Ethiopia Insider


Channel's geo and language: Ethiopia, Amharic


Ethiopia Insider is a digital media that provides news, updates, analysis and features.

Related channels  |  Similar channels

Channel's geo and language
Ethiopia, Amharic
Statistics
Posts filter


ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ ከእስር ተፈታ

በሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ሥር የሚተዳደረው “ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የበይነመረብ ሚዲያ መሥራች እና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ ዛሬ አርብ ሰኔ 6 ቀን፤ 2017 ከእስር ተፈትቷል።

ተስፋለም በእስር ላይ በቆየባቸው ያለፉት ቀናት አስፈላጊውን ትብብር ላደረጋችሁ ጓደኞቹ፣ የሙያ አጋሮቹ እና የ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ቤተሰቦች ሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ምሥጋናውን ይገልጻል። ተስፋለም ወልደየስ ከእስር እንዲፈታ ጥሪ ላቀረባችሁ የሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ምሥጋናችን ላቅ ያለ ነው።




የጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ የዋስትና መብት በፍርድ ቤት ቢረጋገጥም አስካሁን አለመፈታቱን በተመለከተ ከሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን የተሰጠ መግለጫ

ለአምስት ቀናት በእስር ያሳለፈው ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በፍርድ ቤት በተወሰነው መሠረት በዋስትና እንዲፈታ የተደረገው ጥረት አልተሳካም። የአዲስ አበባ ሰበር ሰሚ ችሎት ፖሊስ ያቀረበውን ይግባኝ ውድቅ ካደረገ በኋላ ተስፋለም እንዲፈታ የተሰጠውን ትዕዛዝ ዛሬ ሐሙስ ሰኔ 5 ቀን፤ 2017 ከቀኑ 9:00 ሰዓት ጀምሮ ለቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ለማስረከብ ቢሞከርም ተቀባይ አልተገኘም። በዚህም ምክንያት ተስፋለም ይህ መግለጫ እስከወጣበት ሰዓት ድረስ ከእስር አልተፈታም።

የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስን ለፌድራል ፖሊስ የማስረከብ ፍላጎት እንዳለው ሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ተገንዝቧል።

ተቋማችን የተስፋለም ወልደየስ የዋስትና መብት እንዲከበር በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት፣ ቂርቆስ ምድብ ችሎት፣ የአዲስ አበባ ከተማ ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት እና የአዲስ አበባ ከተማ ሰበር ሰሚ ችሎት የተላለፉ ውሳኔዎች ገቢራዊ እንዲሆኑ አበክሮ ይጠይቃል። ከዚህ በተጨማሪ የፍትህ ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ተቋማት እና ግለሰቦች የፍርድ ቤቱ ውሳኔ እንዲከበር ጥሪያቸውን እንዲያቀርቡ እንጠይቃለን።


የአዲስ አበባ ከተማ ሰበር ሰሚ ችሎት የጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ የዋስትና መብት እንዲከበር አዘዘ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰበር ሰሚ ችሎት የ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የበይነመረብ ሚዲያ መሥራች እና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ የዋስትና መብት ላይ ፖሊስ ያቀረበው አቤቱታ ላይ ውሳኔ አስተላለፏል። የሰበር ሰሚ ችሎቱ የፖሊስን ማመልከቻ ጭብጥ ከመመልከቱ በፊት የቀረበለት ጉዳይ “ይግባኝ ያስቀርባል” ወይስ “አያስቀርብም” የሚለውን ዛሬ ጠዋት መርምሯል። በዚህም ሰበር ሰሚ ችሎቱ ባሳለፈው ውሳኔ የፖሊስን ማመልከቻ ውድቅ በማድረግ የስር ፍርድ ቤቶች የሰጡትን ውሳኔ አፅንቷል። ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ ለሶስተኛ ጊዜ የዋስትና መብቱ ተረጋግጦለታል። ይሁንና ይህ መግለጫ እስከወጣበት ሰዓት ድረስ ከእስር አልተፈታም።

በአዲስ አበባ ከሚገኘው ግዮን ሆቴል ቅጥር ግቢ ውስጥ ሲቪል በለበሱ የፀጥታ ኃይሎች እሁድ ሰኔ 1 ቀን፤ 2017 በቁጥጥር ሥር የዋለው ተስፋለም ወልደየስ በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት፣ የቂርቆስ ምድብ ችሎት በ15,000 ብር ዋስትና ከእስር እንዲፈታ የወሰነው ሰኔ 3 ቀን፤ 2017 ነበር።

መርማሪ ፖሊስ ለአዲስ አበባ ከተማ ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ለጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ የተፈቀደው የዋስትና መብት ላይ ያቀረበው ይግባኝ ትላንት ሰኔ 4 ቀን፤ 2017 ተቀባይነት አላገኘም። የይግባኝ ሰሚ ችሎቱ ለሁለተኛ ጊዜ የጋዜጠኛ ተስፋለምን የዋስትና መብት በድጋሚ አክብሮለታል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰበር ሰሚ ችሎት ዛሬ ሐሙስ የተሰየመው የይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ የህግ ስሕተት አለበት በማለት ፖሊስ አቤቱታ ማቅረቡን ተከትሎ ነበር። የፖሊስ ይግባኝ አቤቱታ “ያስቀርባል” ወይስ “አያስቀርብም” የሚለውን የመረመረው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰበር ሰሚ ችሎት “አያስቀርብም” የሚል ውሳኔ አስተላልፏል።

በተጨማሪም የስር ፍርድ ቤቶች የጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስን የዋስትና መብት እንዲከበር መፍቀዳቸው መሰረታዊ የህግ ስህተት ያልተፈጸመበት እና ህግን የተከተለ ሆኖ ስላገኘው ውሳኔዎቹ እንዲጸኑ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

ሶስቱም ፍርድ ቤቶች ያስተላለፉት ውሳኔ ይህ መግለጫ እስከወጣበት ሰዓት ድረስ በፖሊስ አልተተገበሩም። ሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ፖሊስ በፍርድ ቤቶቹ የተላለፉትን ትዕዛዞች በማክበር ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በተከበረለት ዋስትና መሰረት ከእስር እንዲፈታ በአጽንዖት ጥሪውን ያቀርባል።




ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስን በተመለከተ ከሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን የተሰጠ መግለጫ

የአዲስ አበባ ከተማ ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ዛሬ ሰኔ 4 ቀን፤ 2017 የ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የበይነመረብ ሚዲያ መሥራች እና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በሥር ፍርድ ቤት የተወሰነለትን የዋስትና መብት አጽንቷል። ይሁንና መርማሪ ፖሊስ ለሰበር ሰሚ ችሎት ይግባኝ በመጠየቁ ተስፋለም ወልደየስ ይህ መግለጫ እስከ ወጣበት ሰዓት ድረስ ከእስር አልተፈታም። በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት፣ ቂርቆስ ምድብ ችሎት ተስፋለም ወልደየስ በ15,000 ብር ዋስትና እንዲፈታ የወሰነው ትላንት ሰኔ 3 ቀን፤ 2017 ነበር።

ለዋስትና የተጠየቀው ገንዘብ ከተከፈለ በኋላ በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት፣ ቂርቆስ ምድብ ችሎት የተጻፈው ትዕዛዝ በሚመለከታቸው የፖሊስ መኮንን ሳይፈረም በመቅረቱ ተስፋለም ትላንት ማክሰኞ ሳይፈታ ቀርቷል። መርማሪ ፖሊስ የተስፋለም ወልደየስ የዋስትና መብት እንዲከበር የተላለፈው ውሳኔ ላይ ያቀረበው አቤቱታ በዛሬው የይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ተቀባይነት አላገኘም።

የአዲስ አበባ ከተማ ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ለቂርቆስ ፖሊስ መምሪያ በጻፈው ትዕዛዝ “ይግባኝ የቀረበበት የስር ፍርድ ቤት ውሳኔ የሚነቀፍበት ምክንያት ስላላገኘን” “የይግባኝ አቤቱታውን አልተቀበልንውም” ብሏል። ፍርድ ቤቱ ተስፋለም ወልደየስ “በስር ፍርድ ቤት ዋስትና መሰረት ግዴታቸውን ሲወጡ ከእስር እንዲፈቱ” ለቂርቆስ ፖሊስ መምሪያ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

ይሁንና የቂርቆስ ፖሊስ መምሪያ ዋና ኢንስፔክተር ተስፋለም እንዲፈታ ትዕዛዝ የተሰጠበትን ደብዳቤ “እናንተ ጋር አቆዩትና እኛ ለሰበር ይግባኝ እንላለን” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። የፖሊስ ይግባኝ በአዲስ አበባ ከተማ ሰበር ሰሚ ፍርድ ቤት ቢከፈትም ዛሬ ችሎት አልተሰየመም።


ስለሆነም ነገ ሐሙስ ሰኔ 5 ቀን፤ 2017 የአዲስ አበባ ከተማ ሰበር ሰሚ ፍርድ ቤት መርማሪዎች ባቀረቡት ይግባኝ ላይ ውሳኔ ይሰጣል ተብሎ ይጠበቃል።

በሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ሥር የሚተዳደረው “ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የበይነመረብ ሚዲያ መሥራች እና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ ያለፉትን ሶስት ሌሊቶች በፖሊስ ጣቢያ አሳልፏል። ተስፋለም በአዲስ አበባ ከሚገኘው ግዮን ሆቴል ቅጥር ግቢ ውስጥ ሲቪል በለበሱ የፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር የዋለው ባለፈው እሁድ ሰኔ 1 ቀን፤ 2017 ነበር።

የተስፋለም መታሰር በ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የዘገባ ሥራዎች፣ በተቋሙ ባልደረቦች እና በወዳጆቹ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ አሳድሯል። ተቋማችን ሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ተስፋለም ወልደየስ ከእስር ተፈትቶ ወደ ሥራው እንዲመለስ በድጋሚ በአጽንዖት ጥሪውን ያቀርባል። አሁንም ተስፋለም ወልደየስ ከእስር ተፈትቶ ወደሚወደው እና ወደሚያከብረው የጋዜጠኝነት ሙያው እስኪመለስ ድረስ ሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ከፖሊስ እና ከፍርድ ቤት የሚያገኛቸውን መረጃዎች ለሚዲያው ቤተሰቦች ይፋ የሚያደርግ ይሆናል።




የጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ መታሰርን በተመለከተ ከሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን የተሰጠ መግለጫ

በሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ሥር የሚተዳደረው “ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የበይነመረብ ሚዲያ መሥራች እና ዋና አዘጋጅ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ እሁድ ሰኔ 1 ቀን፤ 2017 በጸጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር ውሏል። በአዲስ አበባ ከሚገኘው ግዮን ሆቴል ቅጥር ግቢ ውስጥ ሲቪል በለበሱ የፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር የዋለው ተስፋለም ሌሊቱን እስጢፋኖስ አካባቢ በሚገኝ የፖሊስ መምሪያ ሕንፃ ውስጥ ወንበር ላይ እንዲያሳልፍ መደረጉን ሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን ተገንዝቧል።

ተስፋለም የመጀመሪያውን ሌሊት ካሳለፈበት እስጢፋኖስ አካባቢ ከሚገኝ የፖሊስ መምሪያ ትላንት ሰኞ ሰኔ 2 ቀን፤ 2017 ቄራ አካባቢ ወደሚገኝ የፖሊስ መምሪያ ተዘዋውሯል። ዛሬ ማክሰኞ ሰኔ 3 ቀን፤ 2017 በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት፣ ቂርቆስ ምድብ ችሎት ቀርቦ በ15,000 ብር ዋስትና እንዲፈታ ተወስኖ ነበር። ለዋስትና የተጠየቀው ገንዘብ ከተከፈለ በኋላ ተስፋለም የጠየቀውን መስፈርት የሚያሟላ በመሆኑ ከእስር እንዲለቀቅ በፍርድ ቤቱ ለቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ ትዕዛዝ ተሰጥቷል። ተስፋለም “ሀሰተኛ መረጃ በማሰራጨት” እንደተጠረጠረ ፍርድ ቤቱ ከእስር እንዲፈታ ትዕዛዝ በሰጠበት ደብዳቤ ላይ ሠፍሯል። የተስፋለም የዋስትና መብት እንዲከበር ከተሰጠው ትዕዛዝ በኋላ መርማሪ ፖሊስ በቃል ይግባኝ እንደሚጠይቅ ገልጿል። ይሁንና እስካሁን በይፋ ፍርድ ቤት ይግባኝ አልጠየቀም።

የተስፋለም ዋስትና እንዲከበር ሐቅ ሚዲያና ኮሚኒኬሽን አስፈላጊውን ክፍያ ፈጽሞ በፍርድ ቤቱ ለቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ የተጻፈው ደብዳቤ በሚመለከታቸው የፖሊስ መኮንን ሳይፈረምበት ቀርቷል። በዚህም ምክንያት ይህ መግለጫ ይፋ እስከሆነበት ሰዓት ድረስ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ በፍርድ ቤት የተረጋገጠለት የዋስትና መብት አልተከበረም።

ለጋዜጠኝነት ባለው ፅኑዕ ክብር እና ለሙያው ባለው ቁርጠኝነት የሚታወቀው ተስፋለም ዳግም በፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ሥር መዋሉ የሥራ ባልደረቦቹን፣ ወዳጆቹን እና ቤተሰቦቹን በእጅጉ አሳስቧል። ተደጋጋሚ ችግሮች ቢገጥሙትም “ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ባለፉት ዓመታት ነጻ እና ገለልተኛ የሆኑ፣ ከፍተኛ ሙያዊ ሥነ ምግባራቸውን የጠበቁ ዘገባዎችን ሲያቀርብ ቆይቷል። በዚህም ተዓማኒነት እና ተቀባይነትን እያፈራ የመጣ የበይነመረብ ሚዲያ ተቋም ነው።

ተቋማችን የዋና አዘጋጁ ተስፋለም ወልደየስ እስር በሚዲያው ሥራዎች ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ የሚያሳድር መሆኑን እየገለፀ፣ በአስቸኳይ ወደ ሥራው እንዲመለስ ጥሪውን ያቀርባል። በተጨማሪም፣ ጉዳዩ እልባት እስኪያገኝ ድረስ ተቋማችን ከፖሊስ እና ከፍርድ ቤት የሚያገኛቸውን መረጃዎች ለሚዲያው ቤተሰቦች ይፋ የሚያደርግ ይሆናል።




በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቡለን ከተማ በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ 10 ሰዎች መገደላቸውን ነዋሪዎች ተናገሩ 

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ በመተከል ዞን፣ በቡለን ከተማ ዛሬ ንጋት ላይ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ቢያንስ 10 ሰላማዊ ሰዎች እና የጸጥታ ኃይሎች መገደላቸውን የከተማይቱ ነዋሪዎች ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናገሩ። የመተከል ዞን እና የቡለን ወረዳ አስተዳደር በከተማይቱ ላይ በተፈጸመ ጥቃት የሰዎች ህይወት መጥፋቱን፣ ባንክ ቤትን ጨምሮ በተቋማት ላይ ዝርፊያ እና ጉዳት መድረሱን አረጋግጠዋል።

ጥቃቱ በቡለን ከተማ ላይ የተሰነዘረው፤ ዛሬ አርብ ግንቦት 29፤ 2017 ከንጋቱ 12 ሰዓት ገደማ ጀምሮ እንደነበር ነዋሪዎቹ እና የቡለን ወረዳ አስተዳደር ገልጸዋል። ለደህንነታቸው በመስጋት ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ ሶስት የቡለን ከተማ ነዋሪዎች ጥቃቱ እስከ ረፋዱ አራት ሰዓት ገደማ ድረስ የቆየ እንደነበር አመልክተዋል።

ታጣቂዎቹ ዛሬ ንጋት ላይ ወደ ከተማ ሲገቡ መመልከታቸውን ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የዓይን እማኝነታቸውን የሰጡ አንድ ነዋሪ፤ መቶ ገደማ የሚሆኑ ታጣቂዎች በአንድ መስመር ሲጓዙ ማየታቸውን ተናግረዋል። ከታጣቂዎቹ ውስጥ ገሚሶቹ ቡላ ቀለም ያለው የደንብ ልብስ እንደለበሱ እና የተቀሩት ግን የሲቪል ልብስ መልበሳቸውን መመልከታቸውን አክለዋል።

ነዋሪው “ክላሽ እና ብሬል የያዙ ነበሩ” ያሏቸው ታጣቂዎች ጥቃት መሰንዘር ሲጀምሩ በቤታቸው እንደነበሩ ገልጸዋል። በጥቃቱ አስር ሰዎች መገደላቸውን፣ የባንክ እና ፖሊስ ጣቢያ መዘረፉን መስማታቸውንም አስረድተዋል።

🔴 ለዝርዘሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16129/

@EthiopiaInsiderNews


የኢትዮጵያን ድንበር የማካለል ስራ “ተቋማዊ ቅርጽ ሰጥቶ” ለማከናወን በዝግጅት ላይ መሆኑን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ

ኢትዮጵያ ከጎረቤት ሀገራት ጋር የምትዋሰንባቸውን በሺህዎች ኪሎ ሜትር የሚቆጠር ድንበርን “የማካለል ስራ”፤ “ተቋማዊ ቅርጽ ሰጥቶ” ለማከናወን በዝግጅት ላይ መሆኗን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ አስታወቁ። ሀገሪቱ ካላት ድንበር “በአግባቡ የተሰመረ እና የተለየው” ከ50 በመቶ በታች መሆኑንም ሚኒስትሩ ተናግረዋል። 

የድንበር ማካለል ጉዳይ የተነሳው፤ ዛሬ ሐሙስ ግንቦት 28፤ 2017 ዓ.ም በተካሄደው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ ነው። በዚሁ ስብሰባ ላይ የውጭ ጉዳዮችን የተመለከቱ የተለያዩ ጥያቄዎች፤ በአምስት የፓርላማ አባላት ቀርበዋል። 

ከጠያቂዎቹ አንዷ የነበሩት ገዢው የብልጽግና ፓርቲን በመወከል ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጊዶሌ መደበኛ ምርጫ ክልል የተመረጡት ይፍቱ ጉዲሳ ናቸው። “አንዳንድ ጎረቤት ሀገራት ሉዓላዊነታችንን በመጣስ የገዛ መሬታችንን መያዛቸው ይነገራል” ያሉት ወ/ሮ ይፍቱ፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ያለውን “እውነታ” እንዲያብራሩላቸው ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን ጠይቀዋል።

ዶ/ር ጌዲዮን በምላሻቸው፤ በአፍሪካ ቀንድ ከሁሉም ሀገራት ጋር የምትዋሰን “ብቸኛ ሀገር” ኢትዮጵያ መሆንዋን አስታውሰዋል። ሆኖም ከዚህ ድንበር ውስጥ “በአግባቡ” “የተከለለ”፣ “የተሰመረ” እና “የተለየው” ከግማሽ በታች እንደሆነ አስረድተዋል። 

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16124/

@EthiopiaInsiderNews


የ2018 የፌደራል መንግስት በጀት በብር ቢጨምርም፤ በዶላር ስሌት ከፍተኛ ቅናሽ አሳየ 

የፌደራል መንግስት ለ2018 ያዘጋጀው በጀት፤ ከዘንድሮው አኳያ በግማሽ ትሪሊዮን ብር ገደማ ዕድገት ቢያሳይም በዶላር ሲሰላ ከፍተኛ ቅናሽ አስመዘገበ። ለሚቀጥለው ዓመት የተዘጋጀው በጀት፤ ሁለት ትሪሊዮን ብር የሚጠጋ እንደሆነ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል።

በጀቱን የያዘው የአዋጅ ረቂቅ ዛሬ ሐሙስ ግንቦት 28፤ 2017 በተካሄደው የሚኒስትሮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ ቀርቦ ውይይት እንደተደረገበት ጽህፈት ቤቱ አመልክቷል። የበጀት ረቂቁ “የሀገር ደህንነትን ከማስጠበቅ”፣ “ምርት እና ምርታማነትን ከማሳደግ” እንዲሁም “በተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ችግሮች ምክንያት የተፈናቀሉ ዜጎችን ከመርዳት አንጻር” የተዘጋጀ እንደሆነ ጽህፈት ቤቱ ገልጿል።

ከዚህ በተጨማሪ በጀቱ ከ2018 እስከ 2022 ዓ.ም ድረስ ያለውን “የመካከለኛ ዘመን” የማክሮ ኢኮኖሚ እና ፊስካል ማዕቀፍን መሰረት በማድረግ የተዘጋጀ እንደሆነ መግለጫው ጠቁሟል። በዚህ ማዕቀፍ መነሻነት የተዘጋጀውን የ2018 በጀት ትክክለኛ መጠን፤ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ዛሬ ባወጣው መረጃ ላይ አልገለጸም።

የ2018 በጀት ከዘንድሮው ጋር ሲነጻጸር በ500 ቢሊዮን ብር ገደማ ጭማሪ ቢኖረውም በዶላር ግን ከፍተኛ ቅናሽ አሳይቷል። በግንቦት 2016 ዓ.ም የጸደቀው የዘንድሮው 971.2 ቢሊዮን ብር መደበኛ በጀት፤ በወቅቱ ምንዛሬ 17 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ነበር።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16120/

@EthiopiaInsiderNews


የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከኤርትራ ጋር “የቃላት ጦርነት ውስጥ አልገባንም” አሉ

በኤርትራ በኩል “ትንኮሳ” ቢኖርም፤ የኢትዮጵያ መንግስት ከሀገሪቱ ጋር “የቃላት ጦርነት ውስጥ አልገባም” ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ ተናገሩ። ኢትዮጵያ ስትራቴጂክ የሆኑ የሀገራዊ ጥቅም ጉዳዮች ስታነሳ “ትኩሳታቸው የሚጨምሩ ሀገራት አሉ” ያሉት ሚኒስትሩ፤ መንግስት በእነዚህ ጉዳዮች ላይ ያለው አቋም “አይዛነፍም” ሲሉ ለፓርላማ አባላት ገልጸዋል።

ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሚኒስትሩ ይህንን ያሉት፤ ከፓርላማ አባላት በቃል ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ዛሬ ሐሙስ ግንቦት 28፤ 2017 በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተገኝተው ምላሽ በሰጡበት ወቅት ነው። ጥያቄ ካቀረቡት አንዱ የሆኑት የአብኑ የፓርላማ ተወካይ ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ፤ የኢትዮጵያ እና ኤርትራን ወቅታዊ ሁኔታ አንስተዋል።

ኤርትራ እና ኢትዮጵያን “ወደ ጦርነት ጅማሮ” እየወሰዳቸው ያለ “የቃል ጦርነቱ የተጀመረ ይመስለኛል” ያሉት የፓርላማ አባሉ፤ ሁለቱ ሀገራት በአሁኑ ወቅት ያላቸው “ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት” በምን መልኩ እንደሚገልጽ ጠይቀዋል። ዶ/ር ደሳለኝ ከኤርትራ ጋር “ወደ ጦርነት መግባት እድል አለ ወይ?” ሲሉም ተጨማሪ ጥያቄ አክለዋል።

ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ለዚህ ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፤ “ከኤርትራ መንግስት ጋር የኢትዮጵያ መንግስት የቃላት ጦርነት ውስጥ አልገባም” ሲሉ አስተባብለዋል። ጉዳዩ የሚያሳስባቸው፣ የሚመለከታቸው ዜጎች፣ የህዝብ ተወካዮች እና የቀድሞ የመንግስት ኃላፊዎች “የራሳቸውን ምልከታ” እንደሚያጋሩ ግን ሚኒስትሩ አልሸሸጉም። እነዚህ አካላት “ጆሮ ሊሰጣቸው ይገባል” ሲሉም አሳስበዋል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16102/

@EthiopiaInsiderNews


የመንግስት እና የግል ሰራተኞች ከደመወዛቸው ላይ ለአደጋ ስጋት ምላሽ ፈንድ እንዲያዋጡ የሚያስገድድ ድንጋጌ ተሰረዘ

ወደፊት ለሚቋቋመው “የአደጋ ስጋት ምላሽ ፈንድ”፤ ከመንግስት እና ከግል ተቋማት ሰራተኞች ደመወዝ መዋጮ እንዲሰበሰብ የሚያስገድደው የአዋጅ ድንጋጌ ተሰረዘ። ድንጋጌው በዛሬው ዕለት በፓርላማ ከጸደቀው “የአደጋ ስጋት ስራ አመራር አዋጅ” ውስጥ እንዲወጣ የተደረገው፤ በሰራተኞች ላይ “ተደራራቢ ጫና እንዳያስከትል” ታስቦ መሆኑ ተገልጿል።

ባለፈው መጋቢት ወር መጀመሪያ ለተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው ይኸው አዋጅ፤ የመንግስት እና የግል ተቋማት ከሚሰጧቸው 15 አይነት አገልግሎቶች “ለአደጋ ስጋት ምላሽ ፈንድ” ገቢ እንዲሰበሰቡ የሚያስገድድ ድንጋጌ በውስጡ ይዞ ነበር። ፈንዱ “ለአደጋ ስጋት ቅነሳ፣ ምላሽ እና መልሶ ማቋቋም” ተግባራት የሚውል እንደሆነ በአዋጁ ላይ ሰፍሯል።

በገቢ ምንጭነት በአዋጁ ተዘርዝረው ከነበሩት መካከል “የመንግስት እና የግል ድርጅት ተቀጣሪ ሰራተኞች ከሚከፈላቸው የተጣራ ደመወዝ ላይ” መዋጮ እንዲሰበሰብ የሚያስገድደው ድንጋጌ አንዱ ነበር። አዋጁ ለውይይት በቀረበበት ወቅት፤ ከደመወዝ ላይም ሆነ ከተለያዩ አገልግሎቶች ለፈንዱ ገቢ የሚሆን ገንዘብ መሰብሰብ “የግለሰቦችን የመክፈል አቅም ያገናዘበ ነው ወይ?” የሚል ጥያቄ አስነስቶ ነበር።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16093/

@EthiopiaInsiderNews


መጪውን ሀገራዊ ምርጫ “ፈቃጅ” እና “አስቻይ” ሁኔታዎች ባሉባቸው አካባቢዎች ለማድረግ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ምርጫ ቦርድ ገለጸ 

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፤ መጪው ሀገራዊ ምርጫ “ፈቃጅ” እና “አስቻይ” ሁኔታዎች ባሉባቸው የምርጫ ክልሎች እንደሚደረግ ገለጸ። በሀገሪቱ ያለው የጸጥታ ሁኔታ “በጣም ተለዋዋጭ በመሆኑ”፤ ምርጫው በሚቃረብበት ወቅት ሁኔታው “በዝርዝር” እና “በጥልቀት” የሚታይ መሆኑንም አስታውቋል። 

ቦርዱ ይህንን ያስታወቀው፤ የሰባተኛው ሀገራዊ ምርጫ ቅድመ ዝግጅት እና ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ ዛሬ ሰኞ ግንቦት 25፤ 2017 በአዲስ አበባው ስካይ ላይት ሆቴል ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ ነው። የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ፤ ምርጫን ለማድረግ በየአካባቢዎቹ “አስቻይ ሁኔታ” መኖር “የግድ” አስፈላጊ እንደሆነ በዚሁ መግለጫ ላይ አመልክተዋል።

በስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ቦርዱ “በሁሉም አካባቢ ምርጫ አካሂዳለሁ ብሎ ነው ያቀደው። አሁንም በሁሉም አካባቢ ምርጫ እናደርጋለን ብለን ነው የምናቅደው” ሲሉ ሜላትወርቅ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል። በሰኔ 2013 ዓ.ም በተካሄደው ስድስተኛው ጠቅላላ ምርጫ፤ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ካሉት 547 መቀመጫዎች ውስጥ 102 በሚሆኑት ላይ ምርጫ አልተካሄደም።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16079/

@EthiopiaInsiderNews


የእነ አቶ ጌታቸው ረዳ ፓርቲ በአንድ ወር ከአጋማሽ ውስጥ “በትግራይ መስራች ጉባኤዬን አካሄዳለሁ” አለ 

በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጊዜያዊ ፍቃድ ያገኘው ዲሞክራሲያዊ ስምረት ትግራይ ፓርቲ (ስምረት)፤ እስከ አንድ ወር ተኩል ባለው ጊዜ ውስጥ መስራች ጉባኤውን እንደሚያካሄድ ገለጸ። ፓርቲው ከመጪው ሰኞ ጀምሮ የአባላት ምልመላ እና ከክልል እስከ ቀበሌ ያሉ አደረጃጀቶችን የመፍጠር ስራዎችን እንደሚያከናውን አስታውቋል። 

ስምረት ፓርቲ ይህን የገለጸው፤ ዛሬ ቅዳሜ ግንቦት 23፤ 2017 በአዲስ አበባው ሸራተን ሆቴል በሰጠው የመጀመሪያው ጋዜጣዊ መግለጫ ነው። ጋዜጣዊ መግለጫውን ከፓርቲው መስራቾች አንዱ የሆኑት የቀድሞው የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት በነበሩት አቶ ጌታቸው ረዳ ይሰጡታል ተብሎ ቢጠበቅም፤ ባጋጠማቸው “የጤና እክል” ምክንያት በመግለጫው ሳይሳተፉ ቀርተዋል።

እርሳቸውን በመተካት መግለጫውን የሰጡት የአዲሱ ፓርቲ የሚዲያ እና የኮሚዩኒኬሽን ዘርፍ አስተባባሪ አቶ ረዳኢ ሓለፎም፤ ፓርቲው በሚቀጥለው አንድ ወር ውስጥ ሁለት መሰረታዊ ስራዎችን እንደሚያከናውን ተናግረዋል። መቶ አባላትን በመያዝ ጊዜያዊ ፍቃዱን ከምርጫ ቦርድ ያገኘው ስምረት፤ በዚህ ጊዜ ውስጥ ከትግራይ እና ከሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች አባላትን የመልመል ስራዎች እንደሚሰራ አቶ ረዳኢ ተናግረዋል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16063/

🔴 ሙሉ መግለጫውን በቪዲዮ ለመመልከት ➡️ https://youtu.be/B-oc3qLdRIg

@EthiopiaInsiderNews


ከ1,700 በላይ “የጥቃቅን ቡድኖች” የምክክር አጀንዳዎችን መሰነዱን ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን አስታወቀ    

እስከ ዛሬ ድረስ ባለው ሀገራዊ የምክክር ሂደት፤ ከ200 ሺህ ሰዎች በላይ መሳተፋቸውን ከኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነሮች አንዱ የሆኑት ዶ/ር አምባዬ ኦጋቶ ተናገሩ። ኮሚሽኑ ከ1,746 በላይ የሆኑ “የጥቃቅን ቡድኖች” የምክክር አጀንዳዎችን መሰነዱንም ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል።

ዶ/ር አምባዬ ይህን ያስታወቁት፤ ዛሬ አርብ ግንቦት 22፤ 2017 በአዲስ አበባው ሚሊኒየም አዳራሽ በተጀመረው የፌደራል ባለድርሻ አካላት የአጀንዳ ማሰባሰብ መርሃ ግብር ላይ ባቀረቡት ገለጻ ነው። ለሶስት ቀናት በሚቆየው በዚህ መርሃ ግብር፤ የተለያዩ የፌደራል ተቋማትን፣ ማህበራትን እና አካላትን የወከሉ 900 የሚጠጉ ግለሰቦች እየተሳተፉ ይገኛሉ።

በፌደራል ደረጃ በሚካሄደው በዚህ የምክክር ሂደት ከሚሳተፉት መካከል ከፍተኛውን ቁጥር የያዙት፤ “ተጽዕኖ ፈጣሪ” የተባሉ ግለሰቦች ናቸው። በኮሚሽኑ ግብዣ በምክክር አጀንዳ ልየታ ላይ እየተሳተፉ የሚገኙት የእነዚህ ግለሰቦች ብዛት 220 እንደሆነ ከተቋሙ የተገኘ መረጃ ያመለክታል።

የሃይማኖት እንዲሁም የሲቪል እና የዲሞክራሲ ተቋማት፤ ከመንግስት ተወካዮች እኩል 160 ተሳታፊዎችን አዋጥተዋል። በፌደራል ደረጃ ያሉ ማህበራት እና ተቋማት በ113 ግለሰቦች ሲወከሉ፣ የመገናኛ ብዙሃን ድርጅቶች እና ማህበራት 96 ግለሰቦችን በምክክሩ ላይ አሳትፈዋል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16053/

@EthiopiaInsiderNews


አይ ኤም ኤፍ ለኢትዮጵያ ከሚሰጠው ብድር ውስጥ 260 ሚሊዮን ዶላር ሊለቅ ነው

ኢትዮጵያ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይ ኤም ኤፍ) ባለሙያዎች፤ በተራዘመ የብድር አቅርቦት ሶስተኛ ግምገማ ላይ ከስምምነት ደረሱ። ግምገማው በአይ ኤም ኤፍ ስራ አስፈጻሚ ቦርድ ሲጸድቅ፤ የኢትዮጵያ መንግስት ከዓለም አቀፉ ተቋም ከሚበደረው 3.4 ቢሊዮን ዶላር ውስጥ 260 ሚሊዮን ዶላር ይለቀቅለታል።

የአይ ኤም ኤፍ ቦርድ ግምገማውን ከማጽደቁ በፊት፤ የኢትዮጵያ መንግስት ከይፋዊ አበዳሪዎች ጋር የመግባቢያ ስምምነት ላይ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል። ይህንን ዛሬ አርብ ግንቦት 22፤ 2017 ይፋ ያደረጉት፤ ከሁለት ወር ገደማ በፊት ወደ አዲስ አበባ መጥቶ የነበረውን የአይ ኤም ኤፍ የባለሙያዎች ቡድን የመሩት አልቫሮ ፒሪስ ናቸው። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

[በዚህ ዘገባ ላይ ተጨማሪ መረጃ ይታከልበታል]

@EthiopiaInsiderNews


ለአንድ ሳምንት አገልግሎት አቋርጠው የነበሩት በመቐለ ከተማ የሚገኙ ፍርድ ቤቶች ወደ ስራ ተመለሱ

በዳኞች ስራ ማቆም ምክንያት ለአንድ ሳምንት ያህል ተዘግተው የነበሩ በመቐለ ከተማ የሚገኙ ፍርድ ቤቶች፤ ዛሬ ሐሙስ ስራ ጀመሩ። “የደህንነት ስጋት አለብን” በሚል ምክንያት አገልግሎት መስጠት ያቆሙት በከተማይቱ የሚገኙ ዳኞች ወደ ስራ የተመለሱት፤ ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ጋር ውይይት ከተካሄደ በኋላ መሆኑን የትግራይ ዳኞች ማህበር ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ገልጿል።

በመቐለ ከተማ የሚገኙ ዳኞች ባቀረቧቸው ጥያቄዎች ላይ ውይይት የተደረገው ባለፈው ሰኞ ግንቦት 18፤ 2017 ነበር። ጉዳዩን በተመለከተ የትግራይ ክልል ፕሬዝዳንት ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ ውይይት ያደረጉት፤ ከክልሉ ፍትህ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሓዱሽ ተስፋ እና ከክልሉ ጠቅላይ ፍርድቤት ፕሬዝዳንት አቶ መንግስቱ ተክላይ ጋር ነው።

የ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ዘጋቢ በዛሬው ዕለት ተዘዋውሮ በተመለከታቸው በመቐለ ከተማ በሚገኙ ፍርድ ቤቶች መግቢያዎች ላይ የተለጠፉ ማስታወቂያዎች፤ ይህንኑ ውይይት መጠቅሳቸውን ታዝቧል። “በዳኞች ላይ ባጋጠመ የደህንነት ስጋት ምክንያት የተቋረጠው አገልግሎት እንዲጀመር ከሚመለከተው አካል ጋራ ውይይት ተካሂዷል” የሚለው ማስታወቂያው፤ “በውሱን መልኩ ጥያቄዎቻችን መፈታት ስለጀመሩ ከዛሬ 21/9/2017 ጀምሮ የዳኝነት አገልግሎት ጀምረናል” ይላል። 

የትግራይ ክልል ዳኞች ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ ዳዊት ሃይለስላሴ “በውይይቱ ለዳኞች ስራ ማቆም ምክንያት የሆኑ ጥያቄዎች እንደሚፈቱ ስለተነገረን ነን ወደ ስራ የተመለስነው” ሲሉ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል። 

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16045/

@EthiopiaInsiderNews


የውጭ ሀገር ስራ ስምሪት አዋጅ በአራት ዓመት ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ተሻሻለ

በውጭ ሀገር ለስራ የሚሰማሩ ኢትዮጵያውያንን የሚመለከተው አዋጅ፤ ከአራት ዓመት በኋላ በድጋሚ ማሻሻያ ተደረገበት። የአዋጅ ማሻሻያው በውጭ ሀገር ለስራ የሚሰማሩ ዜጎች “መብታቸው፣ ደህንነታቸው እና ክብራቸው በዘላቂነት መጠበቁን ለማረጋገጥ” “እንዲያስችል ሆኖ የተዘጋጀ ነው” ተብሏል።

በ2008 ዓ.ም የወጣው “የኢትዮጵያ የውጭ ሀገር ስምሪት አዋጅ” ሰራተኛን በውጭ ሀገር ለስራ ማሰማራት የሚቻለው፤ “በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግስት እና በተቀባይ ሀገር መካከል የሁለትዮሽ ስምምነት ሲኖር ብቻ እንደሆነ” የሚገድብ ድንጋጌ ነበረው። በ2013 ዓ.ም. የጸደቀው የዚህ አዋጅ ማሻሻያ በበኩሉ፤ በውጭ ሀገራት “የሰለጠነ የሰው ኃይል” ለሚፈለግበት ስራ ተጨማሪ ሁለት የስምምነት አማራጮችን አካትቷል።  

የመጀመሪያው አማራጭ፤ ጉዳዩ በሚመለከተው የኢትዮጵያ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት እና በተቀባይ ሀገር ከሚገኘው አቻ ስልጣን ካለው የመንግስት ተቋም ጋር “የሁለትዮሽ ስምምነት” ወይም “መግባቢያ ሰነድ” ሲኖር ሰራተኛን ማሰማራት እንደሚቻል ይፈቅዳል። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ተመሳሳይ ስምምነት በውጭ ሀገር ከሚገኝ “እውቅና ካለው አሰሪ ኩባንያ” ጋር ከፈጸመም፤ ኢትዮጵያውያን ሰራተኞችን መላክ እንደሚቻል በአዋጁ ማሻሻያው ተደንግጓል። 

“የሰለጠነ የሰው ኃይል የሚሰማራበት ስራ አፈላልጎ ያገኘ ኤጀንሲ፤ በተቀባይ ሀገር መንግስት እውቅና ካለው ቀጣሪ አሰሪ ኩባንያ ጋር የስራ ስምሪት ስምምነት እንዲፈጽም” ጉዳዩ የሚመለከተው ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ሊፈቅድ እንደሚችልም በ2013ቱ የአዋጅ ማሽሻያ ላይ ተቀምጧል። 

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/16038/

@EthiopiaInsiderNews

20 last posts shown.