ቤተ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ


Kanal geosi va tili: Efiopiya, Amharcha
Toifa: ko‘rsatilmagan


በዚህ ቻናል የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርቶች እና የአበው ቀደምት የተናገሯቸው መንፈሳዊ ንግግሮች እንዲሁም ልዩ ልዩ ሐይማኖታዊ ትምህርቶችና መልዕክቶች ይተላለፉበታል፡፡

Связанные каналы  |  Похожие каналы

Kanal geosi va tili
Efiopiya, Amharcha
Toifa
ko‘rsatilmagan
Statistika
Postlar filtri


#የበረከት_ጥሪ

ለገጠር አብያተ ክርስቲያናት ድጋፍ ለማድረግ ከየካቲት 23 ጀምሮ እስከ የካቲት 30 ቀን 2017 ዓ.ም የሚካሄድ የመባዕ ሳምንት መርሐ ግብር የማኅበረ ቅዱሳን የወልድያ ወረዳ ማእከል የሙያ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤት ክፍል በዝግጅት ላይ ነው።

የመብዐ ድጋፍ የሚደረግላቸው በተለይ በጉባላፍቶ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ሲሆኑ የማስቀደሻ እጣን፣ ጧፍ እና የካህናት አልባሳት እጥረት ያለባቸው በመሆኑ በዚህ የጾም ወቅት የቤተ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቴሌግራም ቻናል አባላት በዚህ የበረከት ሥራዎችን እንዲሳተፉ ጥሪ ቀርቧል።

ለመሳተፍ ፍላጎቱ ያላችሁ፦
               በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
     ማኅበረ ቅዱሳን ወልድያ ወረዳ ማዕከል
       ሙያና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል
                1000334491602

ለበለጠ መረጃ፦ 0938001464 ይደውሉ


የሚቆጣህ ጓደኛ ይኑርህ

የጓደኝነት ትልቁ ፈተና አንዱ ሌላውን መገስጽ መቻሉ ወይም አለመቻሉ ነው፡፡ ሁላችንም እለት ተእለት ኃጢአት እንሠራለን፤ ለራሳችን ሰበብ እየፈጠርን ኃጢአቱ እንዳልተከስተ በማስመሰል ኃጢአታችንንም ላለመመልከት አይናችንን እናውራለን:: በእንደዚህ አይነት ጊዜያት ለኃጢአታችን ዓይኖቻችንን የሚከፍቱ ጓደኞች ያስፈልጉናል።

ራስህን በጓደኛህ ቦታ አስቀምጠው:: የዚያን ሰው ዓይኖች ለመክፈት ፈቃደኛ ነህ? ያሉትን ሰበቦች ውሸት መሆናቸውን ልትነግረው ዝግጁ ነህ? የሰው ልጅ ስለ እርሱ መጥፎ ሲነገረው ቁስሉ እንደተነካ ይጮኻልና የጓደኛህን ቁጣ ለመጋፈጥ ተዘጋጅተሃል? ወይንስ በዝምታ ታልፈዋለህ?

ጓደኞቻችንን በምንመርጥበት ጊዜ፣ ከእኛ ጋር ሀቀኛ ለመሆን ፈቃደኛ የሆኑትን እና አስፈላጊ ሲሆንም ንዴታችንን ለመቋቋም የተዘጋጁትን መምረጥ አለብን፡፡ እንደዚህ ያለ ሐቀኝነት ከሌለ፣ ጓደኝነት ጥልቀት የለውምና ምንም ፋይዳ የለውም::

ለጓደኛህ ትችት መግለጽ ግዴታህ ቢሆን የጓደኛህን ክብር ዝቅ እንዳታደርግ ተጠንቀቅ:: የእርሱን መልካም ነገሮችንም ከወቀሳህ ጋር አብረህ ማንሳትህ ተግሣጽህን ያለስልሳል:: እናም ጓደኛህን የምትገስጸው ከቀናነት እንጂ ከክፋት አይሁን፤ ቃላቶችህም በፍቅር እንጂ በቁጣ አይሁኑ::

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
(ለነፍስህ ቤት ሥራላት በፍሉይ ዓለም የተተረጎመ ገጽ 236)

2.9k 0 134 2 111

በአንድ ወቅት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በአደባባይ በሚሰብክበት ጊዜ፣ አንድ ሌባ በህዝቡ መሃል እየተንቀሳቀሰ ነበር።

ሌባው ወደዚህ የመጣው ስብከቱን ለመሰማት ሳይሆን ከሰዎች ኪስ ለመስረቅ ነበር፡፡ ነገር ግን፣ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ መናገር ሲጀምር ሌባው በስብከቱ ተማርኮ ፈዞ ቆመ፥ የመጣበትንም የመጀመሪያ ዓላማውን ረሳው፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ ቃላት ማራኪ ከመሆናቸው የተነሳ የሌባወን ሕሊና በጥልቀት ነኩ።

ሌባው ስለ ንስሐ፣ ስለ ይቅርታ እና በጎ ሕይወት ከቅዱስ የሐንስ አፈወርቅ ከሰማ በኋላ የወንጀል ሕይወቱን ለመተው ወሰነ፡፡ ከስብከቱ በኋላ፣ ወደ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቀረበ ኃጢአቱንም ተናዘዘ፤ እናም መንገዱን እንዴት መለወጥ እንዳለበት ምክርን ጠየቀ። በርኀራኄው የሚታወቀው ቅዱስ ዮሐንስም ሌባውን ተቀብሎ አዲስ ሕይወት እንዲጀምር ረዳው፡፡

ይህ ታሪክ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስብከቶች ከየትኛውም ሕይወት የመጡ ሰዎችን፣ ከመልካም ምግባር የራቁትን ሳይቀር ወደ እግዚአብሔር መመለስ ለመቻላቸው ምስክር ነው።

ስብከቱ አእምሮአዊ ብቻ ሳይሆን ሕይወትን የሚለውጥ፣ የአድማጮቹን ልብ የሚነካና መልካም ሕይወት እንዲመሩ የሚያደርግም ነው።

4.9k 0 48 5 226


ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ እውነተኛ ጾም፤ ስለ ሐሜት...በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ፦


የእግዚአብሔር ቸርነት እንደ ምን ከመነገር ያለፈ እንደ ኾነ፣ እንደ ምን ወሰን እንደሌለው፣ እንደ ምን ከምንም ዓይነት አገላለጽ የራቀ እንደ ኾነ ርግጥ ነው! እዚህ ላይ የተሰደበው ሰውም ከእኛ ጋር ተመሳሳይ ባሕርይ [ሰውነት] እንዳለውም እውነት ነው፡፡ የተሰደበውም በንግሥናው ዘመን አንድ ጊዜ ብቻ ነው፤ ይህም ቢኾን እርሱ ፊት ለፊት ቆሞ ወይም እያየ ወይም እየሰማ አይደለም፤ “ምንም እንዲህ ቢኾንም ግን እነዚህን ግብራት የፈጸሙ ስዎች በፍጹም ምሕረትን አላገኙም፡፡

በእግዚአብሔር ዘንድ ግን እንደዚህ ያለ ነገር በፍጹም አይነገርም፤ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል እንዲህ ነው ተብሎ ሊገለጽ የማይችልና የሰው ቋንቋ መናገር የማይችለው ልዩነት አለና፡፡ እግዚአብሔር ዕለት ዕለት ያውም ቀኑን ሙሉ ከፊት ለፊት እያለ፣ እያየና እየሰማ ይሰደባል፡፡ እንዲህ ፊት ለፊት፣ እኔው ራሴ በዓይኔ እያየሁና በጆሮዬ እየሰማሁ ተሰደብሁ ብሎ ግን መብረቅ አይልክም፤ ባሕር ተነዋውጻ ምድርን እንድትከድናትና ስዎችን ኹሉ እንድታስጥማቸው አያዝዝም፤ ምድር ተከፍታ የሚሳደቡትን ኹሉ እንድትውጣቸው አያደርግም፡፡ ከዚህ ይልቅ ዝም ይላል፤ ይታገሣል፤ አልፎ ተርፎም የሰደቡት ሰዎች ንስሐ ከገቡና ከእንግዲህ ወዲህ እርሱን ላለመስደብ ቃል ከገቡ እንዲሁ ምሕረቱን ይለግሳቸዋል! በእውነት ያለ ሐሰት፡- “መኑ ይነግር ኃይለ እግዚአብሔር፥ ወይገብር ከመ ይስማዕ ኵሎ ስብሐቲሁ" - "የእግዚአብሔርን ኃይል ማን ይናገራል? ምስጋናውንስ ኹሉ ይሰማ ዘንድ ማን ያደርጋል?" ብሎ አሰምቶ የመናገር ጊዜው አሁን ነው (መዝ.105፥2)፡፡

አርአያ እግዚአብሔርን የጣሉ ብቻ ሳይኾኑ በእግራቸው የረገጡ ሰዎች ብዛታቸው ምን ያህል ነው? ባለ ዕዳን ስታንቅ፣ ያለውን ኹሉ ገፍፈህ ስትወስድበት፣ እንደዚሁም በምድር ላይ ስትጎትተው አርአያ እግዚአብሔርን በእግርህ እየረገጥህ ነው፡፡ ይህን ልታውቅ ከወደድህ ንዑድ ክቡር የሚኾን ጳውሎስ እንዲህ ያለውን አድምጥ፦ “ወንድ በሚጸልይበት ጊዜ ሊከናነብ አይገባውም፣ የእግዚአብሔር አርአያውና ክብሩ ነውና" (1ኛ ቆሮ.11፥7)። ዳግመኛም እግዚአብሔር ራሱ እንዲህ ያለውን ስማ፦ “ሰውን በአርአያችንና በአምሳላችን እንፍጠር” (ዘፍ. 1፥26)፡፡ “ሰውስ ከእግዚአብሔር ጋር አንድ አይደለም" ብለህ ከተናገርህ እንዲህ መናገርህ ምን ትርጉም አለው? ምክንያቱም ከነሐስ የተሠራው ሐውልትም ከንጉሡ ጋር አንድ አይደለም፣ ነገር ግን እርሱን [ሐውልቱን] የናቁ ሰዎች ከቅጣት አላመለጡም፡፡ ስለዚህ በሰው ልጅ ዘንድም እንደዚህ ነው፧ ስዎች ከእግዚአብሔር ጋር አንድ ባይኾኑም [በእርግጥም አይደሉምና] አርአያው ተብለው ግን ተጠርተዋል፤ ስለዚህ ከእግዚአብሔር ስለ ተቀበሉት ክብር ሊከበሩ ግድ ነው፡፡

አንተ ግን ስለ ጥቂት ወርቅ ብለህ ከእግርህ በታች ረግጠሃቸዋል፤ ጉሮሮአቸውን አንቀሃቸዋል፤ በምድር ላይ ጎትተሃቸዋል፡፡ ምንም ይህን ኹሉ ብታደርግም ግን [ከእግዚአብሔር ዘንድ] ቅጣትህን እስከ ዛሬ ድረስ አልተቀበልህም!

የዚያን ጊዜም ፈጥኖ ምሕረቱና ቸርነቱ ይደረግልን! ይህን አስቀድሜ የምናገረውና የምመሰክረውም፥ ይህ ደመና አልፎ ሳለ እኛ ግን አሁንም እንደዚህ ባለ ግድየለሽነት የምንቆይ ከኾነ አሁን ከምንፈራቸው በላይ እጅግ ጽኑዓን መከራዎችን እንደምንቀበል ርግጥ ስለ ኾነ ነው፡፡ የንጉሡ ቊጣ የእናንተን ግድየለሽነት ያህል አያስፈራኝምና፡፡

በእውነት ያለሐሰት በሕይወታችን ኹሉ ልንለወጥ ያስፈልገናል እንጂ፤ ከክፋት መራቅ ብቻ ሳይኾን መልካም ምግባርንም ዘወትር ልንሠራ ይገባናል እንጂ ምሕረትን ለማግኘት ብለን ለኹለት ወይም ለሦስት ቀናት የምናደርገው ምሕላ በቂ አይደለም፡፡

በደዌ ዘሥጋ የታመሙ ሰዎች ኹልጊዜ ጤንነታቸውን ለመጠበቅ የሚረዱ ምግቦችን ካልተመገቡና እንቅስቃሴዎችን ካላደረጉ በቀር ለኹሉት ወይም ለሦስት ቀናት ብቻ የሚያደርጉት ዕረፍት ምንም ረብ ጥቅም አይሰጣቸውም፤ በኃጢአት ያሉ ሰዎችም ኹልጊዜ ራሳቸውን ካልገዙ በቀርለኹለት ወይም ለሦስት ቀናት ብቻ መሻሻላቸው ምንም አይጠቅማቸውም፡፡ እንደተባለው ገላዉን የታጠበ ሰው መልሶ በጭቃ ቢንከባለል ምንም ጥቅም እንደማያገኝ ኹሉ፥ ለሦስት ቀናት ንስሐ የገባ ሰውም ከዚያ በኋላ ወደ ቀድሞ ኹኔታው ከተመለሰ ምንም ጠቀሜታን አላገኘም፡፡ ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ እንዲህ አናድርግ፡፡ .....

ይቀጥላል....

(ትምህርት በእንተ ምክንያተ ሐውልታት፣ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ገጽ 79-96 በገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተተረጎመ)


ዘመቻ 50k!

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዐቢይ ጾም ስለ እውነተኛ ጾም፤ የሰውን ሥጋ ከመብላት በላይ ክፉ ስለ ኾነው ሐሜት ያስተማረውን ትምህርት ወደ እናንተ እያደረስን እንገኛለን።

እርስዎም ይህ ቤተ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቻናል ለሌሎች ይደርስ ዘንድና እንዲቀላቀሉ ቤተሰብ እንዲሆኑ በተለያዩ ግሩፖችና ቻናሎች ሼር በማድረግ ይተባበሩ!

https://t.me/beteafework
https://t.me/beteafework
https://t.me/beteafework



ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ እውነተኛ ጾም፤ ስለ ሐሜት...በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ፦

ተወዳጆች ሆይ! እንግዲያውስ እንሽሽ፤ ዋናው የሰይጣን ጕድጓድና ወጥመዶቹን ዘርግቶ አድብቶ የሚቀመጥበት ሥፍራ እንደ ኾነ በማወቅ ሐሜትን እንሽሽ! በራሳችን ጉዳይ ላይ ቸልተኞች እንድንኾንና ከዚህም የተነሣ የሚያገኘን ወቀሳ እጅግ ጽኑ እንዲኾን ሽቶ ዲያብሎስ ወደ እንደዚህ ዓይነት ልማድ ይመራናልና፡፡ ከዚህም በላይ ግን፥ ነገሩን እጅግ ከባድ የሚያደርገው ከዚህ በፊት በተናገርነው ነገር መልስ ስለምንሰጥበት ብቻ ሳይኾን በእነዚህ ነገሮች አማካኝነት ወቀሳችን እንዲከብድ በማድረጋችን ራሳችንን ከየትኛውም ዓይነት ይቅርታ ውጪ ስለምናደርገውም ጭምር ነው፡፡ የሌሎች ስዎች ጠባይ መራራነትን የሚመረምር ሰው እርሱ ራሱ ለፈጸማቸው ኃጢአቶች በፍጹም ይቅርታን አያገኝምና፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ፍርድን የሚፈርደው ከመተላለፎቻችን አንጻር ብቻ ሳይኾን አንተ በሌሎች ሰዎች ላይ ባስተላለፍከው ፍርድም ጭምር ተነሥቶ ነው፡፡

“እንዳይፈረድባችሁ አትፍረዱ" ብሎ ተግሣጹን የሰጠውም ለዚህ ነው (ማቴ.7፥1)፡፡ [የዚያን ጊዜ ላይ] የበደልከው ማንኛውም ዓይነት በደል ብቻዉን ሳይኾን በዚሁ [በደልህ ላይ] በባልንጀሮችህ ላይ የፈረድከው ፍርድም ተጨምሮበት ታላቅና ይቅር የማይባል ኾኖ ይገለጣልና፡፡ ርኅሩኅ፣ ቸርና ይቅር ባይ ሰው እርሱ የኃጢአቶቹን ክምር ቆርጦ ይጥላቸዋልና፡፡

መራራ፣ ጨካኝና በጥላቻ የተሞላ ሰው ደግሞ በደሎቹን በላይ በላይ እየጨመረ ያበዛቸዋልና፡፡ እንግዲያውስ ከእርሱ ካልራቅን በቀር ምግባችን ዐመድ ቢኾንም እንኳን ይህ ምንም እንደማይጠቅመን በማወቅ ሐሜትን ኹሉ ከአንደበታችን እናርቅ፡፡ “ወደ አፍ የሚገባ ኹሉ ወደ ሆድ አልፎ ወደ እዳሪ እንዲጣል አትመለከቱምን? ከአፍ የሚወጣ ግን ከልብ ይወጣል፤ ሰውንም የሚያረክሰው ያ ነው" (ማቴ.15፥17-18)፡፡ በመንገድ እያለፍህ ሳለ አንድ ሰው የሰውን ሰገራ ሲቆሰቁስ ብትመለከተው ይህን በማድረጉ አትገሥጸውምን? በሐሜተኞች ላይም እንደዚህ አድርግ፡፡ በእጅ የተቆሰቆሰው የሰው ሰገራ በሐሜት የሌሎች ሰዎችን ኃጢአት የመቆስቆስና ንጹህ ያልኾነ ሕይወታቸውን የማጋለጥ ያህል ሽታ የለውምና፤ ውስጥንም ኾነ ነፍስን አይጎዳምና፡፡ ስለዚህ ራሳችንን ከሐሜትና ከአሉባልታ ከነቀፋም እናርቅ፤ ባልንጀራችንም ኾነ እግዚአብሔርን አንማ!

ምክንያቱም ብዙ ሐሜተኞቻችን ወደ እንደዚህ ዓይነት ዕብደት እየተንደረደሩ ነው፤ ምላሳቸውን ከባልንጀሮቻቸው አልፈው በአምላካቸው ላይእያላቀቁ ነው፡፡ ይህ ምን ያህል ታላቅ ክፋት እንደ ኾነም አሁን ካጋጠመን ነገር መረዳት ትችላላችሁ፡፡

ሰው [ንጉሡ] ተሰድቧል፤ እነሆ በዚህ ወንጀል የተባበሩትም ኾኑ በዚህ ግብር ላይ ምንም እጃቸው እንደሌለ የሚያውቁትም እየፈራን እየተንቀጠቀጥንም ነው! እግዚአብሔር ግን ዕለት ዕለት ይሰደባል! ምን ዕለት ዕለት ብቻ በየሰዓቱ በባለጸጋውም በድኻውም፣ መከራ ባልደረሰባቸውም በደረሰባቸውም፣ በሐሜተኞችም ሐሜተኛ ባልኾኑ ሰዎችም ይሰደባል፡፡ ነገር ግን [አሁን] እንደዚህ ያለ [የሚያስፈራና የሚያርድ የሚያንቀጠቅጥ] ቃልን የሚሰማ ማንም የለም! በመኾኑም እንደ እኛ አገልጋይ የኾነ ሰው [ንጉሡ] ይሰደብ ዘንድ ፈቃዱ ኾነ፤ ይኸውም ይህ ስድብ በመድረሱ ምክንያት እንደ ምን ያለ መከራን እንዳመጣና በአንጻሩም የእግዚአብሔር ርኅራኄ እንደ ምን የበዛ እንደ ኾነ እንድናውቅ ነው፡፡ ምንም እንኳን ይህ የመጀመሪያችንና ብቸኛው ዓመጻችን ቢኾንም ይህ ስለ ኾነ ተብሎ የሚደረግልን ይቅርታም ኾነ ምሕረት ግን የለም፡፡ እግዚአብሔርን ግን በየቀኑ እናስቈጣዋለን! ይህን አድርገን ስናበቃ እንኳን ወደ እርሱ የመመለስ አዝማሚያ አናሳይም፤ ነገር ግን እርሱ ከታላቅ ትዕግሥቱ የተነሣ አሁንም ዝም ብሎናል! እንግዲህ የእግዚአብሔር ቸርነት እንደ ምን ታላቅ እንደ ኾነ ታያለህን? በአሁኑ ዓመጽ ላይ ተሳታፊ የነበሩ ስዎች ተወስደዋል፤ ወደ ወኅኒ ተጨምረዋል፤ ቅጣትም ተላልፎባቸዋል፡፡ እኛ ግን አሁንም ፍርሐት ላይ አለን፡፡ የተሰደበው ሰው እስከ አሁን ድረስ ምን እንደ ተደረገ ገና አልሰማምናº ውሳኔም አላስተላለፈምና እስከ አሁን ድረስ በረዓድ ተይዘናል፡፡ እግዚአብሔር ግን ይህን ስድብ በየቀኑ ይሰማል፤ ይህንን ግን ማንም ልብ አይለውም፤ እግዚአብሔር ቸርና ስውን ወዳጅ ነውና፡፡ በእርሱ ዘንድ ኃጢአትን መናዘዝ ብቻ በቂ ነው፤ ይህን ካደረጉም ያደረጉት ኃጢአት ኹሉ ይሰረዛልና፡፡ በሰው ዘንድ ግን ሙሉ ለሙሉ የዚህ ግልባጭ ነው፡፡ እነዚያ የበደሉ ሰዎች በደላቸውን ሲናዘዙ ቅጣታቸው ይበልጥ ይበረታል፤ ይኸውም ልክ አሁን እንደ ኾነው ማለት ነው፡፡

ዳግመኛም አንዳንዶቹ በስይፍ ጠፍተዋል፤ አንዳንዶቹ በእሳት ተቃጥለዋል፤ ለበረኻ አውሬዎች የተስጡም አሉ፡፡ ዐዋቂ ስዎች ብቻ አይደሉም፤ ሕፃናትም ጭምር እንጂ፡፡ ይህ የዕድሜአቸው ጨቅላነት፤ የሕዝቡ ጩኸት፣ እነዚህን ግብራት ሲፈጽሙ አጋንንት ያደሩባቸው መኾናቸው፣ ሊከፈል ያለው ግብር እንደማይቻል አድርገው ማሰባቸው፣ ድኽነታቸው ወይም ኹሉም ስው ስላመጸ እነርሱም አብረው ማመጻቸው፣ ከእንግዲህ ወዲህ እንደዚህ ያለ ተግባርን ደግመው እንደማይፈጽመ ቃል መግባታቸው ወይም ሌላ ይህን የመሰለ ምክንያት በፍጹም ሊያድናቸው አልቻለም፡፡ ከዚህ ይልቅ ያለ ምንም ጊዜያዊ እፎይታ ማንም እንዳያመልጥ ኾነው በታጠቁ ኃይሎች ተከብበው እየተመሩና እየተጠበቁ ተወስደው፣ ፍርሐት ኀዘናቸውን አስረስቶአቸዋልና ረዓድም ወርሮአቸዋልና እናቶቻቸው ከኋላ ኾነው ቢከተሉአቸውም ዳግመኛም ልጆቻቸው አንገታቸው እየተቈረጠ ሳለ እያዩ ኀዘናቸውን ለመግለጽ ሳያለቅሱ ወደ ጉድጓድ ተጣሉ እንጂ! እነዚህ ወንጀለኞች በሚቀጡበት ሥፍራ የነበሩ ሰዎችም በጥልቅ ኀዘን ተይዘው ነበር፤ ነገር ግን መቅረብና ከስጥመት ሊያድኑአቸው አልተቻላቸውም፡፡ ሌሎች ስዎች ብቻ ሳይኾኑ የገዛ እናቶቻቸው እንኳን ወታደሮቹን ከመፍራታቸው የተነሣ መቅረብ አልተቻላቸውም፡፡ መቅረብና ልጆቻቸውን ማዳንስ ይቅርና እንባቸውን እንኳን ማፍሰስ ይፈሩ ነበር!

ይቀጥላል....

(ትምህርት በእንተ ምክንያተ ሐውልታት፣ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ገጽ 79-96 በገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተተረጎመ)



ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ እውነተኛ ጾም፤ ስለ ሐሜት...በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ፦


ሐሜተኞችን ብቻ ሳይኾን ሌሎች ሰዎች ሲታሙ “እህ” ብለው የሚያደምጡትንም ጭምር ጆሮአቸውን እንዲዘጉ፣ “ወንድሙን በስውር የሚያማን እርሱን አሳደድሁ" ብሎ የተናገረውንም ነቢይ እንዲመስሉት እመክራለሁ (መዝ.100፥5)፡፡

ባልንጀራዉን ለማማት ብሎ ወደ አንተ የመጣውን ስው እንዲህ በለው፡- “ስለ እርሱ መልካም ነገር የምትናገርለት አሊያም ደግሞ የምታመሰግነው ሰው አለህን? ይህን በጎ መዓዛ ያለውን ዘይት ለመቀበል ጆሮዬን እከፍታለሁ፡፡ ክፉ ንግግርን የምታወራ ከኾነ ግን ቃሎችህ ወደ ጆሮዬ እንዳይገቡ እከለክላቸዋለሁ፤ ይህን ፍግና ቆሻሻ ወደ ጆሮዬ ለማስገባት አልፈቅድምና፡፡

ወንድምህ ክፉ መኾኑን ብትነግረኝ ግን ምን ይረባኛል? ይልቁንም እንዲህ ስታደርግ ራሴን እንድጎዳና ያለኝን እንዳጣ ታደርገኛለህ፡፡ ስለዚህ ስለ ወንድማችን ጥፋት ከምናወራ ይልቅ ስለ ራሳችን ኃጢአት እንጨዋወት! የሠራናቸውን መተላለፎች እንዴት ይቅርታ እንደምናገኝባቸው እንጨነቅ፣ ስለ ራሳችን ሕይወት እንደዚህ ያለ ትጋትና ምክክር እናሳይ፡፡

እስኪ ንገረኝ! ስለ ራሳችን ጉዳዮች ምንም ሳናስብ የሌሎች ሰዎችን ኃጢአት ለመመርመር እንዲህ በመፈለጋችን የምናገኘው ይቅርታ ወይም የሚደረግልን ምሕረት እንደ ምን ያለ ነው?! 'ሰው ቤት እንዲሁ ዘው ብሎ ገብቶ መመርመርና ቤቱ ውስጥ ምን ምን እንዳለ መበርበር ወራዳና እጅግ አሳፋሪ ተግባር እንደ ኾነ ኹሉ፥ የሌላ ስው ሕይወት ምን እንደሚመስል መመርመርም እንደዚሁ የመጨረሻው የጨካኝነት ደረጃ ነው፡፡

ከዚህ ኹሉ የከፋው ደግሞ እንደዚህ ዓይነት ሕይወትን የሚኖሩና የራሳቸውን ጉዳይ የረሱ ሰዎች፥ ይህን ሐሜታቸውን የሚነግሩትን ሰው ለሌላ ሰው እንዳይናገር መለመናቸውና መማጸናቸው እነርሱ እንደዚህ መናገራቸው ግን ተግሣጽ እንደ ኾነና ተገቢ ሥራን እንደ ሠሩ አድርገው ማሰባቸው ነው፤ ይህን ለሌላ ስው እንዳይናገር የምትማጸነው ከኾነ፡ አስቀድመህ እነዚህን ነገሮች ከመናገር ልትቈጠብ አይገባህም ነበርን? ጉዳዩ በአንተ እጅ እያለ ምሥጢሩ የተጠበቀ ነበር፤ አሁን ካጋለጥከው በኋላ ግን ለምሥጢሩ መጠበቅ አብልጠህ የምትተጋ ኾንክ፡፡ የሰማህ ሰው ለሌላ ሰው እንዳይናገር የምትፈልግ ከኾነ አንተው ራስህ ቀድመህ አትንገረው፡፡ የጉዳዩን ምሥጢራዊነት ለሌላ ሰው ከገለጥክ በኋላ የነገርከውን ነገር ምሥጢር እንዳያወጣ ብለህ ብታስጠነቅቀውና ብታምለው ግን ግብርህ አፍአዊና ረብ የለሽ ነው፡፡

“ሐሜት ግን'ኮ ይጣፍጣል፡፡" በፍጹም! ጣፋጭስ አለማማት ነው፡፡ ምክንያቱም ሐሜተኛ ሰው ካማበት ጊዜ አንሥቶ ጠበኛ ነው፤ ተጠራጣሪ ነው፤ ይፈራል፤ ይጸጸታል፤ ከዚህም የተነሣ ምላሱን ይነክሳል (ይከነክኗል)፡፡ እንዲህ በፍርሐትና በረዓድ ተይዞ ሳለም ከዕለታት በአንዷ ላይ የተናገረው ነገር ወደ ሌሎች ሰዎች ይዛመታል፡፡ ታላቅ የኾነ መከራ እንደዚሁም ረብ የለሽና የማይገ'ባ ጠላትነትን ያመጣበታል፡፡ የጉዳዩን ምሥጢራዊነት ለሌላ ሰው የማይናገር ሰው ግን ዐረፍተ ዘመኑን ያለስጋትና እጅግ ደስ ብሎት ያሳልፋል፤ እንዲህ ተብሎ እንደ ተጻፈ፡- “የሰማኸው ቃል በአንተ ዘንድ ይሙት! እንዲህ ያደረግህ እንደ ኾነ የሚያገኝህ ክፉ ነገር እንደሌለ እመን” (ሲራ.19፡10)፡፡ “በአንተ ዘንድ ይሙት" ሲል ምን ማለት ነው? አጥፋው፤ ቅበረው! ከዚህ በላይ እንዲኼድ አትፍቀድለት! ምንም እንዳይንቀሳቀስ አድርገው፤ ከዚህ ኹሉ በላይ ግን ሰዎች ሐሜትን ሲለማመዱ ታግሠህ እንዳትስማቸው ተጠንቀቅ፡፡" አንተም ድንገት በኾነ ጊዜ ላይ ሐሜትን ብትስማ የሰማኸውን ቅበረው፤ የተነገረህን አስወግደው፤ ወደ መርሳት ባሕርውስጥ ጣለው፤ ይህን ያደረግህ እንደኾነም ነገሩን እንዳልሰሙት ሰዎች ኾነህ የዚህ ዓለም ሕይወትህን በሰላምና በጸጥታ ታሳልፋለህ፡፡

ሐሜተኞች ከሚያሙአቸው ሰዎች በላይ እኛ እነርሱን [ሐሜተኞቹን] እንደምንጸየፋቸው ቢያውቁ ኖሮ ከዚያን ጊዜ ጀምረው እነርሱ ራሳቸው ይህን ክፉ ጠባይ በተዉ፣ ኃጢአታቸውን ባስወገዱ፣ ከዚያ በኋላም እኛን እንደ ታዳጊዎቻቸውና ረዳቶቻቸው አይተው ባመሰገኑን ነበር፡፡ እኛን ማመስገናቸው የወዳጅነታቸው ምልክት እንደ ኾነ ኹሉ ማማትና ስም ማጥፋትም አሁን ላዳበሩት ጠላትነት፣ ቂምና በቀል ጥንትና መሠረት ነበርና፡፡

ለሐሜት የሚሯሯጥና የሌሎች ሰዎችን ሕይወት በማጥናት የተጠመደ ሰው መቼም መች የራሱን ሕይወት መመልከት አይቻለውምና፥ የሰውን ምሥጢር ለማወቅ ከመጓጓትና በሌሎች ሰዎች ጉዳይ ዘው ብሎ ከመግባት ልማድ በላይ የራስህን ጉዳይየሚያስረሳ ምንም የለም፡፡ ምርምሩ ኹሉ በሌሎች ሰዎች ጉዳይ ጣልቃ መግባት ስለ ኾነ እርሱን የሚመለከቱ ኹሉም አስፈላጊ ነገሮች ለአደጋ የተጋለጡ ኾነው ይተ'ዋሉ፤ ችላም ይባላሉ፡፡ ሰው ትርፍ ጊዜዉን የገዛ ራሱን ኃጢአቶች እንደዚሁም እንዴት ሊያስወግዳቸው እንደሚገባው ቢያስብ መልካም ነው፤ መንፈሳዊ ምንድግናንም ገንዘብ ያደርጋል፡፡ ኹልጊዜ በሌሎች ሰዎች ጉዳይ የምትጠመድ ከኾነ ግን የራስህን ክፉ ግብሮች የምታስተውላቸው መቼ ነው?

ይቀጥላል....

(ትምህርት በእንተ ምክንያተ ሐውልታት፣ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ገጽ 79-96 በገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተተረጎመ)

6k 0 65 3 80


ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ እውነተኛ ጾም፤ ስለ ሐሜት...በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ፦


እየጾምክ ነውን? እንግዲያውስ መጾምህን በተግባር አሳየኝ! "እንዴት አድርጌ ላሳይህ?" ነው ያልከኝ? ድኻው እርዳታህን ፈልጎ እንደ ኾነ ቸርነትን አድርግለት! የጠላኸውን ሰው ስታየው ፈጥነህ ታረቀው! ባልንጀራህ ክብርን አግኝቶ ስታይ አትቅና! መልከ መልካም ሴትን ስታይ ለዝሙት ሳትመኛት እንዲሁ አልፈሃት ኺድ! አፋችን ብቻ ሳይኾን ዓይናችንም፣ ጆሮአችንም፣ እግራችንም፣ እጃችንም፤ በአጠቃላይ የሰውነታችን ሕዋሳት በሙሉ ሊጾሙ ይገባልና፡፡

እጆች ከንጥቂያና ከንፉግነት ይጹሙ፡፡ እግሮች የኃጢአት ትርኢቶችን ለማየት ከመፋጠን ይጹሙ፡፡ ዓይኖች በውጫዊ ውበት ላይከመተከል ወይም እንግዳ በኾነ መልኮች ምክንያት ከመቅበዝበዝ ይጹሙ፡፡ ማየት የዓይኖች ምግብ ነውና፤ እናም የሚታየው ነገር ክፉ ወይም ሥርዓት የለሽ ከኾነ ጾምን ያረክሳል፤ ነፍስንም ያውካል፡፡ የሚታየው ነገር በጎ ከኾነ ግን ጾምን የሰመረች ያደርጋታል፡፡ በጾም ምክንያት ነውር ከሌለባቸው ምግቦች ተከልክለን ሳለ በዓይኖቻችን ነውር የኾኑትን ነገሮች የምንነካ ከኾነ እጅግ ሞኝነት ነው፡፡ ሥጋን ከመብላት ተከልክለሃልን? እንግዲያውስ በዓይኖችህ አድርገህ አመንዝራነትን ሴሰኝነትን አትብላ፡፡ ጆሮም ይጹም፡፡ የጆሮ ጾምም “ሐሰተኛ ወሬ አትቀበል" እንዲል ሐሰተኛ ወሬንና ሐሜትን አለመስማት ነው (ዘጸ.23፡1)፡፡

አንደበትም ከከንቱ ንግግሮችና ከዘለፋ ይጹም፡፡ አዕዋፋትንና™ ዓሦችን ከመብላት ተከልክለን ሳለ ወንድሞቻችንን ግን የምንነክሳቸውና የምንበላቸው ከኾነ ምን ጥቅም አለው? ክፉ የሚናገር እርሱ የወንድሙን ሥጋ ይበላል፤ የባልንጀራዉንም ሰውነት ይነክሳል፡፡ እንዲህም በመኾኑ ተወዳጅ ጳውሎስ “እርስ በርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ" በማለት አስፈሪ ኃይለ ቃልን ተናግሯል (ገላ.5፥15)።

ጥርስህን በሥጋው ላይ አላኖርህም፤ ሐሜትህን በነፍሱ ላይ ተክለህ ግን ቁስሉ ክፉኛ እንዲዛመት አድርገሃል፡፡ በሺሕ መንገዶችም ራስህንና ወንድምህን እንዲሁም ሌሎች ብዙ ሰዎችን ጎድተሃል፡፡ ባልንጀራን በማማትህ ሐሜትህን የሚሰማ ሰው ይበልጥ እንዲያማ አነሣስተኸዋልና፡፡ እንዴት ያልከኝ እንደኾነም፦ ቀድሞም ቢኾን ክፉ ሰው ከነበረ አሁን ደግሞ በክፋቱ ሌላ ተባባሪ ሲያገኝ ይበልጥ ግድየለሽ ይኾናልና፡፡ ሐሜትህን የሚሰማ ሰው ጻድቅ ከኾነ ደግሞ ይታበያል፤ ይኮፈሳል፤ የሌሎች ሰዎችን ኃጢአት ሲሰማ ራሱን ከፍ ከፍ ያደርጋልና፡፡ ከዚህ ጎን ለጎንም” ቤተ ክርስቲያንን በአጠቃላይ ትጎዳለህ፡፡ ይህን የሚሰሙህ ሰዎች ኃጢአተኛ ነው ብለው የሚያስቡት አንተ የነገርካቸውን ሰው ብቻ ሳይኾን አጠቃላይ ክርስቲያኖችን ወደ መንቀፍም ይፋጠናሉና፡፡

ኢ-አማንያኑ “እገሌ'ኮ ዘማዊ ነው፤ ወይም ባለጌ ነው" በማለት ብቻ አያቆሙም፤ ስለዚያ አንድ ኃጢአተኛ ሰው ከመናገር ይልቅ ክርስቲያኖችን በአጠቃላይ ይነቅፋሉ እንጂ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የእግዚአብሔር ክብር እንዲነቀፍ አድርገሃል፤ እኛ በጎ ምግባር ሲኖረን እንደሚከብር ኹሉ ኃጢአት ስንሠራ ደግሞ ይነቀፋልና፤ ይሰደባልምና!

አራተኛ ምክንያት ደግሞ የምታማውን ሰው አዋርደኸዋል፤ አንተን እንዲጠላህ ስላደረግኸውም ከቀድሞ ይልቅ ይበልጥ ሐፍረት የለሽ እንዲኾን አድርገኸዋል፡፡ አምስተኛ በማይመለከትህ ነገር ራስህን በመክተትህ በራስህ ላይ ፍርድን አከማችተሃል። ስለዚህ አንድ ሰውስ እንኳን፦ “የምናገረው ነገር ሐስት ከኾነ ሐሜተኛ ነኝ፤ እውነት ከተናገርሁ ግን ሐሜተኛ አይደለሁም" ብሎ አይንገረኝ፡፡ ምንም እንኳን የምትናገረው ነገር እውነት ቢኾንም ይህም ቢኾን ክፉ ነው፤ ወንጀል ነው:: ያ ፈሪሳዊው ሰው ስለ ቀራጩ እውነት የኾነውን ነገር ተናገረ፤ ነገር ግን እንዲህ ስለ ተናገረ ምንም ጥቅም አላስገኘለትም፡፡

እስኪ ንገረኝ! የኋለኛው ሰውዬ ቀራጭና ኃጢአተኛ አልነበረምን? ቀራጭ እንደ ነበር ለማንም ሰው ግልጽ ነው፡፡ ነገር ግን ፈሪሳዊው ሰው ወንድሙን በማማቱ ምክንያት ከቤተ መቅደሱ አንዳች ረብን ሳያገኝ ተመለስ፡፡

ወንድምህን ማስተካከል ትፈልጋለህን? አልቅስለት፤ ወደ እግዚአብሔር ጸልይለት፡፡ ብቻዉን ወስደህ ገሥጸው፤ ምከረው፤ ለምነው! ቅዱስ ጳውሎስም እንዲህ አድርጓል፡- “እንደገና ስመጣ በእናንተ ዘንድ አምላኬ እንዲያዋርደኝ አስቀድመውም ኃጢአት ከሠሩትና ስላደረጉት ርኵሰትና ዝሙት መዳራትም ንስሐ ካልገቡት ወገን ስለ ብዙዎች ምናልባት አዝናለሁ ብዬ እፈራለሁ" (2ኛ ቆሮ.12፥21)።

ለኃጢአተኛው ፍቅርህን አሳየው፡፡ ለብቻው አድርገህ ስትገሥጸው፤ ስትመክረውና ስትለምነው ከኃጢአቱ እንዲመለስ ካለህ እንክብካቤና ጉጉት እንጂ እርሱን ከማጋለጥ አንጻር እንዳልኾነ አሳምነው፡፡ ስለዚህ በትክክል ከያዘው ደዌ እርሱን መፈወስ ፈልገህ ከኾነ እግሩን ያዘው፤ እቀፈው፤ ይህን ስታደርግም ምንም ምን አትፈር፡፡ ሐኪሞችም ብዙውን ጊዜ እንደዚህ ያሉ ነገሮችን ያደርጋሉ! ታካሚዎቻቸው መድኃኒትን መውሰድ የማይፈልጉ ከኾነ እያቀፉአቸውና እየለመኑአቸው ቆይተው በኺደት ጠቃሚዉን መድኃኒት ይሰጡአቸዋል፡፡ አንተም እንደዚህ አድርግ፡፡ ቁስሉን ለካህን እንዲያሳይ አበረታታው፤ ልክ እንደ ሐኪሙ ኃጢአተኛዉን የሚንከባከበው፤ መድኃኒቱን የሚስጠው፣ ስለ መዳኑም እጅግ የሚጓጓው እርሱ ነውና፡፡

ይቀጥላል....

(ትምህርት በእንተ ምክንያተ ሐውልታት፣ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ገጽ 79-96 በገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተተረጎመ)



ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ እውነተኛ ጾም፤ ስለ ሐሜት...በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ፦

....እንኪያስ የነነዌ ሰዎች እንዴት አድርገው እንደ ጾሙና እንዴት ከዚያ [የእግዚአብሔር] ቊጣ ሊድኑ እንደ ቻሉ እንመልከት "ሰዎችና እንስሶች ላሞችና በጎች አንዳችን አይቅመሱ" ይላል ነቢዩ (ዮና.3፥7)፡፡

አንተ ነቢይ! ምን እያልክ ነው? እስኪ ንገረኝ! ግዕዛን የሌላቸው እንስሳት እንኳን ሳይቀሩ ሊጾሙ፣ ፈረሶችና በቅሎዎችም ማቅ ሊለብሱ ግድ ነውን? “አዎ! እነርሱም ቢኾኑ ሊጾሙ ደግሞም ማቅ ሊለብሱ ግድ ነው" ብሎ ይመልሳል፡፡ ምክንያቱም አንዳንድ ባለጸጎች በሞቱ ጊዜ ዘመድ አዝማዱ፣ የወንድም የሴትም አገልጋዮች ብቻ ሳይኾኑ ፈረሶችም ቢኾኑ የኀዘናቸውን ታላቅነት ለማሳየት ሰው ኹሉ እንዲያለቅስ ለማድረግ ማቅ እንዲለብሱ፣ በጋላቢዎቻቸው አማካኝነት የመቃብሩን ሥፍራ እንዲዞሩ ይደረጋሉና፡፡ በመኾኑም የነነዌ ከተማ ልትጠፋ በተቃረበች ጊዜ ግዕዛን የሌላቸው እንስሳትም ቢኾነ ማቅ ለብሰዋል፤ አርዑተ ጾምንም (የጾምን ቀንበር) ተሸክመዋል፤ እንዲህ ለማለት “እነዚህ እንስሳት የእግዚአብሔርን ቊጣ በአመክንዮ ሊረዱት አይችሉም፤ ስለዚህ ይህ ቊጣ ከእግዚአብሔር ዘንድ የታዘዘ እንደ ኾነ በጾም እንዲገባቸው አድርጉ፡፡ ከተማይቱ ከተገለበጠች መቃብራችን የምትኾነው ለእኛ ለነዋሪዎቿ ብቻ ሳይኾን ለእንስሳቱም ጭምርነውና፡፡ ስለዚህ የቅጣቱ ገፈት ተካፋዮች የሚኾኑ ከኾነ ከጾሙም ተካፋዮች ይኹኑ፡፡" ነቢያቱ ኹልጊዜ ሲፈጽሙት የኖሩና የነነዌ ሰዎች ይህንን ሲያደርጉ ዓላማ ያደረጉት ሌላም ነገር ነበር፡፡

ሰብአ ነነዌ ከሰማያት እጅግ አስፈሪ የኾነ ቍጣ እየመጣ እንደ ኾነ ሲመለከቱ፣ ለራሳቸው ምንም ምን ሳይሉ ሊቀጡ ያሉት እንስሳቱም፡- ማቅ ለብሰው፣ ጥቂት ምሕረት ወይም ይቅርታ እንኳን የማይገባቸው ኾነው፣ ምን እንደሚያደርጉ ወይም ለተግሣጻቸው ረዳትን ከየት ማግኘት እንዳለባቸው ሳያውቁ፥ ግዕዛን የሌላቸው ፍጥረታትን መሸሸጊያ አደረጉ፤ አሟሟታቸው እጅግ አሳዛኝ እንደ ኾነ በመግለጽ በእነርሱ አማካኝነት ምልጃን አቀረቡ፤ ኀዘናቸውንና ጥፋታቸውን እንደ ልመና አቀረቡ፡፡ ስለኾነም በቀደመው ጊዜ እስራኤላውያን ረሀብ በገጠማቸውና አገራቸውንም ትልቅ ድርቅ በመታው ጊዜ እንደዚሁም ኹሉም ነገሮች በወደሙ ሰዓት ከነቢያቶቹ አንዱ እንዲህ አለ፡- “ጊደሮች ከምሳጋቸው ጠፉ፤ ማሰማሪያ የላቸውምና የላምም መንጎች እጅግ ጮኹ፤ እንስሶችም ኹሉ ወደ ላይ ወደ አንተ አንጋጠጡ ፈሳሹ ውኃ ደርቆአልና" (ኢዩ.1፡17)፡፡ ሌላ ነቢይም ከድርቁ የተነሣ እያለቀሰ እንዲህ ብሏል፡- “ዋላ ደግሞ በምድረ በዳ ወለደች፤ ሣርም የለምና ግልገልዋን ተወች፡፡ የሜዳ አህዮችም በወና ኮረብታ ላይ ቆመዋል፤ እንደ ድራጎንም ወደ ነፋስ አለከለኩ፤ ልምላሜም የለምና ዓይኖቻቸው ጠወለጉ” (ኤር.14፡5-6)፡፡ ዳግመኛም ነቢዩ ኢዩኤል ዛሬ እንዲህ ሲል ሰምታችሁታል፡- “ሙሽራው ከእልፍኙ ሙሽራይቱም ከጫጉላዋ ይውጡ፤ ጡት የሚጠቡትን ሕፃናት ሰብስቡ” (ኢዩ.2፡16)፡፡

እንግዲህ እንጠይቅ! እንዲህ ሕፃናት እንዲጸልዩ የሚጠራቸው ስለ ምን ምክንያት ነው? “ለዓቅመ አዳምና ለዓቅመ ሔዋን የደረሱ ሰዎች ኹሉም የእግዚአብሔርን ቍጣ ስለ ቀሰቀሱ፥ እነዚያ በደል በማይሠራበት ዕድሜ ላይ ያሉ ሕፃናት የተቈጣዉን እግዚአብሔርን ይለምኑት” ሲል ነው፡፡

ነገር ግን አስቀድሜ እንደተናገርኩት ይህ ታላቅ የኾነውን የእግዚአብሔርን ቍጣ በምን ምክንያት እንደ ቀረ ማየት አለብን፡፡ እናስ በጾማቸውና ማቅ በመልበሳቸው ብቻ ነበርን? እንዲህስ አንልም፤ ኹለንተናዊ ሕይወታቸው ስለ ተቀየረ ነው እንላለን እንጂ፡፡ ይህስ ከመቼ ጀምሮ ያሳዩት ነው? ገና ነቢዩ ከመናገሩ አንሥቶ! ምክንያቱም ስለ እግዚአብሔር ቍጣ ስለ ጾማቸው የነገረን እርሱ ስለ ዕርቃቸውና የመታረቃቸው ዋናው ምክንያቱ ምን እንደ ኾነ ሲነግረንም እንዲህ ብሏል፡- “እግዚአብሔርም ሥራቸውን አየ” (ዮና.3፡10)፡፡ ምን ዓይነት ሥራቸውን ነው? መጾማቸውን ነውን? [ወይስ] ማቅ መልበሳቸውን ነውን? እግዚአብሔር ያየው ይህንን አይደለም፤ እነዚህን ኹሉ ነጥቦች አልፎ እንዲህ ብሎ ይጨምራልና፡- “ከክፉ መንገዳቸው እንደ ተመለሱ፤ እግዚአብሔርም ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም፡፡” እንግዲህ ከዚህ ቍጣ ያዳናቸው፣ በእነዚህ አሕዛብ ላይ እንዲራራና ምሕረቱን እንዲሰጣቸው ያደረገው የሕይወታቸው ለውጥ እንጂ ጾማቸው እንዳልኾነ ታያለህን?

እነዚህን ነገሮች የምናገራቸው ግን ጾምን ለማንኳስስ ብዬ አይደለም፤ ጾምን እንድናከብር ነው እንጂ፡፡ ጾምን ማክበር ማለት ከምግበ ሥጋ መከልከል ብቻ ሳይኾን ከምግባረ ኃጢአትም ጭምር ነውና፡፡ ጾምን ይበልጥ የሚያቃልለው ሰው እየጾምኩ ነው ብሎ ራሱን ከምግብ ብቻ የሚከለክል ሰው ነውና፡፡

ይቀጥላል....

(ትምህርት በእንተ ምክንያተ ሐውልታት፣ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ገጽ 79-96 በገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተተረጎመ)




#ቅድስት
#የዐቢይ_ጾም_ሁለተኛ_ሳምንት

የቅድስና ባለቤት የሆነው እርሱ እግዚአብሔር አምላክ ነው። እቀደስ አይል ቅዱስ፣ እባረክ አይል ቡሩክ ነው። በእርሱ የባሕርይ ቅድስና እኛን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ ቡሩክ ሆኖ ባረከን፣ ቅዱስ ሆኖ ቀደሰን፣ሕያው ሆኖ ሕያዋን አደረገን። የጸጋ ቅድስናንም ከእርሱ አገኘን። ቅድስናው የተለየ፣ የከበረ፣ የሚመሰገን፣ የሚሰጥ/የሚያድል፣ የሚያነጻ፣ የሚባርክ እናም የሚያስተሰርይ ስለሆነ እንከን፣ ጉድለት የሌለበት ምሉዕ ነው። ለባለሟሎቹ ቢሰጠው የማይጎድል፣ ተከፍሎ የሌለበት ቅድስና ሆኖ እኛም የቅድስና በጸጋ ተካፋይ ሆነናል።

የተሰጠንን ቅድስና ገንዘብ እንድናደርግ እና እንድንጠቀምበት ደግሞ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት፣ በምጽዋትና በሌሎች በጎ ምግባራት መትጋት ይገባናል። ‹‹እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ›› እንዲል፡፡ (ዘፍ.፪፥፫፣ ዘሌ.፲፱፥፪) የት መሄድ እንዳለብንም በግልጽ ልበ አምላክ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹ወደ ቅዱስ መቅደስህ እሰግዳለሁ፤ ስለ ትምህርትህና ስለ እውነትህ ስምህን አመሰግናለሁ፤ በሁሉ ላይ ቅዱስ ስምህን ከፍ ከፍ አድርገሃልና›› ይላል። (መዝ.፻፴፯÷፪) የተቀደሰን መሥዋዕት በተቀደሰ ቦታ እንፈጽማለን። መቼ ቢሉ፣ በሰንበት፣ በበዓላት በማኅበረ ዐቢይ/ክርስቲያኖች በሚሰበሰቡበት፣ ስመ እግዚአብሔር በሚጠራበት፣ ታቦት  ባለበት፣ እግረ እግዚአብሔር በቆመበት ቅዱስ ስሙን ከፍ ከፍ በማድረግ ቅድስናን ገንዘብ እናደርጋለን።

ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ለዐቢይ ጾም ሁለተኛው እሑድ በአዘጋጀው ምስጋና አማካኝነት ዕለቱ ‹‹ቅድስት›› የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ትርጉሙም ‹‹የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች›› ማለት ነው።  (መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ገጽ ፯፻፹፬) ቅድስት የሚለው ቃል ዕለቱ ‹‹ቅድስት›› ተብሎ የተሰየመበት ምክንያት ስለ ዕለተ ሰንበት እንዲሁም ስለ እግዚአብሔር አምላክ ፍጹም ቅድስና የሚያወሳ በመሆኑ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክም ፍጥረታቱ የእርሱን ስም በማመስገን ይኖሩ ዘንድ ለቅድስና ሕይወት ፈጥሯቸዋልና በሰንበት እሑድ ክርስቲያኖች የቅድስና ተግባራትን ከሌላው ቀን አብዝተው ይፈጽማሉ፡፡ ዕለት ከተግባር፣ ስም ከክብር የተባበረባት ክብርት ሰንበት ቅድስት ስለሆነች ቅዱስ ያሬድ “ቅድስት” ብሎ ጠራት። ይኸውም የምትቀድስ፣ ከብራ የምታከብረን፣ አክብረናት የምንከብርባት በመሆኗ ነው።

ለዚህም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በጾመ ድጓ “ግነዩ ለእግዚአብሔር ወጸውዑ ስሞ ወንግርዎሙ ለአሕዛብ ምግባሮ፤ ሀቡ ስብሐተ ለስሙ፤ አክብሩ ሰንበተ ተገበሩ ጽድቀ፤ ዝግቡ ለክሙ መዝገበ ዘበሰማያት ኀበ ፃፄ ኢያማስኖ ወኢይረክቦ ሰራቂ፤ ድልዋኒክሙ ንበሩ ዘበላዕሉ ጸልዩ ኀበ ሀሎ ክርስቶስ” ትርጉም፦ “ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ስሙንም ጥሩ፤ ሥራውንም ለአሕዛብ ንገሯቸው፤ ለስሙም ምስጋናን አቅርቡ ሰንበትን አክብሩ፤ እውነትንም አድርጉ፤ ብል የማያበላሸው ሌባም የማያገኘው በሰማያት ያለ መዝገብን ለእናንተ ሰብስቡ፤ ተዘጋጅታችሁም ተቀመጡ፤ ክርስቶስ ወዳለበት ወደ ላይ አስቡ፡፡“  ስለዚህ ሰው ሰንበትን አክብሮ ጾሞ ጸልዮ፣ ቅድስናን ጠብቆ መኖር እንዲችል እግዚአብሔር የፍቅሩ መገለጫ የሆኑ ትእዛዛቱ ይነግሩናል።

#ቅዱስ_ያሬድም_ወቅቱን “#ቅድስት” ብሎ ሲሰይም፦

፩. #የአርባ_ቀን_ጾም_መጀመሪያ_በመሆኑ፦ ዕለቱ ከዐቢይ ጾም ቀናት ውስጥ አርባው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ጾም መጀመሪያ ስለሆነች፣

፪. #ቅድስት_ሰንበት_ላይ_በመዋሉ፣ እንግዲህ “የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ” ተብሏል፡፡ (ዘፀ.፳፥፰) የሰንበትን ቀን አስቀድሞ የቀደሰ የባረከ ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔርም ሰባተኛውን ቀን ባረከው፤ ቀደሰውም፤ እግዚአብሔር ሊያደርገው ከፈጠረው ሥራ ሁሉ በእርሱ ዐርፎአልና፡፡” (ዘፍ.፪፥፫)

“ከምእመናን ወገን አንድስ እንኳን በእሑድ ቀን ለገንዘብ መትጋት፣ ገንዘቤን አምጣ ብሎ መጣላት እና ዋስ መያዝ አይገባውም። ሁሉም ምእመናን ወደ ቤተ ክርስቲያን በንጽሕና በትሕትና ሆነው። ዳኛ ግብሬን፣ አበዳሪ ብድሬን፣ ኤጲስ ቆጶስ ዐሥራት በኵራት፣ ነጋ ድራስ ቀረጥ አምጡ ይሉናል ብለው ሳይፈሩ ይምጡ።

፫. #ወቅቱ_ወርኃ_ጾም_በመሆኑ፦ ምእመናን ይህንን ወቅት በጾም፣ በጸሎት፣ በእንባ፣ በስግደት፣ በአርምሞ፣ በመልካም ሥራ ቅድስናን የምናገኝበት፣ ጊዜው ሰው ወደ እግዚአብሔር አብዝቶ የሚተጋበት ወቅት በመሆኑ፣ ለእግዚአብሔር የሚገባ ነገር ለማድረግ የነገር ሁሉ መጀመሪያ፣ ለመልካም ነገር መነሻው በቅድስና በንጹሕ ልቡና መቅረብ ስለሆነ ቅድስት ብሏታል።  “እስመ ጾም እማ ለጸሎት ወእኅታ ለአርምሞ ወነቅዓ ለአንብዕ መቅድመ ኩሉ ግብር ሠናይት፤ ጾም ማለት የጸሎት እናት፣ የትሕትና እኅት፣ የእንባ ምንጭ፣የመልካም ሥራ ሁሉ መጀመሪያ ናት” እንዳለው ቅዱስ ያሬድ። ”ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም ዐውጁ” የተባልን የተሰጠንን የጸጋ ቅድስና በእጃችን ላይ መኖሩን አመላካች ቃል ነው። (ኢዩ.፩፥፲፬)

፬. #የወንጌል_ትእዛዝ_በመሆኑ፡ ዕለቱን ተጠቅሞ ዓለምን አስተምሮበታል። “ዛቲ ዕለት እንተ ገብረ እግዚአብሔር ንትፈሣሕ ወንትሐሠይ ባቲ”  ትርጉም፡- “ይህች ዕለት እግዚአብሔር የሠራት ቀን  ናት፤ ሐሤትን እናድርግ፥ በእርስዋም ደስ ይበለን።” (መዝ.፻፲፯፥፳፬) ቅዱስ ዮሐንስም በራእዩ ሰንበት የጌታ ቀን ስለመሆኗ እንዲህ ይላል፤ “በጌታ ቀን በመንፈስ ነበርሁ፡፡” (ራእ. ፩፥፲)

ሊቃውንቱ በፍትሐ ነገሥት “ተጋብኡ ኵሎ ዕለት ኀበ ቤተ ክርስቲያን ወፈድፋደሰ በዕለተ ሰንበት ወበበዓላት ወበዕለተ ትንሣኤ ዘውእቱ ዕለተ እሑድ” ትርጉም፦ “ሁልጊዜ በቤተ ክርስቲያን ተሰብሰቡ፤ ይልቁንም በዕለተ እሑድ፣ በዕለተ ቀዳሚት፣ በጌታ በዓላት ወደ ቤተ ክርስቲያን ተሰብሰቡ” በማለት አዘውናል፡፡ (ፍትሐ ነገሥት፣ ገጽ ፪፶፬)

በትጋት ጾመን፣ ጸልየን ርስቱን እንድንወርስ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምልጃ፤ የቅዱሳን በረከት ይጠብቀን።

የዕለቱ መዝሙር (ከጾመ ድጓ)፦ ግነዩ ለእግዚአብሔር

#ምንባባት
➛ ፩ኛ ተሰ.፬÷፩-፲፫
➛ ፩ኛ ጴጥ.፩÷፲፫-ፍጻ.
➛ ሐዋ. ፲÷፲፯-፴

#ምስባክ
“እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ::
አሚን ወሠናይት ቅድሜሁ፣
ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ፤

(እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ፈጠረ፡፡ እምነትና በጎነት በፊቱ፣ ቅድስናና የክብር ገናናነት በመቅደሱ ውስጥ ናቸው፡፡”
(መዝ.፺፭÷፭)

#ወንጌል
(ማቴ.፮÷፲፮-፳፭)

#ቅዳሴ
ዘኤጲፋንዮስ 

(ማኅበረ ቅዱሳን)

7.7k 1 107 2 57


ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ እውነተኛ ጾም፤ ስለ ሐሜት...በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ፦

እየተናገርሁ ያለሁትም ስለ እውነተኛ ጾም ነው እንጂ ብዙዎች እንደሚጾሙት ያለውን ጾም አይደለም፡፡ እየተናገርሁ ያለሁት ከኃጣውእም ጭምር ስለ መከልከል ነው እንጂ ከጥሉላት ብቻ ስለ መከልከል አይደለም፡፡ የጾም ጠባይዋ እንደዚህ ነውና፤ “በጨዋታ የሚታገል ማንም ቢኾን እንደሚገባ አድርጎ ባይታገል የድሉን አክሊል አያገኝም" እንደ ተባለ እንደሚገባው አድርገው ካልጾሙ በቀር የሚተገብሯትን አታድናቸውም (2ኛ ጢሞ.2፡5)፡፡

በመጾም እየደከምን ሳለ የጾም አክሊልን ካላገኘን እንዴትና በምን ዓይነት አኳኋን ይህን ልንፈጽመው እንደሚገባው ልንረዳ ያስፈልጋል፡፡ ፈሪሳዊዉም ጾሞ ነበርና፤ ከዚያ በኋላ ግን ወደ ቤቱ የኼደው ባዶ እጁንና የጾሙን ፍሬ ሳያገኝ ነውና (ሉቃ.18፥12)፡፡ ቀራጩ ደግሞ በአንጻሩ አልጾመም ነበር፤ ነገር ግን ከጾመው ፈሪሳዊ ይልቅ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ያገኘው እርሱ ነው፡፡ ይህም የኾነበት ምክንያት [ቀራጩ ባይጾምም ተጠቀመ፤ በመፃዒ ሕይወቱም ጾም አላሻውም ለማለት ሳይኾን ከተአምኖ ኃጣውእ ጋር] ሌሎች ግብራት ካልተከተሏት በቀር ጾም ረብ ጥቅም እንደሌላት [እና ትሕትና የጾም አጣማጅ መኾኑን/ የምትሠምረው ከትሕትና ጋር መኾኑን] እንድታውቅ ነው፡፡

የነነዌ ሰዎች ጾመዋል፤ የእግዚአብሔር ምሕረትንም አግኝተዋል (ዮና.3፥10)፡፡ እስራኤላውያንም ጾመው ነበር፤ ነገርግን እያጉረመረሙ ተመለሱ እንጂ በመጾማቸው አንዳች ጠቀሜታን አላገኙም (ኢሳ.58፥3-7፣ 1ኛ ቆሮ.9፥26)፡፡ ስለዚህ እንዴት መጾም እንዳለባቸው ለማያውቁ ሰዎች የጾም ጉዳቱ ትልቅ ነውና በጥርጣሬ እንዳንኼድ፣ እንዲሁ አየርን እንዳንደልቅ፣ እንዲሁ ከጨለማ ጋር እንዳንጋደል ይህን የምናከናውንባቸውን ሕጎች ልንማር ያስፈልገናል፡፡

ጾም መድኃኒት ናት፡፡ አወሳስድዋን በትክክል ላላወቁ ግን ጥቅም የላትም፡፡ ይህችን መድኃኒት የሚወስድ ሰው በየስንት ሰዓቱና በምን ያህል መጠን እንደምትወሰድ፣ ለምን ዓይነት በሽታ እንደምትጠቅም፣ በየትኛው አከባቢና የአየር ኹናቴ እንደምትወሰድ፣ ከእርሷ ጋር የሚኼዱና የማይኼዱ ምግቦችን እንዲሁም ከእርሷ ጋር የማይስማሙ ሌሎች ነገሮችን ለይቶ ማወቅ አለበት፡፡ እነዚህን ግምት ውስጥ አስገብቶ የማይወስዳት ሰው ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ታመዝንበታለች፡፡ አንድ በሐኪም የታዘዘልንን የደዌ ዘሥጋ መድኃኒት እንዲያሽለን ስንፈልግ በጥንቃቄ ልንወስደው ያስፈልጋል፤ የነፍሳችንን ደዌና በአእምሮአችን ውስጥ ያሉ ቁስሎችን ለመፈወስ ብለን በምንወስደው መድኃኒት ደግሞ ከዚህ የበለጠ መጠንቀቅ ይገባናል፡፡

ይቀጥላል....

(ትምህርት በእንተ ምክንያተ ሐውልታት፣ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ገጽ 79-96 በገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተተረጎመ)


ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለ እውነተኛ ጾም፤ የሰውን ሥጋ ከመብላት በላይ ክፉ ስለ ኾነው ሐሜት በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ፦

ወዳጄ ሆይ! ሰው አስፈራርቶሃልን? በሰማያት ወዳለው ጌታ ተፋጠን፤ ምንም ክፉ ነገርም አይደርስብህም፡፡ እንዲህ በማድረጋቸው የቀደሙ ሰዎች ከመከራቸው ሊድኑ ችለዋል፤ ወንዶች ብቻ አይደሉም፤ ሴቶችም ጭምር እንጂ፡፡ አስቴር የምትባል አንዲት ዕብራዊት ሴት ነበረች፡፡ ይህቺ አስቴርሊጠፉ ሲሉ በዚሁ ዘዴ መላው እስራኤላውያንን ታድጋቸዋለች፡፡ የፋርስ ንጉሥ ኹሉም እስራኤላውያን በአስቸኳይ እንዲገደሉ ትእዛዝ ባስተላለፈና በቊጣው ፊት ሊቆም የሚችል ማንም ባልነበረበት ጊዜ+ ይህቺ ሴት የደስታ ልብሷን አውልቃ የኀዘን ልብሷን ስትለብስ፣ በራሷ ላይ ዐመድና ትቢያ ስትነሰንስ፣ ወደ ንጉሡ ስትኼድ ጊዜ ቸሩ እግዚአብሔር ከእርሷ ጋር እንዲኾን ስትማጸን፤ ጸሎቷንም ስታቀርብ የተናገረቻቸው ቃላት እነዚህ ነበሩ “ጌታ ሆይ! ቃሎቼ በአንተ ዘንድ የተወደዱ ይኹኑ፣ በአንደበቴም በጎ ነገርን አድርግ" (አስቴ.4፡17)፡፡ ስለ መምህራችን ወደ እግዚአብሔር የምናቀርበው የእኛ ጸሎትም ይህ ሊኾን ይገባል፡፡ አንዲት ሴት ስለ እስራኤላውያን ስለ ጸለየች የአረማውያንን ንጉሥ ቊጣ ካበረደችው ከዚህ ታላቅ ቤተ ክርስቲያን ጋር ኾኖ ስለ ታላቂቱ ከተማ የሚለምነው መምህራችንም ከዚህ በበለጠ መልኩ ትሑቱንና ርኅሩኁን ንጉሥ ማሳመን ይችላል፡፡

እግዚአብሔርን በመበደል የተሠሩትን ኃጢአቶች የመፍታት ሥልጣን ካለው ሰውን [ንጉሡን] የበደሉትን ደግሞ ይበልጥ ሊፈታቸውና ከቊጣው ሊስውራቸው ይቻሏል፡፡ እርሱ ራሱም ገዢ ነው! ገዢነቱም ከሌላው [ኹሉ] የከበረ ነው፡፡ ምክንያቱም በንጉሡ ላይ ተፈጻሚ የሚኾኑ ቅዱሳት ሕጎችም ቢኾኑ ተፈጻሚ የሚኾኑት በእርሱ ነውና፡፡ ከላይ ከአርያም በጎ ነገርን ሲፈልግ ንጉሡ ወደ ካህኑ ይኼድ ዘንድ አለው፤ ካህኑ ግን ይህን ፈልጎ ወደ ንጉሡ አይኼድም፡፡ [እንዴት ያልከኝ እንደ ኾነም እንዲህ ብዬ እመልስልሃለሁ] እርሱም ጥሩር አለውና ይኸውም የጽድቅ ጥሩር ነው፡፡ መታጠቂያ [ቀበቶ] አለው፤ እርሱም የእውነት መታጠቂያ ነው፡፡ እጅግ የተከበረ ጫማ አለው፤ እርሱም የሰላም ወንጌል ነው፡፡ ሰይፍ አለው፤ ከብረት የተሠራ ግን አይደለም፤ ከመንፈስ እንጂ፡፡ ዳግመኛም በራሱ ላይ ቁር አለው፡፡ ይህ የትጥቅ ልብስ እጅግ ግርማ ሞገስ ያለው ነው፡፡ የጦር ዕቃዎቹ እጅግ ውብ ናቸው (ኤፌ.6፡11-17)። የንግግር ችሎታው ታላቅ እንደዚሁም ኃይልን lots የተሞላ ነው፡፡ ስለዚህ ከሥልጣኑ ከፍተኛነት፣ ከሰውነቱ ታላቅነት፣ ከኹሉም በላይ ደግሞ በእግዚአብሔር ባለው ተስፋ ንጉሡን በነጻነትና በማስተዋል ያናግሯል፡፡

ስለዚህ እንጸልይ፤ ልመናችንን እናቅርብ፤ እንማጸን፤ ወደ ሰማያዊው ንጉሥም ብዙ ዕንባን የተመላ መልእክተኛችንን እንላክ እንጂ ስለ ደኅንነታችን አንሥጋ! ይህን በጎ ምልጃ በምናደርግበት ጊዜ እንደ ወዳጅና ረዳት ኾኖ የሚደግፈንም ይህ ጾም አለልን፡፡

ክረምት አልፎ በጋ ሲመጣ ነጋዴው መርከቡን ወደ ባሕሩ ያስገባል፣ ወታደር የጦር መሣሪያውን ይሰነግላል የውጊያ ፈረሱንም ለጦርነቱ ያዘጋጃል! ገበሬው ማጭዱን ይስላል መንገደኛው በድፍረት ረጅም መንገድን ይጓዛል፤ አርበኛው (wrestler) ልብሱን አወላልቆ ለትግሉ ይዘጋጃል፡፡ እኛም ልክ እንደዚሁ ጾም ሲመጣ መንፈሳዊ በጋ እንደ ገባ በማሰብ እንደ ወታደሩ የጦር ዕቃ መሣሪያዎቻችንን እንሰንግላቸው፤ እንደ ገበሬው ማጭዳችንን እንሳል! እንደ ነጋዴዎቹ አሳቦቻችን ከልክ በላይ በኾኑ የፍላጎቶቻችን ሞገዶች ላይ እንዘዛቸው፤ እንደ መንገድ ተጓዦቹ ወደ መንግሥተ ሰማያት የምትወስደውን መንገድ እንጀምር፣ እንደ አርበኛውም ለተጋድሎው እንዘጋጅ፡፡ ክርስቲያን በአንድ ጊዜ ገበሬም፣ ነጋዴም፣ ወታደርም፣ አርበኛም ተጓዥም ነውና፡፡ እንዲህም ስለ ኾነ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ አለ፡- "መጋደላችን ከሥጋና ከደም ጋር አይደለምና ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ነው እንጂ፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሔርዕቃ ጦር ኹሉ ልበሱ" (ኤፌ.6፡12)፡፡ አርበኛ ሰው አይተሃልን? ወታደርስ ተመለክተሃልን? እንኪያስ አንተም አርበኛ ከኾንክ ለትግሉ ተዘጋጅተህ ዕራቁትህን ልትኾን ያስፈልግሃል፡፡ ወታደር ከኾንክም ኹለንተናህን ታጥቀህ በውጊያው መስመር ላይ ልትሰለፍ ይገባ'ሃል፡፡ “እነዚህ ኹለቱ ነገሮችስ ማለትም ዕራቁት መኾንም ትጥቅ መልበስም በአንድ ጊዜ እንዴት ሊኾኑ ይችላሉ?" የሚል ጥያቄ በአእምሮህ ይመላለስ ይኾናል፤ ግድ የለም እኔ እነግርሃለሁ፡፡

ከዚህ ዓለም አሳብ ራስህን አውጣ፤ ያን ጊዜ አርበኛ ትኾናለህ፡፡ መንፈሳዊዉን የጦር ዕቃ ልበስ፤ ያን ጊዜም ወታደር ትኾናለህ፡፡ ወቅቱ አርበኛ ኾነህ የምትታገልበት ወቅት ነውና የዚህ ዓለም ፍላጎቶችህን አውልቀህ ጣል፡፡ ከአጋንንት ጋር የምናደርገው ጽነ ፍልሚያም አለንና መንፈሳዊ ትጥቅህን ልበስ፡፡ ስለዚህ ዲያብሎስ ከእኛ ጋር ትግል በሚገጥምበት ጊዜ የሚይዘውን እንዲያጣ ዕራቁት መኾን አስፈላጊ ነው፤ ድል የሚያደርግበትን ምት እንዳይመታንም በኹሉም አቅጣጫ በደንብ መታጠቅ ይኖርብናል፡፡

ሰውነትህን ኮትኩተው፡፡ እሾኾቹን መንጥራቸው፡፡ የመልካምነት ዘር ቃልም ዝራበት፡፡ እውነተኞቹን መንፈሳውያን ጥበባትን በታላቅ ጥንቃቄ ኾነህ አፍላቸው፤ ተንከባከባቸውም፤ ይህን ያደረግህ እንደኾነም እውነተኛ ገበሬ ትኾናለህ፡፡ ይህን ስታደርግም ተወዳጅ ጳውሎስ እንዲህ ይልሃል፡-“የሚደክመው ገበሬ ፍሬውን ከሚበሉት መጀመሪያ እንዲኾን ይገባዋል" (2ኛ ጢሞ.2፡6)፡፡ እርሱ ራሱ ይህን ዘዴ ይጠቀምበት ነበር፡፡ በመኾኑም ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ሲጽፍላቸው እንዲህ አለ፡- “እኔ ተከልሁ፤ አጵሎስም አጠጣ፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ያሳድግ ነበር" (1ኛ ቆሮ.3፡6)፡፡

በሆዳምነትህ የደነዘው ማጭድህን በጾም ሳለው፡፡ ወደ መንግሥተ ሰማያት የምትወስደውን መንገድ ተመልከታት፡፡ ውጣ ውረድ ያለባት፣ ጠባብና መከራ የበዛባት መኾኗን አስተውለህ በእርሷ ኺድ፡፡ እነዚህን ነገሮችስ እንዴት አድርገህ ልታደርጋቸው ትችላለህ? ሰውነትህን በመግዛትና [በጾም] በመቆንጠጥ! መንገዱ ጠባብ ስለኾነ ከሆዳምነቱ የተነሣ የወፈረ ሊያልፍባት አይቻለውምና፡፡

ገደብ የለሽ የፍላጎቶችህ ሞገዶችን ቀንሳቸው፡፡ የክፉ አሳቦች ፈተናን ከአንተ አርቅ፡፡ የንግድ መርከብህን ጠብቃት፤ ጥንቃቄ የተሞላበት ክኅሎትህን ተጠቀም፤ ያን ጊዜም የመርከብ አለቃ ትባላለህ፡፡ በእነዚህ ኹሉም ነገሮች ላይ ግን እንደ መሠረትና እንደ መሪ ጾምን ልንይዝ ግድ ይላል፡፡

ይቀጥላል...

(ትምህርት በእንተ ምክንያተ ሐውልታት፣ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ገጽ 79-96 ገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተረጎመው)


ሰላም!

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዐቢይ ጾም ስለ እውነተኛ ጾም፤ የሰውን ሥጋ ከመብላት በላይ ክፉ ስለ ኾነው ሐሜት ያስተማረውን ትምህርት ወደ እናንተ እናደርሳለን።

ሌሎችም ይህንን ቻናል ( https://t.me/beteafework ) እንዲቀላቀሉና ቤተሰብ እንዲሆኑ ሼር በማድረግ ይተባበሩ!

https://t.me/beteafework
https://t.me/beteafework
https://t.me/beteafework


ፋሲካ የሌለው ጾም
በየኔታ መ/ር ኤርምያስ አዳነ


የሰሜን ወሎ መንበረ ጵጵስና ሀገረ ስብከት የስብከተ ወንጌልና የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ ዋና ክፍል ኀላፊ

https://youtu.be/zWpAZcDHJ-c?si=QbWG2sFlpgW01zk2




የቅዱስ ኤፍሬም ድርሳን ስለ ጾም ስለ ጸሎትና ንስሓ


ወዳጄ ሆይ ከመብል ሽሽ፤ ከመጠጥም ራቅ፡፡ ጥጋብ ስንፍናን ትወልዳለችና፡፡ ጾምን ጠብቅ፡፡ በጾም ኃጢአት ይሠረያልና፡፡ እንዳይጠግብ፣ የሚጋልበውንም እንዳይጥለው ፈረስን እንደሚለጕሙት አንተም እንዲሁም ሥጋህ በፍትወት ነፍስህም በኃጢአት እንዳይወድቅ አፍህን ከመብልና ከመጠጥ ለጕም፡፡ ጌታችን እንበላና እንጠጣ ዘንድ አላዘዘንምና፡፡ ነገር ግን ወደ ፈተና እንዳትገቡ ጹሙ ጸልዩ አለን እንጂ፡፡

የሰማይ ወፎችን ተመልከቱ፡፡ ስለ መብል በወጥመድ ውስጥ ይወድቃሉና፡፡ አጥማጆችም በሚያጠምዱበት ጊዜ ወጥመዱን በመብል ይሠውሩታልና፡፡ እንዲሁም ሰይጣን ጣፋጩን ተስፋ አስደርጎ መራራውን ይሰጣል፡፡ ዳግመኛም ብዙውን ተስፋ አስደርጎ ትንሽን ይሰጣል፡፡ አዳምን አምላክ እንደሚሆን ተስፋ እንዲያደርግ አደረገው፡፡ ነገርግን ከገነት ዕራቍቱን አስወጣው፡፡

በጌታውም ዘንድ የተናቀ አደረገው፡፡ በዚህም መርገምን ወረሰ፡፡ በእርሱ ምክንያትም ምድር ተረገመች፡፡ ሞትም በሰው ላይ ሁሉ ሠለጠነ፡፡ የሚበር ወፍ ወደ ምድርካልተመለከተ ወደ ወጥመድ አይወርድም፡፡ እንዲሁም ለሚጾም ሰው ልቡ በሰማይ ያለውን ያስብ ዘንድ ሥጋው በኃጢአት እንዳይወድቅ ለሰውነቱ ምኞቷን ይከለክላት ዘንድ ይገባል፡፡

ጾም የጸናች ናት፡፡ ትሕትናም የንስሓ ራስ ናት፡፡ በጾም ኤልያስ ከመላእክት ጋር ተቆጥሯልና፡፡ ኤልሳዕም የመምህሩን የኤልያስን መንገድ ተከተለ፡፡ ዕጥፍ ድርብ በረከቱንም አገኘ፡፡

ወንድሞቼ ሆይ በአጋንንት ላይ በሥጋ ድል ማድረግን እናገኝ ዘንድ በጾምና በበጎ ሥራ ሁሉ የመምህሮቻችንን መንገድ እንከተል፡፡ ንጹሕና የተመረጠ ጾምን እግዚአብሔርይወዳል፡፡ አመፃ ስንፍና ናት፡፡ እግዚአብሔር አማፅያንን ፈጽሞ ይጠላቸዋል፡፡ በአፉ እየጾመ ወንድሙን ለሚገድል ለእርሱ ወዮለት፡፡ በአፉ ጾምን ለሚያውጅ በአንደበቱ ደግሞ አመፃን ለሚናገር ለእርሱ ወዮለት፡፡

ወንድሜ ሆይ አፍህ ከጾመ ልብህም እንዲሁም ይጾም ዘንድ እለምንሃለሁ። እነሆ ዐይንኖችህ ክፉን ከመመልከት ይጹሙ፡፡ እጆችህና እግሮችህም ከክፉ ሁሉ ይጹሙ፡፡ የጠላት ወጥመዱ ብዙ ነውና፡፡ በንጉሥ ፊት ተጋዳይ ወታደርን ልትሆን ብትወድ የጦር ዕቃን ትይዝ ዘንድ ተገቢ ነው፡፡ እንዲሁም ከሰይጣን ወጥመድ መዳን የሚወድ ሰው የክርስቶስን ትዕዛዙን ይጠብቅ፡፡ ከገሃነም እሳት ትድን ዘንድ ከትዕቢት ራቅ፡፡መንግሥተ ሰማያትንም ትወርስ ዘንድ ትሕትናን ፈልግ፡፡

ወዳጄ ሆይ እኔስ ከመብልና ከመጠጥ ትሸሽ ዘንድ ጾምንም በፍጹም ልብህ ትከተላት ዘንድ እፈልጋለሁ፡፡ ትሑታንን ውደዳቸው ከትዕቢተኞችም ራቅ፤ ከጥላቻ ፈቀቅ በል፤ ሰላምንም ፈልጋት፡፡ የክርስቶስን ትዕዛዝ ትፈጽምም ዘንድ በፍቅር ሩጥ፡፡ በአንተ ላይ የኃጢአት ፍሬ እንዳይታይም ከልብህ ቂምንና በቀልን አስወግድ፡፡ ክፉ ሕሊና በመጣብህ ጊዜ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በምታስፈራ የፍርድ ዐደባባይ የምትቆምባትን የፍርድ ቀን አስባት፡፡

(ቅዱስ ኤፍሬም ድርሳን በእንተ ጾም ወጸሎት ወንስሓ ➛ በድርሳነ ሠለስቱ ሊቃውንት መጽሐፍ ገጽ 189-199 በመምህር ቃለጽድቅ ሕግነህ የተተረጎመ)





የቅዱስ ኤፍሬም ድርሳን ስለ ጾም ስለ ጸሎትና ንስሓ

ወዳጆቼ ሆይ ወደ ሲኦል የሚያወርድ ወደ ሰማይም የሚያሳርግ ጾም እንዳለ ዕወቁ፡፡
የኤልዛቤል ጾም የከፋ ነው፡፡ በጾም ናቡቴን ትገድለው ዘንድ አዘዘች፡፡ አክዓብም በላ ጠጣ፡፡ ሰውነቱም ተደሰች፡፡ የድኃውን ርስት በነጠቀ ጊዜም ከክብሩና ከንግሥናው ወደቀ፡፡

ዳግመኛም ጳውሎስን በቤተ መቅደስ ሊገድሉት የፈለጉ የዓርባ ሰዎች ጾም የከፋ ነው፡፡ የእስራኤል ልጆች ጾም የከፋ ነው፡፡ በአፋቸው ጾምን ብለው በምግባራቸው እግዚአብሔርን አስቈጥተውታልና፡፡ ባዕለ ጸጋም እንዲሁ ይጾማል፤ የሚጾመው ግን ስለ እግዚአብሔር ብሎ አይደለም፡፡ ሀብቱ ንብረቱ እንዲበዛለት ነው እንጂ፡፡

የጦብያ ጾምም የተወደደ ሆነ፡፡ በሀገሩ ውስጥ የወደቀውን የችግረኛውን አስከሬን እስኪቀብር ድረስ ማዕድን አልሠራም ነበርና፡፡ የአይሁድ ጾም ግን ክፉ ጥፉ ነው፡፡ በአፋቸው እየጾሙ በልባቸው ክፋትን ያስባሉና፡፡ ልቡናውን ከክፉ ነገር ሁሉ ለሚያነጻ ሰው ግን ጾም ያማረ የተወደደ ነው፡፡

እግዚአብሔር መብልን አይጠላም እያልህ ጾምን የምትጠላ ባዕለ ጸጋ ሆይ እንዳትስት አስቀድሞ የሆነውን በጀሮህ ስማ፤ በልብህም አስተውል፤ የጾምን መንገድ የመብልንም ሥራ መርምር፡፡ አዳም ትዕዛዙን በተላለፈ ጊዜና ከዕፀ በለስ በበላ ጊዜ ምን ያህል ኀዘን እንደ መጣበት፣ ከክብሩም እንደ ተዋረደ፣ በሁሉም ዘንድ የተጠላ እንደሆነ፣ ወደ ተፈጠረባት መሬትም እንደ ተመለሰ፣ ከሕይወት ዛፍም እንደ ራቀ፣ ዕራቊትነቱንም ባየ ጊዜ መራራ ልቅሶን እንዳለቀሰ፣ ስለ ተሰጠው የብርሃን ልብስ ፈንታም የበለስ ቅጠልን እንደ ለበሰ ዕወቅ፡፡

በጾመ ጊዜ ግን ባዕለ ጸጋ ሆነ፡፡ በበላ ጊዜ ደግሞ ችግረኛ ሆነ፡፡ ለራሱም ጥልንና ቂምን አመጣ፡፡ ከዚህም የተነሣ ቃኤል ወንድሙን ገደለ፡፡ በአፉ ከዕፀ በለስ በላ፡፡ ሥጋውም በችግርና በድካም ጠፋ፡፡ በሰው መካከልም ጥልና አመፃ በዛ፡፡ የአዳም መብሉ የሰውን መንገድ የባሕር ውስጥ ጉዞ አስመሰለው፡፡ ጥጋብ ግን ብዙ ክፉ ሥራ አለባትና፡፡ በጾም ግን ኃጢአት ይሠረያል፡፡ ሰው በአንዱ አፉ ክፉና በጎ ይናገራል፡፡ መራራና ጣፋጭ ውኃ የሚፈስበት ምንጭ ምንኛ የከፋ ነው!

መራራና ጣፋጭ ውኃ የሚመነጭበትን ምንጭ ለሚመስለው ለቃየል ወዮለት፡፡ ወንድሙን ና! ወደ ምድረ በዳ እንውጣ ብሎታልና፡፡ አቤልም በየዋህነት ተከተለው፡፡ ከዚህም በኋላ ቃኤል አቤልን ገደለው፡፡ ቃኤል ሆይወንድምህን ስለምን ገደልኽው? አንተስ ይሁዳ ጌታህን ስለምን ሸጥኸው? ልብህ በአመፃ ተሞልቶ ሳለ በአፍህ ‹‹መምህር ሆይ ቸር ዋልህን?›› ብለኸዋልና፡፡

ይቀጥላል

(ቅዱስ ኤፍሬም ድርሳን በእንተ ጾም ወጸሎት ወንስሓ ➛ በድርሳነ ሠለስቱ ሊቃውንት መጽሐፍ ገጽ 189-199 በመምህር ቃለጽድቅ ሕግነህ የተተረጎመ)



የቅዱስ ኤፍሬም ድርሳን ስለ ጾም ስለ ጸሎትና ንስሓ


ቅዱስ ኤፍሬም ስለ ጾም ስለ ጸሎትና ስለ ንስሓ የተናገረው ድርሳን ይህ ነው።

ቅዱስ ኤፍሬም መልካሙን ክፉ ክፉውን መልካም ለሚሉ ወዮላቸው አለ፡፡ ጾምን የሚንቁ መጾም መልካም አይደለም ለሚሉ ወዮላቸው፡፡ ርስት ትሆነው ዘንድ አዳም በጾምና በጸሎት ወደ ገነት ገብቷልና፡፡ ዳግመኛም ሙሴ በጾምና በጸሎት ከእግዚአብሔር ጋር ይነጋገር ዘንድ ባለሟልነትን ተቀበለ፡፡

ዳግመኛም ኤልያስም በጾምና በጸሎት ወደ ሰማይ ዐረገ፤ ከሞትም ዳነ፡፡ በጾምና በጸሎት የነቢዩ የዳዊት ኃጢአት ይቅር ተባለለት፡፡ ከጻድቃን ጋርም ተቆጠረ፡፡ የነነዌ ሰዎች በጾምና በጸሎት ከጥፋት ዳኑ፡፡ ለሕይወትም የተገቡ ሆኑ። በጾምና በጸሎት ዳንኤል ነቢይ ከተራቡ አናብስት አፍ ዳነ፡፡ ስለ ክርስቶስም ትንቢት ተናገረ፡፡

በጾም በጸሎት ኤርምያስ በሚገባ ስለ ክርስቶስ ስቅለት ትንቢት ተናገረ፡፡ በጾም በጸሎት ነቢዩ ሕዝቅኤል እግዚአብሔር በጌትነቱ ሥልጣን ሁኖ በሠረገላ ተመለከተ፡፡ የጥምቀትን በር ይገልጥ ዘንድ በጾምና በጸሎት ለዮሐንስ ተሰጠው፡፡ በትሕትናው ብዛትም ከሴቶች ከተወለዱት ሁሉ ከፍ ያለ ሆነ፡፡ በጾምና በጸሎት እግዚአብሔር የንጉሡን የሕዝቅያስን ልመና ሰማ፡፡ በዕድሜው ላይም ዓሥራ ዐምስት ዓመት ጨመረለት፡፡

በጾምና በጸሎት እግዚአብሔር ምናሴን ከጋለው የብረት ምስል አዳነው፡፡ ከችግሩም ታደገው:: ያዕቆብ በፍኖተ ሎዛ ተኛ፡፡ በጾምም እስከ ሰማይ የሚደርስ መሰላልን ዐየ፡፡ ጌታችን ዐርባ ቀን ጹሞ ሰይጣንን አሳፈረው፡፡ ሰይጣንም ከፊቱ ሸሸ፡፡ የክርስቶስ ደቀመዛሙርትም በጾም ከትንሣኤ በኋላ አምላካቸውን ክርስቶስን ለማየት በቁ፡፡

ይቀጥላል....

(ቅዱስ ኤፍሬም ድርሳን በእንተ ጾም ወጸሎት ወንስሓ ➛ በድርሳነ ሠለስቱ ሊቃውንት መጽሐፍ ገጽ 189-199 በመምህር ቃለጽድቅ ሕግነህ የተተረጎመ)


ሰናይ ዜና

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ትክክለኛ ውሳኔ

"አገልጋዮች በቅዳሴና ለሌሎች መንፈሳዊ አገልግሎት ሰዓት ሞባይል ስልክ ይዘው ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዳይገቡ" ተከለከለ።

አገልጋዮች በቅዳሴና ለሌሎች መንፈሳዊ አገልግሎት ሰዓት ሞባይል ስልክ ይዘው ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዳይገቡ መከልከሉን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አስታወቀ።

ሀገረ ስብከቱ የዐቢይ ጾምን አስመልክቶ አገልግሎቱ እንዴት መከናወን እንዳለበት ከሁሉም ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ጸሐፊዎችና ሰባክያነ ወንጌል እንዲሁም ቄሰ ገበዞች ጋር ባደረገው ውይይትና ስምምነት መነሻነት የተለያዩ መመሪያዎች መተላለፋቸው ተገልጿል።

ከመመሪያዎች አንዱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚከናወኑ የጸሎተ ቅዳሴና ሌሎች መንፈሳዊ አገልግሎቶች የእጅ ሞባይል ስልክ ይዞ መግባት በጥብቅ የተከለከተለ መሆኑን ለሁሉም ገዳማትና አድባራት በተላከው የመመሪያ ደብዳቤ ለማወቅ ተችሏል።

በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን እምነትና ሥርዓት መሠረት ቅዳሴ፦
➛ የሁሉም ጸሎታት ማጠናቀቂያ፣
➛ ቀራንዮ ላይ ምንገኝበት፣
➛ የበጉ ሠርግ ላይ የምንታደምበት፣
➛ የጌታችንን የአምላካችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን በአንድነት ለኃጢአት ሥርየት፣ ለነፍስ ሕይወት፣ ለሃይማኖት ጽንዐትና ለመንግሥተ ሰማያት መውረሻ ይሆነን ዘንድ የምንቀበልበት ታላቅ የጸሎት ሰዓት ነው።

በመሆኑም አላስፈላጊ የእጅ ስልክ አጠቃቀም ጎልጎታን ከሚያስረሱ፣ በረከትን ከሚያሳጡና ጸጋን ከሚያስወስዱ ድርጊቶች መካከል አንዱ በመሆኑ እንደተከለከለም ተገልጿል።

ይህንን መመሪያም የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችና ሰበካ ጉባኤያት ጥብቅ ክትትል በማድረግ እንዲያስፈጽሙ መታዘዛቸውን በተጻፈ ደብዳቤ ለማወቅ ተችሏል።

(አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሚዲያ )

20 ta oxirgi post ko‘rsatilgan.