#ethiotelecom
" በአክስዮን ሽያጩ የተገኘው 3.2 ቢሊየን ብር ገንዘብ እስካሁን ለምንም አይነት ጥቅም ሳይውል በዝግ አካውንት ተቀምጧል " - ኢትዮ ቴሌኮም
➡️ " ከ47 ሺ በላይ ኢትዮጵያውያኖች የኢትዮ ቴሌኮምን አክስዮን ሼር ግዢ አከናውነዋል ! "ኢትዮ ቴሌኮም በጥቅምት ወር 10 በመቶ ድርሻውን ማለትም እያንዳንዳቸው 300 ብር ዋጋ ያላቸውን 100 ሚሊዮን መደበኛ አክሲዮኖች ለህዝብ በሽያጭ ማቅረቡ ይታወቃል።
ውሳኔው ኢትዮ ቴሌኮም ሙሉ በሙሉ በመንግስት ባለቤትነት ተይዞ ከነበረበት ወደ አክስዮን ማህበርነት ያሻጋገረ ነበር።
ለግዢ የቀረቡት አክስዮኖችን በተመለከተ ተቀባይነት ያገኙ አክስዮን ገዢዎች ከጥር 17/2017 ዓም ጀምሮ እንደሚለዩ ተገልጾ የነበረ ሲሆን ተቀባይነት ያላገኙ አክስዮን ገዢዎች ደግሞ እስከ ሚያዚያ 6/2017 ዓም ገንዘባቸው ተመላሽ ማድረግ እንደሚጀምር ይፋ አድርጎ ነበር።
ተቀባይነት ያገኙ እና ውድቅ የሆኑ አክሲዮኖችን በተመለከተ በተቀመጠው የጊዜ ገደብ መሰረት ምንም አይነት ይፋ ያደረገው መረጃ ሳይኖር ወራትን ያስቆጠረው ኢትዮ ቴሌኮም በጉዳዩ ላይ በዛሬው ዕለት መግለጫ እየሰጠ ይገኛል።
መግለጫውን የሰጡት የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ ምን አሉ ?- የመጀመሪያው ዙር የአክስዮን ሽያጩ ከተጀመረበት ጥቅምት ዘጠኝ እስከ ታሕሳስ 25/2017 ዓም ድረስ ሲከናወን ቆይቷል።
- የሼሩ ዋጋ ዝቅ የተደረገበት ምክንያት ዝቅተኛውን የማህበረሰብ ክፍል ተጠቃሚ ለማድረግ ነበር።
- ዝቅተኛው 33 ከፍተኛው 3,333 ሺ አክስዮን ሽያጭ ማለትም ከ 9,900 ብር እስከ 99,900 ብር ሲከናወን ነበር።
- አክስዮን ሽያጩ ሪፖርት ተገምግሟል ለካፒታል ገበያ ባለሥልጣንም ስለ አክስዮን ሽያጭ በተመለከተ ሪፖርት አቅርበናል።
- በህዝብ ጥያቄ መሰረት የሽያጭ ቀኑ ካበቃ በኋላም የሽያጭ ጊዜው እንዲራዘም ጥያቄ በመቅረቡ እና ህጉም ይህንን የሚፈቅድ በመሆኑ እስከ የካቲት 7/2017 ዓም ተራዝሞ ቆይቷል።
- የአክስዮን ሽያጩ በአጠቃላይ ለ121 ቀናት ቆይቷል።
- አጠቃላይ 47,377 ኢትዮጵያውያን ኢንቨስተሮች ሼሮችን ገዝተዋል ፤ በአጠቃላይ 10.7 ሚሊየን ሼሮችን ሽያጭ ተከናውኗል በገንዘብ ሲተመን 3.2 ቢሊዮን ብር ይይዛል።
- አክስዮን ግዢውን የፈጸሙት ባለድርሻዎች በመጀመሪያው ዙር 43,848 በሁለተኛው ዙር 3,529 በአጠቃላይ 47,377 ኢትዮጵያውያኖች ናቸው።
- ስቶክ ማርኬት ላይ መገበያየት፣ መሸጥ እና መግዛት የሚችሉ ባለሃብቶች ተፈጥረዋል።
- በቀጣይ ባለ አክስዮኖችን የማነጋገር ስራ ይሰራል ይህንንም ለማድረግ የካፒታል ገበያ ባለሥልጣን መብት ሰጥቷል ህጉም ይፈቅዳል።
- በሂደቱ የሚያስፈልጉት ከባለአክስዮኖች የምንጠይቃቸው ማርጋገጫዎች አሉ በመቀጠል ባለቤትነታቸው እንዲረጋገጥ ወድ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ይላካል።
- በመቀጠል ሊስት በማደርግ በካፒታል ገበያ መሸጥ እና መግዛት ወደ ሚችሉበት አጋጣሚ ይፈጠራል አላማውም ይሄ ነው።
ቀጣይ የአክስዮኑ ሽያጭ ይቀጥላል ? የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ ፥ ባንኮች እና ትውልደ ኢትዮጵያውያኖች ጥያቄ ማቅረባቸውን ገልጸዋል።
" ይህንን ታሰቢ በማድረግ እና በመጀመሪያው ሂደት ላይ ያጋጠሙ ነገሮችን በመገምገም እና መንግስትን በማማከር በቀጣይ መሳተፍ የፈለጉ ግለሰብ ፣ ተቋማት እና ትውልደ ኢትዮጵያኖች የቀሩ ሼሮችን እንዲገዙ መቼ ለሽያጭ እንደሚቀርቡ የምናሳውቅ ይሆናል " ብለዋል።
አሁን ላይ በአክስዮን ሽያጩ የተገኘው 3.2 ቢሊየን ብር ገንዘብ እስካሁን ለምንም አይነት ጥቅም ሳይውል በዝግ አካውንት ተቀምጦ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
" የባለአክስዮኖች መብት ባስጠበቀ መልኩ ቀጣይ ሂደቶች ይከናወናሉ " ሲሉ አሳውቀዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
አዲስ አበባ
#TikvahEthiopiaFamilyAA
@tikvahethiopia