ወ/ሮ መሰረት ኃይሌ፤ በብድሩ በዋነኛነት ተጠቃሚ የሚሆኑት ሶስት የመንግስት የገንዘብ ተቋማት እንደሆኑ አስታውቀዋል።
ከእነዚህ ተቋማት መካከል አንዱ የሆነው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፤ ብድሩን ለካፒታል ማሳደጊያነት ከማዋል በተጨማሪ “መሰረታዊ የመዋቅር ማሻሻያ ለማድረግ” “እና “የዘርፉን የስጋት አስተዳደር ከአለም አቀፍ የባንኪንግ ደረጃዎች ጋር በማጣጣም ለማጎልበት” እንዲጠቀምበት የቀረበ መሆኑን አስረድተዋል።
ከአጠቃላይ የብድሩ ማዕቀፉ ውስጥ ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ማሻሻያ፣ ማዋቀር እና መልሶ ማቋቋም የተያዘው የገንዘብ መጠን 560 ሚሊዮን ዶላር ነው።
ከዚህ ውስጥ 550 ሚሊዮን ዶላር ያህሉ፤ ለባንኩ የካፒታል ማሳደጊያ የሚውል መሆኑን ለፓርላማ በቀረበው የማብራሪያ ሰነድ ላይ ሰፍሯል።
🔴 ለዝርዝሩ ➡️
https://ethiopiainsider.com/2025/14921/@EthiopiaInsiderNews