..........
የቀጠለ.......
እንደ አስተያየት ሰጪዋ፣ በቦታው የሚገኘው ካምፕ አራት መጋዘኖች አሉት፡፡ ሦስቱ መጋዘኖች ከተለያዩ አካባቢዎች ታፍሰው የሚመጡ ወንዶች የሚገኙበት ሲሆን አንደኛው ለሴቶች ተብሎ የተለየ ነው፡፡
‹‹መጋዘኖቹ በሰው የተጨናነቁ ናቸው፣ የምንበላው ደረቅ ዳቦ ነው፡፡ ንፅህና የሚባል የለም፣ ሽንት ቤቱም የሚገኘው እዚያው ነው፤›› የምትለው አስተያየት ሰጪዋ፣ በተላላፊ በሽታና በተለያዩ ምክንያቶች በየቀኑ የሰው ሕይወት ያልፍ እንደነበርም ተናግራለች፡፡
የፈጸመችው ምንም ዓይነት ወንጀል እንደሌለና ይህን አድርገሽ ተገኝተሻል የሚላት የሕግ ሰው ሳይኖር፣ ከተያዘች ከ15 ቀናት በኋላ መለቀቋን ተናግራለች፡፡
‹‹በካምፑ ውስጥ እያለሁ ታመምኩ፡፡ ፖሊሶችም ሕክምና ትሄጃለሽ ብለው በመኪና አውጥተው ስሙን የማላስታውሰው ጤና ጣቢያ ጥለውኝ ተመለሱ፤›› የምትለው አስተያየት ሰጪዋ፣ ‹‹ፖሊሶች ቆሎ፣ ለውዝና የመሳሰሉትን መንገድ ዳር መሸጥ አትችሉም በማለት በየጊዜው ከምንሠራበት ቦታ እየመጡ ያባርሩናል፤›› ስትልም ታክላለች፡፡
በጫማ መጥረግ ሥራ የተሰማራውና በካምፑ ሁለት ሳምንት መቆየቱን የሚናገረው ወጣት ስጦታው ካስትሮ እንደገለጸው፣ ጫማ ከሚጠርግበት ቦሌ አካባቢ ፖሊሶች ይዘውት በመኪና ጭነው ቃሊቲ ማሠልጠኛ ውኃ ልማት አካባቢ ወደሚገኘው ካምፕ መወሰዱት ተናግሯል፡፡
‹‹ካምፑ በየዕለቱ ታፍሰው በሚመጡ ሰዎች የተጨናነቀ ነው፡፡ ወንዶችን ከሚያስተናግዱት ሦስቱ መጋዘኖች በአንዱ ብቻ በርካታ ሰዎች ይገኛሉ፤›› የሚለው ወጣቱ፣ በዚህም ምክንያት ከንፅህና ጉድለት ተያይዞ በሚመጣ ተላላፊ በሽታ የሚጠቁ ሰዎች እንደነበሩ አስረድቷል፡፡
በሁለት ሳምንት የካምፕ ቆይታው በታይፎይድ መጠቃቱንና በአጎቱ አማካይነት ሊለቀቅ መቻሉንም ስጦታው ተናግሯል፡፡
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)፣ ‹‹በጎዳና ላይ ያሉ ሰዎችን ያለ ፈቃዳቸው መያዝና ወደ ማቆያ ማዕከላት ማስገባት፣ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን ስለሚያስከትል ሊቆም ይገባል፤›› የሚል መግለጫ ከአንድ ወር በፊት አውጥቶ እንደነበር ይታወሳል፡፡
ኢሰመኮ በመግለጫው፣ ‹‹በአዲስ አበባ ከተማ በተለምዶ ‹‹ቃሊቲ አካባቢ›› ተብሎ በሚጠራው የአሽከርካሪዎች ማሠልጠኛ አካባቢ ባለ ሰፊ መጋዘን ውስጥ ከጎዳና ላይ የተነሱ በርካታ ሰዎች መኖራቸውንና ይህ ሰዎችን የመያዝና ወደ ማቆያ ማዕከል/ቦታ የማስገባት ድርጊት አሁንም እንደቀጠለ ነው፤›› ማለቱ አይዘነጋም፡፡
‹‹ውሎና አዳራቸውን በጎዳና ላይ ያደረጉ ሰዎችን በግዳጅ ወደ ማቆያ ማዕከል (ቦታ) አስገብቶ መያዝ ወይም ያለ ፈቃዳቸው ወደ ተለያዩ አካባቢዎች መውሰድ/እንዲሄዱ ማስገደድ፣ የነፃነት መብትና ከቦታ ቦታ በነፃነት የመንቀሳቀስን ጨምሮ፣ ሌሎች የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ስለሚያስከትል በአስቸኳይ ሊቆም ይገባል፤›› ሲልም አሳስቦ ነበር፡፡
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ባለፈው ሳምንት ባወጣው መግለጫ፣ ‹‹በአዲስ አበባ ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች ላይ ወጣቶች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እየታፈኑ የት እንደገቡ ሳይታወቅ መሰወራቸውን፣ ከቤተሰቦቻቸውና ከተለያዩ አካላት መገንዘብ ችለናል፤›› ሲል አስታውቆ ነበር፡፡
‹‹ይህን የመንግሥት ተግባር ይበልጥ አስከፊ የሚያደርገው ታፍነው የተወሰዱ ወጣቶች የት እንደሚገኙ አለመታወቅና ቤተሰቦቻቸውም በመንግሥት አካል የተያዘ ግለሰብ ሊገኙባቸው ይችላሉ የሚሏቸውን ቦታዎች ቢያስሱም ማግኘት አለመቻላቸው ነው፡፡ በተጨማሪም አንዳንዶቹ ከተወሰኑ ቀናት መሰወር በኋላ በድንገት የት እንደነበሩ እንኳ መናገር በማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ ሆነው ወደ ቤታቸው በመመለስ ላይ ናቸው፤›› በማለት ኢዜማ መግለጹ የሚታወስ ነው፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ ፖሊስ ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ምክትል ኮማንደር ማርቆስ ታደሰ፣ በወንጀል የሚጠረጠሩ ግለሰቦችን ካልሆነ በስተቀር ፖሊስ በዘፈቀደ ከመንገድ ዳር አፍሶ የሚያስረው ሰው የለም ብለዋል፡፡
‹‹በወንጀል የሚጠረጠር ሰው ካለ ሰብዓዊ መብቱ ተጠብቆ በሕግ አግባብ ተጠያቂ እንዲሆን ነው የሚደረገው፤›› ያሉት ምክትል ኮማንደሩ፣ በመንግሥት የተቋቋመ ካምፕ መኖሩንና ሰዎችም ታፍሰው ወደዚያ ይወሰዳሉ የሚባለው ከእውነት የራቀ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
[
@MadoNews ]