ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ
“እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም በእርሱ የሚታመን ሰው ምስጉን ነው ።”
መዝ. 33 ፡ 8 ።
በጣም ደግ የሆኑ ሰዎችን እናውቃለን ። ሰው በልቶ የጠገበ የማይመስላቸው ፣ ያንተ እጅ አያጠግብህም በእኔ እጅ ጉረስ እያሉ በላይ በላዩ የሚያበሉ ሰዎች በዙሪያችን አሉ ። ሰለጠኑ የሚባሉት እንኳን በሰው እጅ ሊጎርሱ የራሳቸውንም እጅ ማመን አቅቷቸው ምግባቸውን ወደ አፋቸው የሚያደርሱት በማንኪያ ፣ በሹካና በቢላዋ ነው ። እንብላ ማለትንም እየረሱ ነው ። ሁሉንም ነገር ስሌት ውስጥ እየከተቱት ነው ። ባልና ሚስትም የየግላቸውን ይከፍሉ ይሆናል እንጂ አንዱ ባንዱ ገንዘብ ማዘዝ አይችልም ። በኅብረት ውስጥ ያለ ግለኝነት እንደ መሰልጠን እየታየ ነው ። ኅብረቱም አይቅርብኝ ፣ ግለኝነቱም አይቅርብኝ እየተባለ ነው ። ቀኑን ሙሉ ጋጋሪ አቁመው እንጀራ የሚያስጋግሩ ፣ የጋገሩትን እንጀራ መንገደኛ በልቶ ካልጨረሰው የሚያዝኑ ፣ እንግዳ መቀበል አገልግሎታቸው የሆኑ ሰዎችን እናውቃለን ። ከቤታቸው ደጃፍ አንድ ጎላ ንፍሮ ቀቅለው መንገደኛ ሁሉ ይበላው ዘንድ በየሰንበቱ የሚያስቀምጡ ቸሮችን አይተናል ። እያዘከሩ ሰው የሚሰበስቡ ፣ ማኅበራዊነትና መንፈሳዊነት እንዳይጠፋ የሚታገሉ ብዙዎች ናቸው ። “እኔ ቤት መጥቶ ሳይበላ ነው የሄደው” በማለት ተቀይመው የሚቀሩ ፣ እንደ እናቱ ባያየኝ ነው ብለው አዝነው የሚጎዱ የዋሃንን በትክክል እናውቃለን ። እነዚህ ደጎች ሳይጎድልባቸው እንደ ሰጡ አልፈዋል ። ስጡ ላለው አምላክ ታዘዋልና ተሰጥቶአቸዋል ። በብዛት ሳይሆን በበረከት መኖር ችለዋል ። ዛሬ ብዙ ገንዘብ አለ ፣ በረከት ግን የለም ። ለድሀ አንሰጥም ፣ ለማንድንበት መድኃኒት ግን ብዙ እናወጣለን ። እግዚአብሔር ስንሰጥ በጤና እንደሚከፍለን አናውቅም ። እናውቃለን ብለን ሞኝ ሆንን ። የሌሎች የረሀብ ሕመም ሲሰማን የእኛ ሕመም እየተፈወሰ ይመጣል ።
ቸሮች በታኞች አይደሉም ። ሰውን የሚያሰክር መጠጥ ፣ ሱስ የሚጋብዙ እነዚህ ጥይት የሚመጸውቱ ናቸው ። ቸሮች የሚዘሩ ናቸው ። ዘሪ መሬቱን ያውቀዋል ፣ ከርሞ ይመለስበታል ። ዛሬ ይዘራል ፣ ነገ እዚያው ያጭዳል ። ቸሮች አንድን ሰው ካለበት ሁኔታ እልፍ ማድረግ ፣ ከግብ ማድረስ ዓላማቸው ነው ። ቸር ሰው በበረሃ እንደ ተገኘ ውኃ ነው ፣ ያረካል ። ቸሮች ውስጣቸው ሕያው ነው ፣ እንቅስቃሴ ላይ ሲሆን ሊወጣ የሚታገላቸው ኃይል አለ ። ራሳቸውን በጣም ስለማያዩት ፣ የሌሎች ጉድለት ስለሚታያቸው ደስተኞች ናቸው ። ፍቅር ተግባራዊ ሲሆን ቸር ያደርጋል ። ስስታም ፣ ንፉግ ሰው አፍቃሪ አይደለም ። እነዚህ ሁሉ ቸሮች ክፉ ቀንን ያለፍንባቸው ፣ ጨለማችን ላይ ብርሃን ያወጁ ናቸው ። ያለ ደጎች ድጋፍ እዚህ አልደረስንም ። ተቀብለን እንዳልተቀበለ መካድ አይገባንም ። እነዚያን ቸሮች ማመስገን ፣ ዛሬ ተራው የእኛ ከሆነ በችግራቸው መርዳት ይገባናል ።
ቸሮች የእግዚአብሔርን ጠባይ የተካፈሉ ናቸው ። እግዚአብሔርን የሚመስሉ ፣ የሚንሰፈሰፉልን ፣ በረከትን በተርታ የሚያቀርቡልን ፣ ልባቸውም እጃቸውም የተከፈተልን ስጦታዎቻችን ናቸው ። እግዚአብሔርን የምናየው በቸሮች ውስጥ ነው ። ሰው ቅባትና የውበት ዕቃ ሲሸምት ይውላል ፤ እውነተኛ ውበት ግን ቸርነት ነው ። እግዚአብሔር በባሕርይው ቸር ነው ። ቸርነቱን በቃላት መግለጥ ፣ በእውቀት ማስረዳት አይቻልም ። የእግዚአብሔር ቸርነት ከሞት መንጋጋ ያስመልጣል ። ይህን ቸርነት ያልተካፈለ ሰው ፣ እንስሳና እጽዋት የለም ። ቸር አንድ ቀን ከሰዎች ብልጠት የተነሣ ቢስ ይሆናል ። “ቸር ሲያጠቁት ቢስ ይሆናል” እንዲሉ ። እግዚአብሔር ግን እያጠቃነው አሁንም ቸር ነው ።
ነቢዩ በመዝሙሩ፡- “እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም በእርሱ የሚታመን ሰው ምስጉን ነው” ይላል ። እግዚአብሔርን ወደ ቤታችን መጋበዝ ፣ እግዚአብሔርን ተሸክሞ ወደ ሰዎች ቤት መሄድ ተገቢ ነው ። መቅመስ ማጣጣም ፣ ለመብላት መዘጋጀት ፣ መሞከር ፣ መለማመድ ነው ። የእግዚአብሔርን ቸርነት መቅመስ አለብን ። ቸርነቱን የሚቀምሱ ቸር ይሆናሉ ። ቀጥሎ፡- “በእርሱ የሚታመን ምስጉን ነው” አለ ። ቸር የማንሆነው ቢጎድልብኝ ብለን ነው ። ቸርነት ግን በእግዚአብሔር በመታመን የሚገኝ ነው ። ስጡ ላለው ቃል ታዝዤ አይጎድልብኝም ብሎ ማመን ይፈልጋል ። እምነት ልምምድ ነው ። መቅመስ ፣ ማየት ይገባል ። የቸርነት ሕይወት ደስ ያሰኛል ። የተቆለፉ ትልልቅ ቤቶች ፣ ምግብ እየተበላሸ የሚደፋባቸው የባለጠጋ ሳሎኖች ይህን ቸርነት ቢለማመዱ የሞት ጥላ ይገፈፍላቸዋል ። እንዴ በየምሽት በሚሊየን እያወጡ ይጋብዙ የለም ወይ? ቢባል እርሱ ንግድና ጉራ እንጂ ቸርነት አይደለም ። ቸርነት የባለጠጎች ዕዳ ሳይሆን ሁሉም የሰው ልጅ የሚለማመደው ሀብት ነው ። በእጃችን ማጉረስ ባንችል በእጃችን የቆሸሸውን ምስኪን ማጠብ እንችላለን ። የሰውነት ክፍሎቻችን የቸርነት መሣሪያ ናቸው ። ቸርነቱን የምንቀምሰው በጸሎት ነው ። የሚለምኑ ይቀበላሉ ፣ ቸርነቱንም ያያሉ ።
እግዚአብሔር በቸርነቱ የሰጠን ሕይወትን ነው ። የሕይወት ዋጋዋ ስንት ነው ? ያኖረን ቸርነቱ ነው ። እስትንፋሳችን በአፍንጫችን ላይ የተንጠለጠለች ፣ ለመሄድ የተዘጋጀች ናት ። እስትንፋሳችንን በአፍንጫችን ያሳደረልን ፣ ያዋለልን ጌታ ቸር ነው ። ይህን ቸርነቱን ማጣጣም ፣ ማመስገን ፣ መመስከር ይገባል ። በእግዚአብሔር የሚታመን ሰው ቸር ነው ።
እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ ።
@Ethiopian_Ortodoks
@Ethiopian_Ortodoks
┈┈┈┈••●◉❖◉●••┈┈┈
“እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም በእርሱ የሚታመን ሰው ምስጉን ነው ።”
መዝ. 33 ፡ 8 ።
በጣም ደግ የሆኑ ሰዎችን እናውቃለን ። ሰው በልቶ የጠገበ የማይመስላቸው ፣ ያንተ እጅ አያጠግብህም በእኔ እጅ ጉረስ እያሉ በላይ በላዩ የሚያበሉ ሰዎች በዙሪያችን አሉ ። ሰለጠኑ የሚባሉት እንኳን በሰው እጅ ሊጎርሱ የራሳቸውንም እጅ ማመን አቅቷቸው ምግባቸውን ወደ አፋቸው የሚያደርሱት በማንኪያ ፣ በሹካና በቢላዋ ነው ። እንብላ ማለትንም እየረሱ ነው ። ሁሉንም ነገር ስሌት ውስጥ እየከተቱት ነው ። ባልና ሚስትም የየግላቸውን ይከፍሉ ይሆናል እንጂ አንዱ ባንዱ ገንዘብ ማዘዝ አይችልም ። በኅብረት ውስጥ ያለ ግለኝነት እንደ መሰልጠን እየታየ ነው ። ኅብረቱም አይቅርብኝ ፣ ግለኝነቱም አይቅርብኝ እየተባለ ነው ። ቀኑን ሙሉ ጋጋሪ አቁመው እንጀራ የሚያስጋግሩ ፣ የጋገሩትን እንጀራ መንገደኛ በልቶ ካልጨረሰው የሚያዝኑ ፣ እንግዳ መቀበል አገልግሎታቸው የሆኑ ሰዎችን እናውቃለን ። ከቤታቸው ደጃፍ አንድ ጎላ ንፍሮ ቀቅለው መንገደኛ ሁሉ ይበላው ዘንድ በየሰንበቱ የሚያስቀምጡ ቸሮችን አይተናል ። እያዘከሩ ሰው የሚሰበስቡ ፣ ማኅበራዊነትና መንፈሳዊነት እንዳይጠፋ የሚታገሉ ብዙዎች ናቸው ። “እኔ ቤት መጥቶ ሳይበላ ነው የሄደው” በማለት ተቀይመው የሚቀሩ ፣ እንደ እናቱ ባያየኝ ነው ብለው አዝነው የሚጎዱ የዋሃንን በትክክል እናውቃለን ። እነዚህ ደጎች ሳይጎድልባቸው እንደ ሰጡ አልፈዋል ። ስጡ ላለው አምላክ ታዘዋልና ተሰጥቶአቸዋል ። በብዛት ሳይሆን በበረከት መኖር ችለዋል ። ዛሬ ብዙ ገንዘብ አለ ፣ በረከት ግን የለም ። ለድሀ አንሰጥም ፣ ለማንድንበት መድኃኒት ግን ብዙ እናወጣለን ። እግዚአብሔር ስንሰጥ በጤና እንደሚከፍለን አናውቅም ። እናውቃለን ብለን ሞኝ ሆንን ። የሌሎች የረሀብ ሕመም ሲሰማን የእኛ ሕመም እየተፈወሰ ይመጣል ።
ቸሮች በታኞች አይደሉም ። ሰውን የሚያሰክር መጠጥ ፣ ሱስ የሚጋብዙ እነዚህ ጥይት የሚመጸውቱ ናቸው ። ቸሮች የሚዘሩ ናቸው ። ዘሪ መሬቱን ያውቀዋል ፣ ከርሞ ይመለስበታል ። ዛሬ ይዘራል ፣ ነገ እዚያው ያጭዳል ። ቸሮች አንድን ሰው ካለበት ሁኔታ እልፍ ማድረግ ፣ ከግብ ማድረስ ዓላማቸው ነው ። ቸር ሰው በበረሃ እንደ ተገኘ ውኃ ነው ፣ ያረካል ። ቸሮች ውስጣቸው ሕያው ነው ፣ እንቅስቃሴ ላይ ሲሆን ሊወጣ የሚታገላቸው ኃይል አለ ። ራሳቸውን በጣም ስለማያዩት ፣ የሌሎች ጉድለት ስለሚታያቸው ደስተኞች ናቸው ። ፍቅር ተግባራዊ ሲሆን ቸር ያደርጋል ። ስስታም ፣ ንፉግ ሰው አፍቃሪ አይደለም ። እነዚህ ሁሉ ቸሮች ክፉ ቀንን ያለፍንባቸው ፣ ጨለማችን ላይ ብርሃን ያወጁ ናቸው ። ያለ ደጎች ድጋፍ እዚህ አልደረስንም ። ተቀብለን እንዳልተቀበለ መካድ አይገባንም ። እነዚያን ቸሮች ማመስገን ፣ ዛሬ ተራው የእኛ ከሆነ በችግራቸው መርዳት ይገባናል ።
ቸሮች የእግዚአብሔርን ጠባይ የተካፈሉ ናቸው ። እግዚአብሔርን የሚመስሉ ፣ የሚንሰፈሰፉልን ፣ በረከትን በተርታ የሚያቀርቡልን ፣ ልባቸውም እጃቸውም የተከፈተልን ስጦታዎቻችን ናቸው ። እግዚአብሔርን የምናየው በቸሮች ውስጥ ነው ። ሰው ቅባትና የውበት ዕቃ ሲሸምት ይውላል ፤ እውነተኛ ውበት ግን ቸርነት ነው ። እግዚአብሔር በባሕርይው ቸር ነው ። ቸርነቱን በቃላት መግለጥ ፣ በእውቀት ማስረዳት አይቻልም ። የእግዚአብሔር ቸርነት ከሞት መንጋጋ ያስመልጣል ። ይህን ቸርነት ያልተካፈለ ሰው ፣ እንስሳና እጽዋት የለም ። ቸር አንድ ቀን ከሰዎች ብልጠት የተነሣ ቢስ ይሆናል ። “ቸር ሲያጠቁት ቢስ ይሆናል” እንዲሉ ። እግዚአብሔር ግን እያጠቃነው አሁንም ቸር ነው ።
ነቢዩ በመዝሙሩ፡- “እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ እዩም በእርሱ የሚታመን ሰው ምስጉን ነው” ይላል ። እግዚአብሔርን ወደ ቤታችን መጋበዝ ፣ እግዚአብሔርን ተሸክሞ ወደ ሰዎች ቤት መሄድ ተገቢ ነው ። መቅመስ ማጣጣም ፣ ለመብላት መዘጋጀት ፣ መሞከር ፣ መለማመድ ነው ። የእግዚአብሔርን ቸርነት መቅመስ አለብን ። ቸርነቱን የሚቀምሱ ቸር ይሆናሉ ። ቀጥሎ፡- “በእርሱ የሚታመን ምስጉን ነው” አለ ። ቸር የማንሆነው ቢጎድልብኝ ብለን ነው ። ቸርነት ግን በእግዚአብሔር በመታመን የሚገኝ ነው ። ስጡ ላለው ቃል ታዝዤ አይጎድልብኝም ብሎ ማመን ይፈልጋል ። እምነት ልምምድ ነው ። መቅመስ ፣ ማየት ይገባል ። የቸርነት ሕይወት ደስ ያሰኛል ። የተቆለፉ ትልልቅ ቤቶች ፣ ምግብ እየተበላሸ የሚደፋባቸው የባለጠጋ ሳሎኖች ይህን ቸርነት ቢለማመዱ የሞት ጥላ ይገፈፍላቸዋል ። እንዴ በየምሽት በሚሊየን እያወጡ ይጋብዙ የለም ወይ? ቢባል እርሱ ንግድና ጉራ እንጂ ቸርነት አይደለም ። ቸርነት የባለጠጎች ዕዳ ሳይሆን ሁሉም የሰው ልጅ የሚለማመደው ሀብት ነው ። በእጃችን ማጉረስ ባንችል በእጃችን የቆሸሸውን ምስኪን ማጠብ እንችላለን ። የሰውነት ክፍሎቻችን የቸርነት መሣሪያ ናቸው ። ቸርነቱን የምንቀምሰው በጸሎት ነው ። የሚለምኑ ይቀበላሉ ፣ ቸርነቱንም ያያሉ ።
እግዚአብሔር በቸርነቱ የሰጠን ሕይወትን ነው ። የሕይወት ዋጋዋ ስንት ነው ? ያኖረን ቸርነቱ ነው ። እስትንፋሳችን በአፍንጫችን ላይ የተንጠለጠለች ፣ ለመሄድ የተዘጋጀች ናት ። እስትንፋሳችንን በአፍንጫችን ያሳደረልን ፣ ያዋለልን ጌታ ቸር ነው ። ይህን ቸርነቱን ማጣጣም ፣ ማመስገን ፣ መመስከር ይገባል ። በእግዚአብሔር የሚታመን ሰው ቸር ነው ።
እግዚአብሔር ቸር እንደ ሆነ ቅመሱ ።
@Ethiopian_Ortodoks
@Ethiopian_Ortodoks
┈┈┈┈••●◉❖◉●••┈┈┈