✞✝✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✝✞
❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖
❖ የካቲት 8 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
+✝" በዓለ ስምዖን "✝+
=>ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን ጌታ በተወለደ በ40 ቀኑ ራሱ የሠራውን ሕግ ይፈፅም ዘንድ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቷል::
እንደ ሥርዓቱም እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምና
አገልጋዩዋ ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ የርግብ ግልገሎችና
ዋኖስ አቅርበዋል::
+ለ284 ዓመታት የአዳኙን (የመሢሁን) መምጣት
ይጠብቅ የነበረው አረጋዊው ስምዖን በዚህች ዕለት
ስላየውና ስለታቀፈው
ዕለቱ በዓለ ስምዖን ይባላል:: (ሉቃ. 2:22) ከዘጠኙ
የጌታ ንዑሳን በዓላት አንዱ ነው::
+ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-
+ከዓለም ፍጥረት በ5,200 ዓመታት (ማለትም
ከክርስቶስ ልደት 300 ዓመታት በፊት) በጥሊሞስ
የሚሉት ንጉሥ በግሪክ
ነገሠ::
+በጊዜውም በኃይለኝነቱ ሁሉን አስገብሮት ነበርና
"ዓለሙን እንደ ሰም አቅልጬ: እንደ ገል ቀጥቅጬ
ገዛሁት:: ምን
የቀረኝ ነገር አለ?" ሲል ተናገረ:: ባሮቹም "አንድ ነገር
ቀርቶሃል:: በምድረ እሥራኤል ጥበብን የተሞሉ 46
መጻሕፍት
አሉ:: እነርሱን አስተርጉም" አሉት::
+ያን ጊዜ እሥራኤላውያንን አስገብሯቸው ነበርና 46ቱን
የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ከ72 ምሑራን (ተርጉዋሚዎች)
ጋር
እንዲያመጡለት አዛዦቹን ላከ:: እነርሱም 46ቱን
መጻሕፍተ ብሉይ ኪዳን ከ72 ምሑራን ጋር አመጡለት::
+አይሁድ ክፋተኞች መሆናቸውን ሰምቷልና 36 ድንኩዋን
አዘጋጅቶ: ጥንድ ጥንድ ሆነው እንዲሠሩ: ሲተረጉሙ
እንዳይመካከሩ
36 ጠባቂዎችን ሾመባቸው:: ይህ ነገር ለጊዜው ከንጉሡ
ቢመስልም ጥበቡ ግን ከእግዚአብሔር ነው::
+ምንያቱም በጊዜ ሒደት መጻሕፍተ ብሉያት በአደጋ
እንደሚጠፉ ያውቃልና ሳይበረዙ ለሐዲስ ኪዳን
ክርስቲያኖች ለእኛ
እንዲደርሱ ነው:: ስለዚህም ከክርስቶስ ልደት 284 ዓመት
በፊት 46ቱም ሁሉም መጻሕፍት (ብሉያት) ከእብራይስጥ
ወደ
ጽርዕ ልሳን በ70ው ሊቃናት አማካኝነት ተተረጐሙ::
(በእርግጥ ከዚያ አስቀድሞ መጻሕፍት (ብሉያት) ወደ
ሃገራችን መምጣቸውና ወደ ግዕዝ ልሳን መተርጐማቸውን
ሳንዘነጋ ማለት ነው)
+ወደ ዋናው ጉዳያችን ስንመለስ ከ70ው ሊቃናት
መካከል በእድሜው አረጋዊ የሆነ (እንደ ትውፊቱ ከሆነ
216 ዓመት
የሆነው) ስምዖን የሚሉት ምሑረ ኦሪት ነበር:: በፈቃደ
እግዚአብሔር ለእርሱ መጽሐፈ ትንቢተ ኢሳይያስ ደርሶት
እየተረጐመ
ምዕራፍ 7 ላይ ደረሰ::
+ቁጥር 7 ላይ ሲደርስ ግን "ናሁ ድንግል ትጸንስ:
ወትወልድ ወልደ" የሚል አይቶ "አሁን እንኳን የአሕዛብ
ንጉሥ
የእሥራኤልስ ቢሆን ድንግል በድንግልና ጸንሳ ትወልዳለች
ብለው እንዴት ያምነኛል!" ሲል አሰበ:: "በዚያውስ ላይ
ኢሳይያስ በምናሴ የተገደለው ስለዚህ አይደል!" ብሎ
ቃሉን ሊለውጠው ወሰነ::
+አመሻሽ ላይም 'ድንግል' የሚለውን 'ወለት-ሴት ልጅ'
ብሎ ቀየረው:: እርሱ ሲያንቀላፋ ቅዱስ መልአክ ወርዶ
'ድንግል'
ብሎ አስተካከለው:: ከእንቅልፉ ሲነቃ ግራ ተጋብቶ እንደ
ገና ፍቆ ቀየረው::
+አሁንም መልአኩ 'ድንግል' ሲል ቀየረበት:: 3 ጊዜ
እንዲህ ከሆነ በኋላ ግን መልአኩ ተገልጦ ገሰጸው::
በዚያውም ላይ
"ይህችን ድንግልና መሲሑን ልጇን ሳታየውና ሳትታቀፈው
ሞትን አታይም" ብሎት ተሰወረው:: አረጋዊ ስምዖን
ከዚያች ዕለት
በኋላ የመድኅን ክርስቶስን መምጣት ሲጠብቅ ለ284
ዓመታት የአልጋ ቁራኛ ሁኖ ኖረ:: አካሉም አለቀ::
+ለስም አጠራሩ ስግደት የሚገባው አምላካችን ኢየሱስ
ክርስቶስ ሰው በሆነበት በዚያ ሰሞን እመቤታችን ቅድስት
ድንግል
ማርያምና ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ ወደ ቤተ መቅደስ ወጡ::
+ሕግን የሠራ ጌታ እርሱ 'ፈጻሜ ሕግ' ይባል ዘንድ
የርግብ ግልገሎችን (ዋኖሶችን) ይዘው በተወለደ በ40
ቀኑ ወደ ቤተ
መቅደስ አስገቡት:: በዚህች ቀንም ቅዱስ መልአክ
መጥቶ ቅዱስ ስምዖንን ከአልጋው ቀሰቀሰው:: ተስፋ
የሚያደርገው አዳኙ
(መሲሑ) እንደ መጣም ነገረው::
+ይህን ጊዜ አረጋዊው አካሉ ታድሶ እንደ 30 ዓመት
ወጣት እመር ብሎ ከአልጋው ተነሳ:: እንደ በቅሎ
እየሠገረም ወደ
መቅደስ ወጣ:: በዚያ መሲሑን (ፈጣሪውን) ሲመለከት
እንደ እንቦሳ ዘለለ:: ቀረብ ብሎም ሕጻን ጌታን ከድንግል
እናቱ እጅ ተቀበለው::
+ከደስታው ብዛት የተነሳም "ይእዜ ትስዕሮ ለገብርከ:
በሰላም እግዚኦ በከመ አዘዝከ-አቤቱ ባሪያህን እንደ
ቃልህ በሰላም
አሰናብተው" ሲል ጸለየ:: ትንቢትንም ተናገረ:: በዚያችው
ዕለትም ዐርፎ ተቀበረ::
+"+ ሐና ነቢይት +"+
+ዳግመኛ በዚህች ቀን አረጋዊቷን ነቢይት ቅድስት ሐናን
እናስባለን:: ይህች ቅድስት ትውልዷ ከነገደ አሴር ሲሆን
አባቷ
ፋኑኤል ይባላል:: በትውፊት ትምሕርት ሐና የተዳረችው
በልጅነቷ (በ12 /15/ ዓመቷ) ነው:: ለ7 ዓመታት ከልጅነት ባሏ
ጋር
ኖራ ዕድሜዋ 19 (22) ሲደርስ ሞተባት::
+እንደ እሥራኤል ልማድ ሌላ እንድታገባ ብትጠየቅም
'እንቢ' ብላ መበለት ሆነች:: ራሷንም ለእግዚአብሔር
አሳልፋ
ሰጠች:: በቤተ መቅደስም ለ84 ዓመታት ለፈጣሪዋ
ተገዛች:: ፈጽማ ትጸልይና ትጾም ነበርና በእነዚህ ሁሉ
ዓመታት ውጪውን
አልተመለከተችም::
+ለእርሷ 103 (106) ዓመት ሲሆን መድኃኒታችን ተወለደ::
በዚህች ቀን ወደ ቤተ መቅደስ ሲገባ ተመልክታም ጌታን
ባረከች::
ደስ እያላትም ትንቢትን ተናገረች:: ወደ ቤቷ ገብታም
ነፍሷን ሰጠች:: (ሉቃ. 2:36-38)
❖ቸሩ መድኃኒታችን ተርፎ ከሚቀረው ዘመን ዕድሜ
ለንስሃ: ዘመን ለፍሥሐ አይንሳን:: ከቅዱሳኑ በረከትም
አይለየን::
✞የካቲት 8 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ስምዖን አረጋዊ
2.ቅድስት ሐና ነቢይት (የፋኑኤል ልጅ)
3.ቅድስት ዓመተ ክርስቶስ እግዝእት
4.አባ ኤልያስ ገዳማዊ (በትህትና ያጌጠ ቅዱስ ሰው)
ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ሙሴ ሊቀ ነቢያት
2.ኪሩቤል (አርባዕቱ እንስሳ)
3.አባ ብሶይ (ቢሾይ)
4.አቡነ ኪሮስ
5.አባ ሳሙኤል ዘደብረ ቀልሞን
6.ቅዱስ ማትያስ ሐዋርያ (ከ12ቱ ሐዋርያት)
❖አረጋዊ ስምዖንን ከድካም አልጋ ያነሳ አምላከ ቅዱሳን
እኛንም ድካመ ነፍስን ከሚያመጣ የበደል ምኝታ በቸርነቱ
ያንሳን::
++"+ እንደ ሕጉ ልማድ ያደርጉለት ዘንድ ሕጻኑን ጌታ
ኢየሱስን በአስገቡት ጊዜ እርሱ ደግሞ ተቀብሎ
አቀፈው::
እግዚአብሔርንም እየባረከ እንዲህ አለ:-
'ጌታ ሆይ! አሁን እንደ ቃልህ ባሪያህን በሰላም
ታሰናብተዋለህ:: ዓይኖቼ በሰዎች ሁሉ ፊት ያዘጋጀኸውን
ማዳንህን
አይተዋልና:: ይህም ለአሕዛብ ሁሉን የሚገልጥ ብርሃን:
ለሕዝብሕም ለእስራኤል ክብር ነው::'
ዮሴፍና እናቱም ስለ እርሱ በተባለው ነገር ይደነቁ ነበር::
+"+ (ሉቃ. 2:27)
✞✝✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞✝✞
የፈለገ ጥበብ የዲጂታል ሚዲያን ይቀላቀሉ ለሌሎች ያጋሩ🙏🙏🙏
👉ዩቲዩብ (Youtube)👉ቲክቶክ (Tiktok)👉ኢኒስታግራም (Instagram)👉ፌስቡክ (Facebook)👉ቴሌግራም (Telegram)