Ethiopia Insider


Channel's geo and language: Ethiopia, Amharic


Ethiopia Insider is a digital media that provides news, updates, analysis and features.

Related channels  |  Similar channels

Channel's geo and language
Ethiopia, Amharic
Statistics
Posts filter


ለገዢው ፓርቲ ማጠናከሪያ በመንግስት ተቋማት የሚደረጉ የገንዘብ ማሰባሰቢያዎች “በአስቸኳይ እንዲቆሙ” ኢዜማ ጠየቀ

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ከመንግስት ተቋማት አገልግሎት ጋር በተያያዘ ለገዢው ብልጽግና ፓርቲ ማጠናከሪያ የሚደረግ የገንዘብ ማሰባሰቢያ “በአስቸኳይ ያስቆም” ዘንድ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጥያቄ አቀረበ። ምርጫ ቦርድ በገዢው ፓርቲ ላይ የሚወስደውን የወሰደውን “የእርምት እርምጃ” ለህዝብ “በግልጽ እንዲያሳውቅም” ፓርቲው ጠይቋል።

ኢዜማ ዛሬ ማክሰኞ መጋቢት 2፤ 2017 ባወጣው መግለጫ፤ ብልጽግና ፓርቲ ባለፈው ጥር ወር መጨረሻ ባካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ካሳለፋቸው ውሳኔዎች አንዱ “ፓርቲውን ማጠናከር” እንደነበር አስታውሷል።

ይህን ተከትሎም ዜጎች “በውድም ሆነ በግድ የፓርቲ ማጠናከሪያ እንዲያዋጡ እየተደረገ” መሆኑን ኢዜማ “ባሰባሰባቸው ማስረጃዎች” ለማወቅ መቻሉን ገልጿል።

በማንኛውም ፓርቲ ያልታቀዱ ግለሰቦች፤ ብልጽግና ፓርቲን ጨምሮ “ለየትኛውም ድርጅት እና በፈቃደኝት የፈለጉትን ድጋፍ የማድረግ መብት እንዳላቸው” እንደሚገነዘብ ኢዜማ አመልክቷል።

ሆኖም ለገዢው ፓርቲ የማጠናከሪያ ገንዘብ እንዲያወጡ እየተገደዱ ያሉት ዜጎች “በተለያዩ የመንግስት ተቋማት ጉዳዮችን ለማስፈጸም በሚንቀሳቀሱበት” ወቅት እንደሆነ ኢዜማ በመግለጫው አብራርቷል።

“ዜጎች አገልግሎት ለማግኘት በሚሄዱባቸው የመንግስታዊ ተቋማት ይህን ተግባር መፈጸም በፍጹም ህገወጥ ተግባር ነው” ሲልም ተቃዋሚ ፓርቲው ነቅፏል።

ብልጽግና ፓርቲ አባላቱ ካልሆኑ ዜጎች “ከመንግሥት ተቋማት አገልግሎት ጋር አያይዞ መዋጮ ማሰባሰብ ምንም ዓይነት የህግም ሆነ የሞራል መሰረት የለውም” ሲልም ተችቷል።

🔴ለዝርዝሩ ➡️
https://ethiopiainsider.com/2025/15356/

@EthiopiaInsiderNews


ሶስት ከፍተኛ የትግራይ ሰራዊት አዛዦች በአቶ ጌታቸው ረዳ ከስራ ታገዱ

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፤ በሶስት የትግራይ ሰራዊት አዛዦች ላይ የስራ እግድ ውሳኔ አስተላለፉ። ፕሬዝዳንቱ ከዛሬ ሰኞ መጋቢት 1፤ 2017 ጀምሮ ከስራ ያገዷቸው ከፍተኛ የጦር መኮንኖች፤ ሜጀር ጄነራል ዮሐንስ ወልደጊዮርጊስ፣ ሜጀር ጄነራ ማሾ በየነ እና ብርጋዴር ጄነራል ምግበይ ኃይለ ናቸው።

አቶ ጌታቸው የእግድ ውሳኔውን ለጦር አዛዦቹ ያሳወቁት፤ ለእያንዳንዳቸው በዛሬው ዕለት በጻፉት ደብዳቤ ነው። ፕሬዝዳንቱ በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ምክትላቸው የሆኑት ሌተናል ጄነራል ታደሰ ወረደንም ጉዳዮን እንዲያውቁት በደብዳቤው ግልባጭ ላይ አካትተዋቸዋል።

ደብዳቤው የሰላም እና ጸጥታ ካቤኔ ሴክሬተሪያት ኃላፊ ከሆኑት ሌተና ጄነራል ታደሰ በተጨማሪ ለጊዜያዊ አስተዳደሩ ሰላም እና ጸጥታ ቢሮም ግልባጭ ተደርጓል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

[በዚህ ዘገባ ላይ ተጨማሪ መረጃ ይታከልበታል]

@EthiopiaInsiderNews


በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሕገ መንግስት ማሻሻያ ላይ አቤቱታ ያቀረቡ የክልል ምክር ቤት አባል ታሰሩ 

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት የቦሮ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ቦዴፓ) ተመራጭ የሆኑት አቶ ዮሐንስ ተሰማ ዛሬ እሁድ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ተኩል ገደማ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ባለቤታቸው እና የፓርቲው ምንጮች ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ገለጹ። አቶ ዮሐንስ በቁጥጥር ስር ከመዋላቸው አስቀድሞ፤ “የጉዞ እግድ እንደተጣለባቸው” ተነግሯቸው ከአሶሳ አየር ማረፊያ እንዲመለሱ መደረጋቸውንም ምንጮቹ ተናግረዋል።

አቶ ዮሐንስ ዛሬ ጠዋት በአሶሳ አየር ማረፊያ የተገኙት፤ ጽህፈት ቤቱ በአዲስ አበባ ለሆነው ለፌደራል የሕገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ያስገቡትን አቤቱታ በአካል እንዲያስረዱ በመጠራታቸው እንደሆነ ምንጮቹ አስረድተዋል። ለአጣሪ ጉባኤው የቀረበው አቤቱታ፤ ከአቶ ዮሐንስ በተጨማሪ አቶ አመንቴ ገሺ እና አቶ ተስፋሁን ኪሉ የተባሉ የቦዴፓ የክልል ምክር ቤት ተመራጮችን ስም የያዘ ነው።

አቤቱታው ከሁለት ሳምንት በፊት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ምክር ቤት በአብላጫ ድምጽ የጸደቀውን የክልሉ ህገ መንግስት ማሻሻያ የተመለከተ ነው። የህገ መንግስት ማሻሻያው “የኢፌዲሪን ህገ መንግስት የሚቃረን ነው” ሲሉ በአቤቱታቸው የጠቀሱት፤ ሶስቱ የክልል ምክር ቤት አባላት አጣሪ ጉባኤው የህገ መንግስት ትርጓሜ በመስጠት “ተፈጻሚ እንዳይሆን” እንዲያደርግ ጠይቀው ነበር። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15303/

@EthiopiaInsiderNews


የመከላከያ አቅሞችን የምናጎለብተው “ለመዋጋት አይደለም” – ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ 

ኢትዮጵያ የመከላከያ አቅሟን የምታጎለብተው “ትናንሽ አቅም ይዘው ለሚሳሳቱ ኃይሎች ብዙ ጊዜ [ሰጥተው] እንዲያስቡ ለማስቻል” እንደሆነ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ “እነዚህን አቅሞች የምናጎለብተው ለመዋጋት አይደለም። ውጊያን ለማስቀረት ነው” ብለዋል።

አብይ ይህን ያሉት “ስካይ ዊን ኤሮኖቲክስ ኢንዱስትሪ” የተባለ የሰው አልባ አውሮፕላኖች (ድሮኖች) ማምረቻ ትላንት ቅዳሜ የካቲት 29፤ 2017 በመረቁበት ወቅት በሰጡት ገለጻ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለወታደራዊ አገልግሎት የሚውሉ ምርቶችን በሚያመርቱ ፋብሪካዎች ተገኝተው ማብራሪያ ሲሰጡ፤ የትላንቱ በአንድ ሳምንት ውስጥ ለሁለተኛ ጊዜ ነው።

ባለፈው ረቡዕ በኦሮሚያ ክልል አምቦ ከተማ አቅራቢያ የሚገኘውን የሆሚቾ ጥይት ፋብሪካ የጎበኙት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ፤ ኢትዮጵያ ከወታደራዊ ግብዓት አንጻር የነበረባትን “ውስንነት ከሞላ ጎደል ፈትታለች” ብለው ነበር። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፋብሪካ ጉብኝትም ሆነ ያቀረቡት ገለጻ፤ ኢትዮጵያ “ከኤርትራ ጋር ወደ ሌላ ዙር ጦርነት ለመግባት በዝግጅት ላይ ለመሆኗ ማሳያ” አድርገው የቆጠሩ ወገኖች አሉ።

ይህን አመለካከት የተረዱ የሚመስሉት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በትላንቱ ገለጻቸው፤ “እነዚህን አቅሞች የምናጎለብተው ለመዋጋት አይደለም። ውጊያን ለማስቀረት ነው። ትናንሽ አቅም ይዘው ለሚሳሳቱ ኃይሎች፤ ብዙ ጊዜ [ሰጥተው] እንዲያስቡ ለማስቻል ነው። ውጊያን ለማስቀረት (deter) ለማድረግ ከፍተኛ አቅም ስላለው ነው” ሲሉ ተደምጠዋል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15295/

@EthiopiaInsiderNews


በትግራይ ክልል የቀድሞ ተዋጊዎችን ወደ መደበኛ ህይወት የመመለስ ሂደት በሚቀጥለው ሳምንት እንደገና ሊጀመር ነው

በትግራይ ክልል “በአንዳንድ ቴክኒካዊ እና ፖለቲካዊ ምክንያቶች ተቋርጦ” ነበር የተባለው የቀድሞ ተዋጊዎችን ትጥቅ አስፈትቶ በማሰልጠን ወደ ማህበረሰቡ የመቀላቀል ሂደት፤ “በሚቀጥሉት ጥቂት ቀናት እንደገና እንደሚጀምር” የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን አስታወቀ። ሂደቱ ዳግም የሚጀመረው፤ በመቐለ እና በዕዳጋ ሀሙስ በሚገኙ ማዕከላት ነው። 

የቀድሞ ተዋጊዎችን ወደ መደበኛ ህይወት የመመለስ ሂደት እንደገና እንደሚጀመር የተገለጸው፤ የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር ብርጋዴየር ጄነራል ደርቤ መኩሪያው ዛሬ በመቐለ ከተማ ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ምክትል ፕሬዝዳንት ሌተናል  ጀነራል ታደሰ ወረደ ጋር ከተነጋገሩ በኋላ ነው። 

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የሰላም እና ጸጥታ ካቤኔ ሴክሬተሪያት ኃላፊ የሆኑት ሌተናል ጄነራል ታደሰ፤ ለሂደቱ መሳካት ክልሉ “አስፈላጊውን ድጋፍ እና ትብብር” እንደሚያደርግ መግለጻቸውን ኮሚሽኑ በዛሬው ዕለት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

ባለፈው ህዳር ወር ተጀምሮ የነበረው ይህ ሂደት፤ “የቀድሞ ተዋጊዎችን የማረጋገጥ፣ ዲሞቢላይዝ የማድረግ፣ የመመዝገብ እና የተሃድሶ ስልጠና በመስጠት ወደ ማህበረሰቡ የመቀላቀል” ስራዎችን ያካትታል።

🔴 ሙሉ ዘገባውን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15287/

@EthiopiaInsiderNews


ቪዲዮ፦ በአርሲ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ጥር 29፤ 2017 የተቀሰቀሰው የእሳት አደጋ እስከ ዛሬ ቅዳሜ የካቲት 29 በቁጥጥር ስር አለመዋሉን የፓርኩ ጽህፈት ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ መሀመድ ቲፎ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል። ለእሳት ቃጠሎው መከሰት መንስኤ ናቸው ተብለው የተጠረጠሩ ግለሰቦች ተይዘው ጉዳያቸው በህግ አግባብ እየታየ መሆኑንም አስታውቀዋል።

በኦሮሚያ ክልል ከሚገኙት ስድስት ፓርኮች ውስጥ አንዱ የሆነው የአርሲ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ፤ በኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ የሚገኙት የምኒልክ ድኩላ፣ የደጋ አጋዘን፣ ቀይ ቀበሮ እንዲሁም የሌሎች እንስሳት መኖሪያ ነው። በ2003 ዓ.ም በብሔራዊ ደረጃ የተመዘገበው ፓርኩ፤ 84,100 ሄክታር የሚሸፍን ቦታን የሚያካልል ነው።

በፓርኩ የእሳት አደጋ ሲቀሰቀስ በዚህ አመት ብቻ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። ከጥር 9 እስከ ጥር 22 በቆየ የእሳት ቃጠሎ አደጋ፤ ከ200 ሄክታር በላይ የፓርኩ ክፍል መቃጠሉን አቶ መሀመድ ገልጸዋል። እስካሁን ሙሉ ለሙሉ ባልጠፋው የእሳት ቃጠሎ ጉዳት የደረሰበት የፓርኩ ክፍል ምን ያህል እንደሆነ በወል እንደማይታወቅም አመልክተዋል።

🔴የአርሲ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ጽህፈት ቤት ኃላፊ እና የእሳት ቃጠሎው የተነሳበት የጢቾ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የሰጡትን አጭር ቃለ ምልልስ ይህን ሊንክ https://youtu.be/XUqweudgk90 ተጭነው ያድምጡ። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

@EthiopiaInsiderNews


በትግራይ “ከመንግስት እውቅና ውጪ” የሚደረግ የሰራዊት እንቅስቃሴ “በአስቸኳይ” እንዲቆም አቶ ጌታቸው ረዳ አሳሰቡ

በትግራይ ክልል “ከመንግስት እውቅና ውጪ” የሚደረግ የሰራዊት እንቅስቃሴ “በአስቸኳይ እንዲቆም” የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ ትዕዛዝ ሰጡ። ይህን ትዕዛዝ ቸል በሚሉ አካላት ላይ “አስቸኳይ” “የእርምት እርምጃ” እንዲወሰድም አሳስበዋል።

አቶ ጌታቸው ይህን ማሳሰቢያ የሰጡት በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ምክትል ፕሬዝዳንት እና የሰላም እና ጸጥታ ካቤኔ ሴክሬተሪያት ኃላፊ ለሆኑት ሌተናል ጄነራል ታደሰ ወረደ በጻፉት ደብዳቤ ነው።

ከሁለት ቀናት በፊት የተጻፈው ይህ ደብዳቤ፤ በጊዜያዊ አስተዳደሩ ስር በሚተዳደረው “ድምጺ ወያነ” ቴሌቪዥን ጣቢያ በኩል ይፋ የተደረገው በዛሬው ዕለት ነው።

“ህገወጥ እንቅስቃሴዎች እንዲቆሙ ስለማሳሰብ” በሚል ርዕስ ስር የተጻፈው ይህ ደብዳቤ፤ “ህገ ወጥ ጉባኤ ያደረገው” በሚል የሚጠራውን ቡድን “ስልጣን ለማግኘት እንቅስቃሴ” እያደረገ እንደሆነ ይወነጅላል።

አቶ ጌታቸው የቡድኑን ማንነት በደብዳቤያቸው በግልጽ ባያስቀምጡም፤ ከዚህ ቀደም ባወጧቸው መግለጫዎች በዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል የሚመራ ስብስብ የህወሓትን “ህገ ወጥ ጠቅላላ ጉባኤ አድርጓል” በማለት ሲተቹ ቆይተዋል።

ይህ ቡድን “የሰራዊት አመራሮች ውሳኔ” በሚል ጀምሮታል ያሉትን “ህገ ወጥ እንቅስቃሴ እንዲያቆም” የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ካቢኔ መወሰኑን አቶ ጌታቸው በደብዳቤያቸው አስታውሰዋል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15283/

@EthiopiaInsiderNews


በአዲስ አበባ ከተማ 18 ሄክታር መሬት ለሊዝ ጨረታ ሊቀርብ ነው

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መሬት ልማት እና አስተዳደር ቢሮ፤ በጥቅሉ 18 ሄክታር ስፋት ያላቸውን 427 ቦታዎች ለሊዝ ጨረታ ሊያቀርብ ነው።

በመዲናይቱ ዘጠኝ ክፍለ ከተሞች የሚገኙት እነዚህ ቦታዎች፤ ለመኖሪያ እና ለንግድ አገልግሎት የሚውሉ መሆናቸው ተገልጿል።

በከተማይቱ የመሬት ልማት እና አስተዳደር ቢሮ የመሬት ዝግጅት እና ባንክ ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ ሀብታሙ ተስፋዬ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” እንደተናገሩት፤ ለጨረታ የሚቀርቡት ቦታዎች “በተለያየ አግባብ ወደ መሬት ባንክ የገቡ ይዞታዎች” ናቸው።

በአሁኑ ዙር ጨረታ በቦሌ እና ልደታ ክፍለ ከተሞች የሚገኙ የመሬት ይዞታዎች እንዳልተካተቱ ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።

ለጨረታ የሚቀርቡት ቦታዎች ዝርዝር፤ በነገው ዕለት ታትሞ በሚወጣው “አዲስ ልሳን” ጋዜጣ ማግኘት እንደሚቻል የአዲስ አበባ ከተማ የመሬት ልማት እና አስተዳደር ቢሮ በዛሬው ዕለት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

ይህንን ተከትሎ የጨረታ ሰነድ ሽያጩ “ከእጅ ንኪኪ በጸዳ መልኩ” ከመጪው ሰኞ መጋቢት 1 እስከ መጋቢት 12 ድረስ ባሉት ቀናቶች የሚከናወን መሆኑንም ጠቁሟል። 

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15278/

@EthiopiaInsiderNews


የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ በመንፈቅ ዓመት ውስጥ ከ6.4 ቢሊዮን ብር በላይ የግብር ዕዳ መሰብሰቡን ገለጸ 

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ ብቻ ከ6.4 ቢሊዮን ብር በላይ የግብር ዕዳ መሰብሰቡን አስታወቀ። ቢሮው ያለባቸውን “ከ3.2 ቢሊዮን ብር በላይ የግብር ዕዳ ለመክፈል ፈቃደኛ አልሆኑም” ያላቸውን 62 ግለሰቦች ሀገር እንዳይወጡ ለኢሚግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት ስም ዝርዝራቸውን ማስተላለፉን ገልጿል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ2017 በጀት ዓመት ለመሰብሰብ ያቀደው ጠቅላላ የገቢ መጠን 230 ቢሊዮን ብር ነው።

የከተማ አስተዳደሩ በዘንድሮው በጀት ዓመት ከታክስ ገቢዎች ለማግኘት ያቀደው 150.1 ቢሊዮን ብር ሲሆን፤ እስከ መንፈቅ ዓመት 111.5 ቢሊዮን ብር ማግኘት መቻሉን ከሁለት ሳምንት በፊት በተካሄደው የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ ላይ ይፋ ተደርጓል።

የከተማይቱ ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ በዚሁ ጉባኤ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት፤ የከተማይቱ አስተዳደር “የታክስ መሰረትን በማስፋት” እንዲሁም “ብክነት እና ብልሹ አሰራርን በመከላከል” የገቢ መጠኑን ማሳደግ መቻሉን ገልጸው ነበር።

ከንቲባዋ ለዚህ በማሳያነት የጠቀሱት፤ ለግብር ስረዛ የቀረቡ ዶክመንቶች ላይ ባለፉት ስድስት ወራት በተደረገ ፍተሻ “10 ቢሊዮን ብር ማዳን መቻሉን” ነው።

የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ ዛሬ ሐሙስ የካቲት 27፤ 2017 በይፋዊ የፌስ ቡክ ገጹ ባወጣው መረጃ፤ ባለፈው መንፈቅ ዓመት ውስጥ ከ6.4 ቢሊዮን ብር በላይ የግብር ዕዳ መሰብሰቡን ገልጿል።

🔴ሙሉ ዘገባውን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15272/

@EthiopiaInsiderNews


የቀድሞው የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ በሁለት ክሶች ጥፋተኛ ተባሉ 

የቀድሞው የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጸጋዬ ቱኬ፤ በሀዋሳ ከተማ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በቀረቡባቸው ሁለት ክሶች ጥፋተኛ ተባሉ። ፍርድ ቤቱ ትላንት ረቡዕ የካቲት 26፤ 2017 በዋለው ችሎት፤ በተመሳሳይ የክስ መዝገብ የተከሰሱ ሌሎች አራት ተከሳሾች ላይም የጥፋተኝነት ውሳኔ አስተላልፏል።

ፍርድ ቤቱ በተከሳሾቹ ላይ ያስተላለፈው የጥፋተኝነት ውሳኔ፤ “ስልጣንን ያለአግባብ በመገልገል”፣ “የመንግስትን ስራ በማያመች ሁኔታ በመምራት”፣ “የማይገባ ጥቅም በማግኘት ጉቦ በማቀባበል” እና “የሀሰተኛ ሰነድ በማዘጋጀት” የሙስና ወንጀል ነው። የሲዳማ ክልል ዐቃቤ ህግ፤ የቀድሞውን ከንቲባ ጨምሮ በአራት ተከሳሾች ላይ ክስ የመሰረተው ባለፈው ዓመት ሚያዝያ ወር ነበር።

ከአቶ ጸጋዬ ጋር በአንድ መዝገብ ክስ ከቀረበባቸው ውስጥ የቀድሞው ከንቲባ ሚስት አባት የሆኑት አቶ ተሰማ ዳንጉሼ ይገኙበታል። የሀዋሳ ከተማ ኮንስትራክሽን እና ቤቶች ልማት መምሪያ ምክትል ኃላፊ የነበሩት አቶ ታሪኩ ታመነ ሌላኛው ተከሳሽ ሲሆኑ፤ እርሳቸው በሚመሩት ቢሮ ውስጥ መሀንዲሶች የነበሩት አቶ ታፈሰ ቱናሻ እና አቶ ሰይፉ ደሌሳም በዚሁ የክስ መዝገብ ስር ተካትተዋል።

የቀድሞው የቢሮ ምክትል ኃላፊ እና ሁለቱ መሀንዲሶች ላይ የክልሉ ዐቃቤ ህግ ክስ ያቀረበው፤ በከተማ ተቋማዊነት እና መሰረተ ልማት ፕሮግራም (urban institutional and infrastructure development program) ስር ሲከናወኑ ከቆዩ አራት ፕሮጀክቶች ጋር በተያያዘ ነው።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15267/

@EthiopiaInsiderNews


ኢትዮጵያ በሩብ ዓመት ውስጥ ብቻ ከጥይት ሽያጭ 30 ሚሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ ማግኘቷን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ተናገሩ

ኢትዮጵያ ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ ለውጭ ሀገራት ከሸጠቻቸው ጥይቶች፤ “ከ30 ሚሊዮን ዶላር ያላነሰ” ገቢ ማግኘቷን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ተናገሩ። ሀገሪቱ ለውጭ ሀገር ገበያ የሚቀርቡ ክላሽ፣ ስናይፐር፣ ብሬን፣ ዲሽቃ፣ ታንክ እና ሁሉንም አይነት መድፎች “የማምረት አቅም ያለው” ፋብሪካ መገንባቷንም አብይ አስታውቀዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ይህን ያሉት፤ በኦሮሚያ ክልል፣ ምዕራብ ሸዋ ዞን፣ በቶኬ ኩታዬ ወረዳ የሚገኘውን የሆሚቾ ጥይት ፋብሪካ ትላንት ረቡዕ የካቲት 26፤ 2017 በጎበኙበት ወቅት ነው።

አብይ በዚሁ ወቅት በሰጡት ገለጻ፤ ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያ ውስጥ “በተወሰነ ደረጃ” ጥይት እና መሳሪያ “የማምረት ሙከራዎች” እንደነበሩ አስታውሰዋል።

በ2015 ዓ.ም በአምቦ ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው የሆሚቾ አሙኔሽን ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ውስጥ ተከላው የተጀመረው ዘመናዊ ፋብሪካ፤ “ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ” ጥይቶችን እና የተለያዩ አይነት የጦር መሳሪያዎችን ወደ ማምረት መሸጋገሩን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ጊዜ ይፋ አድርገዋል።

በ2014 ዓ.ም “ጥይት እንገዛ ነበር” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ፤ “እነዚህን አይነት ነገሮች ከመግዛት ወጥተን፣ አምርተን፣ ለሌሎች የምንሸጥ ሀገር መሆናችን እና በጣም በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሄ አቅም ተገንብቶ በማየቴ በጣም ከፍተኛ ክብር እና ደስታ ይሰማኛል” ሲሉ ስሜታቸውን አጋርተዋል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15258/

@EthiopiaInsiderNews


የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ያሻሻለው ህገ መንግስት “ተፈጻሚ እንዳይሆን”፤ ለሕገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ አቤቱታ ቀረበ 

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት የዛሬ ሁለት ሳምንት ባካሄደው መደበኛ ጉባኤው ላይ ያጸደቀው የክልሉ ህገ መንግስት ማሻሻያ፤ “የኢፌዲሪን ህገ መንግስት የሚቃረን ነው” ያሉ የተቃዋሚ ፓርቲ የምክር ቤት አባላት “ተፈጻሚ እንዳይሆን” አቤቱታ አቀረቡ።

የምክር ቤት አባላቱ አቤቱታቸውን ያቀረቡት ለፌደራል የሕገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ነው። የሕገ መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ፤ በተለያዩ አካላት የሚቀርቡለትን ሕገ መንግስታዊ ጉዳዮችን የማጣራት ስልጣን ያለው ነው።

ጉባኤው በሚያደርገው ማጣራት መሰረት ህገ መንግስቱን መተርጎም አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ለፌደሬሽን ምክር ቤት የውሳኔ ሃሳብ ያቀርባል። አጣሪ ጉባኤው፤ በተሻሻለው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ህገ መንግስት ላይ ትርጓሜ የሚጠይቅ አቤቱታ እንደቀረበለት ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” አረጋግጧል።

ይህን አቤቱታ በትላንትናው ዕለት ያቀረቡት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት የቦሮ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ቦዴፓ) ተመራጭ የሆኑት አቶ አመንቴ ገሺ፣ አቶ ዮሐንስ ተሰማ እና ተስፋሁን ኪሉ ናቸው። ሶስቱ የቦዴፓ የክልል ምክር ቤት ተመራጮች የህገ መንግስት ትርጉም ከጠየቁባቸው ጉዳዮች ውስጥ፤ የክልሉን ምክር ቤት መቀመጫ ቁጥር ማደግን የተመለከተው ይገኝበታል።

በ1995 ዓ.ም የወጣው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ህገ መንግስት፤ የክልሉ ምክር ቤት አባላት ቁጥር ከ100 እንደማይበልጥ ይደነግጋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት የካቲት 11 ባካሄደው መደበኛ ጉባኤው፤ የመቀመጫ ብዛቱን ከ99 ወደ 165 ከፍ አድርጓል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15236/

@EthiopiaInsiderNews


በሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ላይ ተጥሎ የነበረው እገዳ ተነሳ

የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን “ህግን ተላልፈው ተገኝተዋል” በሚል በሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ላይ ጥሎት የነበረውን የእግድ እርምጃ’፤ “ማስጠንቀቂያ” በመስጠት ከዛሬ ጀምሮ ማንሳቱን አስታወቀ። ባለስልጣኑ እገዳውን ያነሳው፤ ከታገዱት ድርጅቶች ጋር ባደረገው ውይይት “በተፈጠረ መግባባት” እና የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ያቀረበውን ምክረ ሃሳብ ከግምት ውስጥ በማስገባት እንደሆነ አስታውቋል።

ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የዛሬውን ውሳኔ ያስተላለፈው “በታገዱት ሁሉም ድርጅቶች” ላይ መሆኑን ዛሬ ሰኞ የካቲት 24፤ 2017 ባወጣው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል። ተቆጣጣሪ መስሪያ ቤቱ ባለፈው መንፈቅ ዓመት ብቻ በሰባት ድርጅቶች ላይ የእግድ ውሳኔ ማስተላለፉን ባለፈው ጥር ወር መጨረሻ በፓርላማ በተካሄደው የቋሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ መግለጹ ይታወሳል።

በዚሁ ጊዜ ውስጥ ከታገዱት መካከል አራቱ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ናቸው። “ከተቋቋሙበት ዓላማ ውጭ ተንቀሳቅሰዋል” በሚል ባለፈው ታህሳስ ወር አጋማሽ የታገዱት እነዚህ ድርጅቶች፤ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ)፣ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ማዕከል (EHRDC)፣ የመብቶች እና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል (CARD) እና የሕግ ባለሙያዎች ለሰብአዊ መብቶች (LHR) ናቸው። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ▶️ https://ethiopiainsider.com/2025/15215/

@EthiopiaInsiderNews


ከአዲግራት ከተማ አቅራቢያ በሬክተር ስኬል 5.2 የተለካ ርዕደ መሬት ተከሰተ

ዛሬ እሁድ ከአዲግራት ከተማ 46 ኪሎ ሜትር በስተምስራቅ ርቀት ላይ በሚገኝ አካባቢ ላይ በሬክተር ስኬል 5.2 የተለካ የመሬት መንቀጥቀጥ መከሰቱን የአሜሪካ የጂኦሎጂካል ሰርቬይ መስሪያ ቤት ገለጸ። ርዕደ መሬቱ የተከሰተው ከቀኑ 5 ሰዓት ከ14 ደቂቃ ላይ መሆኑንም መስሪያ ቤቱ አስታውቋል።

በኢትዮጵያ በአፋር ክልል ባሉ አካባቢዎች ካለፈው መስከረም ወር ጀምሮ ተደጋጋሚ የመሬት መንቀጥቀጥ ቢከሰትም፤ በትግራይ ክልል ከተሞች አቅራቢያ ርዕደ መሬት ሲመዘገብ ግን በዚህ ዓመት የመጀመሪያው ነው። የዛሬው የመሬት መንቀጥቀጥ በኢትዮጵያ እና ኤርትራ ድንበር ቀጠና የተከሰተ መሆኑን የጠቆመው የአውሮፓ ሜዲትራንያን ሴይስሞሎጂ ማዕከል (EMSC)፤ መጠኑም በሬክተር ስኬል 5.3 የተለካ እንደሆነ አስታውቋል።

በኤርትራ ከአንድ ሳምንት በፊት የደረሰ ርዕደ መሬት በሬክተር ስኬል 4.6 ሆኖ ተመዝግቧል። የመሬት መንቀጥቀጡ የተከሰተው በቀይ ባህር ሰሜናዊ አቅጣጫ ከአስመራ 24 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ባለ አካባቢ ነበር። በሀገሪቱ ባለፈው ታህሳስ ወር አጋማሽም እንዲሁ ተመሳሳይ ርዕደ መሬት ተመዝግቧል።

በሐምሌ 2015 ዓ.ም. በኤርትራ ባህር ዳርቻ ዳህላክ ደሴት አካባቢ የተከሰተው የመሬት መንቀጥቀጥ፤ በትግራይ ክልል የተለያዩ ከተሞች ተደጋጋሚ ንዝረቶች አስከትሎ እንደነበር ይታወሳል። ንዝረቱን በሽሬ፣ አዲግራት፣ አድዋ፣ አክሱም እና መቐለ ከተማ ያሉ ነዋሪዎች መስማታቸውን በወቅቱ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ገልጸው ነበር። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

@EthiopiaInsiderNews


ወንዞችን በቆሻሻ የሚበክሉ ግለሰቦችን እና ተቋማትን እስከ አንድ ሚሊዮን ብር የሚያስቀጣ ደንብ ተግባራዊ ሊደረግ ነው

በአዲስ አበባ ከተማ ያሉ ወንዞችን፤ በባህሪያቸው “አደገኛነት” ባላቸው ደረቅም ይሁን ፈሳሽ ቆሻሻ የሚበክሉ ድርጅቶችን አንድ ሚሊዮን ብር ቅጣት የሚጥል ደንብ ተግባራዊ ሊደረግ ነው።

ከመኖሪያ ቤቶች የሽንት ቤት አሊያም ማንኛውንም ያልተጣራ ፍሳሽ ቆሻሻ ወደ ወንዝ መልቀቅ እስከ 300 ሺህ ብር እንደሚያስቀጣ ደንቡ ይደነግጋል። የወንዞችን ብክለት ለመከላከል የሚያስችለውን ይህ ደንብ የጸደቀው፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ ባለፈው ታህሳስ ወር ባደረገው ስብሰባ ላይ ነው።

በደንቡ ላይ የሰፈሩ ድንጋጌዎች ከታህሳስ 2፤ 2017 ጀምሮ ተፈጻሚ እንደሚሆኑ በሰነዱ ላይ ቢገልጽም፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ደንብ ማስከበር ባለስልጣን በዚህ መሰረት ገና መቅጣት አለመጀመሩን የመስሪያ ቤቱ ስራ አስኪያጅ ሻለቃ ዘሪሁን ተፈራ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።

ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ከከተማይቱ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን እና የውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ጋር በመሆን፤ ደንቡን የተመለከተ ስልጠና እና የግንዛቤ ማስጨበጫ በትላንትናው እና በዛሬው ዕለት አካሄዷል።

ስልጠናው የተመረኮዘበት “የወንዞች ዳርቻ ልማት እና ብክለት መከላከል ደንብ”፤ በሰባት ክፍሎች እና በ21 አንቀጾች የተከፋፈለ ነው። በደንቡ መጨረሻ በአባሪነት የተካተተው ሰንጠረዥ፤ በወንዝ እና በወንዝ ዳርቻ ላይ ብክለት በሚፈጸሙ ድርጅቶች እና ግለሰቦች ላይ የሚጣሉ አስተዳደራዊ የገንዘብ ቅጣቶችን ዘርዝሯል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15201/

@EthiopiaInsiderNews


በኢትዮጵያ ከሚከሰተው የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ የ47 በመቶው መንስኤ “ዛፎች የሚፈጥሩት ንክኪ ነው” ተባለ 

በኢትዮጵያ በተለያዩ አካባቢዎች ለሚከሰት የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ 47 በመቶ የሚሆነውን ድርሻ የሚይዘው፤ ዛፎች እና ቅርንጫፎች በኤሌክትሪክ መስመሮች ላይ የሚፈጥሩት ንኪኪ መሆኑ ተገለጸ።

በመሰረተ ልማት ላይ የሚደርሱ ስርቆቶች እና ጉዳቶች የኃይል መቆራረጥ እንዲከሰት የሚያደርጉ ሌሎች ዋነኛ ምክንያቶች መሆናቸውንም ተነግሯል።

ይህ የተገለጸው፤ የኤሌክትሪክ ኃይል ማከፋፈያ መስመሮችን የማስተዳደር እና የኤሌክትሪክ ኃይልን በጅምላ ገዝቶ ለደንበኞች የመሸጥ ኃላፊነት ያለፈበት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት፤ ዛሬ ሐሙስ የካቲት 20፤ 2017 በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የኃይል አቅርቦት እና ጥራትን ለማሻሻል በአጭር ጊዜ ለመተግበር ካቀዳቸው ተግባራት መካከል፤ በኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ውስጥ የገቡ ዛፎች እና ቅርንጫፎችን መቁረጥ አንዱ እንደሆነ የተቋሙ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ጌቱ ገረመው በዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል።

በኤሌክትሪክ መስመሮች ላይ አደጋ የሚፈጥሩ ዛፎች እና ቅርንጫፎችን የመቁረጥ ተግባር ከሁለት ወር በፊት እንደተጀመረ የገለጹት አቶ ጌቱ፤ የስራው አፈጻጸም በአዲስ አበባ 50 በመቶ እንዲሁም በሀገር አቀፍ ደረጃ 30 በመቶ እንደደረሰ አስረድተዋል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15194/

@EthiopiaInsiderNews


በመሬት መንቀጥቀጥ “ከፍተኛ ጉዳት” የደረሰበት የከሰም ስኳር ፋብሪካ፤ ሰራተኞቹን በመጪዎቹ ወራት ሊያሰናብት ነው 

ባለፉት ወራት በተደጋጋሚ በተከሰቱ የመሬት መንቀጥቀጦች “ከፍተኛ ጉዳት” የደረሰበት የከሰም ስኳር ፋብሪካ፤ ከአንድ ሺህ በላይ ሰራተኞቹን እስከ መጪው ግንቦት ወር ባለው ጊዜ ውስጥ ለማሰናበት ቅድመ ማስጠንቀቂያ ሰጠ።

የስኳር ፋብሪካው የሰራተኞች ማህበር በበኩሉ ሰራተኞቹ ሳይሰናብቱ ወደ ሌሎች ፋብሪካዎች እንዲበተኑ ለማድረግ ጥረት እያደረገ መሆኑን ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” አስታውቋል።

በስሩ ከአራት ሺህ በላይ ሰራተኞችን የሚያስተዳድረው የከሰም ስኳር ፋብሪካ፤ የቅድመ ማስጠንቀቂያ በመስጠት የሰራተኞቹን የስራ ውል ያቋረጠው ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ የካቲት 11 ዓ.ም ባወጣው ማስታወቂያ ነው።

በፋብሪካው የማስታወቂያ ሰሌዳ ላይ የተለጠፈው እና “ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የተመለከተችው ይህ ማስታወቂያ፤ የስራ ውላቸው የተቋረጠ ከአንድ ሺህ በላይ ሰራተኞችን ስም ዝርዝር የያዘ ነው።

ይኸው ማስታወቂያ፤ ፋብሪካው ከዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው ከታህሳስ 20 ጀምሮ በተደጋጋሚ የተከሰተው ርዕደ መሬት ባስከተለበት “ከፍተኛ ጉዳት” መሆኑን ያስረዳል።

የስኳር ፋብሪካው በዚህ ምክንያት “ስራውን ሙሉ ለሙሉ ያቆመ በመሆኑ”፤ በማስታወቂያው ስማቸው የተዘረዘረ ሰራተኞቹ የስራ ውል ከየካቲት 10፤ 2017 ጀምሮ “በቅደመ ማስጠንቀቂያ” መቋረጡንም አትቷል።

ይሁንና በዚያው ዕለት ፋብሪካው ማስተካከያ በማድረግ በለጠፈው ማስታወቂያ፤ ሰራተኞቹ ከየካቲት 10 ቀን ጀምሮ መሰናበታቸውን በማስቀረት ከዚሁ ቀን ጀምሮ እንደ የአገልግሎት ቆይታቸው ቅድመ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው መሆኑን ገልጿል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15186/

@EthiopiaInsiderNews


በአማራ ክልል ታስረው የነበሩ ሁሉም ዳኞች መለቀቃቸውን የክልሉ የዳኞች ማህበር አስታወቀ 

በአማራ ክልል እስከ ትላንት ድረስ በእስር ላይ የነበሩ ዳኞች ሙሉ ለሙሉ መለቀቃቸውን የአማራ ክልል ዳኞች ማህበር አስታወቀ። ካለፈው ሁለት ወር ወዲህ እስከ አርብ የካቲት 14፤ 2017 ድረስ ባሉት ጊዜያት ከእስር የተለቀቁት ዳኞች ብዛት 36 እንደሆነ የማህበሩ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ብርሃኑ አሰፋ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።

በክልሉ ታስረው የነበሩ ሁሉም ዳኞች መፈታታቸው የተገለጸው፤ የአማራ ክልል ምክር ቤት የዳኞች ያለመከሰስ መብትን ያካተተ የህግ ማሻሻያ ካጸደቀ ከአስር ቀናት በኋላ ነው።

በአማራ በተለያየ እርከን በሚገኙ ፍርድ ቤቶች የሚሰሩ ዳኞች ለእስር ይዳረጉ የነበረው፤ በሚይዟቸው መዝገቦች ላይ በሚሰጧቸው ውሳኔዎች ምክንያት እንደሆነ አቶ ብርሃኑ ገልጸዋል።

“አብዛኞቹ ከስራ ጋር የተገናኘ ነው። ምክንያቱ ‘ዋስትና ጋር ተያይዞ ለምን ፈቀዳችሁ? ለምን ትዕዛዝ ሰጣችሁ? ለምን እግድ ሰጣችሁ?’ [የሚል ነው]። ያው በፍርድ ቤት ዳኞች በህግ የተሰጣቸውን ስልጣን መሰረት አድርገው ሲሰሩ፤ ከአስፈጻሚው ጋር የሚገናኙ አለመግባባቶች ጋር መነሻ በማድረግ የታሰሩ ናቸው” ሲሉ የአማራ ክልል ዳኞች ማህበር ምክትል ፕሬዝዳንት የእስሮቹን መንስኤ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” አብራርተዋል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15176/

@EthiopiaInsiderNews


በኢትዮጵያ በሬክተር ስኬል 5.0 የተለካ የመሬት መንቀጥቀጥ ዛሬ እሁድ ለሊት 8 ሰዓት ከ44 ደቂቃ ላይ መከሰቱን የአውሮፓ ሜዲትራንያን ሴይስሞሎጂ ማዕከል (EMSC) አስታወቀ። ዘለግ ላሉ ሰከንዶች የቆየው የዛሬው የመሬት መንቀጥቀጥ ያስከለው ንዝረት መዲናዋ አዲስ አበባ ድረስ ተሰምቷል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

@EthiopiaInsiderNews


ቪዲዮ፦ የስራ ዘመኑ ለተጨማሪ አንድ ዓመት በፓርላማ የተራዘመለት የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን፤ ወቅታዊ የስራ እንቅስቃሴዎቹን በተመለከተ በዛሬው ዕለት ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥቷል። በጋዜጣዊ መግለጫው ለተገኙ የኮሚሽኑ ኮሚሽነሮች ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች መካከል፤ “በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች መሳሪያ አንግበው ከሚፋለሙ ታጣቂዎች ጋር ንግግር ለማድረግ ሞክራችኋል?” የሚለው ይገኝበታል።

የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ፤ የኮሚሽኑ ዋና አላማ “ሁሉም በምክክር ሂደቱ ላይ ተሳታፊ እንዲሆኑ ነው” ብለዋል። ዋና ኮሚሽነሩ በዚሁ ምላሻቸው ከአንድ የታጣቂ ቡድን አመራር ጋር መነጋገራቸውን፤ ሆኖም ግን “ፋኖ መሆናቸውን እንደማያውቁ” ተናግረዋል።

“አንድ ታጣቂ ቡድን ራሳቸው ደውለውልኝ፤ አነጋግረውኝ ‘የምክክር ኮሚሽኑን ስራ ተገንዝበናል። ገለልተኛ መሆኑን ተገንዝበናል። በዚህ መሰረት ቀጥታ አጀንዳችንን ለእናንተ አቅርበን፤ ወደ ዱር የገባንበትን አጀንዳ ለእናንተ አምጥተን፤ ወደ ውይይት የሚቀርብ ከሆነ መሳሪያችንን ለማስቀመጥ ዝግጁ ነን’ የሚል ጥያቄ በቀጥታ ለእኔ ቀርቦልኛል” ሲሉ ፕሮፌሰር መስፍን ለጋዜጠኞች አስረድተዋል።

ኮሚሽኑ በአማራ ክልል ከሚያደርገው የምክክር ሂደት ጋር በተያያዘም፤ በዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ጥያቄ ቀርቧል። የምክክር ኮሚሽኑ በአማራ ክልል በሚያደርገው እንቅስቃሴ “በህዝቡ ዘንድ ያለው አመኔታ እና ተቀባይነትን ምን ያህል ነው?” ለሚለው ጥያቄ፤ ከአስራ አንዱ የተቋሙ ኮሚሽነሮች አንዱ የሆኑት አቶ መላኩ ወልደማርያም ምላሽ ሰጥተዋል።

🔴 በዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ለተነሱ ጥያቄዎች የተሰጠውን ሙሉ ምላሽ ይህን ሊንክ ተጭነው ይመልከቱ ▶️ https://youtu.be/C5Q9ITR45qk

@EthiopiaInsiderNews

20 last posts shown.