እጅግ ተጠራጣሪዎች፣ አማኝ የምንመስል እጅግ ኢ-አማኞች፣ አስመሳዮችም ሆነናል። እኛ ኢትዮጵያውያን በአገዛዞች ጭካኔና ያንን አሜን ብሎ በሚቀበለው ባህላችን የተነሳ በጊዜ ሃ ሂደት አውቀንም ይሁን ሳናውቀው፣ የእስስትነት ባህርይን ተላብሰናል።
በመልታይፖላር ፐርሰናሊቲ ዲስኦርደር የተጠቃ ትውልድ ታቅፈን ነው የቀረነው። ኢትዮጵያዊ በቤተክርስትያንና መስጊድ ሌላ ሰው ነው። በሥራ ቦታ ሌላ። በአደባባይ ሌላ። በጓዳ ሌላ። ብቻውን ሌላ። ከወዳጆቹ ጋር ሌላ። ከትዳር አጋሩ ጋር ሌላ። ...
በኛ ማኅበረሰብ አንድ ሰው አንድ ብቻ አይደለም። የማይጨበጥና እርስበርሱ የሚቃረን ብዙ ሰው ነው! ከአንበሣነት ወደ እስስትነት ራሳችንን በአዝጋሚ ለውጥ የቀየርን ሕዝቦች ነን ቢባል ማጋነን አይሆንም።
ይህ ሁሉ የእኛ ኢትዮጵያውያን የወል መለያ ባህርይ፣ በመንግሥት ሥልጣን ላይ ለወጡ አፈሙዝ ለጨበጡ ኃይሎች ሁሉ፣ አመቺ ሆኖላቸዋል።
ለመጋለብ ያመቸ፣ ለመግዛት የተመቸ፣ ለመረገጥ የተዘጋጀ፣ ለመገረፍ ጀርባውን፣ ለመጫን ጫንቃውን ያደነደነ ህዝብ መሆኑን አገዛዞቹ አሳምረው ያውቃሉ። ጥቂቱን ጥቅም እያንጠባጠቡ፣ ሌላውን ጅራፍ እያወዛወዙ ይገዙታል።
ህዝቡም አንድ ገዢ አካል የመጨረሻ የማማረር ደረጃ ላይ ደርሶ ሆ ብሎ ካልተነሳ በቀር ይህ የመረገጥ እውነት፣ የአገዛዞች ሀሉ ባህርይ ነው ብሎ ተቀብሎታል።
የሐመር ሚስት ለአዲሷ ሚስት ባሏ የገረፋትን የጀርባዋን ጠባሳ እያሳየች፣ ባሌ ከአንቺ ይልቅ እኔን ነው የበለጠ የሚወደኝ እንደምትላት የመሠለ ነው!
ሚስቱን የሚማታው ቅናተኛ ባል ሚስቱን የሚወድ ነው! ይወደዳልም! መረገጥ ባህል ሲሆን በሁሉም የህይወት ዘርፍ ይንፀባረቃል!
ይህ ሁሉ አልበቃ ብሎ ደግሞ፣ በ20ኛው ክፍለዘመን በሀገራችን ሥልጣን ላይ የወጡ መንግሥቶች ራሳቸውን በህግ ሀገሩን ወደሚያስገብር አምባገነንነት ቀይረውታል።
ህጎች ሁሉ በሲስተም ዲዛይን የሚደረጉት የዜጎችን መብት ለመጠበቅ ሳይሆን፣ በይስሙላ የተረጋገጡ መብቶችን በሌላ ስልታዊ መንገድ ከዜጎች ላይ መቀማት የሚቻልበትን ሥርዓት በመዘርጋት ነው።
ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ሁለት ጊዜ ህገመንግሥት አሻሽለዋል። ሶስተኛው ጅምር ረቂቅ ሆኖ ቀርቷል፣ በለውጡ ተቀድሞ ቀረ። በእነዚህ ሁሉ ውስጥ አንድም ጊዜ፣ ዜጎች ለፖለቲካ ዓላማ ተሰባስበው የፖለቲካ ፓርቲ የመመሥረትና በረላማዊ መንገድ የመንቀሳቀስ መብት አላቸው የሚል አንዲት ሰባራ አንቀፅ አልደነገጉም!
የሕዝብን መብት አስከብራለሁ ብሎ የመጣው የደርጉ ወታደራዊ መንግሥት፣ ለጊዜው በለውጡ ሰሞን አቅሙን እስኪያደራጅ በዝምታ ይመለከታቸው የነበሩ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ሁሉ በሚዘገንን አብዮታዊ በትር አንድ በአንድ ድራሻቸውን አጥፍቶታል።
በቀኃሥና በደርግ (በኢህዲሪ) ዘመን ለስሙም ቢሆን በኢትዮጵያችን በህገመንግሥት ለስሙ እንኳን የተረጋገጠው የዜጎች የመደራጀት መብት ለኢኮኖሚ ዓላማ ብቻ እስከሆነ ድረስ ነበር።
የሙያ ማኅበራትን (trade unionsን) መመሥረት ብቻ ለዜጎች ተፈቅዶ፣ ለፖለቲካ ዓላማ መደራጀት ግን ለገዢ መንግሥት ብቻ የተፈቀደ ነበር።
ንጉሡም በሞናርክ ርዕዮት ተመራሁ በማለት፣ ንጉሡን ገረሰስን ያሉትም አብዮተኞች በማርክሲዝም ተመራን በማለት - ሁለቱም የሕዝብን የተደራጀ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ለማፈን ቆርጠው የተነሱ በህግ የሚያስገብሩ አምባገነኖች ነበሩ!
ይሄ ታሪካችን ይገርማል! ምክንያቱም በጠባይና በርዕዮተዓለም፣ በሕዝባዊ መሠረትና በአባሎቻቸው ዓይነች ፍፁም የሚለያዩ አገዛዞች፣ ነገር ግን የሕዝብን የፖለቲካ ተቃውሞ በማፈን ላይ አንድ ሆነው መገኘታቸው ይገርማል። የኛን የኢትዮጵያውያንን የረግጠህ-ግዛው ውርዴ በዘመን ለውጥ አለመፈወስ የሚያረጋግጥም ነው!
በኢትዮጵያ 3ሺህ ዓመት የሀገረመንግሥት ታሪክ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያችን፣ ለይስሙላም ቢሆን ለፖለቲካ ዓላማ ተሰባስቦ ማኅበር የመመሥረትን፣ በሠላማዊ መንገድ የፖለቲካ ፓርቲ መሥርቶ የመንቀሳቀስን የዜጎች መብት በመጀመሪያ በሽግግር ወቅት ቻርተር፣ ቀጥሎም በህገመንግሥት ያሰፈረው የወያኔ-ኢህአዴግ መንግሥት ነው!
ለዚህ ታሪካዊ ተግባሩ ሊመሠገን ቢገባውም፣ በተግባር ግን ሥጋውን ሰጥቶ ቢላዋውን የመንሣት የተለመደ ጨዋታውን ይጫወት የነበረ አገዛዝ ነው። ከሌሎቹ ብዙም የተለየ የሚመሠገን ባህርይ አልነበረውም።
የመግዣ ሥልቱን አራቀቀው፣ እና ትያትራዊነቱን ጨመረው እንጂ፣ የዜጎችን የልዩነት የፖለቲካ ሃሳብን የመግለፅ መብት በህጎቹም ሎነ፣ በአፈና ተቋሞቹ በተግባር ሲጨፈልቅ የኖረ - እናም ለምሥጋና የማይመች - አምባገነን መንግሥት ሆኖ አልፏል! (አልፏል ስንል አርፏል እንዳይመስል፣ ስሙንና መልኩን ቀይሮ አሁንም አለ!)
ፅሑፌን ስደመድም፣ የአትዮጵያ ሕዝብ የመብት ጥያቄውን በተደራጀ መልክ እንዳያቀርብ፣ በመብት ጥያቄው እንዳይገፋበት፣ ዋናው አስሮ ያስቀመጠው ነገር፣ ባጠቃላይ፣ በመሠረታዊነት፣ ከሌላ የውጭ አካል የሚመጣ ነገር ሳይሆን፣ ሕዝቡ ራሱ ለመገዛት የተመቸ ሕዝብ ስለሆነ ነው!
የመንግሥቶቹ አፋኝነት በሁለተኛ ደረጃ የሚመጣ ጉዳይ ነው። አመቺ ለም መሬት ያገኘ ዘር በቀላሉ ይበቅላል። አመቺ ተገዢ ህዝብ ያገኘ መንግሥትም፣ በቀላሉ የተቃወሙትን የመውጊያ ቀንድ ያበቅላል።
በዚያም ላይ ገዢ ሆነው የሚመጡትም ከጃፓን ወይ ከፓፓዋ ጊኒ የመጡ ሰዎች አይደሉም። ከኛው መሐል የወጡ፣ በአስተሳሰብም፣ በስነልቦናም፣ በባህርይም እኛኑ የመሠሉ ሰዎች ናቸው! ገዢነትንና ተገዢነትን የሣሉበት መንገድ ከሌሎቻችን የተለየ አይደለም። ሥልጣን ላይ ሲወጡም የሚያሳዩት ባህርይ ያንኑ እኛ ውስጥ ያለውን ቢሆን የሚገርም ነገር የለውም!
ለማንኛውም ይህን ለዘመናት የተጣባንን የተገዢነት ስነልቦና በምንድነው መስበር የምንችለው? ምን ብናደርግ ከአፈና ቀንበር መውጣት እንችላለን? የሚለው ላይ መነጋገር፣ መወያየት፣ ራሳችንን መፈተሽና መቀበል፣ ....
ራሳችንን ለመለወጥ የግልና የጋራ እንቅስቃሴዎችን መጀመር፣ በህግ የታሠረ መንግሥትን ለመፍጠር መታገል፣ እኛ ባይኖረኅ ልጆቻችን ዘመናዊ ዕውቀት እንዲኖራቸው የቻልነውን ሁሉ መጣር... ለነገዬ የሚባሉ የቤትሥራዎች አይመስሉኝም!
ሕዝቡን የሚያስፈራራ ሳይሆን፣ ሕዝቡን የሚፈራ መንግሥት ለማምጣት የተገዢነት ቀንበራችንን ሰብረን ለመብቶቻችን በጋራ መነሳት ብንችል፣ ከዘር የወረደ የፖለቲካ ውርዴያችን ቢያንስ በኛ ላይ ማብቃት ይችላል!
በነገራችን ላይ፣ እኛ ነፃ ነን የምንለው ኢትዮጵያውያን ለአገዛዞች የመገዛት ስነልቦናችን፣ ከተቀሩት በቅኝግዛት ባርነት ሥር ከማቀቁት ሌሎች ሕዝቦች የተለየ አይደለም! እጅጉን ይመሳሰላል ብቻ ሳይሆን፣ almost አንድ ዓይነት symptoms ናቸው ያሉብን!
ታዲያ ብዙዎች ከቅኝተገዢነት ነፃ ከወጡ እኛም ከአፋኝ አገዛዞች የመብት አፈና ነፃ መውጣት እንችላለን ማለት ይመስለኛል።
በርግጥ ከቅኝገዢዎች መላቀቅ ቀላል ነው። ከቅኝተገዢነት አስተሳሰብ መላቀቅ ነው ከባድ ሆኖ የተገኘው። ብዙዎች ዛሬ ነፃ ወጥተው፣ ግን አሁንም ነፃ አልወጡም። አሁንም ሥሪታቸው የተቀረፀው ከተገዢነት ቁስ ውስጥ ነው። እስካሁን ነፃ ወጣን የሚሉት ጨርሰው በመንፈስ ነፃ መውጣት ፈተና ሆኖባቸዋል!
እኛ ኢትዮጵያውያን ሙሉ መብት የተጎናፀፍን ዜጎች እንዳንሆን ጠፍሮ የያዘንን፣ የአካልም የመንፈስም እሥራት በጣጥሰን፣ እስስትነታችንን አውልቀን፣ ሙሉ ሰው፣ ሙሉ ዜጋ፣ ሙሉ አትዮጵያዊ፣ ሙሉ ጌቶች የምንሆንበትን ዘመን እናፍቃለሁ!
ተነሣ፣ ተራመድ፣ ክንድህን አበርታ!
ሰናይ ጊዜ!!
@zephilosophy