Ethiopia Insider


Channel's geo and language: Ethiopia, Amharic


Ethiopia Insider is a digital media that provides news, updates, analysis and features.

Related channels  |  Similar channels

Channel's geo and language
Ethiopia, Amharic
Statistics
Posts filter


በኢትዮጵያ በጋዜጠኞች ላይ ስለሚፈጸመው ተደጋጋሚ እስር ሲፒጄ ምን አለ?

በኢትዮጵያ ከመጋቢት ወር አጋማሽ እስከ ሚያዝያ ወር አጋማሽ ባለው አንድ ወር ጊዜ ውስጥ ብቻ 14 ጋዜጠኞች እና የመገናኛ ብዙሃን ተቋማት ሰራተኞች ለእስር ተዳርገው እንደነበር ዓለም አቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት (ሲፒጄ) አስታወቀ። ከታሰሩት ጋዜጠኞች እና ሰራተኞች ውስጥ ሁለቱ አሁንም በእስር ላይ እንደሚገኙ ሲፒጄ ገልጿል።

ሲፔጄ ይህን የገለጸው፤ በየሀገራቱ ያሉ ጋዜጠኞችን የተመለከቱ ሰሞነኛ ጉዳዮችን አጠናቅሮ ይፋ በሚያደርግበት ዘገባ ላይ ነው። ድርጅቱ ትላንት አርብ ግንቦት 8፤ 2017 ባወጣው ዘገባ፤ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ከሰሃራ በታች ካሉ ሀገራት በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደተቀመጠች አስታውሷል። 

በእስር ላይ ያሉ ጋዜጠኞችን በተመለከተ ድርጅቱ በየዓመቱ በሚያወጣው ዓመታዊ ሪፖርት፤ ከሰሃራ በታች ካሉ ሀገራት ከኢትዮጵያ በላቀ ጋዜጠኞች የታሰሩባት ሀገር ኤርትራ መሆኗ ተመልክቷል። ዓመታዊ ሪፖርቱ እስከተጠናቀረበት እስካለፈው ህዳር ወር መጨረሻ ድረስ በኢትዮጵያ የታሰሩ ጋዜጠኞች  ስድስት እንደነበሩ ሲፒጄ በትላንቱ ሪፖርቱ ጠቅሷል።

ይህ ቁጥር ባለፈው መጋቢት እና ሚያዝያ ወር በተፈጸሙ እስራቶች በከፍተኛ ሁኔታ አሻቅቦ ነበር። በመጋቢት ወር ከተፈጸሙ የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች እስሮች ከፍተኛው ቁጥር የተመዘገበው በኢቢኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ ሰራተኞች ላይ ነው።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15939/

@EthiopiaInsiderNews


በሀገራዊ ምክክር ሂደት የሚታየው የምሁራን ተሳትፎ ከሚጠበቀው አንጻር “አነስተኛ ነው” ተባለ

በኢትዮጵያ ያሉ ምሁራን በሀገራዊ የምክክር ሂደት ላይ ያላቸው ተሳትፎ፤ ሊኖራቸው ከሚገባው “አስተዋጽኦ” አንጻር ሲታይ “አነስተኛ ነው” ሲሉ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ምክትል ዋና ኮሚሽነር ሂሩት ገብረስላሴ ተናገሩ። አብዛኞቹ ምሁራን ከሂደቱ “ራሳቸውን የማግለል” አሊያም ሁኔታውን “በዝምታ የመመልከት” አካሄዶችን የመከተል “አዝማሚያዎች” እንደሚታይባቸውም ገልጸዋል።

ምክትል ዋና ኮሚሽነሯ ይህን የገለጹት፤ በሀገራዊ የምክክር ሂደት ምሁራን የሚኖራቸውን ሚና በተመለከተ ዛሬ ቅዳሜ ግንቦት 9፤ 2017 በተካሄደ የውይይት መርሃ ግብር ላይ ባደረጉት ንግግር ነው። በአዲስ አበባው ሃይሌ ግራንድ ሪዞርት በተካሄደው በዚህ መርሃ ግብር ላይ ከአማራ፣ ኦሮሚያ እና ደቡብ ኢትዮጵያ ክልሎች የተመረጡ 90 ምሁራን ተሳትፈዋል።

ይህን መርሃ ግብር በንግግር የከፈቱት ምክትል ዋና ኮሚሽነሯ፤ በሌሎች ሀገራት የተከናወኑ ሀገራዊ ምክክሮች “ውጤታማ እንዲሆኑ” ካደረጓቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ “የምሁራኖቻቸው አስተዋጽኦ” እንደሆነ አስገንዝበዋል። ምሁራን ሀገራዊ ምክክርን “በተለየ መልኩ ማየት አለባቸው” የሚል አቋም ኮሚሽኑ እንዳለው የጠቀሱት ሂሩት፤ ጉዳዩ “በአመለካከት ልዩነቶች ሳይጋረዱ” “ያለስስት አስተዋጽኦ ሊያበረክቱለት የሚገባ” እንደሆነም አሳስበዋል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15933/

@EthiopiaInsiderNews


የአማራ ክልል ዳኞች በፖለቲካ ጉዳዮች ላይ በማንኛውም ማህበራዊ ሚዲያ ላይ “ሃሳብ እንዳይሰጡ” የሚከለክል ደንብ ወጣ   

በአማራ ክልል የሚገኙ ዳኞች፤ በፖለቲካ፣ በሃይማኖት ወይም “አወዛጋቢ በሆኑ ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ “በየትኛውም” ማህበራዊ ሚዲያ “ሃሳብ እንዳይሰጡ” የሚከለክል ደንብ ጸደቀ። ደንቡ በክልሉ የሚገኙ ዳኞች “ሀሰተኛ ማህበራዊ ሚዲያዎችን “እንዳይጠቀሙ”፣ “እንዳይከተሉ” እና “አባል እንዳይሆኑ” ይከለክላል።

የዳኞች እና የጉባኤ ተሿሚዎችን የስነ-ምግባር እና የዲሲፕሊን የሚመለከተው ይህ ደንብ የጸደቀው ከትላንት በስቲያ ማክሰኞ ግንቦት 5፤ 2017 ነው። ደንቡን ያጸደቀው የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የዳኞች አስተዳደር አብይ ጉባኤ፤ ደንቡ ከዚሁ ዕለት ጀምሮ ተግባራዊ እንዲሆን ውሳኔ አስተላልፏል።

የአማራ ክልል ፍርድ ቤቶች የዳኞች አስተዳደር ጉባኤን ለማሻሻል በ2014 የወጣው አዋጅ፤ ለዳኞች እና ለጉባኤ ተሿሚዎች የስነ ምግባር እና የዲሲፒሊን ደንብ የማውጣት ስልጣን የሰጠው በጠቅላይ ፍርድ ቤት ስር ላለው አብይ ጉባኤ ነው። እስካሁን በስራ ላይ የቆየው የስነ ምግባር እና የዲሲፒሊን ደንብ የወጣው በ2007 ዓ.ም ነበር።

ይህ ደንብ “በርካታ ጉዳዮችን ያካተተ ቢሆንም ግልጽነት የጎደላቸው ጉዳዮችን ይበልጥ ግልጽ ለማድረግ” በአዲስ መልክ እንዲዘጋጅ መደረጉን የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በትላንትናው ዕለት ባሰራጨው መረጃ አስታውቋል። አዲሱ ደንብ እንዲዘጋጅ ከተደረገባቸው ምክንያቶች አንዱ፤ በቀድሞው ደንብ ያልነበረ “የዳኞች ማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀምን” ማካተት በማስፈለጉ እንደሆነ ፍርድ ቤቱ ገልጿል።

🔴 ዝርዝር ዘገባውን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15924/

@EthiopiaInsiderNews


ህወሓት ከፖለቲካ ፓርቲነት መሰረዙን ምርጫ ቦርድ አስታወቀ

ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ከትላንት ማክሰኞ ግንቦት 5፤ 2017 ዓ.ም ጀምሮ ከፖለቲካ ፓርቲነት መሰረዙን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታወቀ። የምስረታውን የወርቅ ኢዮቤልዮ ባለፈው የካቲት ወር ያከበረው ህወሓት ከፓርቲነት የተሰረዘው፤ ቦርዱ ያዘዘውን “የእርምት እርምጃ” ተግባራዊ ባለማድረጉ መሆኑን ገልጿል። 

ምርጫ ቦርድ ይህን ውሳኔ ያሳለፈው፤ ባለፈው የካቲት ወር መጀመሪያ ለፓርቲው የሰጠው ቀነ ገደብ በዛሬው ዕለት መጠናቀቁን ተከትሎ ነው። ቦርዱ ይህንን ቀነ ገደብ ባሳወቀበት መግለጫው፤ ህወሓት ጠቅላላ ጉባኤ ለማካሄድ የሚያስችል “የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን” በሶስት ወራት ውስጥ እንዲያካሄድ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር።

ቦርዱ ህወሓትን ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያካሄድ ያዘዘው፤ “በአመጽ እና በህገ- ወጥ መንገድ ሲንቀሳቀሱ” የነበሩ የፖለቲካ ፓርቲዎችን “በልዩ ሁኔታ” እንደሚዘገቡ የሚያስችለው አዋጅ በሚያስቀምጠው ድንጋጌ መሰረት ነው። ይህ አዋጅ “በልዩ ሁኔታ” የሚመዘገቡ የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ በስድስት ወራት ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤያቸውን እንዲያካሄዱ በምርጫ ቦርድ ሊታዘዙ እንደሚችሉ ይደነግጋል። 

ይህን አዋጅ መሰረት በማድረግ በነሐሴ 2016 ዓ.ም ለህወሓት የህጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት የሰጠው ምርጫ ቦርድ፤ ፓርቲው “የቦርዱ ታዛቢዎች” በተገኙበት በስድስት ወራት ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲያደርግ ቀነ ገደብ አስቀምጦ ነበር። ቦርዱ የቅደመ ጉባኤውን የዝግጅት ስራዎች ለመከታተል እንዲረዳው፤ ፓርቲው ጠቅላላ ጉባኤውን ከማካሄዱ 21 ቀናት በፊት ለመስሪያ ቤቱ እንዲያስታውቅም ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15908/

@EthiopiaInsiderNews


አቶ ጌታቸው ረዳ ሶስት ከፍተኛ የትግራይ ሰራዊት አመራሮች “በዘረፋ እና በሰዎች ንግድ ላይ ተሳትፈዋል” ሲሉ ወነጀሉ  

የቀድሞው የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፤ ሶስት ከፍተኛ የትግራይ ወታደራዊ አመራሮች “በወርቅ ቁፋሮ እና ንግድ”፣ “የመንግስት ገንዘብ በመዝረፍ” እንዲሁም ”በህገወጥ የሰዎች ዝውውር ላይ ተሳትፈዋል” ሲሉ ወነጀሉ።

አቶ ጌታቸው ረዳ ከፋና ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ባደረጉት ቃለ መጠይቅ በስም ጠቅሰው የወነጀሏቸው ሶስቱ አመራሮች፤ ብርጋዴር ጀነራል ምግበይ ሃይለ፣ ብርጋዴር ጀነራል ሃይለስላሴ ግርማይ እና ኮሎኔል ተወልደ ገብረትንሳኤ ናቸው። 

ትላንት ሰኞ ግንቦት 4፤ 2017 ምሽት በፋና ቴሌቪዥን የተላለፈው የቀድሞው የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንት ክፍል አንድ ቃለ መጠይቅ፤ ስለ እርሳቸው የፖለቲካ ተሳትፎ አጀማመር፣ በትግራይ ክልል ስለ ተካሄደው ጦርነት፣ የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አመራሮች እና የትግራይ ሰራዊት አዛዦች “ፈጽመዋቸዋል” ስላሏቸው ወንጀሎች የዘረዘሩበት ነበር።

አቶ ጌታቸው ተፈጽመዋል ካሏቸው ወንጀሎች ቅድሚያውን የሰጡት ለወርቅ ንግድ ነው። በትግራይ ክልል በህገወጥ መንገድ የሚካሄደው የወርቅ ንግድ የተጀመረው፤ ህወሓት እና የኢትዮጵያ መንግስት የፕሪቶሪያ ስምምነትን ከተፈራረሙ ከጥቅምት 2015 ዓ.ም. በኋላ የሚመስለው በርካታ ሰው እንዳለ አቶ ጌታቸው በቃለ መጠይቃቸው ላይ አንስተዋል።

ሆኖም በክልሉ ህገወጥ የወርቅ ቁፋሮም ሆነ ንግድ የተጀመረው፤ የትግራይ ጦርነት እየተካሄደ በነበረበት ወቅት ጭምር እንደሆነ የቀድሞው የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንት ይፋ አድርገዋል።    

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15872/

@EthiopiaInsiderNews


ለጤናው ዘርፍ “ከፍ ያለ” በጀት ለመመደብ ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆኑን የጤና ሚኒስትሯ ገለጹ

ለጤናው ዘርፍ በ2018 ዓ.ም. “ከፍ ያለ” በጀት ለመመደብ፤ “በቂ ዝግጅቶች” እየተደረጉ መሆኑን የጤና ሚኒስትሯ ዶ/ር መቅደስ ዳባ ተናገሩ። የዘርፉን በጀት ከፍ ማድረግ ያስፈለገው አሁን ካለው “ወቅታዊ” እና “ነባራዊ” ሁኔታ አንጻር እንደሆነም ሚኒስትሯ ገልጸዋል። 

የጤና ሚኒስትሯ ይህን ያሉት ከብሔራዊው ቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ባደረጉት እና ዛሬ ሰኞ ግንቦት 4፤ 2017 በተላለፈው ቃለ ምልልሳቸው ነው። ዶ/ር በዚሁ ቃለ ምልልሳቸው፤ የጤና ዘርፉን በተመለከተ ባሉ ወቅታዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል። 

የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ለሚኒስትሯ ካቀረበው ጥያቄ አንዱ፤ የጤናው ዘርፍ የገንዘብ አቅምን የተመለከተ ነው። መንግስት ከሚመድበው በጀት በተጨማሪ ለጋሾች በሚሰጡት ገንዘብ በሚደገፈው በዚህ ዘርፍ፤ በአሁኑ ወቅት ስራዎች በምን መልኩ እየተሰሩ እንደሆነ እና ያጋጠሙ ተግዳሮቶች ምን እንደሆኑ ለሚኒስትሯ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል።  

ዶ/ር መቅደስ ለዚህ ጥያቄ በሰጡት ምላሽ በኢትዮጵያ ለጤናው ዘርፍ የሚመደበው በጀት ባለፉት ዓመታት እየጨመረ ቢመጣም፤ ከዓለም አቀፍ ስምምነቶች አንጻር ሲታይ መጠኑ “ዝቅተኛ” መሆኑን ተናግረዋል። ሚኒስትሯ ለዚህ በማጣቀሻነት ያነሱት፤ በቀድሞው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) የመሪዎች ጉባኤ ላይ በሚያዝያ 1993 ዓ.ም. የጸደቀውን የአቡጃ ድንጋጌ ነው።

🔴 ለዝርዘሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15860/

@EthiopiaInsiderNews


መንግስት ለመጪው ምርጫ “ሰላማዊ የውድድር ሜዳ እንዲፈጥር” አራት የተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥሪ አቀረቡ

በኢትዮጵያ ጠቅላላ ምርጫ ለማካሄድ አንድ ዓመት ከመቅረቱ አኳያ፤ ገዢው ፓርቲ “እውነተኛ” እና “ሁሉን አካታች” የሆነ ድርድር “በአስቸኳይ” በማድረግ እና በሀገር ውስጥ የተፈጠሩ ቀውሶችን በመፍታት፣ “ሰላማዊ የውድድር ሜዳ እንዲፈጥር” አራት የተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥሪ አቀረቡ። ፓርቲዎቹ “ለሰላማዊ ትግል ውጤታማነት” እገዛ ለማድረግ፤ መንግስት “የፖለቲካ እስረኞችን” እንዲፈታም ጠይቀዋል።

ዛሬ ሰኞ ግንቦት 4፤ 2017 በጋራ ባወጡት መግለጫ ጥሪ፣ ጥያቄ እና ማሳሰቢያቸውን ያቀረቡት፤ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፣ የኢትዮጵያ ህዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢህአፓ)፣ የአማራ ግዮናዊ ንቅናቄ እና እናት ፓርቲ ናቸው። በወቅታዊ ጉዳይ ላይ የተሰጠው የአራቱ ፓርቲዎች የዛሬ መግለጫ ትኩረቱን ያደረገው፤ በ2018 ዓ.ም. ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቀው ሰባተኛው ዙር ሀገር አቀፍ ምርጫ ላይ ነው። 

“ኢትዮጵያ ሀገራችን አሁን ካለችበት የጦርነት አዙሪት ለመውጣት እና የህዝብ ጭቆና፣ አፈና፣ ሰቆቃና እልቂትን ማስቆም የሚቻለው፤ ከማጭበርበር የጸዳ፣ ነጻ፣ ፍትሃዊና ተአማኒ ምርጫ በማካሄድ ብቻ መሆኑን እኛ በሰላማዊ መንገድ የምንታገል የትብብር ፓርቲዎች በጽኑ እናምናለን” ሲሉ ፓርቲዎቹ በመግለጫቸው ላይ አስፍረዋል። እነዚህን መስፈርቶች የሚያሟላ ምርጫ፤ በተፈጥሮው “ሰላማዊ የመከወኛ ሜዳ የሚሻ” መሆኑንም ጠቅሰዋል።

🔴 ለዝርዘሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15857/

@EthiopiaInsiderNews


ዘንድሮ 47 ቢሊዮን ብር የከሰረው ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ፤ በሁለት ዓመት ውስጥ ወደ ትርፋማነት እንደሚሸጋገር የኩባንያው ኃላፊዎች ገለጹ 

ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ በተያዘው ዓመት ኪሳራ ቢያጋጥመውም፤ በሁለት ዓመታት ውስጥ ወደ ትርፋማነት ይሸጋገራል ተብሎ እንደሚጠበቅ የእናት ኩባንያው ኃላፊዎች ተናገሩ። መቀመጫውን በኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ ያደረገው ሳፋሪኮም ኩባንያ፤ እስከ መጋቢት ወር ባለው የአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ካገኘው 3 ቢሊዮን ዶላር የአገልግሎት ገቢ 10 በመቶ ገደማ የሚሆነው የኢትዮጵያ ገበያ ድርሻ እንደሆነ አስታውቋል።

ኩባንያው የሚመራበት በጀት ዓመት መጠናቀቁን በማስመልከት ባለፈው ሐሙስ ይፋ የተደረገ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ገቢ ባለፈው ዓመት 2.7 ቢሊዮን ብር የነበረ ሲሆን ዘንድሮ 7.2 ቢሊዮን ብር ደርሷል።

የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ገቢ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ270 ፐርሰንት እድገት ቢያሳይም፤ 47 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ኪሳራ እንደገጠመው ዋና ስራ አስፈጻሚው ዊም ቫንሔለንፑት ገልጸዋል።

“ይህ ኪሳራ በአብዛኛው ኩባንያው በሚገኝበት ከፍተኛ የኢንቨስትመንት ምዕራፍ ከምንጠብቀው ጋር የተስማማ ነው” ያሉት ዋና ስራ አስፈጻሚው፤ ከዚህ በተጨማሪ የኢትዮጵያ መንግስት በሐምሌ 2016 ዓ.ም. ተግባራዊ ያደረገው የውጭ ምንዛሬ ግብይት ስርዓት ለውጥ በኩባንያው ላይ ተጽዕኖ እንዳሳደረ ጠቁመዋል።

የውጭ ምንዛሬ ግብይት ስርዓት ለውጡ፤ በአጭር እና መካከለኛ ጊዜ የሚያሳድራቸውን ተጽዕኖዎች ለመቋቋም “እርምጃዎች መወሰዳቸውን” የሳፋሪኮም ኃላፊዎች አብራርተዋል። እርምጃው በውጭ በሳፋሪኮም ኢትዮጵያ የተቀጠሩ የውጪ ሀገር ዜጎችን መቀነስን የካተተ ነው።

🔴ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15849/

@EthiopiaInsiderNews


የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር “አላማው ያልታወቀ” ከማንኛውም የውጭ ኃይል ጋር የሚደረግ ግንኙነት “ተቀባይነት የለውም” አለ

ከማንኛውም የውጭ ኃይል የሚደረግ “አላማው እና ስትራቴጂካዊ ስልቱ ያልታወቀ” ግንኙነት “ተቀባይነት የለውም” ሲል የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ገለጸ። ይህን መሰሉ ግንኙነት፤ የትግራይ ክልልን “መንግስት አልባ የሚያደርግ አደገኛ አካሄድ ነው” ሲልም ጊዜያዊ አስተዳደሩ አቋሙን አስታውቋል።

ጊዜያዊ አስተዳደሩ ይህን ያስታወቀው፤ ወቅታዊ ጉዳዮችን በተመለከተ በትግራይ ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ በኩል ዛሬ ባወጣው መግለጫ ነው። የትግራይ ህዝብ “ህልውናውን እና ብሔራዊ ጥቅሙን” ለማረጋገጥ “ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል እያካሄደ” መሆኑን የጠቀሰው መግለጫው፤ ዋናው ጥያቄው የፕሪቶሪያ ስምምነት “ሳይሸራረፍ ተግባራዊ ይደረግ” የሚል እንደሆነ አስገንዝቧል።

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በጥቅምት 2015 ዓ.ም በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ከተማ የተፈረመው የግጭት ማቆም ስምምነት የፈጠረውን ዕድል  ተፈጻሚ ለማድረግ በእንቅስቃሴ ላይ እንደሚገኝም ቢሮው አመልክቷል። የትግራይ ህዝብን “ጥቅሞችን እና መብቶች ለማስከበር” እንዲሁም “ከጦርነት ስጋት እንዲጠበቅ ለማድረግ” ጊዜያዊ አስተዳደሩ እየሰራ መሆኑንም ቢሮው አክሏል።

ከፌዴራል መንግስት ጋር ብቻ ሳይሆን ከማንኛውም ኃይል ጋር የሚኖሩ ልዩነቶች ለመፍታት፤ “በሰላማዊ” እና “ህጋዊ መንገድ” “የተቻለውን ሁሉ ጥረት” ማድረግ ተገቢ መሆኑንም መግለጫው አትቷል። ሆኖም “አላማው እና ስትራቴጂካዊ ስልቱ ያልታወቀ”፤ ከማንኛውም የውጭ ኃይል ጋር የሚደረግ ግንኙነት “ተቀባይነት እንደሌለው” ጊዜያዊ አስተዳደሩ ገልጿል።  

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15840/

@EthiopiaInsiderNews


ኢትዮ ቴሌኮም 40 ተቋማት አገልግሎት መስጠት የጀመሩበትን “የዲጂታል ገበያ” ይፋ አደረገ

መንግስታዊው የቴሌኮም አገልግሎቶች አቅራቢ የሆነው ኢትዮ ቴሌኮም፤ “ዘመን ገበያ” የተሰኘ ሀገር አቀፍ “የዲጂታል ገበያ” መጀመሩን አስታወቀ። የዲጂታል ገበያው በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ አምራች እና ነጋዴዎችን፣ ገዢዎችን እና የሎጅስቲክስ ተቋማትን “በቀላሉ ለማገናኘት የሚያስችል ነው”ተብሎለታል።

ኩባንያው የዲጂታል ገበያውን ይፋ ያደረገው፤ ዛሬ ሐሙስ ሚያዝያ 30፣2017 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው የሳይንስ ሙዚየም ባዘጋጀው መርሃግብር ላይ ነው። በመርሃ ግብሩ ላይ ገለጻ ያደረጉት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ፤ የዲጂታል ገበያው የተጀመረው በ40 ተቋማት እና በ14 ምርቶች መሆኑን ተናግረዋል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

[በዚህ ዘገባ ላይ ተጨማሪ መረጃ ይታከልበታል]

@EthiopiaInsiderNews


የትግራይ የጤና ባለሙያዎች የ17 ወራት ውዝፍ ደመወዝ እንዲከፈላቸው በሰልፍ ጠየቁ

የትግራይ ክልል የጤና ባለሙያዎች በክልሉ በተካሄደው ጦርነት ወቅት ሳያገኙ የቀሩት የ17 ወራት ውዝፍ ደመወዝ እንዲከፈላቸው በሰልፍ ጠየቁ። የጤና ባለሙያዎቹ ምቹ የስራ ሁኔታ እንዲፈጠርላቸውም ጥያቄ አቅርበዋል።
 
ባለሙያዎቹ ጥያቄያቸውን ያሰሙት፤ ዛሬ ረቡዕ ሚያዝያ 29፤ 2017 ዓ.ም. በመቐለ ከተማ በሚገኙ የተለያዩ የጤና ተቋማት ውስጥ ባካሄዱት ሰላማዊ ሰልፍ ነው። ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ተከታታይ ቀናት በክልሉ በሚገኙ የተለያዩ የጤና ተቋማት እንደሚካሄድ የተገለጸውን ይህ ሰላማዊ ሰልፍ የጠራው የትግራይ የጤና ባለሙያዎች ማህበር ነው። 

የማህበሩ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፍስሃ አሸብር የጤና ባለሙያዎች በትግራይ ጦርነት ወቅት በስራ ገበታቸው በመገኘት ለህዝብ አገልግሎት ሲሰጡ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። የጤና ባለሙያዎቹ የህክምና አገልግሎት ሲሰጡ የቆዩት፤ ለ17 ወራት ያህል ደመወዝ ሳይከፈላቸው እንደነበርም ጠቁመዋል።

🔴 ስለ ጤና ባለሙያዎቹ ጥያቄ ዶ/ር ፍስሃ የሰጡትን ማብራሪያ በቪዲዮ ለመመልከት ይህን ሊንክ ይጫኑ ➡️ https://youtu.be/wAzt4yXbj98

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15825/

@EthiopiaInsiderNews


የኢቢኤስ ቴሌቪዥን እና ሶስት የጣቢያው ሰራተኞች በጥላቻ ንግግር እና ሀሰተኛ መረጃ በማሰራጨት ተከሰሱ 

የኢቢኤስ ቴሌቪዥን፣ እህት ኩባንያው እና ሶስት የጣቢያው ሰራተኞች የጥላቻ ንግግር እና ሀሰተኛ መረጃ በማሰራጨት ወንጀል ክስ ቀረበባቸው። በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በቀረበው በዚህ የክስ መዝገብ ክስ፤ ጋዜጠኛ መዓዛ መሐመድ፣ በኢቢኤስ ቴሌቪዥን “ሀሰተኛ ታሪኳ ተሰራጭቷል” የተባለችው ብርቱካን ተመስገንን ጨምሮ ስድስት ተጠርጣሪዎች በሽብር ወንጀል ተከስሰዋል።

በአጠቃላይ 16 ተከሳሾች የተካተቱበትን የክስ መዝገብ፤ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የህገ መንግስት እና ሽብር ወንጀል ጉዳዮች ችሎት ዛሬ ማክሰኞ ሚያዝያ 28፤ 2017 ያቀረበው የፌደራል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ነው። ከተከሳሾቹ መካከል ስምንቱ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቢሮ እና በወረዳ ደረጃ ያሉ ኃላፊዎች እና ሰራተኞች ናቸው። 

ዐቃቤ ህግ ለፍርድ ቤቱ ባቀረበው መዝገብ ሶስት የክስ አይነቶች ጠቅሷል። የመጀመሪያው ክስ፤ የሽብር ወንጀልን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር በ2011 ዓ.ም. የወጣን አዋጅ በመተላለፍ የቀረበ ነው። ዐቃቤ ህግ በክሱ የጠቀሰው የአዋጁ ድንጋጌ፤ “የሽብር ድርጊት” በመፈጸም “የሰው ህይወትን ለአደጋ ማጋለጥን” ይመለከታል። 

ይህ ድንጋጌ ተጠቅሶ ክስ ከቀረበባቸው ተጠርጣሪዎች ውስጥ በቀዳሚነት የተቀመጡት በአሁኑ ወቅት ነዋሪነታቸውን በውጭ ሃገር ያደረጉት ጋዜጠኛ መዓዛ መሐመድ እና ተስፋዬ ወልደስላሴ ናቸው። 

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15811/

@EthiopiaInsiderNews


በአምስተኛው ዙር የውጭ ምንዛሬ ጨረታ 60 ሚሊዮን ዶላር ለሽያጭ ማቅረቡን ብሔራዊ ባንክ አስታወቀ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ነገ ረቡዕ በሚያካሄደው የውጭ ምንዛሬ ጨረታ፤ 60 ሚሊዮን ዶላር ለሽያጭ ማቅረቡን አስታወቀ። በጨረታው መሳተፍ የሚፈልጉ ባንኮች የሚያቀርቡትን ዋጋ ነገ ከረፋድ አራት ሰዓት እስከ እኩለ ቀን እንዲያስገቡ ብሔራዊ ባንክ ጥሪ አቅርቧል።

ለነገ የታቀደው ጨረታ፤ ኢትዮጵያ የውጭ ምንዛሬ ስርዓት ለውጥ ካደረገች ከሐምሌ 2016 ዓ.ም. ወዲህ አምስተኛ ነው። ብሔራዊ ባንክ ባለፉት አራት ዙሮች ባካሄዳቸው ጨረታዎች፤ በድምሩ 355 ሚሊዮን ዶላር ለተሳታፊ ባንኮች አቅርቧል።

አቶ ማሞ ምህረቱ በገዢነት የሚመሩት ብሔራዊ ባንክ፤ “በየሁለት ሳምንት” ልዩነት ተመሳሳይ ጨረታ እንደሚያካሄድ ያስታወቀው ባለፈው መጋቢት ወር መጨረሻ ገደማ ነበር። በዚህ መልኩ የሚካሄደው ጨረታ እስከ 2017 በጀት ዓመት መጨረሻ ድረስ እንደሚካሄድ ብሔራዊ ባንክ ማስታወቁ አይዘነጋም።

በእነዚህ ጨረታዎች የሚቀርበው የውጭ ምንዛሬ መጠን፤ “በወቅቱ ያለውን የውጪ ምንዛሬ ፍላጎት በማገናዘብ” እንደሚሆን አቶ ማሞ ምህረቱ በዚሁ ወቅት ተናግረው ነበር። በዚህ መሰረት ባለፈው መጋቢት ወር መጨረሻ በተካሄደው ጨረታ 50 ሚሊዮን ዶላር ለጨረታ የቀረበ ሲሆን፤ በዚሁ ጊዜ ለአንድ ዶላር የቀረበው አማካይ ዋጋ 131.7 ብር ሆኖ ተመዝግቧል።

በተመሳሳይ መልኩ በሚዝያ ወር የመጀመሪያ ሳምንት በተካሄደ ጨረታ 70 ሚሊዮን ዶላር ለጨረታ ቀርቧል። ለአንድ ዶላር በአማካይ 131.1 ብር በቀረበበት በዚህ ጨረታ፤ በጥያቄያቸው መሰረት ለ26 ባንኮች የውጭ ምንዛሬ መከፋፈሉን ብሔራዊ ባንክ አስታውቋል። የነገው ጨረታ ውጤት አመሻሽ 11 ሰዓት ላይ ይፋ እንደሚደረግ ባንኩ ገልጿል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

@EthiopiaInsiderNews


በሽብር ወንጀል ጉዳይ ተጠረጥረው በእስር ላይ የሚገኙ አራት የኢቤኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ ሰራተኞች፤ ዋስትና በማስያዝ እንዲለቀቁ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰጠ። ሁለት የጣቢያው ሰራተኞችን ጨምሮ 16 ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ መመስረቱን የፌደራል ዐቃቤ ህግ ለፍርድ ቤት አስታውቋል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

[በዚህ ዘገባ ላይ ተጨማሪ መረጃ ይታከልበታል]

@EthiopiaInsiderNews


የህወሓት ህጋዊ ሰውነት በፕሪቶሪያ ስምምነት መሰረት እንዲመለስለት የፓርቲው መካከለኛ እና ከፍተኛ አመራሮች ጠየቁ

በዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል የሚመራው የህወሓት ጎራ መካከለኛ እና ከፍተኛ አመራሮች፤ ፓርቲው ዳግም ምዝገባ እንዲያካሄድ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተላለፈውን ትእዛዝ በመኮንን፤ ህጋዊ ሰውነቱ በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት እንዲመለስለት ጠየቁ። እነዚሁ አመራሮች በክልሉ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላትን ያቀፈውን የጊዜያዊ ምክር ቤት ህልውና እንደማይቀበሉትም አስታውቀዋል።

የፓርቲው አመራሮች ይህን ያስታወቁት፤ ከሐሙስ ሚያዝያ 23 ጀምሮ በመቐለ ከተማ በሚገኘው የሰማእታት ሃውልት አዳራሽ ሲያካሄዱት የቆዩትን ስብሰባ በትላንትናው ዕለት ሲያጠናቀቁ ባወጡት የአቋም መግለጫ ላይ ነው። “ብሔራዊ አንድነታችን ሉአላዊነታችን ለማረጋገጥ” በሚል መሪ ቃል በተካሄደው በዚህ ስብሰባ፤ 1,337 የፓርቲው መካከለኛ እና ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል ተብሏል።

የስብሰባው ተሳታፊዎች በስብሰባቸው ማጠቃለያ ባወጡት ባለ 10 ነጥብ የአቋም መግለጫ ካነሷቸው ጉዳዮች አንዱ የህወሓት የህጋዊ ሰውነት የማግኘት ጉዳይ ነው። ህወሓት 50 ዓመት የሞላው እና “በህዝቡ ልብ የታተመ” መሆኑን በመግለጫቸው የጠቆሙት አመራሮቹ፤ የፓርቲው እውቅና “በትግራይ ህዝብ የሚወሰን ነው ብለን እናምናለን” ሲሉ አቋማቸውን አስታውቀዋል።

ከፕሪቶሪያ ስምምነት በተቃራኒ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ህወሓትን በድጋሚ ለመመዝገብ የሚያደርገውን ተደጋጋሚ ሙከራ እንደሚያወግዙም አመራሮቹ በአቋም መግለጫቸው ላይ አስፍረዋል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15799/

@EthiopiaInsiderNews


በኢትዮጵያ ሀሳብን የመግለጽ ነጻነት አሁንም “በከፍተኛ ጫና” ውስጥ እንደሆነ 14 ሀገራት በጋራ ባወጡት መግለጫ አስታወቁ 

ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የ14 ሀገራት ኤምባሲዎች፤ በኢትዮጵያ ሀሳብን በነጻነት መግለጽ ላይ ያለው “ከፍተኛ ጫና” መቀጠሉ እንደሚያሳስባቸው ገለጹ። በኢትዮጵያ የአውሮፓ ህብረት ተልዕኮ በበኩሉ የፕሬስ ነጻነት አለመኖር “መረጃ የማግኘት መብትን እና የመተቸት ነጻነትን ያጓድላል” ብሏል።
 
ኤምባሲዎቹ እና የአውሮፓ ህብረት ይህን ያሉት በዛሬው ዕለት በመላው ዓለም የሚከበረውን የዓለም የፕሬስ ነጻነት ቀን በማስመልከት በየፊናቸው ባወጡት መግለጫ ነው። ፈረንሳይ፣ ስዊድን፣ ኔዘርላንድስ፣ ዩናይትድ ኪንግደም እና ኒውዚላንድ የተካተቱበት የ14 ሀገራት ስብስብ፤ በኢትዮጵያ እና በመላው ዓለም ነጻ፣ ደህንነቱ የተጠበቀ እና ገለልተኛ ጋዜጠኝነት አስፈላጊነትን በመግለጫቸው አስታውሰዋል።

በመላው ዓለም ለሚገኙ ጋዜጠኞች ነጻነት እና ደህንነት መጠበቅ ያላቸውን ድጋፍ የገለጹት ሀገራቱ፤ በኢትዮጵያ አስተውለናዋል ያሉትን ወቅታዊ ሁኔታም አንስተዋል። በኢትዮጵያ ሀሳብን በነጻነት መግለጽ ላይ ያለው “ከፍተኛ ጫና” መቀጠሉን እንዳስተዋሉ የጠቀሱት ሀገራቱ፤ ይህ ሁኔታ እንደሚያሳስባቸውም በመግለጫቸው አስፍረዋል። 

🔴 ሙሉ ዘገባውን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15792/

@EthiopiaInsiderNews

#WorldPressFreedomDay


#WorldPressFreedomDay

በፕሬስ ነጻነት ከኢትዮጵያ በታች ያሉ የአፍሪካ ሀገራት የትኞቹ ናቸው?

ምስላዊ መረጃ:- ድንበር የለሽ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት (RSF) በየዓመቱ የ180 ሀገራትን የፕሬስ ነጻነት በመመዘን ያስመዘገቡትን ደረጃ ይፋ ያደርጋል። ድርጅቱ በትላንትናው ዕለት ባወጣው የዘንድሮው ዝርዝር ኢትዮጵያ 145ኛ ደረጃ አግኝታለች። ይህ ውጤት ሀገሪቱ አምና ከነበረችበት በአራት ደረጃዎች መውረዷን ያመለከተ ሆኗል።

በድርጅቱ ዝርዝር መሰረት የኢትዮጵያ የፕሬስ ነጻነት ዘንድሮም “በጣም አሳሳቢ” በሚባለው ውስጥ ምድብ ውስጥ የሚገኝ ነው። ከዓለም ህዝብ ከግማሽ በላይ የያዙ 42 ሀገራት በዚሁ ምድብ ውስጥ የሚገኙ መሆኑን ድርጅቱ አስታውቋል። እነዚህ ሀገራት የጋዜጠኝነት ሙያን መተግበር “አደገኛ የሆነባቸው” አሊያም ደግሞ የፕሬስ ነጻነት “ከእነአካቴው የሌለባቸው” እንደሆኑ ድርጅቱ ገልጿል።

ኢትዮጵያ በRSF ዝርዝር የመጨረሻዎቹን ደረጃ ከያዙ ሰባት የአፍሪካ ሀገራት ውስጥም ተካትታለች። ኢትዮጵያን ተከትላ በ146ኛ ደረጃ የተቀመጠችው ሩዋንዳ ናት። ሁለቱ የኢትዮጵያ ጎረቤቶች ሱዳን እና ጅቡቲ እንደ ቅደም ተከተላቸው 156ኛ እና 168ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጡ ግብጽ 170ኛ ደረጃን አግኝታለች። ሌላኛዋ የኢትዮጵያ ጎረቤት ኤርትራ እንደ አምናው ሁሉ በድርጅቱ ዝርዝር የመጨረሻውን 180ኛ ደረጃ ይዛለች። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

@EthiopiaInsiderNews


በአዲስ አበባ ለትራንስፖርት አገልግሎት የሚውሉ ብስክሌቶች፤ ከተመረቱ ሁለት ዓመት ያላለፋቸው መሆን እንደሚገባ የሚያዝ ደንብ ተግባራዊ ሆነ   

በአዲስ አበባ ከተማ በብስክሌት የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት የስራ ፈቃድ የሚጠይቅ ሰው፤ 300 እና ከዚያ በላይ ብስክሌቶች ለአገልግሎት ማቅረብ የሚችል መሆን እንዳለበት የሚደነግግ ደንብ ስራ ላይ ዋለ። ለአገልግሎት የሚቀርበው ብስክሌት ደረጃውን የጠበቀ ጂፔኤስ የተገጠለመት እና የተመረተበት ዘመን ከሁለት ዓመት ያልበለጠ መሆን አንዳለበትም አዲሱ ደንቡ ይደነግጋል።

“የብስክሌት መጋራት አገልግሎት እና የብስክሌት መስመር አጠቃቀም” የተሰኘ መጠሪያ ያለው ይህ ደንብ፤ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ የጸደቀው ባለፈው ጥር ወር መጨረሻ ነበር። ደንቡን ማዘጋጀት ካስፈለገባቸው ምክንያቶች አንዱ በአዲስ አበባ ከተማ የተሽከርካሪ ቁጥር “በከፍተኛ ሁኔታ በመጨመሩ” ምክንያት የሚፈጠረውን “የትራፊክ እንቅስቃሴ መጨናነቅን ለማቃለል” እንደሆነ ተገልጿል።

በስድስት ክፍሎች እና በ25 አንቀጾች የተከፋፈለው ይህ ደንብ የስራ ፈቃድ አሰጣጥን ጨምሮ ሌሎች ድንጋጌዎችን አካትቷል። አዲሱ ደንብ ማንኛውም በብስክሌት ትራንስፖርት አገልግሎት ለመሰማራት የሚፈልግ ሰው፤ ከአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ የስራ ፈቃድ ማውጣት እንዳለበት ይደነግጋል።

“በኦፕሬተርነት ስራ” ለመሰማራት የሚፈልግ ማንኛውም ሰው በመስፈርትነት ሊያሟላቸው የሚገባቸው መስፈርቶችም በደንቡ ላይ ተዘርዝረዋል። በስራው የሚሰማራ ሰው ቢያንስ 300 እና ከዚያ በላይ ብስክሌቶች ወይም ከ100 የማያንስ ስኩተሮች ለአገልግሎት ማቅረብ የሚችል መሆን እንዳለበትም በደንቡ ላይ ሰፍሯል።

🔴 ዝርዝርን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15786/

@EthiopiaInsiderNews


የትግራይ ሲቪል ማህበረሰብ ማህበራት ህብረት የክልሉ አስተዳደር አዲስ ካቢኔ ያዋቀረበትን መንገድ ተቸ  

የትግራይ ሲቪል ማህበረሰብ ማህበራት ህብረት አዲሱ የክልሉ የጊዜያዊ አስተዳደር ካቢኔ፤ የፕሪቶሪያውን ግጭት በዘላቂነት የማቆም ስምምነት “መሰረት ያደረገ አይደለም” በማለት እርምት እንዲደረግ ጠየቀ። የትግራይ ልማት ማህበር ባለፈው ሳምንት ያደረገው ጉባኤ “ፖለቲካዊ ውግን እና ቅስቀሳ የታየበት ነው ያለው” ህብረቱ፤ ጉባኤው እንደገና እንዲካሄድ ጥሪ አቅርቧል። 

ሰባ ሁለት የሲቪል ማህበረሰብ ማህበራትን ያቀፈው ህብረቱ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ አቋሙን ያሳወቀው፤ ከትላንት በስቲያ ረቡዕ ሚያዝያ 22፤ 2017 ባወጣው መግለጫ ነው። ህብረቱ በዚሁ መግለጫው “በአሁኑ ጊዜ የትግራይ ፖለቲካዊ ቀውስ ወደ ባሰ ሁኔታ ተሸጋግሮ አሸናፊ እና ተሸናፊ ወደ ሌለበት አደገኛ ሁኔታ ተገብቷል” ብሏል።

ህብረቱ በዚሁ መግለጫው በቅርቡ የተቋቋመው የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ካቢኔ፤ በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት “አቃፊ ሆኖ መመስርት ይገባው” እንደነበር ጠቅሷል። ሆኖም በሌተናል ጄነራል ታደሰ ወረደ የሚመራው ካቢኔ፤ የፌደራል መንግስት በክልሎች ጣልቃ የመግባት አሰራርን ብቻ ተከትሎ የተመሰረተ እና “በጥቂት አካላት የሚመራ” በመሆኑ፤ አካሄዱ “ለቅቡልነት፣ አቃፊነት እና ውጤታማነት እንቅፋት ይሆናል” ሲል ህብረቱ አስገንዝቧል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15781/

@EthiopiaInsiderNews


የውጭ ዜጎች የመሬት እና የንብረት ባለቤት እንዲሆኑ የሚፈቅድ አዋጅ ለፓርላማ ተመራ

የውጭ ዜጎች በኢትዮጵያ ውስጥ የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለቤት ወይም የመሬት ባለይዞታ እንዲሆኑ የሚያስችላቸው የአዋጅ ረቂቅ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተመራ። አዋጁ የተዘጋጀው “የዜጎችን የመሬት ይዞታ የማግኘትና የመጠቀም መብት በማያጣብብ መልኩ” እንደሆነ ተገልጿል።

የውጭ ዜጎች ካፒታላቸውን “በኢትዮጵያ ስራ ላይ እንዲያውሉ ለማበረታታት” የታለመ ነው የተባለለት ይህን የህግ ረቂቅ ለፓርላማ የመራው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ነው። ምክር ቤቱ ዛሬ ሐሙስ ሚያዝያ 23፤ 2017 ዓ.ም ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ፤ የአዋጅ ረቂቁን ጨምሮ በስድስት ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ ማሳለፉን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል።

ኢትዮጵያዊ ያልሆኑ ዜጎች የመሬት እና የንብረት ባለቤት እንዲሆኑ የሚያስችላቸው ህጋዊ አሰራር እንዲዘረጋ ከተደረገባቸው ምክንያቶች አንዱ፤ ለኢትዮጵያውያን “የስራ ዕድል ለመፍጠር ትልቅ ጠቀሜታ” ያለው በመሆኑ እንደሆነ ጽህፈት ቤቱ ገልጿል። በኢትዮጵያ የሚታየውን የመኖሪያ ቤት ፍላጎት እና አቅርቦት “ሚዛን ለማስጠበቅ” አዋጁ ጠቀሜታ እንደሚኖረውም ጽህፈት ቤቱ አመልክቷል።

የአዋጅ ረቂቁ የቤት ልማት እና ተደራሽነትን “ይበልጥ ለማነቃቃት” የሚያስችል መሆኑም በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት መግለጫ ላይ ተጠቅሷል። ይህ የህግ ረቂቅ የተላለፈለት የተወካዮች ምክር ቤት፤ የውጭ ባለሃብቶች በሪል ስቴት ልማት ዘርፍ በስፋት እንዲሰማሩ የሚያስችል ሌላ አዋጅ ባለፈው ህዳር ወር መጨረሻ ማጽደቁ አይዘነጋም። 

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15770/

@EthiopiaInsiderNews

20 last posts shown.