Фильтр публикаций


ረመዷን -13
****
በሚስቶች ልፋትና ትዕግሥት የቆሙ ብዙ ቤቶች አሉ። አላህ ምንዳቸውን ያብዛው።
እናት ያልተነሳችበት ቤት ሁሉ ሱሑር የለም።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


አምላኬ ሆይ!
አንተ የለጋሾች ሁሉ ለጋስ፣
የአዛኞች ሁሉ አዛኝ ነህ፡፡
ባንተ ላይ ተስፋ የጣለን ሰው፤
አንተን ያመነና የተማመነን ሰው፤
ባሮችህን ወደ መንገድ የጠራን ሰው፣
በርግጥ
ለቸርነትህ ተገቢ ባይሆንም፣
ባንተና በባሮቹ መካከል ለመገኘት ደረጃው ባይመጥንም ...
ቸርነትህን፣ እዝነትህን አስቧልና ተስፋውን መና አታድርግበት፡፡

አንተ የቸርነትና የልግሥና ባለቤት ነህና፡፡
ቸሩ አምላክ በቸርነቱ ሁሉን ጥፋት ያልፋልና፡፡ 

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ምኞታችን የተለያየ ነው። አምላካችን አንድ አላህ ነው። አላህ ሆይ ተቀበል።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ረመዷን 11
****

እንዲሁም ሰውን አዛ ከማድረግ እንፁም

https://t.me/MuhammedSeidAbx


በፆመ አንጀት ውለው ቅበላህን ለሚሹ ሁሉ፣ በቤትህ ተሰብስበው እዝነትህን ለሚከጅሉ ሁሉ
አላህ ሆይ እዘንላቸው።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


Репост из: Nejashi Printing Press
ረመዷንና ቁርአን
****

ሥራቸውን በሙሉ አላህ ይውደድላቸውና! ቀደምት ደጋግ አባቶቻችን በረመዷን ወር ውስጥ በሶላት ውስጥም ይሁን ከሶላት ውጪ ቁርአን ማንበብ ያበዙ ነበር፡፡

አላህ ይዘንላቸውና! ሸይኽ አዝ-ዙህሪይ የረመዷን ወር ሲገባ፣ ቁርአን አብዝተው የሚቀሩበትና በልግስና የሚያበሉ የሚያጠጡበት ብሩኩ ወር ገባ ማለት ያዘወትሩ ነበር፡፡

ማሊክ ኢብን አነስ፣ ይህ ታላቅ ወር ሲገባ፣ ሐዲሥ ማጥናታቸውንና ትምህርት ከሚሰጥባቸው የተለያዩ ማዕከሎች ላይ መታደማቸውን አቁመው፣ ሙሉ ጊዜያቸውን ለቁርአን ይሰጡ ነበር፡፡

ቀታዳህ (አላህ ይዘንላቸው!) ምንጊዜም በሰባት ሌሊቶች ቁርአን ያኸትሙ ነበር፡፡ በረመዷን ወር ግን በመጀመሪያዎቹ ሀያ ቀናት በየሦስት ሌሊቶች፣ በመጨረሻዎቹ አሥር ቀናት ደግሞ በየሌሊቱ ያኸትሙ ነበር፡፡

ኢብራሒም አን-ነኸዒይ (አላህ ይዘንላቸው!) በመጀመሪዎቹ ሃያ ቀናት በየሦስት ሌሊቶች በመጨረሻዎቹ አስር ቀናት ውስጥ ደግሞ በየሁለት ሌሊቶች ያኸትሙ ነበር፡፡

አላህ ይዘንላቸውና! አል-አስወድ በበኩላቸው በየሁለት ሌሊቶች በማኽተም በወሩ ውስጥ አሥራ አምስት ጊዜ ያኸትሙ ነበር (ለጧኢፍ አል-መዓሪፍ)

ሙስሊም፣ ይህን ከቁርአን ጋር ያለውን ግንኙነት የሚያፀናበትን ወርቃማ አጋጣሚ ወይም ትልቅ ዕድል በጉጉት ይጠባበቃል፡፡ በመልካም መዓዛ እስኪታወድ፣ በረካ እስኪጎርፍለት፣ ፀጋ እስኪንቧቧለት ድረስ ዘወትር በማንበብ በአግባቡ ይጠቀምበታል፡፡ የሚከተለውን ሐዲሥ ልብ ብለው ያንብቡ፡-

“ከዱንያዊ ችግሮች ውስጥ አንድን ችግር ከሙእሚን ላይ ያቃለለ ሰው፣ በፍርዱ ቀን ከሚገጥሙ ችግሮች ውስጥ አንድ ችግሩን አላህ ያቀልለታል፡፡ የሙስሊም (ወንድሙን) ነውር የደበቀ ሰው በዚህችም ይሁን በሚቀጥለው ዓለም ውስጥ አላህ ነውሩን ይሸፍንለታል፡፡ የተወሳሰበበትን ጉዳይ ያፍታታ ሰው በዚህችም ይሁን በሚቀጥለው ዓለም ውስጥ አላህ (ውስብስብና ከባድ ጉዳዮቹን) ያግራራለታል፡፡ አንድ የአላህ ባሪያ፣ ወንድሙን በመርዳት ላይ እስካለ ድረስ አላህም እርሱን በመርዳት ላይ ይገኛል፡፡ እውቀት ፍለጋ መንገድ ለወጣ ሰው፣ የጀነትን መንገድ አላህ ያገራለታል፡፡ ሰዎች ከአላህ ቤቶች መካከል በአንዱ ቤቱ ውስጥ ቁርአንን በማንበብና እርስ በርሳቸው በመማማር ዓላማ አይሰባሰቡም፤ የውስጥ ሰላም የምትወርድላቸው፤ እዝነት የምትሸፍናቸው፣ መላኢካዎች የሚያጅቧቸው እንዲሁም ከሁሉም በላይ የተላቀና አሸናፊ የሆነው አላህ ከእርሱ ዘንድ ካሉት ጋር በመሆን የሚያወሳቸው ቢሆን እንጅ...”
(አህመድ፣ ሙስሊም፣ ኢብን ማጃህ ዘግበውታል።)

https://t.me/NejashiPP


ረመዷን - 10
****

ተሳደበ የተባለውን ሰው ድምፅ አሁን ድረስ አልሰማሁም ። መታገስ አልችልም ብዬ ፈራሁ። እታመማለሁ። ብቻ ምን ማለት እንደሚያስፈልግ ግራ ይገባል።

ሰው ያመነበትን የራሱን እምነት መስበክና ማስተማር ሲችል የሌላውን እምነትና መገለጫዎቹን ስለምን ይሳደባል ? ለምንስ በሌላው ላይ ድንበር ያልፋል? የሌላውን መሳደብ የራስን ወይስ መሳደብ ስብከት ሆነ።

ሙስሊም እንኳን በረመዷን በሌላም ጊዜ ምላሱ ቁጥብ ነው። ሰውንም ሆነ ሰዎች አምላኬ ነው ብለው የያዙትን ነገር አይሳደብም፣ በአንደበቱ ክፉ አይናገርም።

የሚገርመው በዚህ ዘመን ከመሳደብ አልፎ ለተሳዳቢ ጠበቃ የሚሆኑ መምጣታቸው ነው። ሐቂቃ ያስገርማል። ሲሆን ሲሆን አጥፊን አሳልፎ መስጠት ሲገባ ለርሱ ድጋፍ መስጠት አሳፋሪ ነው። ይህ እውነትን መደገፍ ሳይሆን ከዚህ ቀደም የተደበቀ ጥላቻን ማውጣት ነው። ቆም ብለው ሊያስቡ ይገባል ።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ረመዷን - 9
**


ረመዷን የብዙ ኸይር ሥራ ወር ነው። ረመዷን እንደዋዛ መታየት የሌለበት ውድ ወር ነው። እነኚህን መልካም ሥራዎች ያስታውሱ -

* ሱሑር መመገብ፣
* ቁርአን መቅራት፣
* ዱዓ ማብዛት፣
* ኢስቲግፋር ማዘውተር ፣
* ሱናዎችን መተግበር ፣
* ዚክርን መላመድ፣
* ለወላጆች በጎ መዋል፣
* ሰዎችን በመልካም ነገር ማስታወስ፣
* ሶላትን በወቅቱ መስገድ፣
* ሶደቃ መስጠት፣
* ዝምድናን መቀጠል፣
* ችግረኛን መርዳት፣
* የታመመን መጠየቅ፣
* ለሞቱት ምህረት መለመን፣
* የቲሞችን መንከባከብ፣
* ፆመኛን ማስፈጠር
*
*
https://t.me/MuhammedSeidAbx


ረመዳን አመታዊ የዒባዳ ጉዞ በቁርአን ከቁርአን ጋር

ወሰን የሌለው ምስጋና በረመዳን ወር ቁርአንን ላወረደልን ለአላህ (ሱብሃነሁ ወተአላ) ይሁን፤
ሂባውን በቁርአን ለሰጣቸውና ባህሪያቸው ቁርአን ለነበረውና ለተሞገሱት ነቢዩ ሙሐመድ ( ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም )
ብሩሁን የተሟላውን የኢስላምን ስርአተ ህግ ለአለም ላዳረሱና እነርሱን እስከ መጨረሻ ለተከተሉ (አላህ ስራቸውን ይውደድላቸው) እላለሁ!

በየዓመቱ በሂጅራ ቀመር አቆጣጠር በዘጠነኛ ወር የሚነግሰው የቁርአን ወር የሆነው ረመዳን ሙስሊሙን ብቻ ሳይሆን የሚያነቃው ሌላውንም የእምነት ተከታይ ህብረተስብ በደመነፍስ የሚያኗኗር ፈጥኖ ገብቶ ፈጥኖ ከስራችን ጋር የሚሰወር ወር ነው፡፡
ይህ በረመዳን የሚደረገው የሩሃኒያ የቁርአን ጉዞ በሁሉም አቅጣጫ በግል ይሁን በጋራ በማታ በለው በቀን ጾመንም ይሁን ካፈጠፈርን በኋላ ከመጀመሩ እስኪያበቃ ድረስ ነዳጁ የፍጡር ማእድ ሳይሆን የአላህ ቃል የሆነው ቁርአን ሲሆን መጓጓዣው ረመዳን የሆነና ተሳፋሪው ፣ ደጃፉ ረያን ወደ ሆነው ጀነት የሚያቀኑት አንተና የቁርአን ቤተሰቦች ብቻ ናቸው፡፡
እዚህ ላይ አንድ በማህበራዊ ድረ ገጽ ከሰማሁት ምርጥ አባባል የደስታህ መጠን እንዲበዛ ከፈለግክ ቁርአንን መቅራት አብዛ የሚል ነበር!
የረመዳንም የአይን ማረፊያ እርካታ መለኪያው ይብዛም ይነስም የተለመደው የፍጡር ማእድ ሳይሆን በአንደበታችን የምንቀራው ወይም በጆሮዋችን በጥሞና የምናዳጠው የአላህ ቃል የሆነው ቁርአን ነው፡፡ በዚህ ወር በተለምዶ የሚሰራው ዋናው ተግባር ከጠዋት እስከ ማታ ከምግብ ፣ ከመጠጥ ከስጋ ግንኙነት መታቀብ ሲሆን ብታውቅም፣ ባታውቅም፣ በትረዳውም፣ ባትረዳውም፣ መንገድህን የሚያበራልህ ነገ አማላጅ የሚሆንልህ ቁርአንና እርሱን ተከትለው የሚመጡ ተግባራት ናቸው ፡፡
አላህም ( ሱብሃኑ ወተዓላ) በቁርአኑ ሲያስታውስህ፡-
شَهْرُ رَمَضَانَ الَّذِي أُنزِلَ فِيهِ الْقُرْآنُ هُدًى لِّلنَّاسِ وَبَيِّنَاتٍ مِّنَ الْهُدَىٰ وَالْفُرْقَانِ ۚ
(እንድትጾሙ የተጻፈባችሁ) ያ በርሱ ውስጥ ለሰዎች መሪ ከቅን መንገድና (እውነትን ከውሸት) ከሚለዩም ገላጮች (አንቀጾች) ሲኾን ቁርኣን የተወረደበት የረመዳን ወር ነው፡፡(አል በቀራህ ፡ 185)
በእርግጥ የአላህ (ሱብሃኑ ወተኣላ) ቁርአን በሁሉም ወራት እንደቅርበትህ ይዘህ ወይም ሃፍዘህ የምትቀራው ህይወትህን ህያው የሚደርግልህ ሲሆን በረመዳን ደግሞ የበለጠ ደረጃህን ከፍ የሚያድግ ነው፡፡
አላህ (ሱብሃኑ ወተኣላ) በረመዳን የቀን ሰአት ከምግብ ፣ ከመጠጥ ከስጋዊ ግንኙነት እንድንታቀብ ሲያዝ ነፍሳችንን በቁርንና በርሱ ነጸብራቅ በሆኑት ተግባራት እንድንሞላ ፣ በቁርአን ከመቸውም በበለጠ እንድኖር የበለጠ የነቢዩ ሙሐመድ ( ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ) አጭር የህይወት ገጽታ ይነግረናል፡፡
ነቢዩ ሙሐመድ ( ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ) በህይወታቸው አስተማሪያቸው ጂብሪል (ዓለይሂ ሰላም) የተለመደው የዋህይ ማስተላለፍ ዚያራ ያደርጋቸው እንደነበረና በረመዳን ጊዜ የሚደርገው ዚያራ ቁርአንና ስለ ቁርአን ብቻ ነበር፡፡
እንዲህም ሲዘይራቸው ልግስናቸው ዝናብ ከሚያመጣው ንፋስ የበለጡ ፈጣን ነበሩ ይባላል፡፡ምን ያህል ቢደሰቱ ነው ? ድሮም ሲለግሱ ድህነትን የማይፈሩ ሆነው ነበር የሚለግሱት!
ይህ ታላቅ ወር ሲገባ ከጂብሪል(ዓለይሂ ሰላም) ጋር በቁርአን መማማር ብቻ ነበር ስራቸው ወይም በመስጊድ ዒእቲካፍ (በመስጊድ ውስጥ ለኢባዳና በኢባዳ) መቆየት ነበር፡፡እድሜህ አብቅቷልና በመጽሐፍ መልክ አዘጋጅም ብሎ አላዘዛቸውም ፤ግን እንደማይረሱት ማንም ሊበርዘው እንደማይችል ቃል የተገባላቸው ነበር፡፡
ለዚህም ነው የነቢዩ ሙሀመድ( ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ) ብዙው ትኩረት አብዛኞቻችን ስለምንዘጋጅለት የፍጡር አይነት ሳይሆን የተለያዩ የዒባዳ አይነቶችና በቁርአን ስለምናደርገው የዒማን ጉዞ ነው፡፡
የቁርአን ጉዞ ምንዳው ቁጥር ስፍር የሌለው በአንድ ፊደል እስከ አስር ምንዳ የሚያስገኝ ሲሆን ፣በረመዳን ግን "እኔ ነው የምመናዳው "
በእርግጥም ይህ መለኮታዊ ቃል ኪዳን ልክ የሌለው እንደ እዝነቱ ወሰን የለሽ ነው፤ ከሰው መረዳት በላይ ነው!
ይሁንና ይህ የተቀደሰ ጉዞ ብዙ መሰናክሎች ፣ፍጥነቱን የሚቀንሱ ውጣ ውረዶች እና ችግሮች የተከበበ ለመሆኑ የሚካድ አይደለም፡፡ካልተፈለገ የረመዳን ገበያ መውጣት ባሻገር የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች(በተለይ በውድድር ስም ፣በሽልማት የታጀበ ) ፣ በእጃችን የሚገኘው ሞባይል እና መሰል መገልገያዎችና አፕሊኬሽንስ ከአላማችን እንዳያዘናጉን ልንጠቀቃቸው እና መስመር ልናስይዛቸው የሚገቡ ናቸው!

የረመዳን በቁርአን ጉዞዬ ለመሆኑ ስለ እኔ አላህ ምን ብሏል ብል ማንም እናቴም ትሁን ወይም አባቴ ያላሉኝን ቀድሞ ገልጾኛል !….ከሙታን እንደነበርኩ ፣ በፍትወት ጠብታ ህይወት እንደሰጠኝ ገልጾኛል፡፡
ከዚያም በተጠበቀ ጠባብ የእናቴ ማህጸን ለተወሰነ ጊዜ እንዳቆየኝ ከዚያም እርቃኔን ተወልጄ ነውሬ እንዲሸፍኑና ስም እንዲሰጡኝ እና የምድርን ሃላል እንድመገብ ፣ ከእናቴ ጡት ወይም ከሌላ አጥቢ ቢያንስ ሁለት አመት እንድጠጣ አዞ ፣ አድጌ እድማር ፣ እርሱን እንድገዛ ወላጆቼን እንዳከብር ፣ ዘመድ እንድ ጠይቅ ፣ ለጎረቤት ፣ለእንግዳ መልካም እንድውል ፣ እንዳገባ ቤተሰብ እዳፈራ ፣ከሰጠኝ ልጆችን ባግባቡ እንደሳግድ እንዳስተምር ፣ ሌላውን በምችለው እንድጠቅም በቁርአኑ ጉዞዬ የነገረኝ ነው፡፡
መኖር እንዳለም መሞት ለነቢዩም( ሰለላሁ ዓለይሂ ወሰለም ) እንዳልቀረ ቀብር የሚባል ጊዚያዊ መቆያ የአኪራ መሸጋገሪያ እንዳለ ፣ከዚያም መቀስቀስ ብሎም በአላህ ፊት መቆምና መጠየቅ ጀነት ወይም ጀሃነም እንደተዘጋጀ መሃል ሰፋሪ እንደሌለ በቁርአን ጉዞዬ የተነገረኝ ነው ፡፡
ሁሉም በረመዳን የቁርአን ጉዞው ስለራሱ ብዙ ማለት ይችላል ፤ባለው የቁርአን ግንኙነት የህይወትን ቀና መንገድ ያስቀምጣል ፣ጠማማውንም ያስጠነቅቃል ፡፡
እንዲህ እያለ ቁርአን በህይወት ጉዞህ ይመሰክርልሃል ወይም ይመሰክርብሃል!


መልካም የቁርአን ወር

ወሂብ ኩርቱ
ረመዳን 1446
ከዶሃ -ቀጠር
https://t.me/MuhammedSeidAbx


ረመዷን -8
**

በዚህ ረመዷን ውስጥ በደል ላይ የተሠማራ፣ ወንጀል የሚሠራ፣ ክፉ ባህሪ የሚያንፀባርቅ ሰው ያ ፀባዩ የርሱ የራሱ ነው። በሸይጧን ማሳበብ አይችልም ። ሸይጧን አሳሳተኝ ማለት አይገባውም ። ሸይጧን ታስሯልና ይላሉ።

በረመዷን ያልታረመ፣ በዚህ ወር ውስጥ ያልተሻሻለ መቸም አይታረም አይሻሻል።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


Репост из: Nejashi Printing Press
ረመዷን እና ቁርኣን
**
“የረመዳን ትርፋማ ስምምነቶች እና ወርቃማ እድሎች” ከተሠኘው መጽሐፍ
ነጃሺ ማተሚያ ቤት

ረመዷን ወርቃማ ዕድል ነው፡፡ የዚህ ወርቃማ ዕድል ቀዳሚ አርአያችን ነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ) ናቸው፡፡ ነቢያችን (ሰ.ዐ.ወ) ከቁርአን ጋር ያላቸው ቁርኝት፣ ከሌላው ጊዜ የበለጠ በዚህ ታላቅ ወር ውስጥ ጎልቶ ይታይ ነበር፡፡ ከቁርአን ጋር ይኖሩ ነበር፡፡

ቁርአን ብርሃን ነው፡፡ ልብን ያበራል፣ ጎጆን ያበራል፣ አዕምሮን ያበለፅጋል፣ ኢማም አል-ገዘሊ እንዳሉት የቁርአን እና የአዕምሮ ግንኙነት፣ ልክ እንደ ብርሃንና እንደ ዓይን ነው፡፡ አዕምሮዬ ብቻ ይበቃኛል ቁርአን አያስፈልገኝም የሚል ሰው፣ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ዓይኖቹን አፍጥጦ ለማየት የሚሞክር ሰው ነው፡፡ በተቃራኒው ቁርአንን ከያዝኩ አዕምሮዬን ብዘጋም ችግር የለውም ብሎ የሚያምን ሰው፣ በተጥለቀለቀ ብርሃን ውስጥ ዓይኖቹን ጨፍኖ ለማየት እንደሚሞክር ሰው ነው፡፡

ቁርአን ከልብ ጋር፣ ቁርአን ከጎጇችን ጋር ያለው ግንኙነትስ ምን ይመስላል? ከዚህ በታች የተጠቀሱትን ሐዲሶች ልብ ብለው ያንብቧቸው፡-
“ከቁርአን ምንም ነገር በውስጡ ያልያዘ ሰው፣ የፈራረሰ ወና ቤት ማለት ነው፡፡” (ቲርሚዚ)

“ጌታውን የሚያወሳ ሰው፣ እና ጌታውን የማያወሳ ሰው ምሳሌያቸው፣ እንደ ህያው እና ሙት ነው፡፡” (ቡኻሪ)

“አላህ የሚወሳበት ቤት እና አላህ የማይወሳበት ቤት ምሳሌያቸው፣ እንደ ህያው እና ሙት ነው፡፡” (ሙስሊም)

ቁርአን ለማንኛውም ሙስሊም፣ መሪ ብርሃኑ ነው፡፡ በዚህም ይሁን በሚቀጥለው ዓለም ለእውነተኛ እና ለዘላቂ ስኬት የሚበቃበት የህይወት ጎዳናው ነው፡፡

ቁርአንን በማንበብና በማስተንተን የሚገኘውን ደስታ፣ ሌላ የትኛውም ዓይነት ደስታ አይሰተካከለውም፡፡ ያጣጣመው ሰው ብቻ እንጂ ሌላው ሰው አይረዳውም፡፡ የተስተካከለ ኢማን እና ጤናማ ቀልብ ያሉት አማኝ የኃያል ጌታውን ንግግሮች አንብቦ አይጠግብም፡፡ የተወሰኑ ሰዎች ወደ ኸሊፋው ዑሥማን ኢብን ዐፋን (ረ.ዐ) ዘንድ በመምጣት፡-
“ቁርአን እንቀራለን፣ ነገር ግን ጣዕሙን ማግኘት አልቻልንም፡፡” ያሏቸው ጊዜ፣ የሰጧቸው መልስ እንዲህ የሚል ነበር፡- “ልቦቻችሁ ደህና ቢሆኑ ኖሮ ከጌታችሁ ቃላት አትጠግቡም ነበር፡፡”

https://t.me/NejashiPP


ረመዷን - 7
***

ወዳጆቼ! ችግር ሲገጥማችሁ፣ መከራ ሲያገኛችሁ፣ ሲያማችሁ፣ ግራ ሲገባችሁ፣ የሆነ ነገር ሲያሳስባችሁ … አላህን በልባችሁ አውሩት፤ መልካም ሥራዎችን በመሥራት ለምኑት፡፡ መልካም ቃል ሶደቃ ናት፣ ድብቅ ሶደቃ የአላህን ቁጣ ታበርዳለች፣ የታመመን ትፈውሳለች፣ መልካም ሥራ ከክፉ ኻቲማ ይጠብቃል፡፡
እናም ለልጁም፣ ለሀብቱም፣ ለኢማኑም፣ ለትዳሩም … ዱዓ ማድረግ ብቻ ሳይሆን ደጋግ ሥራዎችንም አብዙ፡፡ በተለይ በረመዷን፡፡ ችላ አትበሉ ይህን ዕድል በደንብ ተጠቀሙበት፡፡ በየትኛው መልካም ሥራችሁ ሀሳባችሁ ሊሳካ እንደሚችል፣ ጭንቀታችሁ እንደሚወገድ አታውቁምና።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


የረመዷን ቀናት ሚቆጠሩ ቀናት ናቸው። 30 ወይም 29 ቀናት።
አላህ ሆይ አጅራችንን አብዛው።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ረመዷን - 6
***,

ነቢ ሰዐወ እና ነቢ ዘመን ሰዎች የተለመደ ምግባቸው ተምር፣ ዘቢብ፣ የገብስ ቂጣ፣ ውሃ ነበር ። እንዲያም ሆኖ

{ ثُمَّ لَتُسۡـَٔلُنَّ يَوۡمَئِذٍ عَنِ ٱلنَّعِيمِ }
ከዚያም ከድሎታችሁ ሁሉ በዚያ ቀን ትጠየቃላችሁ፡፡
አላቸው።
ሁኔታቸውን ላየ የትኛው ፀጋ ? ያስብላል ።

የኛን የረመዷን ውስጥ ምግብ ደግሞ አስቡ። እንጠየቃለን ወላሂ።

በተለይ በዚህ ብዙዎች ማፍጠሪያም የፆም ማሠሪያም ባጡበት የኑሮ ውድነት ዘመን ከማባከንና ከማበላሸት እንጠንቀቅ።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ረመዷን - 5
****
እንደ ሶደቃ ነገሮችን የሚያገራ ነገር አለ ብዬ አላስብም። የትኛውንም የሚያጋጥማችሁን የዱንያ ላይ ፈተናና ህመም ከሰውነታችሁ፣ ከገንዘባችሁ፣ ከጊዜያችሁም ሆነ ከክብራችሁም ጭምር በመመጽወት ተሻገሩ። መልካም ነገርን ስትመኙ የሆነ ነገርን መመጽወት አስቀድሙ።

ከባለፈው ፈተና በፊት ሰዎች የሠጡኝን አማና ለማድረስ ቁርአን ተሸክሜ በየመስጊዱ ሳደርስ ነበር ። ለአላህ ስትሠራ ነገሩም፣ መንገዱም ሁሉ ይገራል።

በሕይወት ዘመኔ ሁሉ የትኛውንም ፈተና ቀላል ነው ብዬ አላውቅም ። ነገሮችን በቅጽበት የሚቀያይር ጌታ መሻቱ ምን እንደሆነ አናውቅም ። ገር ነገር የሚገራው አላህ ሲያገራው ነው። ከባዱም ነገር የሚገራው አላህ ሲያገራው።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ቀናት ሁሉ ረመዷን ቢሆኑ እንዴት ደስ ይላሉ መሠላችሁ !
እርካታ ፣ እርጋታ፣ ሰላም፣ ደስታ

ረመዷንን የሠጠኸን ጌታ ወላሂ ብዙ ነገር ሠጠኸን።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ሓጃዬ ወጥቷል በረካ ሁኑ። ከሁለት ሰዓት በላይ ፈተና ላይ ነበርኩ። የዶክትሬት /ፒ ኤች ዲ ትምህርቴን ዛሬ ጨረስኩ።

አልሐምዱ ሊላህ

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ትንሽ ሐጃ ገጥሞኝ ነው በዱዓችሁ። አላህ መልካሙን እንዲወፍቀኝ።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ረመዷን -3
****
ቀንና ሌሊቱን ጭምር ለፆመኞች ማፍጠሪያ በማዘጋጀት ተጠምደው የታላቁን ፆም ድባብ፣ ጣእምና እርካታ ለማጣጣም ጊዜ እንዳጡ ረመዷን የሚወጣባቸው ሁሉ ትልቅ ምንዳ ይገባቸዋል ።
አላህ ጀዛቸውን አብዝቶ ይክፈልልን።

https://t.me/MuhammedSeidAbx


ረመዷን -2
***
ረመዷን ገባ ማለት የጀነት በር ተከፈተ ማለት ነው። ከኛ የሚጠበቀው ጀነት የሚጠበቀው ጀነት የሚያስገቡ የአምልኮ ተግባራትና መልካም ሥራዎች ላይ የሙጥኝ ማለት ነው። ጀነትን እያሰቡ መፆም ።

አላህ ከጀነት ሰዎች ያድርገን።

https://t.me/MuhammedSeidAbx

Показано 20 последних публикаций.