Ethiopia Insider


Гео и язык канала: Эфиопия, Амхарский
Категория: Новости и СМИ


Ethiopia Insider is a digital media that provides news, updates, analysis and features.

Связанные каналы  |  Похожие каналы

Гео и язык канала
Эфиопия, Амхарский
Категория
Новости и СМИ
Статистика
Фильтр публикаций


በጋምቤላ ክልል በተከሰተ የአተት ወረርሽኝ፤ ዘጠኝ ሰዎች ሲሞቱ 136 ሰዎች በበሽታው ተይዘዋል

በጋምቤላ ክልል ከባለፈው ሳምንት ጀምሮ በተከሰተ የአጣዳፊ ተቅማጥ እና ትውከት (አተት) ወረርሽኝ የዘጠኝ ሰዎች ህይወት ማለፉን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ።

በክልሉ በአራት ወረዳዎች ላይ የተከሰተው ወረርሽኝ፤ መነሻው በአጎራባች ከሚገኙት የደቡብ ሱዳን አካባቢዎች መሆኑንም የጤና ቢሮው ገልጿል።

የክልሉ ጤና ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ የሆኑት አቶ ወንድማገኝ በላይነህ፤ ወረርሽኙ ለመጀመሪያ ጊዜ የታየው ከአንድ ሳምንት ገደማ በፊት በአኮቦ ወረዳ መሆኑን ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።

በአተት ወረሽኝ ለመጀመሪያ ጊዜ መያዛቸው በምርመራ የተረጋገጠው በዘጠኝ ሰዎች ላይ ቢሆንም፤ ከአንድ ሳምንት በኋላ በበሽታው የተያዙ ሰዎች ቁጥር 136 መድረሱን ኃላፊው አስረድተዋል። 

በወረርሽኙ የተጠቁ ሰዎች በአጣዳፊ ተቅማጥ እና ትውከት የሚያጋጥማቸው በመሆኑ በአተት መጠቃታቸው ይገልጽ እንጂ፤ የበሽታው ምልክቶች የዓለም ጤና ድርጅት (WHO) ትንታኔ በኮሌራ መያዛቸውን የሚያመለክት መሆኑን አቶ ወንድማገኝ አብራርተዋል።

የክልሉ ጤና ቢሮ ወረርሽኙ ኮሌራ መሆን አለመሆኑን ለማረጋገጥ ናሙና ወደ አዲስ አበባ አበባ መላኩንም አክለዋል።   
“እኛ ከዚህ ወደ ኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ናሙና ልከናል። ትክክለኛ ኮሌራ ነው ብሎ ማረጋገጫ አላከልንም” ሲሉ አቶ ወንድማገኝ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።

ኮሌራ አጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት በማስከትል፣ በሰውነት ውስጥ የሚገኝን ፈሳሽ አሟጥጦ በማስወጣት፣  አቅምን በማዳክም፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለሞት የሚዳርግ በሽታ ነው።  

🔴 ለዝርዘሩ ▶️ https://ethiopiainsider.com/2025/15099/

@EthiopiaInsiderNews


ፓርላማው በመጪው ማክሰኞ በሚያካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ፤ የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽንን የስራ ዘመን ያራዝማል ተብሎ ይጠበቃል

የሶስት አመት የስራ ዘመኑን እያገባደደ የሚገኘው የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን፤ አጠቃላይ የስራ አፈጻጸም ሪፖርቱን በመጪው ማክሰኞ በሚካሄድ አስቸኳይ የፓርላማ ስብሰባ ላይ ሊያቀርብ ነው።

በዚሁ ስብሰባ ላይ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ “የስራ ዘመን ይራዘማል” ተብሎ እንደሚጠበቅ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።

በታህሳስ 2014 ዓ.ም የጸደቀው የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅ፤ የኮሚሽኑ የስራ ዘመን ሶስት ዓመት እንደሆነ ይደነግጋል።

የኮሚሽኑ የስራ ዘመን የሚቆጠረው፤ በአዋጁ መሰረት የሚመረጡ ኮሚሽነሮች በፓርላማ ከተሾሙበት ጊዜ ጀምሮ እንደሆነ በድንጋጌው ላይ ሰፍሯል።

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ በዕጩነት የቀረቡ 11 ኮሚሽነሮችን ሹመት ያጸደቀው የካቲት 14፤ 2014 ዓ.ም. ነው።

ፓርላማው ለአንድ ወር እረፍት የተበተኑ አባላቱን ለመጪው ማክሰኞ አስቸኳይ ስብሰባ የጠራው፤ የኮሚሽኑ የስራ ዘመን ድፍን ሶስት ዓመት ከሚሞላበት ዕለት ሁለት ቀናት አስቀድሞ ነው።

የተወካዮች ምክር ቤት ባለፈው ረቡዕ ለአባላቱ ባሰራጨው የስብሰባ ጥሪ፤ ለኮሚሽኑ ጥያቄ ማቅረብ የሚፈልጉ አባላት እስከ ዛሬ ቅዳሜ የካቲት 8፤ 2017 ድረስ እንዲመዘገቡ አሳስቦ ነበር።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15089/

@EthiopiaInsiderNews


ከመተሐራ ከተማ አቅራቢያ በሬክተር ስኬል 6.0 የተለካ የመሬት መንቀጥቀጥ ተከሰተ

ከመተሐራ ከተማ ስድስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ አካባቢ ላይ በሬክተር ስኬል 6.0 የደረሰ የመሬት መንቀጥቀጥ መከሰቱን የአሜሪካ የጂኦሎጂካል ሰርቬይ መስሪያ ቤት አስታወቀ። ከምሽቱ 5:28 ደቂቃ ላይ የደረሰው ርዕደ መሬት፤ ባለፈው አንድ ወር ውስጥ ከተመዘገቡት ሁሉ በመጠን ከፍተኛው ነው።

የዛሬው የመሬት መንቀጥቀጥ ያስከተለው ንዝረት “በጣም ጠንካራ” ሆኖ የተሰማው በመተሐራ ከተማ ይሁን እንጂ መዲናይቱን አዲስ አበባን ጨምሮ በርካታ ከተሞችን ማዳረሱን የአሜሪካው የምርምር ተቋም ገልጿል። የርዕደ መሬቱ ንዝረት በአዋሽ ከተማ “መጠነኛ” እንደነበር ያመለከተው ተቋም፤ በአዳማ፣ ሞጆ፣ ቢሾፍቱ እና ደብረ ብርሃን ከተሞችም በተመሳሳይ መጠን መከሰቱን ጠቁሟል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

@EthiopiaInsiderNews


የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ህወሓትን ለሶስት ወራት ከማንኛውም የፖለቲካዊ እንቅስቃሴ አገደ 

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፤ ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ለሶስት ወራት “በምንም አይነት” ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ እንዳይሳተፍ አገደ። በዚህ ጊዜ ውስጥ ህወሓት ጠቅላላ ጉባኤ ለማካሄድ የሚያስችል “የእርምት እርምጃ” ካልወሰደ፤ የፓርቲው ምዘገባ በቀጥታ እንደሚሰረዝ ቦርዱ አስታውቋል።

ብሔራዊው ምርጫ ቦርድ ይህን ያስታወቀው፤ ህወሓትን በተመለከተ ዛሬ ሐሙስ የካቲት 6፤ 2017 ባወጣው መግለጫ ነው። ቦርዱ ለህወሓት ህጋዊ ሰውነት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት “በልዩ ሁኔታ” መስጠቱን የገለጸው፤ በነሐሴ 2016 ዓ.ም. መጀመሪያ ላይ ነበር። 

ይህ እርምጃ በጥር 2013 ዓ.ም. በምርጫ ቦርድ አማካኝነት ከፓርቲነት የተሰረዘው ህወሓትን፤ ወደ “ህጋዊ ሰውነት” የመለሰ እንደሆነ በወቅቱ ተገልጾ ነበር። ቦርዱ ህወሓትን ከፓርቲነት ሰርዞ የነበረው፤ “ኃይልን መሠረት ባደረገ የአመጻ ተግባር ላይ መሳተፉን” እንዳረጋገጠ በመጥቀስ ነበር። 

ለህወሓት ህጋዊ ሰውነት ማጣት በምክንያትነት ተጠቅሶ የነበረው የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት፤ በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ በተካሄደ የግጭት ማቆም ስምምነት በጥቅምት 2015 ዓ.ም. መቋጨቱ ይታወሳል።

ስምምነቱን ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር የተፈራረመው ህወሓት፤ ህጋዊ ሰውነቱ እንዲመለስ ለቦርዱ ያቀረበው ጥያቄ “በህግ የተደገፈ አይደለም” በሚል ውድቅ ተደርጎ ነበር። 

🔴 ለዝርዝሩ:- https://ethiopiainsider.com/2025/15059/

@EthiopiaInsiderNews


ኢትዮ ቴሌኮም በግማሽ አመት ብቻ 32.8 ቢሊዮን ብር ያልተጣራ ትርፍ ማስመዘገቡን ገለጸ

ኢትዮ ቴሌኮም ባለፈው ግማሽ ዓመት 61.9 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ ማግኘቱን አስታወቀ። በዚሁ ጊዜ ውስጥ 32.8 ቢሊዮን ብር ያልተጣራ ትርፍ ማስመዘገቡን የገለጸው ተቋሙ፤ የደንበኞቹን ቁጥር 80.5 ሚሊዮን ማድረስ መቻሉንም ይፋ አድርጓል።

ይህ የተገለጸው የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ የሆኑት ፍሬሕይወት ታምሩ፤ የተቋማቸውን የግማሽ አመት አፈጻጸም ዛሬ ረቡዕ የካቲት 5፣ 2017 በአዲስ አበባው ስካይ ላይት ሆቴል ባቀረቡበት ወቅት ነው። ኢትዮ ቴሌኮም በ2017 በጀት ዓመት ለማግኘት ያቀደው አጠቃላይ ገቢ 163.7 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ባለፈው መስከረም አስታውቆ ነበር።

መንግስታዊው የቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢ ኩባንያ በመንፈቅ ዓመቱ ያገኘው ገቢ፤ ከእቅዱ 90.7 በመቶ ያሳካ መሆኑን አመልክቷል። ኩባንያው በዚሁ ወቅት ያስገባው ገቢ፤ በ2016 ዓ.ም. ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በ19 ቢሊዮን ብር ጨምሯል።

ኢትዮ ቴሌኮም ለገቢው መጨመር በምክንያትነት ከጠቀሳቸው ውስጥ፤ የሞባይል ስልክ ደንበኞቹ የዳታ እና የድምጽ አጠቃቀም ማደግ ይገኝበታል። የኩባንያው ደንበኞች የዳታ አጠቃቀም፤ ከባለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ ሲነጻጸር በ48.8 በመቶ እድገት ያስመዘገበ መሆኑ በዛሬው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተጠቅሷል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)


ከአማራ ክልል ተማሪዎች 60 በመቶ የሚጠጉት “ከትምህርት ገበታ ውጭ” መሆናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድሩ አስታወቁ

በአማራ ክልል ከሚገኙ ተማሪዎች ውስጥ 59.8 በመቶ የሚሆኑት፤ በዘንድሮው የትምህርት ዘመን “ከትምህርት ገበታ ውጭ” መሆናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ተናገሩ።

በክልሉ ከሚገኙ ትምህርት ቤቶች መካከል 32 በመቶ የሚሆኑት ከመማር ማስተማር ተልዕኮዋቸው “መስተጓጎላቸውንም” ርዕሰ መስተዳድሩ አስታውቀዋል።

አቶ አረጋ ይህንን ያሉት፤ ትላንት ማክሰኞ የካቲት 4፤ 2017 ዓ.ም በተጀመረው እና ዛሬም በቀጠለው የአማራ ክልል ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ ላይ ባቀረቡት የግማሽ ዓመት የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ነው። አቶ አረጋ በዚሁ ሪፖርታቸው ካነሷቸው ጉዳይ መካከል በክልሉ ያለውን የትምህርት ሁኔታ የተመለከተው ይገኝበታል።

በአማራ ክልል በአሁኑ ወቅት “በተጨባጭ በመማር ማስተማር ሂደት እየተሳተፉ” የሚገኙ ተማሪዎች ብዛት 2.78 ሚሊዮን እንደሆኑ ርዕሰ መስተዳድሩ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት ላይ ጠቅሰዋል።

ይህ አሃዝ በክልሉ በትምህርት ገበታቸው ላይ ሊገኙ የገባቸው ከነበሩ ተማሪዎች ውስጥ 40.2 በመቶ የሚሆኑት ተማሪዎች ብቻ የሚሸፍን እንደሆነም አቶ አረጋ አስረድተዋል።

“ቀሪ 59.8 በመቶ የሚሆነው ተማሪ ከትምህርት ገበታ ውጭ መሆኑን ለተከበረው ምክር ቤት ማስረዳት ያስፈልጋል” የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በትላንቱ ጉባኤ ውሎ ላይ አጽንኦት ሰጥተዋል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15040/

@EthiopiaInsiderNews


አሜሪካ ለሶማሌላንድ ዕውቅና በመስጠት “ቀዳሚዋ ሀገር ትሆናለች” የሚል ተስፋ እንዳላቸው የራስ ገዟ መሪ ተናገሩ

አሜሪካ ለሶማሌላንድ ዕውቅና የምትሰጥ “የመጀመሪያዋ ሀገር ትሆናለች” የሚል ተስፋ እንዳላቸው የራስ ገዝ አስተዳደሯ ፕሬዝዳንት አብዲራህማን ሞሐመድ አብዲላሒ ተናገሩ።

አዲሱ የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር፤ ሶማሊያ “ግዛቴ ናት” ለምትላት ሶማሌላንድ ዕውቅና ከሰጠ ሌሎች ሀገራት ይከተላሉ የሚል እምነት እንዳላቸውም ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።

አዲሱ የሶማሌላንድ ፕሬዝዳንት ይህን ያሉት፤ ዛሬ ማክሰኞ የካቲት 4፤ 2017 በዱባይ በተካሄደ የዓለም የመንግስታት ጉባኤ ውይይት ላይ ነው።

አብዲራህማን ኢሮ በሚል ቅጽል ስማቸው የሚታወቁት አዲሱ ፕሬዝዳንት የዛሬ ሶስት ወር ገደማ ወደ ስልጣን ከመምጣታቸው አስቀድሞ፤ ለሶማሌላንድ ዕውቅና በመስጠት ቀዳሚዋ ሀገር ትሆናለች የሚል ተስፋ የተጣለው በኢትዮጵያ ላይ ነበር።

ባለፈው ዓመት ታህሳስ ወር ላይ ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ጋር “የአጋርነት እና የትብብር የመግባቢያ ስምምነት” የተፈራረሙት የቀድሞው የሶማሌላንድ ፕሬዝዳንት ሙሴ ቢሒ አብዲ፤ ውሉ ተግባራዊ ሲሆን “ኢትዮጵያ ለሶማሌላንድ ዕውቅና እንደምትሰጥ” በይፋ መናገራቸው ለዚህ ተስፋ በማስረጃነት ሲጠቀስ ቆይቷል።

የሶማሌላንድ ልሂቃን ከፍተኛ ተስፋ የሰነቁበት የኢትዮጵያ የመግባቢያ ስምምነት ወደ ተግባር ሳይቀየር ቢዘገየም፤ የራስ ገዝ አስተዳደሯ አጥብቃ የምትሻውን ዕውቅና ከአሜሪካ ልታገኝ እንደምትችል ለትራምፕ አስተዳደር ቅርበት ያለው ተቋም ከወር በፊት ጥቆማ ሰጥቶ ነበር።

አዲሱ የሶማሌላንድ ፕሬዝዳንት በዛሬው የዱባይ ጉባኤ ላይ ይህንኑ የሚያጠናክር አስተያየት አንጸባርቀዋል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15030/


በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ግማሽ ቢሊዮን ብር የሚጠጋ የአፈር ማዳበሪያ ዕዳ አለመሰብሰቡን ርዕሰ መስተዳድሩ ተናገሩ

በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኙ ስድስት ዞኖች፤ 469.9 ሚሊዮን ብር ከአርሶ አደሮች ያልተሰበሰበ “ቀሪ የማዳበሪያ ዕዳ” እንዳለባቸው የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር ነጋሽ ዋጌሾ  ተናገሩ።

ዞኖቹ ዕዳቸውን ወቅቱን ጠብቀው ባለመክፈላቸው፤ ለልማት ሊውል ይገባ የነበረ “ሰፊ ሀብት” በወለድ መልክ ከበጀታቸው ተቀንሶ ለባንክ እየተላለፈ እንደሚገኝም ርዕሰ መስተዳድሩ ገልጸዋል። 

ርዕሰ መስተዳድሩ ይህን የገለጹት፤ ዛሬ ማክሰኞ የካቲት 4፤ 2017 በተርጫ ከተማ በተጀመረው የክልሉ ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ ላይ ባቀረቡት የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ነው።

ዶ/ር ነጋሽ በዚሁ ሪፖርታቸው፤ ክልሉ ያለበትን የአፈር ማዳበሪያ ዕዳ እና የወለድ ክምችት “አሳሳቢ ጉዳይ” እንደሆነ ለምክር ቤቱ አባላት አስገንዝበዋል። 

የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ከተመሰረተበት ከ2014 ዓ.ም. ጀምሮ ለአርሶ አደሮች የተሰራጨውን የአፈር ማዳበሪያ መጠን በዝርዝር ያቀረቡት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ በሶስት የምርት ዘመኖች ብቻ በክልሉ በአጠቃላይ ያልተከፈለ የማዳበሪያ ዕዳ እና ወለድ ግማሽ ቢሊዮን ብር እንደሚጠጋ አስታውቀዋል።

ዕዳው እንዲከማች ያደረጉ የክልሉ ዞኖች፤ ቤንች ሸኮ፣ ምዕራብ ኦሞ፣ ዳውሮ፣ ከፋ፣ ሸካ እና ኮንታ መሆናቸውንም ይፋ አድርገዋል።

ካልተከፈለው ቀሪ የአፈር ማዳበሪያ ዕዳ ውስጥ 203 ሚሊዮን ብር ያህሉን ከፍተኛ መጠን በመያዝ፤ ቤንች ሸኮ ዞን ቀዳሚው ነው።

🔴 ለዝርዝሩ ▶️ https://ethiopiainsider.com/2025/15027/

@EthiopiaInsiderNews


በአፋር ክልል ባለ ብሔራዊ ፓርክ ባለፈው ቅዳሜ የተቀሰቀሰ ሰደድ እሳት እስካሁን በቁጥጥር ስር አለመዋሉ ተገለጸ

በአፋር እና በኦሮሚያ ክልሎች መካከል በሚገኘው ሃላይዳጌ አሰቦት ብሔራዊ ፓርክ ከትላንት በስቲያ የተቀሰቀሰው ሰደድ እሳት እስከ ዛሬ ሰኞ እኩለ ቀን ድረስ በቁጥጥር ስር አለመዋሉን የፓርኩ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አህመድ እድሪስ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናገሩ። በሰደድ እሳቱ 200 ሄክታር የሚገመት የፓርኩ ክፍል መቃጠሉን ኃላፊው ገልጸዋል።

ከ1965 ዓ.ም ጀምሮ የዱር እንስሳት ጥብቅ ቦታ ሆኖ የቆየው ሃላይዳጌ አሰቦት ብሔራዊ ፓርክ፤ 1099 ገደማ ስኩዌር ኪሎ ሜትር ስፋት ያለው ነው።

ከ2006 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ብሔራዊ ፓርክ ደረጃ ያደገው ጥብቅ ቦታው፤ የ325 የእጽዋት ዝርያ፣ የ244 የአእዋፍ ዝርያ እና ከ42 በላይ አጥቢ እንስሳት መኖሪያ ነው።

በኢትዮጵያ እና በኬንያ ብቻ የሚገኝ የሜዳ አህያ ዝርያ እንዲሁም ሳላ የተሰኘው አጥቢ እንስሳ በብዛት በሚገኝበት በዚህ ፓርክ፤ የእሳት አደጋ የተከሰተው ከትላንት በስቲያ ቅዳሜ የካቲት 1፤ 2017 ከቀኑ ስምንት ሰዓት በኋላ ባለው ጊዜው ውስጥ ነው።

እሳቱ በከፍተኛ ንፋስ የታገዘ በርካታ ቦታ ማዳረሱን ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” የተናገሩት የፓርኩ ጽህፈት ቤት ኃላፊ፤ እሳቱን ለማጥፋት የአካባቢው ነዋሪዎች፣ የመከላከያ ሰራዊት አባላት እና የአካባቢው አስተዳደር ሰራተኞች ርብርብ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15018/

@EthiopiaInsiderNews


ባለፉት ስድስት ወራት የተከሰተው የወባ ወረርሽኝ፤ አምና በተመሳሳይ ጊዜ ከነበረው “በሁለት እጥፍ” ጨምሯል ተባለ

የወባ ወረርሽኝ ስርጭት፤ ተፈናቃይ ዜጎች በሰፈሩባቸው አካባቢዎች እንዲሁም የመስኖ ስራ እና የስንዴ ልማት ባሉባቸው ቦታዎች ላይ “በእጅጉ መጨመሩን” የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ደረጀ ድጉማ ገለጹ።

በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ባለፈው ስድስት ወራት የተከሰተው የወባ ወረርሽኝ፤ ከአምናው ተመሳሳይ ጊዜ ጋር ሲነጻጸር “በሁለት እጥፍ” መጨመሩም ተነግሯል።

ይህ የተገለጸው ዛሬ ረቡዕ ጥር 28፤ 2017 በተካሄደ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቋሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ነው። የፓርላማው የጤና፤ ማህበራዊ ልማት፣ ባህል እና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የዛሬውን መድረክ ያዘጋጀው፤ የጤና ሚኒስቴርን የ2017 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የስራ አፈጻጸም ለማዳመጥ ቢሆንም በስብሰባው የቀረበው ግን የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ሪፖርት ብቻ ነው።

የኢንስቲትዩቱ የመንፈቅ ዓመት ሪፖርት በዋነኛነት ያተኮረው፤ በኢትዮጵያ ከ2016 ዓ.ም አጋማሽ ጀምሮ በወረርሽኝ ደረጃ በተከሰተው በወባ በሽታ ስርጭት ላይ ነው።

በተቋሙ ሪፖርት መሰረት፤ ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ 658 ሰዎች በወባ ወረርሽኝ ህይወታቸው አልፏል። በዚሁ ጊዜ ውስጥ በወባ በሽታ የተጠቁ ሰዎች ብዛት ሰባት ሚሊዮን ገደማ እንደሆነም በሪፖርቱ ላይ ሰፍሯል።

በመንፈቅ ዓመቱ ከፍተኛው የወባ ህመምተኞች የተመዘገቡበት ክልል ኦሮሚያ ነው። ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ በኦሮሚያ ክልል በወረርሽኙ የተጠቁ ሰዎች ብዛት 3.2 ሚሊዮን መድረሱን የኢንስቲትዩቱ ሪፖርት አመልክቷል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15011/

@EthiopiaInsiderNews


በታገዱ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ላይ “ተጨማሪ ምርመራ” እየተከናወነ መሆኑን ተቆጣጣሪ ባለስልጣኑ አስታወቀ

የእግድ እርምጃ በተወሰደባቸው የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ላይ ተጨማሪ “የማጣራት” እና “የምርመራ” ስራ እያከናወነ መሆኑን የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን አስታወቀ።

ባለስልጣኑ በዚህ ምርምራ ግኝቱ ላይ ተመስርቶ፤ እግዱ “በመጨረሻ ማስጠንቀቂያ እንዲነሳ” ሊያደርግ አሊያም ድርጅቶቹ “እንዲፈርሱ” ወይም “እንዲሰረዙ” ለመስሪያ ቤቱ ቦርድ የውሳኔ ሃሳብ ሊያቀርብ እንደሚችልም ገልጿል።

የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በተመዘገቡበት ዓላማ መሰረት ስራቸውን ማከናወናቸውን የመከታተል እና የመቆጣጠር ኃላፊነት በአዋጅ የተሰጠው ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ፤ ባለፈው መንፈቅ ዓመት ብቻ ሰባት ድርጅቶች ላይ የእግድ ውሳኔ አስተላልፏል። ባለስልጣኑ በዚሁ ጊዜ ውስጥ ለ10 ድርጅቶች ማስጠንቀቂያ መስጠቱም፤ ዛሬ ረቡዕ በፓርላማ በተካሄደ የቋሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ይፋ ተደርጓል።

በቋሚ ኮሚቴው ስብሰባ የጥያቄ እና ምላሽ ወቅት የመናገር ዕድል የተሰጣቸው የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳምሶን ቢራቱ፤ መስሪያ ቤታቸው በሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ላይ የሚያደርገው “ክትትል፣ ቁጥጥር እና ምርመራ” “ተጠናክሮ ቀጥሏል” ብለዋል።

“የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ለተቋቋሙለት ዓላማ፣ በዚያ መስመር ላይ እንዲሰሩ፤ ህግን እና ህግን ብቻ አክብረው እንዲሰሩ ያላሰለሰ ጥረት እያደረግን ነው” ሲሉም አቶ ሳምሶን ለቋሚ ኮሚቴው አባላት ተናግረዋል። እርሳቸው የሚመሩት መስሪያ ቤት፤ “ከተቋቋሙበት ዓላማ ውጭ ተንቀሳቅሰዋል” ያላቸውን 4 የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች ባለፈው ታህሳስ ወር አጋማሽ ማገዱ ይታወሳል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15007/


ቪዲዮ፦ ከቀናት በፊት አዳዲስ አመራሮችን የመረጠው የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ)፤ በኢትዮጵያ እየተካሄደ ነው ያለውን “የእርስ በእርስ ጦርነት” ዘላቂ መፍትሔ እንዲያገኝ የበኩሉን አስተዋጽኦ ለማድረግ መወሰኑን ገለጸ። ፓርቲው “የተበላሸ” ሲል የጠራውን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ስርዓት ለማረምም “ከምንጊዜውም በላይ እታገላለሁ” ብሏል።

መኢአድ ይህን ያለው ባለፈው ሳምንት መጨረሻ በአዲስ አበባ ያካሄደውን 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በተመለከተ በዛሬው ዕለት በሰጠው መግለጫ ነው። ፓርቲው በዚሁ ጉባኤው፤ የድርጅቱን ፕሬዝዳንት እና ምክትል ፕሬዝዳንት ጨምሮ የስራ አስፈጻሚ፣ የማዕከላዊ ምክር ቤት እንዲሁም የኦዲትና ኢንስፔክሽን ኮሚቴ አባላትን መርጧል።

ተመራጮቹ ፓርቲውን “ለቀጣዩ ሶስት ዓመታት ሊመሩ የሚችሉ” እና ድርጅቱን “ወደተሻለ ደረጃ ያደርሳሉ” በሚል በጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፊዎች የታመነባቸው እንደሆኑም መኢአድ አስታውቋል። ጠቅላላ ጉባኤው “አዳዲስ እና ወጣት የሴት አመራሮችን ወደፊት እንዲመጡ አድርጓል” ሲልም ፓርቲው በመግለጫው አክሏል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

🔴 መኢአድ በዛሬው ዕለት የሰጠውን መግለጫ ይህን ሊንክ ተጭነው ይመልከቱ 👉 https://youtu.be/6mj2ndmiGOA

@EthiopiaInsiderNews


ከዩ.ኤስ.ኤይድ ገንዘብ የሚያገኙ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ንብረቶቻቸውን እንዳይሸጡ እና እንዳይስተላልፉ ክልከላ ተጣለባቸው

የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን፤ ከአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት (USAID) የገንዘብ ድጋፍ የሚያገኙ ድርጅቶች ያለ መስሪያ ቤቱ “ግልጽ ፍቃድ”፤ ንብረት የማስተላለፍ፣ የማስወገድ እና የመሸጥ ድርጊቶችን እንዳያከናውኑ ከለከለ። መስሪያ ቤቱ የሰጠውን “ጥብቅ ማሳሰቢያ” በመተላለፍ በሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች ላይ “ተገቢውን እርምጃ” እንደሚወስድም አስጠንቅቋል።

ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ማሳሰቢያውን እና ማስጠንቀቂያውን ያስተላለፈው፤ ዛሬ ማክሰኞ ጥር 27፤ 2017 ባወጣው “አስቸኳይ መግለጫ” ነው። መስሪያ ቤቱ መግለጫውን ያወጣው፤ በአዋጅ በተሰጠው ስልጣን መሰረት ስራቸውን ለሚከታተላቸው እና ለሚቆጣጠራቸው የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በሙሉ ነው።

ተቆጣጣሪ መስሪያ ቤቱ በዚሁ መግለጫው፤ ከሰሞኑ በአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት በኩል “የእርዳታ ማቆም ውሳኔ” መተላለፉን መረዳት እንደቻለ ጠቅሷል። “ጉዳዩን በቅርበት እየተከታተለ” እንደሚገኝ የገለጸው ባለስልጣኑ፤ “ዝርዝር ሁኔታዎችን መሰረት በማድረግ” በቀጣይ ባሉት ጊዜያት ለሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች “አስፈላጊውን ድጋፍ እና ክትትል” እንደሚያከናውን አስታውቋል።

እስከዚያው ጊዜ ድረስ ግን ከUSAID የገንዘብ ድጋፍ የሚያገኙ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች፤ ያላቸውን ንብረት “ማስተላለፍ”፣ “ማስወገድ” እና “መሸጥ” እንደማይችሉ ባለስልጣኑ ገልጿል። የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶቹ ከመደበኛ ወይም ፕሮጀክት ስራዎቻቸው ጋር ተያያዥ ከሆኑ ጉዳዮች ውጭ፤ ሃብት እና ገንዘባቸውን “በማናቸውም መልኩ” ለሶስተኛ ወገን ማስተላለፍ የተከለከለ መሆኑንም መስሪያ ቤቱ አስታውቋል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

@EthiopiaInsiderNews


የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን አዋጅ እንዲያሻሽል፤ የፓርላማ ቋሚ ኮሚቴ ለተቆጣጣሪ መስሪያ ቤት አቅጣጫ ሰጠ

የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን የቦርድ ውክልናን ጨምሮ “በርካታ ክፍተቶች አሉበት” ያለውን የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች አዋጅ እንዲሻሻል ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገለጸ።

ባለስልጣኑ “አላሰራ ያሉ አዋጆችን እንዲሻሻሉ ለማድረግ” ለሚያከናወናቸው ስራዎች፤ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት “ተገቢውን ድጋፍ” እንደሚያደርግ ተገልጿል።

ይህ የተገለጸው የፓርላማው የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፤ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣንን የስራ እንቅስቃሴ ትላንት ሰኞ ጥር 26፤ 2017 ተዘዋውሮ በተመለከተበት ወቅት ነው።

በመስክ ምልከታው የተገኙ አምስት የቋሚ ኮሚቴው አባላት፤ የባለስልጣን መስሪያ ቤቱን የስራ ኃላፊዎች፣ ሰራተኞችን እና ተገልጋዮችን ማነጋገራቸውን ከተወካዮች ምክር ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

በዚሁ ጊዜ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣንን ያለፉትን የስድስት ወራት የስራ እንቅስቃሴ በተመለከተ፤ የመስሪያ ቤቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳምሶን ቢራቱ ለቋሚ ኮሚቴው አባላት ገለጻ አድርገዋል።

አቶ ሳምሶን በዚሁ ገለጻቸው፤ ባለስልጣኑ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች አዋጅን ለማሻሻል “እየሰራ” እንደሆነ መናገራቸውን የተወካዮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት በማህበራዊ የትስስር ገጹ ባሰራጨው መረጃ ላይ አስፍሯል።

🔴 ለዝርዝሩ ▶️ https://ethiopiainsider.com/2025/14994/

@EthiopiaInsiderNews


መኢአድ ፓርቲውን በፕሬዝዳንት እና በምክትል ፕሬዝዳንትነት የሚመሩ አዲስ አመራሮችን መረጠ 

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ትላንት እሁድ ጥር 25፤ 2017 ባካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ፤ የፓርቲው ተቀዳሚ ፕሬዝዳንት የነበሩትን አቶ አብርሃም ጌጡን ፓርቲውን እንዲመሩ መረጠ። ፓርቲው በዚሁ ጉባኤው፤ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ ማሻሻያ አድርጓል።

በኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነምግባር አዋጅ መሰረት በምርጫ ቦርድ ተመዝግበው ህጋዊነት ያገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ ቢያንስ በሶስት ዓመት አንድ ጊዜ ጠቅላላ ጉባኤ ማካሄድ አለባቸው።

ሀገር አቀፍ ፓርቲ የሆነው መኢአድ፤ በትላንትናው ዕለት ያካሄደው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ለ10ኛ ጊዜ የተካሄደ ነው።

በአዲስ አበባ ቴዎድሮስ አደባባይ አካባቢ በሚገኘው የመኢአድ ዋና ጽህፈት ቤት በተካሄደው በትላንትናው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ 550 ገደማ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል።

በዚሁ ጉባኤ ላይ በተደረገው የአመራር ምርጫ፤ መኢአድን ስድስት ለሚጠጉ ዓመታት ሲመሩ በቆዩት አቶ ማሙሸት አማረ ምትክ አቶ አብርሃም ጌጡ የፓርቲው ፕሬዝዳንት ሆነው ተመርጠዋል።

አቶ አብርሃም በአቶ ማሙሸት የኃላፊነት ዘመን የፓርቲው ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንት ሆነው አገልግለዋል። አዲሱ የፓርቲው ፕሬዝዳንት ይዘው የቆዩትን የተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንትነት ቦታ በጉባኤው ምርጫ የተረከቡት አቶ ሰማኝ አብርሃም ናቸው።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/14987/

@EthiopiaInsiderNews


ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ ያሉ ግጭቶች ጠንሳሾች፤ “ትላንትና ፖለቲካ ሲያንቦራጭቁ የነበሩ ሰዎች ናቸው” አሉ

በኢትዮጵያ በተለያዩ አካባቢዎች ያሉ ግጭቶች “ጠንሳሽ” እና “ጨማቂዎች”፤ “ትላንትና ፖለቲካ ሲያንቦራጭቁ የነበሩ ሰዎች ናቸው” ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ወነጀሉ።

አብይ በሚመሩት ብልጽግና ፓርቲ መደበኛ ጉባኤ መክፈቻ ላይ ዛሬ አርብ ባደረጉት ንግግር፤ ባለፉት ስድስት ዓመታት በኢትዮጵያ ውስጥ “ሰው torture አይደረግም” ሲሉ ተደምጠዋል።

ገዢው ፓርቲ እስከ መጪው እሁድ ጥር 25፤ 2017 የሚቆየውን ሁለተኛ ጠቅላላ ጉባኤ እያካሄደ ያለው፤ በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኘው የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም የመሰብሰቢያ አዳራሽ ነው።

የብልጽግና ፓርቲ ፕሬዝዳንት የሆኑት አብይ፤ ፓርቲው ቃል ከገባቸው ጉዳዮች መካከል “በኢትዮጵያ ቶርቸር ይቁም” የሚለው አንዱ እንደነበር አስታውሰዋል።

ብልጽግና ፓርቲ “ባለፉት ጥቂት ዓመታት” በተጓዘበት “የመጀመሪያ ምዕራፍ” ካሳካቸው ጉዳዮች አንዱ፤ ይኸው እንደሆነም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለጉባኤው ታዳሚያን ተናግረዋል። “ላለፉት ስድስት ዓመታት፤ ብታምኑም ባታምኑም አንድ ሰው ኢትዮጵያ ውስጥ torture አይደረግም። በዚህ እኛ እንኮራለን” ብለዋል አብይ።

አብይ በዚህ ንግግራቸው “ፖለቲካን በቅጡ አልተለማመዱም” ያሏቸውን “አባቶች” ወርፈዋቸዋል። “አባቶቻችን ሀገርኛ ሀሳብ አላፈለቁም። በተዋሱት ሃሳብ ሲጨቃጨቁ፣ ሲጋደሉ የኖሩ ስለሆነ፤ አሁንም ያንን ማስቀጠል ይፈልጋሉ” ብለዋል።

🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/14973/

@EthiopiaInsiderNews


አዲሱን የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ሹመት አስመልክቶ የተቃዋሚ ፓርቲ የፓርላማ አባላት ምን አሉ?

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ሐሙስ ጥር 22፤ 2017 ባካሄደው መደበኛ ስብሰባው፤ ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) አዲስ ዋና ኮሚሽነር ሾሟል። ብሔራዊውን የሰብአዊ መብት ተቋም እንዲመሩ ስለ ተሾሙት አቶ ብርሃኑ አዴሎ፤ የፓርላማ አባላት አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል።

🔴 የአብኑ ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ እና የኢዜማው ዶ/ር አብርሃም በርታ የሰጡትን አስተያየት እና የአፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎን ምላሽ ይህን ሊንክ ተጭነው https://youtu.be/tDX2wcAcfDA?feature=shared ያድምጡ። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)

@EthiopiaInsiderNews


የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራር የነበሩት አቶ ብርሃኑ አዴሎ፤ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንን እንዲመሩ ተሾሙ

በቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የስልጣን ዘመን ለስድስት ዓመት ገደማ የካቤኔ ጉዳዮች ኃላፊ ሆነው የሰሩት አቶ ብርሃኑ አዴሎ፤ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽንን (ኢሰመኮ) እንዲመሩ በፓርላማ ተሾሙ።

አቶ ብርሃኑ የብሔራዊው የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር የሆኑት፤ ተቋሙን ለአምስት ዓመታት የመሩትን ዶ/ር ዳንኤል በቀለን በመተካት ነው። ዶ/ር ዳንኤል ከኃላፊነታቸው የተሰናበቱት፤ የስራ ዘመናቸው ባበቃበት ባለፈው ዓመት ሐምሌ ወር ነበር።

ላለፉት አምስት ወራት ኢሰመኮን የመምራት ኃላፊነት በተጠባባቂነት ተረክበው የቆዩት የእርሳቸው ምክትል የነበሩት ራኬብ መሰለ ናቸው።

ተጠሪነቱ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሆነው ኢሰመኮ፤ ለሰብዓዊ መብቶች መስፋፋት፣ መከበር እና ጥበቃ የመስራት ስልጣን በአዋጅ የተሰጠው ነው።

በ2012 ዓ.ም. የተሻሻለው የኢሰመኮ ማቋቋሚያ አዋጅ፤ ተቋሙን በዋና ኮሚሽነርነት፣ በምክትል ዋና ኮሚሽነርነት እና በዘርፍ ኮሚሽነርነት የሚያገለግሉ ኃላፊዎች በተወካዮች ምክር ቤት እንደሚሾሙ ይደነግጋል። 

ዛሬ ሐሙስ ጥር 22፤ 2017 በተካሄደው የተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ፤ ኮሚቴው የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር እንዲሆኑ አቶ ብርሃኑ አዴሎን በዕጩነት አቅርቧል። ላለፉት አስር አመታት በግል አማካሪነት እና ጠበቃነት እየሰሩ የቆዩት አቶ ብርሃኑ፤ በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን በከፍተኛ የኃላፊነት ቦታ የሰሩ ናቸው። 

🔴 ለዝርዝሩ:- https://ethiopiainsider.com/2025/14962/

@EthiopiaInsiderNews


የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት እና ስርጭት መዘግየት፤ ዘንድሮም በፓርላማ ማነጋገሩን ቀጥሏል

የግብርና ሚኒስቴር ኃላፊዎች የሩብ፣ የመንፈቅ፣ የዘጠኝ ወር አሊያም የዓመት የስራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን ለማቅረብ ወደ ፓርላማ በሚመጡበት ጊዜ ሁልጊዜም ከአንድ ጉዳይ ጋር የተያያዙ በርከት ያሉ ጥያቄዎች ይቀርቡላቸዋል። ጉዳዩ አብዛኛውን የሀገሪቱን ህዝብ ብዛት የሚወክለውን አርሶ አደር በቀጥታ የሚመለከተው የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት እና ስርጭት ነው።

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ትላንት ሰኞ ጥር 19፤ 2017 ባካሄደው ልዩ ስብሰባ ላይ ይህ ጉዳይ ተነስቶ መወያያ ሆኗል። ለልዩ ስብሰባው በቀዳሚነት የተያዘው አጀንዳ፤ “የግብርና ሚኒስቴር የ2017 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ማዳመጥ” የሚል ነበር።

በዚህም መሰረት የግብርና ሚኒስትሩ ዶ/ር ግርማ አመንቴ የመስሪያ ቤታቸውን የመንፈቅ ዓመት የስራ አፈጻጸም፤ ግማሽ ሰዓት ያህል ወስደው በንባብ አሰምተዋል። ሚኒስትሩ በሪፖርታቸው ካነሷቸው አንኳር ጉዳዮች መካከል የአፈር ማዳበሪያን የተመለከተው ይገኝበታል።

የኢትዮጵያ መንግስት ለዘንድሮ በጀት ዓመት ለአፈር ማዳበሪያ ግዢ የሚውል 1.3 ቢሊዮን ዶላር እና 156 ቢሊዮን ብር በጀት መያዙን ዶ/ር ግርማ በሪፖርታቸው ላይ አስታውሰዋል። በተያዘው የ2017 በጀት ዓመት፤ ለመኸር፣ ለበልግ የምርት ወቅቶች እና ለመስኖ ልማት የሚውል 24 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለመግዛት በእቅድ መያዙንም ጠቁመዋል።

የግብርና ሚኒስትሩ ሪፖርት ከተጠናቀቀ በኋላ በተከተለው የጥያቄ እና መልስ ጊዜ የመናገር ዕድል ያገኙ የፓርላማ አባላት የአፈር ማዳበሪያን ጉዳይ በድጋሚ አንስተዋል።

🔴 ዝርዝሩን ለማንበብ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/14946/

@EthiopiaInsiderNews


ኢዜማ ከመጪው ምርጫ ጋር “የተያያዘ በሚመስል መልኩ”፤ “አባላቶቼ እየታሰሩብኝ ነው” አለ

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ ፓርቲ (ኢዜማ) 75 አባላቶቹ በእስር ላይ እንደሚገኙ አስታወቀ። ፓርቲው በአባሎቹ ላይ እስር እና ማዋከብ እየተፈጸመ የሚገኘው፤ ከአንድ ዓመት በኋላ ይካሄዳል ተብሎ ከሚጠበቀው ሀገራዊ ምርጫ ጋር “የተያያዘ በሚመስል መልኩ ነው” ሲል ወንጅሏል። 

ኢዜማ ዛሬ ማክሰኞ ጥር 20፤ 2017 ባወጣው መግለጫ፤ በአባሎቹ ላይ ድርጊቶቹ እየተፈጸሙ ያሉት በአማራ፣ ሀረሪ እና ደቡብ ኢትዮጵያ ክልሎች እንደሆነ ገልጿል። ፓርቲው “ታስረውብኛል” ካላቸው አባላቶቹ ውስጥ አብዛኞቹ የሚገኙት፤ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ ጋሞ ዞን፣ አርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ፣ ዘይሴ ቀበሌ መሆኑን በመግለጫው ላይ ጠቅሷል። 

የዘይሴ ቀበሌ በ2013 ዓ.ም በተካሄደው ሀገር አቀፍ ምርጫ፤ ኢዜማ የተወካዮች ምክር ቤት ያሸነፈበት ነው። የኢዜማ የህግ እና የአባላት ደህንነት መምሪያ ኃላፊ አቶ ስዩም መንገሻ፤ በቀበሌው ባሉ የኢዜማ አባላት ላይ እየተፈጸመ የሚገኘው እስር እና መዋከብ “ከፍተኛ” እንደሆነ ለ“ኢትዮጵያ ኢንሳይደር” ተናግረዋል።

አቶ ስዩም እነዚህ እርምጃዎች በቀበሌው በሚገኙ የጸጥታ አካላት እየተወሰዱ ያሉት፤ ኢዜማ በአካባቢው “ጠንካራ የፖለቲካ መሰረት ስላለው ነው” ባይ ናቸው። “የፖለቲካ መሰረታችን ጠንካራ የሆነባቸው ቦታዎች ላይ አሁንም ጠንካራ ዱላ አለ። ዘይሴ አንዱ ነው” ይላሉ የፓርቲው የመምሪያ ኃላፊ። 

🔴 ለዝርዝሩ ▶️ https://ethiopiainsider.com/2025/14943/

@EthiopiaInsiderNews

Показано 20 последних публикаций.