በመንግስት የሚፈጸሙ የድሮን ጥቃቶች ሰላማዊ ዜጎችን ለህልፈት እየዳረገ ነው”- ኢሕአፓየኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ “የዜጎችን ህይወት የመጠበቅ ሃላፊነት ያለበት መንግሥት ቢሆንም በሚያሰማራቸው የጸጥታ ሃይሎችና የአገር መከላከያ ሠራዊት አባላት ጭምር የዜጎች ህይወት በበርካታ የሀገሪቱ ክፍሎች እንደቅጠል እያረገፈ ይገኛል” ብሏል፡፡
ኢሕአፓ ዛሬ ባወጣው መግለጫ ህገመንግሥቱን የመንግሥት አካላት ራሳቸው ካላከበሩት እንዴት ሊያስከብሩት ይችላሉ “በንጹሀን ዜጎች ላይ የሚደረጉት ግድያዎች ይቁሙ” ሲል አሳስቧል፡፡
እንዲሁም የተለያዩ የመንግስት መገናኛ ብዙሀን ከመዘገብ ቢቆጠቡም በውጪ የመገናኛ ብዙሀን ጭምር ጥቃቱ መፈጸሙን እየገለጹ መሆኑን እና ፓርቲውም አጣርቻለሁ ያለውን በየክልሉ የደረሱትን ጥቃቶች አስታውቋል፡፡
ፓርቲው አጣርቻለው ባለው መሰረት ኦሮሚያ ክልልን ጨምሮ በተለያዩ አካባቢዎች የሚደርሱ ጥቃቶች የሟቾችን ቁጥር እያሻቀበ መሆኑን እና ጥቃት ከተፈጸመባቸው ውስጥም ነፍሰጡሮች፣ የጤና ባለሙያዎች እና በትምህርት ቤት ውስጥ የነበሩ ተማሪዎች እንደሚገኙበት አመላክቷል፡፡
በመሆኑም “ወደፊት ትውልድ እንዲከፍል በብድር በመጣ የጦር መሳሪያ ንጹሀን ዜጎች ላይ የጅምላ ጭፍጨፋ ማካሄድ አግባብነት የለውም”፤ መንግሥት ኃላፊነቱን እየተወጣ ነው ለማለት እንደዚህ ያለውን ሁኔታ በዝምታ ማስቀጠል አይችልም ሲል ኮንኗል፡፡
ኢሕአፓ መንግሥት በተለይ የጦርነት አውድማ በተደረጉት በአማራ፣በኦሮሚያ፣ በቤኒሻንጉል ጉምዝና በደቡብ ክልሎች ዉስጥ የሚደረገውን ህገመንግሥቱን እየጣሱ ያሉትን፣ መንግሥት መር የዜጎች ግድያዎችን በጥብቅ ማውገዙን እና ጦርነቶቹ አሁኑኑ ይቁሙ ሲልም አሳስቧል፡፡
@MeribahTimes